Friday 31 August 2018

የሰርቢያ ትምሕርት ለአማራ ብሄርተኝነት

የሰርቢያ እና የአማራ ታሪክ ብዙ ልዩነቶች አሉት። ግን አንድ ሁለት ተመሳሳይ ነገሮች አሉ፤

1. ልክ እንደ ኢትዮጵያ ዙርያ አማራው እንደተበታተነው ሰርቢያኖች ዩጎስላቪያ ዙርያ ከሌሎች ጎሳዎች በጣም በይበልት ተበታትነው ይኖራሉ። በርካታ አማራ በየ ክልሉ ይኖራል። ከኦሮሞ ክልል ውጭ የሚኖር የኦሮሞ ህዝብ ከዚህ አንጻር እጅግ አነስተኛ ነው።

2. ከዮጎስላቭ መሪ ቲቶ ሞት በኋላ የዩጎስላቪያ የተለያዩ ጎሳዎች ከሰርቦች በቀር ጎሰኝነታቸው እያየለ ሲሄድ ከሀገሪቷ እንገንጠል ማለት ሲጀምሩ ሰርቦቹ እንደ መልስ «ጠንካራ» ጸንፍ የያዘ በእሾኽ በእሶኽ የሚያምን መሪ ሚሎሴቪች ወደ ስልጣን አመጡ። የሚሎሴቪች ምሳሌ የአማራ ብሄርተኝነት ነው።

እዚህ ላይ አንድ ነጥብ… ስሎቦዳን ሚሎሴቪች «አክራሪ» ሰርብ ቢሆንም በምዕራባዊያን የተከሰሰበት ወንጀሎች ሃሰት ናቸው ማለት ይቻላል። የጎሳ ወንድሞቹን ሰርቦቹን ባሉበት እካካከልላቸዋለው ብሎ ነበር የሚዋጋው ልክ እንደ ሌሎቹ ጎሳዎች ክሮአቶች፤ ቦስኒያኖች፤ ኮሶቮች እንደ ሚዋጉት። ስለዚህ ያአማራ ብሄርተኞች እንደ ሚሎሴቪች ናቸው ማለት ወንጀለኞች ናቸው ማለት አይደለመ።

ሆኖም ሚሎሴቪች እና ደጋፊዎቹ ታላቅ የፖለቲካ ስህተት ነው የፈጸሙት። ሰርቢያኖቹ ሶስት ነገሮች አዩ፤

1. ስሎቬኒያኖቹ፤ ክሮአቶቹ፤ ቦዝኒያኖቹ እና ኮሶቮቹ ሁሉ መገንጠል እንደሚፈልጉ
2. እነዚህ በሙሉ ሰርቢያ ውስጥ ብዙ ነዋሪ የላቸውም ግን ሰርቢያኖች በነዚህ «ክልሎች» ብዙ ናቸው። መገንጠል ከመጣ ስሎቬኒያ፤ ክሮኤሺያ፤ ቦዝኒያ እና ኮሶቮ የሚኖሩ ሰርቦች ናቸው ዋና ሰለቦች ሀገር የለሽ የሚሆኑት። ሰርቢያ ውስጥ ብዙ ስሎቪኖች፤ ክሮአቶች፤ ቦስኒያኖች፤ ኮሶቮዎች ስለሌሉ እነሱ ግድ አልነበራቸውም መገነጣጠልን ይፈልጉታል።
3. የምዕራብ ዓለም በሙሉ ዩጎስላቪያ እንዲበታተን እና ሰርቦቹ እንዲንበረከኩ (ሩስያን ለመጉዳት እና የአውሮፓ ህብረትን ለማጠንከር) ነው የሚፈልገው።

የሰርቢያ ልሂቃን ይህን አይተው በዜዴ የሀገራቸውን ጥቅም አስከብሮ ከመስራት ፋንታ ለምሳሌ ስሎቪኒያን እና ክሮኤሺያን በስምምነት ለቆ አቁምን በቦዝኒያ እና ኮሶቮ ላይ ከማዋል ፋንታ ሁሉንም እንዋጋ አሉ። ሰርቢያ እንዳለ ምዕራብ አለሙን ሲዋጋ ማን እንዳሸነፈ እናውቃለን። አሁን በክሮኤሺያ የሚኖሩት ሰርቦች፤ በቦዝኒያ የሚኖሩት ሰርቦች እና በኮሶቮ የሚኖሩት ሰርቦች የዚህ ያልበሰላ ፖለቲካ አካሄድ ዋና ሰለቦች ሆነው ቀርተዋል። ሰርቢያም እጅግ ተጎሳቁላለች ሞራልዋ ሞቷል።

የአማራ ብሄርተኝነት እሾኽ በ እሾኽ አመለካከትም እንዲሁ ይሆናል ብዬ እሰጋለሁ። በነ ኦሮሚያ፤ ቤኒሻንጉል፤ ደቡብ፤ ሶማሌ ወዘተ ክልሎች የጎሳ ብሄርተኝነት ጠንከር ያለ ነው። የነዚህ ክልል «ጎሳዎች» ከክልላቸው ወጭ በብዛት አይኖሩም። አሉ ግን ብዛታቸው ውስን ነው። አማራው ግን በሚሊዮን የሚቆጠር ከክልል ውጭ አለ።

አማራው ጠንክሮ በአማራነቱ ቢደራጅ እና ከሌሎች የጎሳ ድርጅቶች (ወኪሎች) ሲደራደር እነሱ ለሚያደርጉት እሾኽ በ እሾኽ (tit for tat) ልመልስ ከሆነ ውጤቱ ምን ይሆን። አማራው ምንም ጠንካራ ቢሆን ከግዴለሽነት ጋር መዋጋት አይችልም። ኦሮሚያ አማራው ዜጋ አይደለም ቢል የአማራው መልስ በአማራ ክልል ያሉትን ኦሮሞዎችን እንደዛው ማደረግ ነው። ግን ኦሮሞ ብሄርተኛው ግድ የለውም እንደዚህን ለመሰዋት ዝግዱ ነው።

አያችሁ ሁኔታው ሚዛናዊ አይደለም። Asymmetrical ነው። አማራ በየቦታው አለ ሌላው ግን ክልል ውስጥ ነው። ይህ ማለት ሁለቱ ወገኖች የሚጠቀሙበት የትግል ዘዴ መለያየት አለበት። የአኖሌ ሃውልት ገንብተሃል እና የጣይቱ ሃውልት ልገንባ (አዎ አኖሌ ታሪኩ ሃሰት ነው አውቃለው) ማለት የተሳሳተ ብድር መላሽ ፖለቲካ ነው።

አማራው ግን በኢትዮጵያዊነት ከተደራጀ በዛ ጥላ ስር በርካታ አማራ ያልሆኑም ይይዛል። እነዚህ ሰዎች ኦሮሚያ ውስጥ ውግያ ሳይፈጥሩ ግን በዘዴ ታላቅ የፖለቲካ ኃይል መያዝ ይችላሉ። ይህን ኃይል ተተቅሞ የጎሳ ብሄርተኝነትን የሚቀንሱ ፖሊሲዎችን ለማራመድ ድጋፍ አስፈላጊ ድጋፍ ይሰጣሉ። እነዚህ ፖሊሲዎች ለዓመታት ከሰሩ በኋላ የጎሳ ብሄርተኝነት ይቀንሳል። ከዛ በኋላ የጣይቱ ሃውልት ይሰራ ቢባል ማንም አያስቸግርም። ዘዴው እንዲህ ነው።

የሰርቦች እጣ ፋንታ እንዳይደርስብን። ስሜታዊ ፖለቲካ በጀግንነት እና ፍልፍና ሸፍነን አናራምድ። ከልባችን አለ bias ጉዳዩን በክፍት የሆነ አዕምሮ እናስብበት።

የቻይና ገብረ ገብ እጦት፤ ትምሕርች ለኢትዮጵያ

የሰው ልጅ ከወደቀ ጀምሮ የግብረ ገብ ጉድለት እንዳለው ነው። በማህበረሰብ ደረጃ የግብረ ገብ እጦት ጎልቶ የሚታይበት ደግሞ ደበቅ የሚልበት ሁኔታዎች እና ወቅቶች አሉ።

ብዙዎቻችን በኢህአዴግ አገዛዝ ዘመን በሀገራችን ታልቅ የግብረ ገብ እጦት እየታየ ነው እንላለን። ለማ መገርሳም አብይ አህመድም ይህን ጉዳይ በተደጋጋሚ ያነሱታል። ባለ ስልጣን ይጨቁናል እና ይሰርቃል፤ የመንግስት ስራተኛ ጉቦ ይጠይቃል፤ ብዙሃኑ ያጭበረብራል፤ ስርቆት፤ ግድያ፤ ማጭበርበር፤ ለሰው ግድ ዬለሽነት፤ ዝሙት፤ ርክሰት፤ ሌብነት ወዘተ። ሁላችንም ሰምተነዋል አይተነዋልም።

መፍትሄውን ለማግኘት ለምን ይህ ሆነ ብለን መጠየቅ አለብን። ስንጠይቅ በቅርብ ያረፉት ታዋቂ የቻይና የፖለቲካ ተንታኝ እና እስረኛ ሊዩ ሺያዎቦ ጥሩ መልስ ይሰጡናል። የቻይና እና የኢትዮጵያ የፖለቲካ አገዛዝ እና በማሀበረሰቡ ላይ ያሳደረው ጫና በተወሰነ ደረጃ ተመሳሳይነት አላቸው።

በቻይና አንድ አውራ ፓርቲ በሙሉ ስልጣን ይገዛል። የማይፈልጋቸውን ያስራል ይገላል (በአመት ወደ 2,000 ሰዎች በይፋ በሞት ፍርድ ይገደላሉ)። ማንም ሰው መማር ማደግ ወይንም ስልጣን መያዝ ከፈለገ ከገዥ ፓርቲው ጋር ጥሩ ወይም ቢያንሽ መልካም ግንኙነት ሊኖረው ይገባል። ከፓርቲው ጋር ጥሩ ግንኙነት ያላቸው ከሌላው ሀብረተሰብ ሃብታም እና ባለ ስልጣን ይሆናሉ። ይህ ሃብት እና ስልጣን በስራ እና እውቀት የተገኘ ሳይሆን ከፓርቲ አባል እና መሪዎች ጋር በመሻረክ ነው የሚመጣው። በዚህ ምክንያት በርካታው የሀገሪቷ ሃብት በጥቂት ሰዎች የተቆጣጠረ ነው።

እንዲሁም ሆኖ የቻይና ኮምዩኒስት ፓርቲ ህዝቡ ከስልጣን በአመጽ እንዳያወርደው ብሎ ኤኮኖሚው የገበያ ኤኮኖሚ እንዲሆን እና በፍጥነት እንዲያድግ አድርጓል። ለብዙ ዓመት ኤኮኖሚው በየአመቱ ከ10% በላይ ነው እድገቱ። በርካታ ስዎች በፍጥነት ሃብታም ሆነዋል። መካከለኛ መደቡም አድጓል። ግን የእድገት ፍጥነቱ በሃብታም እና ድሃ ያለውን ልዩነት በጣም አስፍቶ ከዓለም አንደኛ አድርጎታል (30 ዓመት በፊት በእውነተኛ ኮምዩኒዝም ዘመን እኩልነቱ በዓለም አንደኛ ነበር)። ግን ብዙ ሰው ማደግ የሚችለው ሃብት ማከማቸት የሚችለው አጭበርብሮ፤ ጉቦ ከፍሎ ወይንም ወስዶ ወይንም በተለያየ መንገድ ህግን ጥሶ ወይን ስነ መግባርን ጥሶ ነው።

