Monday 17 September 2018

ችግሩም የኛ ነው መፍትሄውም የኛ

በምን «ሞራል» ነው ቅንጅት ያፈራረስነው አሁን ሀገራችን የደረሰበትን ሰቆቃ በኦሮሞ ብሄርተኞች፤ ህወሓት፤ ወዘተ የምናሳብበው? መብም «ሞራል» ነው ኢዲኡን ያፈረስነው ችግሮቻችንን በነዚህ የምናሳብበው? በምን ሞራል ነው ላለፉት 27 ዓመታት ይህ ማለት የሚቻል ድርጅት ማቋቋም ያልቻልነው የአንድ አናሳ አምባገነናዊ መንግስት ማውረድ ያልቻልነው ችግራችንን በሌሎች የምናሳብበው? እስከ ዛሬ እርስ በርስ እየተጣላን፤ እከሌ አላከበረኝም፤ እከለ ሰላም አላለኝም፤ እከሌ የሌላ ቡድን ነው ወዘተ እያልን ለጥፋታችን ሃላፊነት ከመውሰድ «ኦኤምኤን» እንደዚህ አደረገን ጃዋር እንደዚህ አደረገን ስብሃት ደጋ እንደዚህ አደረገን የምንለው? ጥፋቱ የኛ ነው መፍትሄውም ከኛ ብቻ ነው መምጣት የሚችለው። የዘራነውን እያጭድን ነው። የክፍፍላችን ውጤት ይህ ነው። 

ካሁን ወድያ እራሱን «ኢትዮጵያዊ ነኝ» በ«ኢትዮጵያዊነት አምናለው» የሚል ሰው ችግራችን ሌሎች ላይ ከለጠፈ ኢትዮጵያዊ አይደለም። ለራሱ ችግር ሃላፊነት መውሰድ የማይፈልግ ገጓደኞቹ ጋር በሰላም ተባብሮ ተማምኖ አብሮ ከመስራት በጠላቶቹ መገዛት የሚመርጥ ነው! 

ይቅርታ ካሁን ወድያ መወሰን አለብን። የሰፈር ህፃናት ነን «እሱ ነው፤ እሱ ነው» ብለን የምናሳብብ ወይን አዋቂዎች ነን ችግራችንን አይተን ሃላፊነት ወስደን የምናስተካክል። ሃላፊነት ወስደን። ሃላፊነት ወስደንጅን!!

ጃዋር አያረገውም። እነ ስብሃት ነጋ አያረጉትም። እነሱ ላይ መቾህ እና መለመን የህፃን በሃሪ ነው ፋይዳ የለውም። ይህ ግልጽ ነው እንዴት አይገባንም። ምናልባት በህፍረት አንገታችን ድረስ ተሞልተን ከህፍረታችን መሸሽ ወድደን ይሆን? እስከ ዛሬ ምንም ስላላደረግን አፍረን እውነታን እየሸሸን ይሆን? አላውቅም? አይገባኝም።

እንዴ፤ ጣልያን ሲወርረን የኛ ህዝብ እና መሪ ጣልያንን አትወሩን ብለው ሲለምኑ አልሰማንም! ተደራጅተው ተዋጉ። አላለቀሱም። ጣልያኖችን አለመኑም። እርስ በርስ ተባብረው አብረው የሚችሉትን ሰሩ።

አሁን ግን ላለፉት 50 ዓመት እርስ በርስ መቃረን፤ መተቸት፤ እንደ ተራ ሰፈር ወረኞች «ጸጉር መጎተት» ነው ስራችን። መከፋፈልን «ስፖርት» አድርገነዋል። እንጂ በምን ሂሳብ ነው 8% እወክላለሁ የሚል ህወሓት ሀገራችንን ለ27 ዓመት የገዛው?! 

አሁንም ይህን ነው በሽታችን። ይህን ከመስተካከል በቀር ምንም ምንም አማራጭ የለም። የራሳችንን ችግር ማየት ማመን ማስተካከል ከባድ እና ቁስል የሚነካ ስራ ነው የሚሆነው ግን ግድ ነው። ማንም የሚንበረከከልን የለም።

ችግሩም የኛ ነው መፍትሄውም የኛ። 


No comments:

Post a Comment

ለሀሳብዎ አመሰግናለሁ!