በአጭሩ የቻይና መንግስት ከህዝቡ ጋር ያለው ስምምነት እንዲህ ነው፤ በፖለቲካ እና ስልጣናችን አትምጡ ከመጣችሁ እናጠፋችኋለን፤ ግን እንደፈለጋችሁ ሃብታም ሁኑ ከፈለጋችሁ ከኛ ጋር ተሻረኩ እና ስረቁ። የቻይና «ልማታዊ መንግስት» እና «አውራ ፓርቲ» አገዛዝ ርዕዮእተ ዓለም እንዲህ ነው። በህወሓት ዘመን የነበረውን በተለይ ከምርጫ 97 ወዲህ የነበረውን አገዛዝ ሊያስታውሳችሁ ይገባል። አንድ ነው።

ወደ የቻይና የፖለቲካ ተንታኙ ሊዩ ሺያዎቦ እንመለስ። ሊዩ ይህንን ልማታዊ መንግስት ሲተቹ ይህ ስርአት የሚያመጣውን የስነ መግባር እጦትን በደምብ ተንትነዋል (https://www.nybooks.com/articles/2012/02/09/liu-xiaobo-he-told-truth-about-chinas-tyranny/)።  ከዚህ ጽሁፍ የተወሰነውን ተርጉሜ ከታች አቀርባለሁ…

ኅብረተሰብን በመቀየር አገዛዙን እንቀይር» በሚል ጽሁፉ ሊዩ ሺያዎቦ ለቻይና ያሉትን ተስፋዎቹን ዘርዝሯል። የፖለቲካ አንባገነንነቱ ቢቀጥልም ህዝቡ ድንቁርናውን እና መከፋፈሉን ያሸንፋል። ህዝቡ ያለውን ኢፍትሃዊ አሰራር ለመታገል አስፈላጊ የሆነውን ህብረት ይረዳል እና መተባበርን ይጀምራል። ህዝቡ አይን ያወጣ ሙስናውን እና ሹማምንቱ የሚሰራውን አድሎአዊ ስራዎችን አብሮ በህብረት እንደሚቃውም ተረድቷል። ማህበራዊ ጥንካሬ እና ስለ ህዝብ መብት ማወቅ ይስፋፋል። ዜጎች የኢኮኖሚያዊ ነፃነት ሲያገኙ መረጃ ለማግኘት እና ለመቀያየር ይቀላቸዋል።

ህዝቡ በቀላሉ መንግስት መቆጣጠር በማይችልበት መንገድ ሃሳብ እንዲቀያየር ኢንተርነት ይፈቅዳል ያጎላብታል። የምነግስት የመረጃ አፈናን አቅመ-ቢስ እያደረገ ይሄዳል። የቻይና ህብረተሰብ ነፃ መሆን የሚችለው ህብረተሰቡ ከታች (ከብዙሃኑ) ወደ ላይ ቀስ በቀስ እየተሻሻለ ሲሄድ ነው። ይህ ቀስ በቀስ የህብረተሰብ ለውጥ አገዛዙን በግድ እንዲቀየር ያደርገዋል።

ሊዩ እነዚህን ተስፋዎች እየዘረዘርም በተቃራኒው የቻይና ህብረተሰብ የመንፈሳዊ ድኻነት በአሳዛኝ መልኩ ይገልጻል። መንግስት ህዝብ ታሪክን እንዲረሳ አውጆ ለማስረሳት ትልቅ ስራ እየሰራ ነው። የቲዬንአንሜን ጭፍጨፋ (Tiananmen Massacre) ታሪክ ከአዲሱ ትውልድ አዕምሮ እንዲጠፋ ተደርጓል (ለኢትዮጵያ ተመሳሳዩ ክስተት ምርጫ 97 እና የተከተሉት ጭቆናዎች ናቸው)። የቻይና መንግስት ወጣቱ ይህን ትዝታ እንዲረሳ በጭፍን ብሄርተኝነት ይተከዋል ወጣቱ ያሉትን እውነታዊ ችግሮችን እንዲረሳ (በኢትዮጵያ context መንግስት ወጣቱን በ «ልማት» ፕሮፓጋንዳ ነው የሚሞላው) ነው። ሥን ጽሑፍ፤ መጽሔት፤ ፊልም እና ቪዲዮዎች ሁሉ በዝሙት እና ሁከት (violence) የተሞሉ ናቸው «የህብረተሰባችን የግብረ ገብ በርሃነትን» ያንጸባረቃል።
«ቻይና የተስፋ መቁረጥ እና ጥርጣሬ ዘመን ውስጥ ገብታለች ማንም በምንም አያምንም… የኮምዩኒስት ፓሪቲ መሪዎቹም አባላቶቹም በራሳቸው ፓርቲ ፕሮፓጋንዳ ማመን ትተዋል። በመርህ፤ ስነ መግባር፤ እምነት መመራት ትተን አሁን በገንዘብ እና አለማዊ ነገር ሆናል «እምነታችን»። የቻይና ኮምዩኒስት ፓርቲ ልክ የለሽ የማያቋርጥ ፕሮፓጋንዳ ትዝታ እና ታሪክ የለለው ትውልዶች ፈጥሯል…
በደህና የኑሮ ሁነታ ያደገው ከ«ቲዬንአንሜን» ቀጥሎ የተወለደው ትውልድ አሁን እንደ አላማ ያለው የመንግስት ሹም መሆን (አስፋው፤ በጉቦ ሃብታም ለመሆን)፤ ሃብታም መሆን ወይንም ውጭ ሃገር መሄድ… ስለ ታሪካዊ ስቃዮች መስማት አይፈልጉም ትዕግስቱ የላቸውም… «ታላቁ እርምጃ» (ወደ 40 ሚሊዮን የሞቱበት ማኦ የፈጠረው ርሃብ "The Great Leap Forward")፤ «ባህላዊ አብዮት» (አንዱ የቻይና ቀይ ሽብር "Cultural Revolution")፤ የቲዬንአንሜን ጭፍጨፋ። ለአዲሱ ትውልድ እነዚህን የመንግስት ጥፋቶች ማንሳት እና የህብረተሰባችን «ጭለማ ወገን» ማሳየት አስፈላጊ አይደለም። የራሳቸውን የሞልቃቃ አኗኗር እና የመንግስትን ፕሮፓጋንዳ ተጠቅመው ቻይና ታላቅ ተራምዳለች ማለት ይሻላቸዋል።»
አንዳንድ ምዕራባዊ ሊበራሎች የማኦ ጥብቅ ዘመን ሲፈርስ የዝሙት ነፃነት ይመጣ እና እንደ ቦምብ የህብረተሰባዊ እና ፖለቲካዊ ነፃነት ያመጣል ብለው ይገምቱ ነበር። አሁን ግን ሊዩ እንደሚለው የ«ዝሙት ፌሽታ» ሀገሪቷን አጥለቅልቆታል። ሀገሪቷን በዝሙት፤ ሁከት እና ስግብግብነት ሞልቶታል። ህብረተሰቡ በረዥም ዓመታት ጭቆና እና ውሸት ፕሮፓጋንዳ ምክንያት የግብረ ገቡን ማጣት ነው ይህ ሁሉ የሚያሳየው። «ድሮ ለፖለቲካዊ አብዮት ያበደው ዛሬ ለገንዘብ እና ዝሙት አብዷል» ይላል ሊዩ።

አንዳንድ የግራ ፖለቲካ አማኞች የዛሬ የቻይና የግብረ ገብ እና መንፈስ እጦትን በገበየ ኤኮኖሚው (market economy) እና ግሎባላይዛሽን (globalization) የመጣ ነው ብለው ያሳብባሉ። እነዚህም ናቸው የቻይናን ግዙፍ የሙስና ችግር ያመጡት ያላሉ። ግን ሊዩ በተቃራኒው የዛሬው ተስፋ መቁረጥ፤ ጥርጣሬ፤ እምነት ማጣት፤ ርክሰት፤ ብልግና እና ጥቅላላ የግብረ ገብ እጦትን በማኦ ዘመን ያሳብባል። የዛ የ«ንፁ» የኮምዩኒዝም ዘመን ነው የሀገሪቷን መንፈስ የዘረራት ይላል። ያ መንግስት፤
«ኢ-ሰባዊ እና ገብረ ገብ የሌለው ነበር። የማኦ አምባገነናዊ መንግስት ሰዎችን መንፈሳቸውን እንዲሸጡ ሰውነታቸውን እንዲከዱ አድርጓል። ባለቤትን መጥላት፤ አባትን ማውገዝ፤ ጓደኛን መካድ፤ ተጎጂን ይበልጥ ምጉዳት፤ ጥሩ ኮምዩኒስት ለመባል ማንኛውም ነበር ማለት። ልክ እና ገደብ ያልነበረው አለማቆም ጨፍላቂ የሆነው የማኦ የፖለቲካ እርምጃዎች መሰረታዊ የሆኑትን የቻይና ህዝብ ስነ መግባሮችን አጠፋ።»
ከማኦ በኋላ ይህ አካሄድ ቢቀንስም አለ። ከቲዬንአንሜን ጭፍጨፋ በኋላ መንግስት ህዝቡ እንዲረሳው ጣላቅ ፕሮፓጋንዳ እና ሽብር አራመደ (አስፋው፤ ልክ እንደ ኢህአዴግ ከምርጫ 97 በኋላ እንዳረገው ሰውው ትዝታ እንዳይኖረው ስለ «ልማት» ብቻ እንዲያስብ)። ህዝቡ ህሊናውን ክዶ ለምንግስት ተገዢነቱን እንዲያሳይ ተገደደ። «ቻይና ህዝቧ ለህሊናው የሚዋሽ ሀገር ከሆነች በምን ተዓምር ነው ጤናማ ግብረ ገብ ያለው ህብረተሰብ መገንባት የሚቻለው?» ሊዩ ይቺን ምዕራፍ እንደዚህ ደመደመው፤
«ቻይናን ያረከሳት ዛሬ የምናየው በሀገሪቷ ዙርያ የሰፈነው የግብረ ገብ እጦት ምንጩ የማኦ ኢ-ሰባዊ ዘመን ነው። በዚህ ዘመን የዝሙት ማሳደድ ዘመቻ ለአምባገናናዊ ስረዓቱ እጅግ ይጠቅመዋል። ህዝቡ በልማት እየተጠቀመ ቢሆንም ወደ ፖለቲካ እንዳያስብ ያደርገዋል። የዝሙት «ነፃነት» ዴሞክራሲን ከማምጣት ይልቅ የድሮ የመሳፍንቶቻን የዝሙት ጥንቅን ነው የሚመልሰው… ይህ የዛሬዎቹን አምባገነኖችን በጣም ይመቻቸዋል። ከዘመናት ግብዝነት ያመጣውን ገብረ ገብ መበስበስ እና የፖለቲካ ጭቁና ጋር አብሮ ይሄዳል። ህዝቡ የፖለቲካ ነፃነት ከመጠየቅ በርክሰት እንዲጨማለቅ ያረገዋል።»
በሌላ ጽሁፍ ይህ እንዴት ኢትዮጵያን እንዲሚመለከት እወያያለሁ።

Thursday 30 August 2018

የአጥንት ቆጠራ ወይንም የአድሎ ማስተካከያ?

ጃዋር መሃመድ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለሱ እና ለሌሎች ያቀረበለት የሠራተኞቹ ጎሳ ሰነድ (https://www.facebook.com/Jawarmd/posts/10104092557488783) አሳይቶናል።

ጥሩ ነው። ይህ ጉዳይ በኢትዮጵያ ፖለቲካ መነሳቱ አይቀርም እና መወያየቱ ጠቃሚ ነው።

ሆኖም ይህ ሰነድ የተሟላ አይደለም። የሠራተኞቹ ብሄርን ነው ወይንም የትውልድ ወይንም የመኖርያ ክልልን ነው የሚያሳየው ግልጽ አይደለም። የተጻፉት ክልሎች ናቸው፤ «ሌላ»፤ «ደቡብ ክልል»፤ «ኦሮሞ ክልል»፤ «አማራ ክልል» እና «ትግራይ ክልል» ነው።

ግን ይህን አይተን ሠራተኞቹን በመጡበት ክልል ነው ያስቀመጧቸው ለማለት ይከብደናል ሌሎች ክልሎች በተለይ አዲስ አበባ ክልል ስለሌሉበት! «ክልል» ብለው ጻፉት እንጂ «ብሄር» ማለታቸው ነው ከሆነ ደግሞ ለምን እንደዛ አላሉትም ማለት ይቻላል። አየር መንገዱ ሠራተኛ ሲቀጥር ብሄሩን እንደ መረጃ ያስቀምጠዋል ወይ የሚለው ጥያቄም ይነሳል።

ስለዚህ ስለዚህ ሰነድ ከመወያየታችን በፊት ሙሉ መረጃ ያስፈልጋል። ያንን ከአየር መንገዱ ወይንም ከአቶ ጃዋር (ነግረውት ከሆነ) ካላገኘን ዋጋ የለውም።

ግን በጠቅለል ያለ መልኩ ስለ «ኮታ» (በጎሳ፤ በጾታ ወይንም በመደብ የሥራ ወይንም የትምሕርት እድል መመደብ) ያለኝን አመለካከት ልግለጽ… ጠቃሚ ከሆነ። ይህ አካሄድ አደገኛ እና ህዝብን የሚያከፋፍል መሆኑ ምንም ጥያቄ የለውም። የግጭት ምንጭ መሆኑ ኢትዮጵያም የትም የታየ ነው።

ሆኖም አድሎ የትም ቦታ ያለ ነገር ነው። ኦሮምያ ያደገች አማርኛ በደምብ የማትችል ሴት ለአየር መንገድ የአስተናጋጅ ስራ ስትወዳደር በአማርኛ ጉድለቷ ትቸገራለች። ብቁመቷም ልትቸር ትችላለች። ምናልባት በተፈጥሮ ሳቂታ ከሰው ጋር በቀላሉ የምትግባባ ላትሆን ትችላለች። መልኳም «እስከዚህ» ሊሆን ይችላል። ወዘተ። ብዚህ ዓለም «እኩልነት» የለም። የሰው ልጅ አብዛኛውን ማንነቱን ይወርሳል በትንሹ ነው የራሱ ሚና ያለበት።

እንዲህ ሆኖ መንግስት ወይንም ሌላ ተቋማት እኩልነት ውየን "fairness" ለማምጣት ጣልክቃ ገብተው ኮታ ቢጠቀሙ ይጠቅማል ወይ? እኔ የሚሻለኝ መሰረታዊ ችግሮቹ ላይ ብናተኩር ነው። የቋንቋ ችግር ካለ ይፈታ። የአድሎ ችግር ካለ ይፈታ። ቁጥር ላይ ማተኮሩ ወይንም ኮታ እንዳ አንድ መሳርያ መጠቀሙ ጉዳቱ ከጥቅሙ ያይላል ብዬ ነው የምገምተው።

ይህን ለማየት ለጀዋር ጽሁፍ የቀረቡትን አስተያየቶችን ማየት ይበቃል! ጉድ ነው ግን ያልተጠበቀ አይደለም። እስቲ ጉዳዩን ሰክን ብለን እናስብበት። በደመነፍስ አንግባበት።

በመጨረሻ ስለ ኢትዮጵያ አየር መንገድ ትግሬ ብቻ ሆኗል የሚለው ዘፈን አንድ ነገር ብል ደስ ይለኛል። ትግሬዎች አላግባብ ተቀጥረው ይሆናል ቢሆንም አይገርምም እንደማንኛውም መስሪያቤት አየር መንገዱም ብዙ ሰው የሚቀጥረው በትውውቅ ነው። በህወሓት አገዛዝ ዘመን ይህ የትውውቅ ድር (network) ወደ ትግሬዎች ማዳላቱ ምንም አይገርምም። መሰረታዊ ችግሩ የህወሓት አገዛዝ ነው እንጂ ትግሬዎች አለአግባብ መቀጠራቸው አይደለም። መሰረታዊው ችግር ከተፈታ ሌላውም ይፈታል።

እኔ የትግሬ አድሎ አለ ብዬ ማልቀስ ድሮም ወድጄ አላውቅም (https://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/04/blog-post_16.html)። ማልቀስ እና ማማረር ሽንፈት ነው የበታችነት እና የዝቅተኝነት ስሜትን (inferiority complex) ያዳብራሉ። ሃላፊነት-ቢስ ያደርጋሉ። ሰውን ተግባራዊ ስራ ከመስራት ወሬ ብቻ እንዲሆን ያደርጋል። Empower ከማድረግ disempower ያደርጋል። ይህን ችግር አንድ በደንብ የሚያሳየን ነበር አሁንም ህወሓት ከስልጣን ከወረደ በኋላ ሰዎች ስለ ትግሬ አድሎ በማሰብ ጊዜአቸውን ሲያባክኑ ነው። ወይንም ስለ በረከት ስምዖን ሲያወሩ። አዎ ሰው ቅስለኛ ነው ግን ክብሩንም ያጣ ይመስለኛል።

Tuesday 28 August 2018

ከአማራ እና ከአማራ ውጭ የተወለዱ አማሮች…

ካአማራ ክልል ውጭ የተወለድን አማራዎች እና አማራ ክልል የተወለዱ አማራዎች ትንሽ የትውውቅ ጉድለት ያለን ይመስለኛል። በተለይም የአዲሱ የኢህአዴግ ዘመን ትውልድ በዚህ ዙርያ የመረጃ እጦት አለው። በዚህ ጽሁፍ ይህንን የመረጃ እጦት ለማስተካከል እና መተዋወቅን ለማምጣት ነው የምሞክረው።

እኔ ከ«ነፍጠኛ» ቤተሰብ ነው የተወለድኩት። አያቶቼ፤ ቅድመ አያቶቼ፤ ቅድመ ቅድመ አያቶቼ የትወለዱት ከምዕራብ ሃረርጌ «ጨርጨር» ከሚባለው አካባቢ ነው። አያቶቼ ከጎጃም፤ ከአማራ ሳይንት፤ ከወሎ እና ከመራቤቴ ነበር «ነፍጠኛ» ሆነው ወደ ሃረር የመጡት።

«ነፍጠኛ» ምን ማለት ነው? ወታደሮች ከነቤተሰቦቻቸው፤ መሬት የሚፈልግ ብዙሃን ገበሬ፤ አዲስ መሬት የሚፈልግ ባላባት/ባለሃብት፤ ለአስተዳደር ስራ የተገመገመ ግለሰቦች፤ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚፈልጉ ካህነት ወዘተ። እነዚህ በሙሉ አጼ ምኒልክ አካባቢውን ከተቆጣጠሩት አብረው ወይንም በኋላ የገቡ ናቸው። የመጡበት ደግሞ ከተለያየ ቦታ ነው ግን አብዛኛው የአማርኛ ተናጋሪዎች ነበሩ።

ነፍጠኛው አንዳንዱ በደሞዝ እና ንግድ ይተዳደር ነበር። ብዙዎቹ (እንደ የኔ ቤተሰብ) ለመተዳደርያ ተብሎ መንግስት መሬት ሰጣቸው። ከፊሉ መሬት ባዶ ሰው ያልሰፈረበት የማይጠቀምበት ነበር። ሌላው ደግሞ ሰዎች (ገበሬዎች) የሚኖሩበት ነበር። የኔ ቤተሰብ መሬቶች ሁለቱም አይነት ነበራቸው የመሬታቸው ስፋት ደግሞ እጅግ ትልቅ ነበር። መሬታቸው የተነጠቀባቸው ነባር ገበሬዎቹ በአብዛኛው ጭሰኛ ወይንም ገባር ሆኑ። አልፎ ተርፎ በምዕራብ ሃረርጌ በርካታው የመንግስት እና አስተዳደር ስራ የተሰጠው ለነባሩ ሳይሆን ለነፍጠኛች ነበር። ሁሉም ሳይሆን አብዛኛው እንዲህ ነበር።

ስለዚህ የነባሩ ህብረተሰብ ቁጭቱ ባጭሩ ሁለት ነበር፤ በገዛ መሬቱ ጭሰኛ መሆኑ እና በ«ወራሪ» መስተዳደሩ። በወራሪ መስተዳደር ኢትዮጵያ ውስጥ የተለመደ ነበር በየ ጊዜው መግዛት መገዛት ስለነበር ኦሮሞም ምዕራብ ሃረርጌ የገባው በወረራ ስለነበር (ግን ከመቶ አመታት በፊት)። ሆኖም ብዙ ጊዜ ወራሪው ከነበሩ ጋር ከጊዜ በኋላ ይወሃዳል። ግን በኔ አያቶች ዘመን የሃይማኖት ልዩነት ስለነበር በቂ ጊዜም ስላልቆጠረ በምዕራብ ሃረርጌ በነፍጠኛው እና ነባሩ ብዙ ውህደት አልተካሄድም።

ይህ እንደሆነ በኔ እይታ እኛ እንደ ነፍጠኞች እና የነፍጠኞች ልጆች ሁለት ነገሮች ማድረግ ነበረብን። አንዱ ከገበሬዎች የተነጠቀውን መሬት መመለስ ከቻለ ከነ ካሳ ሲሆን ሁለተኛው ስረዓቱ በሚፈቅደው ደረጃ የነባሩ ቋንቋ እና ባህል በትምሕርት እና አስተዳደር ደረጀ እንዲንጸባረቅ ማድረግ።

ሁለቱንም ማድረግ ስላቃተን ደርግ መጥቶ የሁላችንንም መሬት ወሰደ ጭሰኛውንም ባላባቱንም የመንግስት ጭሰኛ አደረገ! የቋንቋ እና ባህል «እኩልነትንም» ማስፋፋት ሞከረ። የነፍጠኛ ዘመን አበቃ። በደርግ ዘመን የነፍጠኛውም ልጆች የነባሩም ልጆች በመንግስት አይን እኩል ሆኑ። በነገራችን ላይ በርካታ የነፍጠኛ ልጆች በተማሪ ንቅናቄው ተሳትፈው ለደርግ መምጣት ታላቅ አስተዋጾ አድርገዋል።

ኢህአዴግ ስልጣን ሲይዝ እና የጎሳ አስተዳደር እና ጎሰኝነትን ሲሰብክ ከነ «ጨቋኝ አማራ» የሚለው ትርክት እኛ የነፍጠኛ ልጆች በከባድ ተጠቃን። የቅርብ ዘሞደቼ በአማራነታቸው ብቻ ከመረሸን ለጥቂት ነው የተረፉት። ታሪኩንም ለመናገር ከብዷቸው ብዙ አይናገሩትም ነበር።

በጠቅላላ አማራው እና ሊላው እንደ «መጤ» እና «ክርስቲያን» የሚሰየመው ጉዳት የደረሰበት አካላዊ ብቻ አይደለም። ከሞላ ጎደል በሀገሩ ሁለእኛ ዜጋ ሆነ። በመንግስት ደረጃ በተለያየ መንገድ በቢሮክራሲውም በፍትህም (በፍርድ ቤት) ይጨቆናል። በማህበራዊ ኑሮ ደረጃም በየጊዜው ዛቻ እና ማስፈራርያ ያጋጥመዋል። ሙስሊም ካሎንክ መሬትህን ልቀህ ውጣ ይባላል። በየጊዜው ዘረፋ እና ግድያ ይፈጸማል። በየ ጊዜው ነገሮች ሲብሱ ፌደራል ፖሊስ ውየን ጦር ስራዊት ገብተው ወንጀለኞቹን ይረሽኗቸዋል። ግን በሌላው ጎን መንግስት ጎሰኝነትን በመስበክ ጸንፈኛ ጎሰኛ እና ሙስሊሞችን ያበረታታል። «መጤዎቹ» በጨርጨር ለ120 ዓመት በላይ የኖሩ የዛሬ ኑሮዋቸው በቢለዋ ስል ላይ ነው። በጣም ብዙዎቹ ገና 20 ዓመት በፊት ይህ ሀገራቹህ አይደለም ተብለናል ብለው ወደ አዲስ አበባ ወጥተዋል። ቀሪዎቹ በከፊል ፍርሃት ነው የሚኖሩት።

ይህ ነው ባጭሩ የአንድ ነፍጠኛ ልጅ ቤተሰብ እና ሀገር ታሪክ። እኔ አሁን ጨርጨር አልኖርም። ተመልሰህ ትኖራለህ ወይ ብባል አይመስለኝም። በአድነት ይሰማኛል እንዲሰምኝ ይደረጋል። የቋንቋ ጉዳይ አይደለም። ኦሮምኛን መቻል ግድ ነው ባይሆንም አምንበታለው። ግን አማራ በመሆኔ በመንግስት ደረጃም በ27 ዓመት የጎሰኝነት ስብከት ምክንያት በማህበረሰብ ደረጃም እንደ ሁለተኛ ዜጋ እንዳ በአድ ነው የምታየው።

ግን የደብረ ማርቆስ አማራ ይህን ስሜት አያውቀውም። በደርግ ወይንም ኢህአዴግ ወይንም በሌላ ምክንያት ከደብረ ማርቆስ ተሰድዶ አሁን ልመለስ ቢል ሀገር አለው! በአድነት እንዲሰማው የሚያደርግ የለም። መንግስትም ህዝብም ይቀበለዋል። ሀገሬን ልርዳ ቢል ልጃችን እንኳን ደህና ተመለስክ ነው የሚባለው። ሄዶ ቢኖር እንደ ማንኛውም ዜጋ በእኩልነት ይኖራል። «መጤ» አይባልም።

የደብረ ማርቆስ አማራው በኢህአዴግ ዘመን እንደ ማንም በፖለቲካ ተጨቁኛለሁ ሊል ይችላል። በአማራነቴም ተጨቁኛለሁ ማለት ይችላል። ግን ማንም ደብረ ማርቆስ ሀገርህ አይደለም ውጣ ያለው የለም። አብዛኞቹ የጨቆኑት ደግሞ «የራሱ» ሰዎች በገንዘብ ወይንም ርዕዮተ ዓለም የተገዙ ነበሩ። ህወሓት ደብረ ማርቆስ መጥቶ በቀጥታ አልገዛም፤ በወኪል (proxy) ነው ያደረገው። ከሞላ ጎደል አማራው ስለ ህወሓት ብሎ አማራውን እንዲጨቁን ነው የተደረገው። ከሃዲዎች ብዙ ነበሩ። ይህ በደብረ ማርቆስ ልጅ በአማራነቱ እንዲያፍር ሳያረገው አይቀርም። በትንሹ ህወሓት ተገዛሁኝ ብሎ ተገቢ ህፍረት ይሰማዋል። የራሴ ወንድሞች ካዱኝ ብሎ ያስባል። በራሱ መተማመን እና በራሱ በማንነቱ መኩራት እየከበደው ሄዷል።

አያችሁ የሁለቱ ታሪክ ልዩነቶች። ብዙ ነው። ሁለቱም በአማራነታቸው ቢጨቆኑም ታሪካቸው ይለያያል። የጨርጨሩ አማራ የችግሩን አመጣት ይረዳል። ቅድመ አያቶቼ ባደረጉት ነው ብሎ ይገበዋል። አሁን የሚደረገው ተገቢ ባይሆንም አመጣጡ ይገበዋል። ግን የደብረ ማርቆስ ልጁ አይገባውም። ቤተሰቡ ነፍጠኛ ሆኖ አያውቅም ነፍጠኝነት ምን እንደሆንም ላያውቅ ይችላል። የገበሬ፤ ወዛደር ወይንም ነጋዴ ልጅ ነው ማንንም አስገብሮ አያውቅም። ግን አማራ ነፍጠኛ ትምክህተኛ ነው ተብሎ ተጭቆኔ። እድል አጋጥሞት ከመንደሩ ወጥቶ ከፍተኛ ትምሕርት ከገባ የሚጠሉት ኦሮሞ እና ትግሬ ብሄርተኞች ያጋጥሙታል። ዘሮቼ ምን አድርገው ነው ይላል? ታሪኩን ያውቅ ይሆናል ግን በቀጥታ የሱ ታሪክ ስላልሆነ በተወሰነ ደረጃ ለጉዳዩ ባይተዋር ነው።

አሁን የደብረ ማርቆሱ ልጅ በአማራነትህ ተጨቁነሃል በአማራነትህ ተነሳ ሲባል አዎን አለምክንያት ተጨቁኛለሁ ብሎ ሊነሳ ይችላል። ግን የሃረጉ አማራ ምክንያቱን ይበልጥ በግል ደረጃ ያውቀዋል። የጭቆናው ምክንያት ተገቢ አይደለም ሃረር ለኔም እኩል ሀገሬ ነው ቢልም የችግሩ የታሪክ አመጣጡን ያውቀዋል። በዚህ ምክንያት ምናልባትም ስለ መፍትሄው ሲያስብ ሰከን እና ለዘብ ያለ አመለካከት ይኖረዋል። አልፎ ተርፎ ስተት ከተፈጠረ የሚጠብቀው ጉዳት እጅግ ከባድ እንደሆነ ስለሚያውቅ ከወደ ጽንፈኝነት መንቀዥቀዥ ይቆጥበዋል። የደብረ ማርቆሱ ልጅ ግን ከፖለቲቃ ቀውስ በቀር ምንም አይደርስበትም። አይታረድም። ሀገር አለው። የማንነት ኩራቱን ነው መመለስ የሚፈልገው።

ይህ ወደ መጨረሻ የሳፍኩት በሙሉ ግምቴ ነው። እንስቲ እናስብበት እንወያይበት። ይህ የኔ አመለካከት ብቻ ነው። ግን በአማራ ውጭ እና አማራ ውስጥ የተወለዱ አማሮች መከከል የታሪክ እና የልምድ ልዩነቶች በደምብ እንዳሉ ማወቅ አስፈላጊ ነው። መግባባት እና መናበብ እና መተባበር እንድንችል ስለዚህ መወያየት ግድ ይመስለኛል።




Monday 27 August 2018

Some thoughts on Oromiffa as the second federal language...

I fully support the idea that Oromiffa should become the second federal language, for various reasons. These include the relatively large number of Oromiffa speakers in Ethiopia, political events over the past few decades, including Oromo nationalism, Oromo region ensuring Amharic is not taught in Oromo schools as part of its drive towards Oromo nationalism, thereby created facts on the ground to force the issue, etc. make this seem to be the most prudent political direction. And I would add - and I would consider this the most important benefit of having Oromiffa as a federal language - that this can actually reduce ethnic nationalism and thereby ethnic conflict by increasing integration and the integrated population. I've written previously about this (https://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2016/09/curbing-ethnic-nationalism-via_26.html and http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/07/towards-integrated-ethiopia.html). To repeat, this means that by making Oromiffa a federal language, and thereby, for example, encouraging Amhara Region to achieve full fluency in Oromiffa, we increase integration, and we reduce ethnic nationalism, which for me is one of the existential issues for Ethiopia.

However, I think there are two very important points to make here. First, the issue of Oromiffa as a federal language is often presented as one of principle, and this is done so to claim a moral high ground. I think that in order to avoid building on sand,  we have to be honest and acknowledge that this is a political issue, not one of 'principle', insofar as principle exists. By principle I mean values such as equality, restoration, fairness, etc. By principle, a Somali can demand the same for the Somali language. Why should Amharic and Oromiffa be privileged, he can rightly ask? He might even add that while before only Amharic speakers had an 'advantage' over him, now both Amharic and Oromo speakers have this 'advantage'. (I put 'advantage' in quotes because it can easily be considered a disadvantage. A Somali who is properly taught Amharic and Oromiffa in school becomes trilingual whereas the Oromo remains monolingual - the Somali is better off.) So let us not pretend this is an issue of principle, of righteousness vs unrighteousness, of morality vs immorality, of oppressed vs oppressor. Oromiffa becomes a federal language not because of the need for equality, restoration, or fairness, but for political and practical reasons, for the same reasons as Amharic remains, because it is spoken, natively or not natively, by a large number of citizens who have the political power to enforce their demand.

A second, implicit idea in all of this is the desire for many to make this a political negotiating tool vs Oromo ethnic nationalism. "If you want us to support you in making Oromiffa a federal language, then give us ... in exchange." What most are asking in return is, I think, a revision of ethnic federalism to make it less ethnic and more national - a revision of the constitution in other words. Some are also asking for culturally symbolic concessions such as changing the script to Geez. As I said above, given that the demand is political, the demand for political concessions is certainly fair, in my mind. It makes sense, and it makes sense to carry this into the negotiating room and the public discussion sphere. What will come of it, we'll see.

Thursday 23 August 2018

ስለ አማራ ብሄርተኝነት ንቅናቄ ልሟገት

እስቲ በጠ/ሚ አብይ የተለምዶ አካሄድ (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/08/blog-post_10.html) ልጀምር… የድሮ ንጉሦቻችን ታላቅ ውሳኔዎች ለመወሰን ዘንድ አማካሪዎቻቸውን ሰብስበው ጉዳዩን እየገለባበጡ ከጫፍ እስከ ጫፍ ተሟገቱበት እና ፈትሹት ይሏቸው ነበር። አማካሪዎቻቸው ሁሉንም የሚቃረኑትን ሀሳቦችን ወክለው እርስ በርስ ተከራክረው አሸናፊውን (አሸናፊዎቹን) ለንጉሡ ያቀርባሉ። ንጉሡ ይህን መረጃ ተጠቅመው ይወስናሉ። ይህ ትውፊታችን ነው።

በአማራ ብሄርተኝነት ፅንሰ ሃሳብ አልስማማም። ሆኖም ሃሳቡን በሚገባው ለመረዳት እና ለመፈተሽ ሃሳቡን ደፌ ለመሟገት እወዳለሁ። በአማራ ብሄርተኝነት እና ኢትዮጵያዊ ብሄርተኝነት ያለው ውይይት ትንሽ የረከሰ ነው ማለት ይቻላል። ውይይትም ማለት አይችላልም። በስድብ፤ ዘለፋ እና በመግባባት እጦት የተሞለ ነው። አንዱ ወገን (እዚህ ላይ እራሴን አካትቼ ነው የምናገረው) ለሌላው ወገን አይቆረቀሩምጅ("empathy" የለም)። የዚህ ጽሁፍ አንዱ አላማ ይህንን ለማስተካከል ነው።

ሌላው አላማ ይውይይት ነጥቦቹን ለማጠንከር ነው። ይህን ማድረግ የሚቻለው የሌላውን ወገን ክርክሮች ስንመለከት ጠንካራ ጎኑን (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/03/blog-post_21.html) በማየት ነው። ፉክክር ላይ ደካማ ጎን ላይ እናተኩራለን። ገምቢ ውይይት ላይ ግን ጠንካራ ወገን ላይ ነው ማተኮር ያለብን። ስለዚህ ከአማራ ብሄርተኝነት መከራከርያ ነጥቦቻቸው ደካማ ወይንም ስሜታዊ ወይንም መሰረት የሌላቸውን ነጥቦች ትተን ምክንያት እና አቅም ያላቸውን ነጥቦች ማየት ይገባል።

ክዚህ ጽሁፍ ልመልሰው የምፈልገው ጥያቄ ይህ ነው፤ « ለመን በአማራነት መደራጀት አስፈለገ በኢትዮጵያዊነት መደራጀት አይሻልም ወይ?»። ለዚህ ጥያቄ አጭር መልሱ ይህ ይመስለኛል፤

1. የጎሳ ብሄርተኝነት አሁንም በኢትዮጵያ ዙርያ ሰፍኗል እያደገም እያለ ነው እነ ጠ/ሚ አብይ ለመቀነስ ምንም እየሞከሩ ቢሆንም። የጎሳ ብሄርተኝነት በደምብ ያልነገሰው ቦታ የአማራ ክልል ነው። ሌሎች ክልሎች በሙሉ ፖለቲካቸውን በጎሰኝነት እና ጎሰኝነት ብቻ አደራጅተዋል።

2. የዛሬው ሁኔታ ይህ በመሆኑ እና ሀገሪቷ ለ27 ዓመት በጎሳ አስተዳደር ፕሮፓጋንዳ መሞላቱ ለአማራው ህልውና እና ጠቃሚ ስልት (strategy) ሲባል ለአማራው በጎሳ ብብሄርተኝነት መልክ መደራጀት ይመረጣል በኢትዮጵያዊነት ወይንም አንድነት ከመደራጀት ይልቅ።

3. የአማራ ህዝብ ላለፉት 27 ዓመት ስለተጨቆነ እና የሀገራዊ ብሄርተኝነት ራዕይ አልሰራም የሚል አመለካከት አንዳንዱ ላይ ስላለ የአማራ ህዝብ የሀገራዊ ብሄርተኛ የሆኑት ድርጅቶችን ደግፍ ቢባልም በሙሉ ልቡ አይደግፍም።

4. ሀገሪቷ በጎሳ ብሄርተኝነት ስለጥለቀለቀች ከአማራ ውጭ ለሀገራዊ ብሄርተኝነት ያለው ድጋፍ እጅግ ዝቅተኛው ነው የሚሆነው። የነ ለማ ቡድን ኢትዮጵያ ብሄርተኛ ቢሆንም ፖለቲካ ውድድር ቢካሄድ (እንደ ምርጫ) የኦሮሞ ብሄርተኞች በቀላሉ እነ ለማ ቡድንን ያሸንፏቸዋል። ሰለዚህ በመጨረሻ የሀገራዊ ብሄርተኛ ፓርቲዎች ከአማራ ውጭ ኢሚንት ድጋር ይኖራቸዋል በአማራ ክልል ደግሞ ደካማ ድጋፍ ይኖራቸዋል። ስለዚህ ሀገር ዙርያ ሲደመር የኢትዮጵያ ብሄርተኝነት ንቅናቄው ደካማ ይሆናል ከጎሳ ብሄርተኝነት አንፃር። የጎሳ ብሄርተኝነት በደምብ አይሎ አሸናፊ ሆኖ ይገኛል።

5. ይህ ብዙ ድጋፍ የሌለው የኢትዮጵያ ብሄርተኝነት ፓርቲ የኢትዮጵያ ብሄርተኝነትን የሚደግፈው ህብረተሰብ ከነ አማራውን በሚገባው መወከል አይችልም ኃይሉ ከጎሳ ብሄርተኞች እጅግ ደካማ በመሆኑ። በድርድር ጠረጵዛ፤ ፓርላማ፤ ወይንም በፖለቲካ ኃይል ሙግት የሀገራዊ ፓርቲው ይጨፈለቃል።

6. ገን አማራው በአማራ ብሄርተኝነት ስር ከተደረጀ ለአመታት የተከማቸውን ብሶት እንደ ኃይል ተጠቅሞ ጠንካራ አማራውን በማንኛውም ደረጃ መወከል የሚችል ድርጅት ይገነባል። አሁን ባለው የጎሳ ብሄርተኝነት ያጥለቀለቀው የሀገራችን የፖለቲካ ሁኔታ የአማራ ህዝብን የብሶት ስሜት እንደ ኃይል ተጠቅሞ ጠንካራ እና ቋሚ ድርጅት ማቋቋም ለአማራው ህልውና ግዴታ ነው።

7. ጠንካራ የአማራ ፓርቲ ከተቁቁመ ሌሎች የጎሳ ፓርቲዎችን በኃይል ሚዛን ይይዛቸዋል። ምክንያቱም የአማራ ብሄርተኛ ፓርቲው የጎሳ ፓርቲ ቢሆንም አማራ ጎሰኝነት በባህሪው ከኢትዮጵያ ብሄርተኝነት የተቆራኘ ስለሆነ። በዚህም ብምክንያት የአማራ ብሄርተኝነት ፓርቲው ከክልል ውጭ ላሉት አማሮች ያገለግላል።

እኔ እንደሚመስለኝ የአማራ ብሄርተኝነት ንቅናቄ መኖር ምክንያት ባጭሩ ይህ ነው።

እስካሁን ባየሁት የተለየዩ ሰዎች አስተያየት ሌሎች የክርክር ነጥቦች ይነሳሉ። ለምሳሌ «አምራ ከሁል ተጨቁኗል»፤ «ሌላው ሲደራጅ ልምን አማራ ይጠየቃል»፤ «በአማራ ብሄርተኝነት ምን አገባችሁ»፤ «ኢትዮጵያዊ ድርጅቶች በአማራ ትከሻ ላይ ነው የተቁቁሙት»፤ «የአንድነት ኃይሎች አማራን ዘርፈውታል ነግደውታል»፤ «የአንድነት ኃይሎች ሌቦች ናቸው» ወዘተ። እነዚህ ስሜታዊ፤ ከመሰረተ ጉዳዩ ውጭ፤ ወይንም ሃሰት የሆኑ የክርክር ነጥቦች ስለሆኑ አልተጠቀምኳቸውም ክርክሩን ያደክማሉ እና።

ስለዚህ የአብን ከአንድነት ይልቅ በአማራነት መደራጀት ምክንያት እንዲህ ነው። እስቲ ህልችሁም በሁለቱም ወገን ያላችሁ ይህን አንብቡ እና እናንተም ከአቋማችሁ ተቃራኒ የሆነውን ወገን ይዛችሁ መከራከር ሞክሩ። እንዲህ እያደረግን ወደ መስማማት ወይንም በሰላም ላለመስማማት ደረጃ (https://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2016/10/blog-post.html) እንደርሳለን ብዬ እገምታለሁ።

Monday 20 August 2018

ከሰው ማንነት ጋር መከራከር ያስቸግራል

ድሮ ከኤርትራዊያን፤ ትግራይ፤ ኦሮሞ ብሄርተኞች ጋር ስንከራከር እንዲህ አይነቱ ነጥቦችን እናነሳ ነበር፤

  • ሁላችንም ኢትዮጵያዊ ነን ማንም ከማንም በላይ አልተጠቀመም አልተጨቆነም
  • መንግስት በጎሳ ወይም ብሄር አድሎ አድርጎ አያውቅም
  • ከሁሉም ጎሳ የፖለቲካ መሪዎች አሉ ታላላቅ መሪዎቻችን ብዙ የተለያየ የጎሳ ደም አላቸው
  • የሁላችንም ጥቅም አብሮ ከመሆን የተያያዘ ነው
  • ጎሰኝነት የጋራችንንም የያንዳንድ ጎሳችንንም ጥቅም ይጎዳል ግጭት እንዲሰፍን ያደርጋል
    ወዘተ

እነዚህን አይነት ፍሬአማ ነጥቦች ላይ ከተወያየን ብኋላ ሁልጊዜ መጨረሻ ላይ ወደ አንድ ነጥብ እንመለሳለን። ኤርትራዊያኖች «እኛ ኤርትራዊያን ነን ኢትዮጵያዊ አይደለንም» ትግራዮውቹ «እኛ መጀመርያ ትግራይ ነን» ኦሮሞ ብሄርተኞች «እኛ ኦሮሞ ነን ኢትዮጵያዊ አይደለንም» ብለው ውይይታችንን ያቆማሉ። የአባባላቸው ትርጉም ግልጽ ነበር፤ ማንነታችን ይህ ነው እና ስለ ማንነታችን ምንም ማለት አይቻልም ነው። ጉዳዩ ሌላ አይደለም፤ ጥቅም እና ጉዳትም አይደለም፤ «ማንነት» ነው።

እንዲሁም አሁን ከአማራ ብሄርተኝነት ደጋፊዎች ይህንን ነው የማየው። ባለፉት 45 ዓመት የፖለቲካ ችግሮቻች (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/07/blog-post_15.html) ምክንያት የተወሰነው የአማራ ህብረተሰብ ውስጥ አዲስ የአማራ ማንነት (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/08/blog-post_17.html) ተፈጥሯል። ይህ ማንነት የአማራ ብሄርተኝነት ንቅናቄ መሪ @  የጻፉት በደምብ የሚገልጸው ይመስለኛል፤

«አማራ ነኝ ፣ አማራ ነን ፤ እንደአማራነት የተሰነዘረብኝን ጥቃት በአማራነት ተደራጅቼ እመክታለሁ ፤ በዚህም ህልዉናዬን፣ ፍላጎቶቸንና ዘላቂ ጥቅሞችን አስከብራለሁ»
(https://www.facebook.com/photo.php?fbid=1934811083224914&set=a.308423195863719&type=3)

ጉዳዩ የማንነት ስለሆነ ምንም አይነት «ሎጂካል» ሙግት ማንነትን እንደሚያጣጥል ሊቆተር ይችላል። ውይይት ቶሎ ወደ ቅራኔ ይወሰዳል። ለምሳሌ እንደ እኔ አይነቱ በኢትዮጵያዊነት መደራጀትን የሚያምን «የአማራ ጥቅምን የሚያሟላው በኢትዮጵያዊነት መደራጀት ነው» ብል ለአማራ ብሄርተኛው ማንነቱን የተቸትኩኝ ይመስለዋል እና መልሱ ከጉዳዩ ጋር ሳይሆን ከማንነቱን መከላከል ጋር የተያያዘ ይሆናል። «ይህን ሁሉ ጥቃት ደርሶብን እንዴት በአማራነት አትደራጁ ትላለህ» ይባላል። «ድሮስ እናንተ በኛ ትነግዱ ትጫወቱ ነበር አህን ያበቃል» ይባላል። «ሌሎች የጎሳ ብሄርተኞችን ለምን አትተቹም?» ይባላል። ወዘተ።

የነ ጃንሆይ፤ ደርግ፤ ኢህአፓ፤ መኢሶን፤ መላው አማራ/ኢትዮጵያ፤ ቅንጅት፤ ግንቦት ሰባት ወዘተ ኃጢአቶች በሙሉ በ«አንድነት ድርጅቶች» እና በ«ኢትዮጵያዊነት» ርዕዮተ ዓለም ላይ ይለጠፋሉ! ይህ ሁሉ የማይሆኑ («ኢሎጊካል») መልሶች የሚሰነዘሩት ጉዳዩ በዋናነት የማንነት ስለሆነ ነው።

አንዴ በበሶት እና «ጭቁንነት» የተመሰረተ ማንነት ስር ከሰደደ በሎጂክ የተመሰረተ ሙግት ምንም መቀየር አይቻልም። ወይ ከነሱ ጋር ነህ ወይንም ጠላት ነህ።

እዚህ ላይ አንድ መናገር የምፈልገው ነገር አለ። በነዚህ የአማራ ብሄርተኞች ምንም ምንም አልፈርድም። ያወረስናቸው ኢትዮጵያ እጅግ ህመምተኛ እና ደካማ ናት (አሁንም እንዳ አብይ አህመድ አይነት ጀግና መውለድ ብትችልም)። ያወረስናቸው የፖለቲካ ባህል ጥላቻ የቶሞለው ስልት-ቢስ የሆነ ነው። በጃንሆይ ዘመን በሰላም ነገሮችን ከማስተካከል ሀገሪቷን ወደ ገደል ወሰድናት (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/07/blog-post_15.html)። ለዚህ ማንም ላይ ጣቴን አልጠቁምም። እንደ በኢትዮጵያዊነት የሚያምን ኢትዮጵያዊ ብሄርተኛ የኔ ጥፋት ነው ብዬ ሃላፊነት እወስዳለሁ። ይቅርታም እተይቃለሁ።

ይህን ካልኩኝ በኋላ የአማራ ብሄርተኞችን እንደ ኦርሞ ብሄርተኞች ተጠንቅቆ መያዝ ያስፈልጋል እላለው። እርግጥ የአማራ ብሄርተኞች በአብዛኛው በጎሳ ብሄርተኝነት አናምንም ስትራቴጂ ነው ወይንም ሌሎቹ በጎሳ ስለተደራጁ ግዴታ ሆኖብን ነው ይላሉ። በኢትዮጵያዊነት እናምናለን ይላሉ። ነገ ህገ መንግስቱ ቢቀየር እኛም በጎሳችን መደራጀት እናቆማለን ይላሉ። አቃፊ ብሄርተኞች ነን ይላሉ።

ሆኖም የጎሳ ማንነት በደምብ ገብቶባቸዋል። መጀመርያ አማራ ነን ቀጥሎ ኢትዮጵያዊ የሚሉ አሉ። ኢትዮጵያዊነት ጠፍቷል የሚሉ አሉ። አንቀጽ 39 ጥሩ ነው የሚሉ አሉ። በመታወቅያ ላይ ጎሳ ቢኖር ጥሩ ነው የሚሉ አሉ። አማራ ብሄርተኛ ያልሆነ አማራ አይደለም የሚሉ አሉ። ወዘተ።

ስለዚህ ይህን ማንነት በዘዴ መያዝ ይኖርብናል። ከሙግት ይልቅ empathy ወይን መቆርቆር ነው የሚያስፈልገው። ከሙግት በፊት መተማመንን መፍጠር ያስፈልጋል (አንድ የሆንን እና የምንተማመን መስሎኝ ነበር ግን ለካ የማላውቀው ብዙ ግጭት እና ቁስል አለ በአምራ ብሄርተኞች እና «አንድነት ኃይሎች»)። ትክክለኛ መተማመን ጋር ከደረስን በኋላ ብቻ ነው ወደ ውይይት እና ሙግት መግባት ያሚቻለው።

የ27 ዓመት ጥቃትን አናጣጥል። የብዙ አማራ «ሞራል» ተሰብሯል። ጥቂት ትግሬ ገዝቶን ነበር ብለው የሚያስቡ ብዙ አሉ። ትክክለኛውን ሚዛናዊውን ግንዛቤ ላይ ከመድረስ በራስ አለመተማመን እና የ«ጭቁን» ስሜት ብዙዎቻችን ላይ አድሯል። ይህን እኔ በበኩሌ አልተገነዘብኩትም ነበር። ምን ያህል ስር እንደሰደደ አልገብኛም ነበር። ድሮ ኩሩ የነበረው አማራ ምን ያህል ሞራሉ እንደተጎዳ እና ወደ ጎሳ ብሄርተኝነት ማዘንበል እንደሚችል አልገባኝም ነበር። አሁን ግን ትንሽ የገባኝ ይመስለኛል። ከተሳሳትኩኝ አርሙኝ።

አዲሱ ትውልድ አዲስ በመሆኑ ምክትንያት ብቻ ከድሮው ይሻላል ማለት ስህተት ነው

በርካታ ወጣቶች የኢትዮጵያ የፖለቲካዊ እና መህበራዊ ችግሮችን በበፊቶቹ ተውልድ እያሳበቡ ይገኛሉ (አንዱ ምሳሌ ይህ ነው፤ https://www.facebook.com/photo.php?fbid=1934811083224914&set=a.308423195863719&type=3)። የበፊት ትውልድ ያጠፋው የሚያጠፋው ለሁሉም ግልጽ ነው። ግን አዲሱ ትውልድ አዲስ በመሆኑ ብቻ ይሻላል ማለቱ ትልቅ ስህተት ነው!

ጠ/ሚ አብይም ይህንን በትክክል አስረድተዋል። ጠማማ አያት ኣን አባት ያለው ልጅ ከጠማማነት ውጭ ነኝ ማለት አይችልም። ማለቱ እራሱ ያለውን ችግር ይገልጻል! ትህትና እና እራስን መመርመር ብቻ ነው መፍትሄው። ተሳስቼው ይሆናል እነሱም ተሳስተዋል ግን አልፈርድባቸውም ነው ትክክለኛው አስተሳሰብ የሚመስለኝ።

ስለዚህ ጉዳይ ዘጠኝ ዓመት በፊት ደሳለኝ አስፋው የጻፈውን ልጥቀስላችሁ። በዛን ወቅት ልደቱ አያሌው እነ ኃይሉ ሻውል፤ ብርሃኑ ገጋ ወዘተ እየወቀሰ ፖለቲካውን ለኛ ለአዲሱ ትውልድ ተውት እያለ ነበር…

------------------------------------------------------------------
Is The New Generation Really Better Than The Old?

In his essay, "Civility and Political Discourse in Ethiopia: Time to Change the Guard," Dr. Yacob Hailemariam makes two broad points: 1) The Marxist-Leninist upbringing of most Ethiopian politicians has resulted in a dysfunctional political culture lacking civility and compromise; and, partly for this reason, 2) it is time for the younger generation (presumably untainted by Marxism-Leninism) to take over the political landscape. 

Solomon G. Selassie, in his comment on Dr. Yacob Hailemariam's essay, addresses Dr. Yacob's first point. He illustrates that even those groups (and individuals) far from Marxist ideology - Medhin, EDP, AEUP, UDJ, etc. - suffer from the same dysfunctional traits as the ex-Marxists. This suggests that Marxism-Leninism is not the only problem. Ato Solomon suggests that cultural traits - specifically, a militaristic and uncompromising tradition - have also played a role in our dysfunctional politics. Needless to say, I agree wholeheartedly with him.

Here in this article, I would like to briefly comment on Dr. Yacob's second point. Certainly he is right to say that there must be a culture of 'passing the baton' in Ethiopian politics. No doubt about it - the old personalized, patron-client politics must come to an end, giving way to healthy, strong, and stable institutions. Nobody would disagree with this.

What I have trouble with is the (perhaps unintended) assumption that the inheritors of the baton, the 'younger' generations, will do a better job than their predecessors because they are unburdened by Marxist-Leninist thought. I would counter that not only can we not assume that the younger generations would do better, but there is a good possibility that they would do worse.

Let me offer a couple of small anecdotes. I remember a video of an EDP meeting taken during the difficult months in 2005 when the opposition was under intense pressure. In the video, a young party member stood up and ranted against "diaspora PhD's, tired of eating Big Macs in the West, coming to Ethiopia to tell opposition activists what to do." As I watched his speech, I thought that I could close my eyes and picture any 'old guard' politician making the same sort of dysfunctional remarks.

Another example is of course Lidetu Ayalew, who in his book YeArem Ersha (The Weed Farm) wrote about this very topic. No matter how empathetic one is towards Ato Lidetu, it would be hard to say that his behaviour is markedly different from his elder colleagues. Perhaps on a superficial level, perhaps in the way he talks. But when it comes to fundamentals, especially when it comes to the great weakness of Ethiopian politicians - their incapacity to manage conflict - he is no different from his predecessors. The apple does not fall far from the tree.

Why might our younger politicians have the same or perhaps even less ability than their elders? Well, it is quite simple - if we assume that the old guard of Ethiopian politicians are a troubled, dysfunctional lot, then we have to say that the new guard, their children in essence, have had a terrible childhood! They have been brought up with poor or no role models and exhibit the resulting symptoms - identity crises and rootlessness, inferiority complex, fear, rebellious character, etc. In addition, they have been brought up in a toxic political environment. They need healing, and in order to heal, they need good, positive role models and mentors. They need a positive connection with the past. They need the guidance of elders who have learned from the past, such as Dr. Yacob, to help them avoid making the same mistakes as their predecessors.

In my opinion, those members of the older generation who have some connection with and appreciation of the past glories of Ethiopia, but yet have learned from past errors, who know what introspection means, who know to say sorry, and who have a burning desire for positive change are few and far between and therefore invaluable to the democracy movement. If they leave the political scene, they are leaving it to their peers who remain unchanged and dysfunctional, and to younger colleagues who are lost, having not had the benefit of positive inter-generational guidance. This, I think, presents a grave danger to the state of Ethiopian politics.


Dessalegn Asfaw can be reached at dessalegn_asfaw@yahoo.com

Friday 17 August 2018

የአማራ ኩራት የት ሄደ?

ለመጀመርያ ጊዜ በአማራ ስም ፋንታ በኢትዮጵያ ስም ብትደራጁ አይሻልም ወይ ብዬ የአማራ ብሄርተኞችን ስጠይቅ ያገኘሁት መልሶች (ስድቦቹን ትተን) አስገራሚ ነበር። ምናልባት 80% ስለ አማራ ላይ ባለፉት 27/40 ዓመት የደረሰበት በደል እና ጭቆና ነው። የአማራ ህዝብ ጥቅም ይበልጥ የሚከበረው በአማራነት በመደራጀት ነው ወይንም በኢትዮጵያዊነት በሚለው ዙርያ ከመወያየት ፋንታ ስለ አማራ መጨቆን የጭቆና ቆጠራ ውስጥ ገባን። ይህን ስል አማራው አልተጨቆነም ማለቴ አይደለም ከሌሎች ይልቅ በመንግስት ብቻ ሳይሆን በግለ ሰብ እና በቡድን በአማራነቱ ተጭቁኗል «መጤም» እየተባለ በትውልድ ሀገሩ ባይተዋር ሆኗል። ይህ ሁሉም የሚያቀው ነው። ግን ይህ በፍፁም የአማራ ማንነት መግለጫ መሆን የለበትም። ላስረዳ…

እንደገባኝ ይህ የ27 ዓመት ጭቆና የዛሬው የአማራ ማንነት መሰረት ሆኗል። እስቲ ስለ አማራ እና አማራነት ንገረኝ ሲባል የዘመኑ አማራ ላለፉት አመታት «እጅግ የተጨቆነ፤ የተበድለ፤ የተፈናቀለ፤ የተዋረደ፤ ባሁሉ የተሰደበ፤ ማንነቱ የተገፈፈ» ወዘተ ነው የሚለው። የድሮ አማራ ይህንን ቢሰማ እጅግ ግራ ነበር የሚገባው። ማን ነው አማራ ምንድነው አማራነት ብለህ የድሮ አማራን ብትጠይቀው 3000 ዓመት ታሪክ ያለው፤ ሃይማኖት ያለው፤ ስልጣኔ ያለው፤ የአፍሪካ ቁንጮ፤ የሰው ልጅ ቁንጮ፤ ፍርሃ እግዚአብሔር ወዘተ ነው የሚለው! ልዩነቱን አያችሁ። አማራ በወጉ መሰረት እራሱን የሚሰይመው ማንነቱን የሚገልጸው በአዎንታዊ መንገድ ነው። ዛሬ ግን እድሜ ለረዥም ዓመት ጫና እና የጎሳ ብሄርተኝነት እና የማርክሲዝም ፕሮፓጋንዳ አማራው ማንነቱን ስቷል።

የዛሬ አማራ የበታችነትን ስሜት (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/07/blog-post_30.html) መቀበል ብቻ ሳይሆን የማንነቱ መሰረት ያደረገው ይመስላል። የሰለባ አመለካከት (victim complex)፤ የበታችነት ስሜት (inferiority complex) አጥቅቶናል። እንደ ጥቁር አሜሪካኖች ወይንም ሌሎች በጭቆና ምክንያት ማንነታቸውን ሙሉ በሙሉ ለ«ጭቁን ነው ማንነቴ» የሚለው አስተሳሰብ እራሳችንን ሰጥተናል።

በራሳችን መተማመን እና መኩራት ቀርቷል። ጣልያን ለአምስት ዓመት ኢትዮጵያ ውስጥ ቆይቶ ተጭቁነናል ተገዝተናል ብለን አናውቅም። የድሮ አማራ ምንም ያህል ቢጭቆን እራሱን «ተጨቋኝ ነኝ» ብሎ አይሰይምም። ጦርነት ላይ ነኝ ነው የሚለው። እንደ አያቶቼ አሸንፋለው ነው የሚለው። እንጂ እጁን ለበታችነት ስሜት አይሰጥም ምን እንደሆነም አያቅም። ለዚህ ነው እስከ ዛሬ ጣልያን ገዝቶናል አንልም። ውግያ ላይ ነበርን ነው የምንለው። ይህ ነበር የድሮ እና ትክክለኛ ተውፊተኛ የአማራ ስለራሱ ማንነት አስተሳሰብ።

ዛሬ ግን ይህ ባለመሆኑ ብዙ አማራ በተለይ ወጣቱ «ጭቁን ብሄረሰብ» ነኝ የሚለው አስተሳሰብ አምኖበት ውጦታል (internalize) ተዋህዶታል። ስለዚህ ይመስለኛል የ«አማራ ብሄርተኝነት» ድሮ ታይቶ የማይተወቀው ዛሬ እንደዚህ መነሳት የጀመረው። በጎሳ ብሄርተኝነት የማናምነው ወንድሞች እና እህቶች ይህ የአማራ ብሄርተኝነት ፖለቲካ ለአማራ ህዝብ ያዋጣል ወይ በሚለው እንነጋገር ስንል ብዙ ጊዜ ስሜታዊ መልስ እና ስድብ ነው የሚጠብቀን። ምክንያቱ የአማራ ብሄርተኛውን ማንነት ጥያቄ ውስጥ ስላደረግን ነው። ማንነቱ «ጭቁን አማራ» ሆኗል። አንድ ሰው ይህ ነው ማንኔቴ ብሎ ከሰየመ አልፎ ተርፎ ቁስል ያለው ከሆነ በዚህ ዙራይ መወያየት አይችልም። ውይይቱ በሃሳብ ሳይሆን በማንነት ስለሆነ በዚህ መደራደር የለም። ስሜት እና ቁጣ ብቻ ነው።

ይህ ክስተት እነ ሻዕቢያ፤ ህወሓት፤ እና ኦነግ ሲመሰረቱ አይተነዋል። ወደነዚህ የሚያዘንብሎ ሰዎችን ድሮ ስናናገር አንዴ እንዲሁም እንዴት ማንነቴን በጥያቄ መልክ ታቀርበዋለሁ ብለው ይናደዱ ነበር። በማንነት ድርድር የለም ይሉ ነበር። መገንጠል አይበጅም ኢትዮጵያዊ ናችሁ ወዘተ አይነት ነበር በፍፁም መስማት ብቻ ሳይሆን ስለዚህ መነጋገርም አይፈልጉም። አንዴ ማንነት ከተቀየረ በአጭር ጊዜ ምንም ማድረግ አይቻልም።

ስለዚህ አሁን ጥንቃቄ ያስፈልጋል። ብዙ በተለይ ልጅ የሆኑ አማራ እህት እና ወንድሞቻችን ባለፈው 27 ዓመት የጎሰኝነት፤ ፀረ አማራ፤ ማርክሲዝም ፕሮፓጋንዳ ቶሞልተው የአማራ ማንነታቸው ተቀይሯል። «ጭቁን» ነኝ ብለው አምነዋል። ለዚህ ጭቆና መልሱ ወደ «አማራነት» ከ«ኢትዮጵያዊነት» ማስቀደም ነው ብለው አምነዋል። ይህን በሰላም መተቸት ማንነትን መተቸት ሆኗል።

ጉዳዩ እንደዚህ ባይሆን እና የበታችንነት እና የ«ጭቁን» አስተሳሰብ ባይህኖር መርሰረታዊ ጥያቄውን በአማራ ስም ነው ወይም በኢትዮጵያ ስም ነው መደራጀት የሚበጀን መወያየት እንችል ነበር። አሁን ግን ለብዙዋች ውይይት አቻልም ስሜት ይነካልና ማንነትን ይነካልና።

አንድ ማረግ የምንችለው የአማራ ባህል እና ወግ በትክክሉ ማስተማር ነው። የአማራ 3000 ዓመት ታሪክ በራሱ መኩራት እና መተማመን ነው። ፍርሃት የለውም። እንደ ጠ/ሚ አብይ (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/08/blog-post_10.html) ማንም አይነት ሰውን አቅፎ ይዞ እግዚአብሔር ልጅ መሆኑን አምኖ ወደ ትክክለኛ መንገድ ማምጣት ነው ባህላችን።  ወደዛ ለመመለስ እንጥራ። መሰረታዊ ማንነቱን ያጣ ህብረተሰብ ይወድቃል።

Wednesday 15 August 2018

ከአንድ የ«አምራ ብሄርተኛ» ያደረግኩትን ቃለ ምልልስ

ከአንድ የ«አምራ ብሄርተኛ» ያደረግኩትን ቃለ ምልልስ ላቀርብላቹ እወዳለሁ። እኔ አስፋው ጠያቂው ሆኜ እንግዳዬ ደግሞ ግዮናዊት ሀገሬ ትባላለች እራሷን የአማራ ብሄርተኛ ብላ የምትሰይም የ28 ዓመት መምህርት ናት። ቆይታችን እንዲህ ነበር፤

አስፋው፤ ለቃለምልልስ ፈቃደኛ በመሆንሽ አመሰግናለሁ፤ እንኳን ደህና መጣሽ።

ግዮናዊት፤ ምንም አይደለም፤ እኔም አመሰግናለሁ።

አስፋው፤ እስቲ ስለ አማራ ብሄርተኝነት ርዕዮተ ዓለም ትንሽ ንገርኝ።

ግዮናዊት። የአማራ ብሄርተኝነት የአማራ ህዝብ ለአማራ ህዝብ መቆም አለበት የሚል ርዕዮተ ዓለም ነው። የአማራ ህዝብ ባለፉት 27 ዓመት፤ 40 ዓመት ማለት ይቻልም ይሆናል፤ ብዙ ግፍ እና ሰቆቃ የደረሰበት ነው። ክብሩን ከማጣት እስከ ቡድናዊ ግድያ (genocide) ተፈጽሞበታል። ከበየ ኢትዮጵያ ክልሎች ተፈኛቅሏል። ህዝቡ ተገድሏል። የመንግስት በጄቱ ተቀምቷል። አማራ ሀገር ከሁሉም ድኻ ሆኖ ግን በጨቋኝነት ይፈረጃል። እስካሁን እንደ ጨቋኝ ይታያል እንደ ህዝብ መቀጣት አለበት ተብሎ ይሰበክበታል። የአማራ ብሄርተኝነት ይህን ያለፈውንም፤ ያለውንም፤ ወደ ፊት የሚመጣውንም አማራ ላይ ጥቃት ለመቋቋም ነው የሚቆመው። ከዛ አልፎ ተርፎ የአማራ ህዝብ መደራጀት ያለበት እራሱን ለመከላከል ብቻ ሳይሆን ለመቋቋም እና ለመበልጸግ። ልጆቻችን እንዲማሩ፤ እርስ በርስ እንድንረዳዳ፤ ለራሳችን ልማት እንድናመጣ ወዘተ የሚታገል ርዕዮተ ዓለም ነው።

አስፋው፤ ግን እስቲ «አማራ» ከሌላው ይበልት ተጨቁኗል ማለት ይቻላል። ባለፉት 27 ዓመት ሁሉም ትግራይ ያልሆነ ተጨቁኛለሁ ይላል። ኦሮሞ በስመ ኦነግ። ጋምቤላ ለመሬቱ፤ አኟክ ጭራሽ ጄኖሳይድ ተፈጽሞበታል። ሲዳማ በየጊዜው ተመቷል። ወዘተ።

ግዮናዊት። አዎን ህወሓት ሁሉንም መትቷል ግን እንደ አማራ በየ ክልሉ የሚገደል የለም። እንደ አማራ የህዝብ ቁጥሩ እንዲመነምን የተደረገ የለም። እንደ አማራ በየ ክልሉ የሚፈረጅበት ጭቋኝ ተብሎ የሚረገጥ የለም።

አስፋው፤ አዎ ግን ሁሉም ጎሳ እንዲሁ የራሱ እሮሮ አለው እኮ።

ግዮናዊት፤ አይደለም፤ ሁሉም መንግስት ጭቁኖኛል ማለት ይችላል እንበል። በዚህ እንስማማ። ግን አማራ የተጠቃው በመንግስት ብቻ ሳይሆን በሌላው ህዝብም ነው። ይህ ነው ልዩነቱ። ሲገደል ሲፈናቀል መንግስት ብቻ አይደለም ይህን የሚያደርግ የነበረው። መንግስት «ጭቋኝ» ብሎ ሰየመው ከዛ በኋላ የተለያዩ ግለሰብ እና ቡድኖች ይህን ይዘው አማራን በየቦታ ያሰቃያሉ። ይህ ነው ልዩነቱ። አማራ የትጠቃው በመንግስት ብቻ ሳይሆን በህዝብም ነው።

አስፋው፤ ግን እኮ የአርሲ ኦሮሞን ብትጠይቀው የአማራ መንግስት ለ100 ዓመት ጨቁኖኝ ነበር ሰለዚህ እኔም በመንግስት ብቻ ሳይሆን በግለሰቦች ተጨቁኛለሁ ይላል። አማራ ብቻ አይደለም እንደዚህ አይነት ጭቆና ዘመን ያሳለፈው ይላል። የ«ተጨቆንኩኝ» እሽቅድድም አልሆነምን?

ግዮናዊት፤ ያየድሮ ታሪክ ነው ባለአባቶች መሬታቸውን ከተነጠቁ 44 ዓመት አልፏል። አማራ ላይ ግን አሁንም ነው ጥቃት የሚደረገው።

አስፋው፤ ግን የታሪካዊው ጭቆና አሁንም ርዝራዥ አለው ይሉናል። አማራው ጨቁኗል አሁንም የድሮ ጭቆናው ውጤት ነው የሚያገኘው ይላሉ። መቼም ወደ ኋላ እየተሄደ ሁሉም የግፍ ቆጠራውን ያደርጋል ከሁሉም እበልጣለሁ ይላል አይደለምን?

ግዮናዊት፤ በዚህ አንስማማም። የድሮ የድሮ ነው። ዛሬ ግን ከሁሉም ሰለባ አማራ ነው ብለን ነው በአማራ ብሄርተኝነት የምናምነው።

አስፋው፤ ጥሩ። ግን ከሌሎች ድጋፍ አትጠብቁ። ከኛ በሙሉ እናንተ ናችሁ የተጨቆናችሁት እንዲሏችሁ አትጠብቁ። በዛ መሰረት እንደረደራለን ብላችሁ አታስቡ።

ግዮናዊት፤ ይሁን የራሳቸው ጉዳይ በዚህ መስማማት አያስፈልግም። ግን ለኛ ለአማራ ህዝብ እኛ ዋና ተጨቋኝ እንደሆንን እናምናለን ይህንንም እንደ ምክንያት አድርገን ነው የምንደራጀው።

አስፋው፤ እሺ አማራው ተጎድቷል እየተጎዳ ነው። ለምንድነው በአማራነት መደራጀት የሚያስፈልገው ይህን ጥቃት ለመቋቋም? ለምን በኢትዮጵያ ወይንም በ«ኢትዮጵያ-አማራ» ስም መደራጀት ለዚህ አይበጅም? በኢትዮጵያ ስም ብንደራጅ አማሮች ብቻ ሳይሆን ሌሎችም ለኛ ይቆሙ ነበር።

ግዮናዊት፤ ተጨቋኙ አማራ ነውና። ምን ሌላ ምክንያት አለው። በአማራነቱ እየተሰደበ እየተኮነነ እየተገደለ እያለ እራሱን በአማራነቱ መከላከል አለበት። ማን ሌላ ይከላከልለት? እራሱን ካደራጀ አይጠቃም። ሌላን ከጠበቀ ይጠቃል። ግልጽ ነው እኮ።

አስፋው፤ ማለት የፈለግኩት እንዲህ ነው። የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ እንውሰድ። ይህ ድርጅት እራሱን የ«ኢትዮጵያ ብሄረአዊ ንቅናቄ» ብሎ ቢሰይም አሁን የሚሰራውን መስራት አይችልም ነበር ያውም ሌሎችን አካቶ እና ተጨማሪ ኃይል አከማችቶ?

ግዮናዊት፤ አይችልም። ስሙ «ኢትዮጵያ» ከሆኑ ሁሉንም ማቀፍ ይኖርበታል ለአማራ የተለየ ጭቆና ብቻ መቆም አያችልም። ይህ «ኢትዮጵያዊ» ድርጅት የአማራ ህዝብ ለብቻ የጎደለውን ማሟላት አይችልም። የአማራን ርስት ማስመለስ አይችልም። ወዘተ።

አስፋው፤ ግን በዚህ መልኩ ይችላል። ኢትዮጵያዊ ድርጅት ከሆነ ሁሉንም ለተጨቆነው አማራ ለመቆም ማስተባበር ይችላል። ሁሉንም ለተጭቆነው ኦሮሞ ማስተባበር ይችላል። ይህ ከአማራ በቻ ይበልጥ ትልቅ ኃይል አደለምን?

ግዮናዊት፤ በቴኦሪ ደረጃ ጥሩ ይመስላል ግን በዚህ ዘመን ከአንድ ብሄር በላይ ሲቀላቀል መዘዙ ብዙ ነው። እስካሁኑም አልሆነልንም። አማራ አማራ አትበሉ እንባላለን። ይህ ደግሞ አይመቸንም።

አስፋው፤ እስካሁን አልሆነምን ተይው! የአማራ ብሄርተኝነትም እስካሁን አልሆንም። በደምብ ላልተሞከረ ነገር አልሆነም ማለት ሃሰት ነው። የአንድነት ድርጅቶች ያልተሳካላቸው በአንድነት ስለሚያምኑ አይደለም በእርስ በርስ የጎሳ ፍጭት አይደለም።

ግዮናዊት፤ ምንም ቢሆን እኛ አማሮች ለአማራ መስራት ነው የምንፈልገው።

አስፋው፤ ታድያ ይህ አቋማችሁ ከሌሎች ጎሰኞች እንደ ህወሓት ወዘተ ምን ይለያችኋል?

ግዮናዊት፤ ቅድም እንዳልኩት እኛ ለብቻ ይበልጥ ተጨቁነናል። አልፎ ተርፎ እኛ በኢትዮጵያዊነት እናምናለን። እንገንጠል አንልም። አማራ ኢትዮጵያዊ ነን ነው የምንለው። ይህ ነው ትልቁ ልዩነት።

አስፋው፤ በክልሌ ያለው አማራ «መጤ» ነው የሚለው የኦሮሞ ብሄርተኛውም እንዲሁ ነው የሚለው እኮ። ተበድያለሁ። መገንጠል አልፈልግም (መብቱ አይወሰድብኝ እንጂ) እና እኔ መጀመርያ ኦሮሞ ነኝ ቀጥሎ ኢትዮጵያዊ (የብሄር ፌደራሊዝም እስካለ አለ በለዛ ለቃለው!) ። እንዲሁ ነው የሚሉት። አሁንም ምን ይለያችኋል።

ግዮናዊት፤ እኛ ደግሞ ማንንም አንጨቁንም ከክልላችን ይውጣልን አንልም ብለንም አናውቅም። ይህ ነው ሌላ ልዩነታችን።

አስፋው፤ ግዮናዊት፤ ሌሎቹም እኮ ማንንም አንጨቁንም። ታሪካዊ ጭቆናን እናስተካክላለን ለምሳሌ በaffirmative action አይነት ነገሮች መሬተም ወደ ድሮ የተቀማበት በመመለስ ወዘተ። በክልላችን የኛ ቋንቋ ነው የሚሰፍነው እንላለን በመንግስት በትምሕርት ደረጃ ወዘተ። ሌላው ይህን ካልተቀበለ ይውጣ ከፈለገ ነው የሚሉት። በአማራ ክልልም የአማራ ብሄርተኝነት ከሰፈነ እንዲሁ እይደለም የሚሆነው? በአማራ ክልል ያለው አማራ ያልሆነው ህብረተሰብ ሁለተኛ ዜጋ አይሆንም?

ግዮናዊት፤ አይሆንም ብቻ ነው ማለት የምችለው። አሁን በአማራ ክልል ያሉ የኦሮሞ ዞኖች ውስጥ ነዋሪዎቹ ሙሉ ነፃነት አላቸው በቋንቋቸው በፍላጎታቸው መተዳደር። አገውም እንዲሁ።

አስፋው፤ ስለዚህ አማራው በክልሉ ያሉትን «አናሳ ብሄሮችን» አይጨቁንም የመጨቆን ባህሪውም የለውም እንበል። ጥሩ። ግን ሌሎቹም እንደዚህ እያሉ ግን በደል ያደርሳሉ። ለምሳሌ በኦሮሞ ክልል የአማርኛ ትምሕርት ይቀራል ቢባል አንቺ እንደ ጭቆና ታዪው ይሆናል ግን ኦሮሚያ ቋንቋችን እንዳይሸረሸር ነው ይላል። አማራው በአማራነቱ መደራጀቱ ይህን ጉዳይ እንዴት ያደርገዋል?

ግዮናዊት፤ የአማራ ድርጅት ለዚህ መልስ ይኖረዋል። ከኦሮሚያ ለሚኖረው አማራው መብት ይቆማል ይታገላል።

አስፋው፤ ከመፈክር አልፎ በተግባር ያልሸው ምን ማለት ነው?

ግዮናዊት፤ በአማራ ክልል እንደዛው አይነት ፖሊሲ እናመጣለን። በኛ ኦሮሞ ዞኖችም ትምሕርት ቤት በአማርኛ ብቻ ማድረግ ነው።

አስፋው፤ ግን አማራ በብዛት በየክልሉ አለ። በዚህ ብድር በመመለስ (tit for tat)ተሸናፊ አማራው ነው የሚሆነው። ልክ እንደ ሰርቢያኖች በዩጎስላቪያ በኢትዮጵያ የጎሳ ግጭት ከተነሳ አማራው ነው ከሁሉም በላይ የሚጎዳው አይደለም?

ግዮናዊት፤ አማራው በደምብ ከተደራጀ ሁሉንም አማራ በየ ቦታው ያለውንም መጠበቅ ይችላል። ጦር ይኖረዋል ሄዶ ይከላከላል።

አስፋው፤ የአማራ ጦር አዲስ አበባ ሄዶ የአዲስ አበባ አማራዎችን መብት ሊጠብቅ ነው? ሻሸመኔ ሄዶ አማራውን ሊጠብቅ ነው? ይህ አጉል ፉከራ ከእውነታ የራቀ አይደለም።

ግዮናዊት፤ አዎን ዝም ብዬ የኛ የአማራ ብሄርተኞች ስሜታዊ መልስ ነበር የሰጠውህ! ትክክለኛ መልስ እንዲህ ነው፤ አማራው ተደራጅቶ ሲጠነክር ሌሎች ክልሎች/ብሄሮች ይጠነቀቃሉ ከጸንፈኝነት ይቆጥባቸዋል። ከግጭት ይልቅ ወደ win-win ያመጣቸዋል ነው።

አስፋው፤ ሁሉም አሸናፊ አካሄድ ቢቻል ኖሮማ እስካሁን እናደርገው ነበር! የጎሳ አስተዳደር የሁሉም አሸናፊ ሳይሆን የዚህ ተቃራኒ የሆነው የሁሉም ግጭት ውጤት ነው የሚያመጣው። ያለፈው 27 ዓመት ይህን አሳይቶናል ብለሽ አታምኝም?

ግዮናዊት፤ አዎን ለዚህም ነው የአማራ ብሄርተኞች የጎሳ ፌደራሊዝምን የምንቃወመው። የአማራ ብሄርተኝነት ንቅናቄ (አቤን) አቋሙም እንዲሁ ነው የጎሳ አስተዳደርን ለመቀየር።

አስፋው፤ እንዲህ ከሆነ እንዴት ጠንካራ አማራ ከጎሳዊ ግጭት ያድነናል ትያለሽ? ላለፉት 27 ዓመት በዚህ ክፉ "experiment" እንዳየነው የጎሳ አስተዳደር በጎሳዎች መካከል ግጭት ያመጣል። በሺዎች የሚቆጠሩ ግጭቶች በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ህይወት አልፏል፡ እኔ ሀገር አልባ ሆኛለው።

ግዮናዊት፤ ምን ማለትህ ነው?

አስፋው፤ አንቺ ከደብረ ማርቆስ ከአማራ ክልል በመሆንሽ የኛን ከአምራ ከአዲስ አበባ ውጭ የምንኖረውን አማሮች ታሪክ አትረድቱም። ከኔ ቤተሰቦች ሀገር በምዕራብ ሀረርጌ በጣም ብዙ አማሮች ሁለተኛ ዜጋ ላለመሆን ለህይወታቸው ሁልጊዜ ላለመስጋት ብለው ወደ አዲስ አበባ ተሰድደዋል። ይህ የሆነው ከ1983 ጀምሮ ነው። እስካሁን። ትውልድ ተሰድዷል ሀገር አልባ ሆኗል። ልጆች ሀገሬ ነው ብለው መጎብኘትም አይችሉም። በአካል መሄድ ይችላሉ ግን ሀገርህ አይደለም ስለሆነ የቦታው መንፈስ ዋጋ የለውም። የጎሳ አስተዳደርን በዚህ በተጨባጭ መንገድ ጉዳቱን አይተነዋል ደርሶብናል። ምናልባት እናንተ አምራ ክልል ያላችሁ ምንም ቢደርስባችሁ ሀገር አልባ አልሆናችሁም። የረሳችሁ ከሃዲዎች ናቸው የሚጨቁኗችሁ የነበሩት። ግን ሀገር አላችሁ ዛሬ በነፃነት ዘመን ሀገር አላችሁ። እኛ ግን የለንም። ሰለዚህ ስለ የጎሳ አስተዳደር ጉዳት እናውቃለን። ይህን አውቀን ነው አማራ እራሱን ማደራጀት ለኛ ዋጋ እንደሌለው የምናውቀው።

ግዮናዊት፤ አሳዛኝ ነው ግን መቼስ መደራጀታችን ይጠቅሟችኋል። ቢያንስ በገንዘብ እና ሌላ ነገር ድጋፍ ልንሰጣችሁ እንችላለን።

አስፋው፤ እስቲ ወደ ሌላ ርዕስ እንሂድ… ለምንድነው የአማራ ብሄርተኝነት የሚያስፈልገው ብሄ ስጠይቅሽ በመጀመርያ እና አጥብቀሽ የነገርሽኝ ስለ አማራ ላይ የደረሰው በደል ነው። ሌሎችንም ሳናግር ስለ አማራ ብሄርተኝነት አንድ ገጽ ከጻፉ 70% ስለ አማራ መጨቆን ነው። ይህ የ«ጭቁን» ስነ ልቦና (victim mentality) እንዲሰፍንብን አያደርግም? ይህ አይነት አስተሳሰብ ደግሞ ጎጂ አይደለም እንደ ጥቁር አሜሪካኖች፤ አቦሪጊኖች፤ ኦሮሞ ብሄርተኞች ወዘተ ማንነታችን ከመጨቆን ጋር አቆራኝቶ ወደ ታች አይጎትተንምን?

ግዮናዊት፤ እውነት ከሆነ ተጨቆንኩኝ ማለት ምን ጉዳት አለው? እውነት ነው። መካድ የለበትም። እውነቱን ካላመንን ደግሞ ወደ ፊት ሊደገም ይችላል አጥፊዎቹም ላይማሩ ይችላሉ እኛም ይቅር ማለት ያቅተን ይሆናል።

አስፋው፤ እውነት እማ እውነት ነው። ይካድ አይደለም የምለው። ምን ላይ እናተኩራለን ነው ጥያቄው። አዎን ጥቁር አሜሪካኖች እጅግ ተጨቁነዋል። ግን ያንን ከማመን አልፎ ማንነታቸውን ከመጨቆን ጋር አያይዘው ምንም ነገር ጉዳይ ላይ መጨቆናቸውን እንደ ምክንያት ሰበብ ይጠቀማሉ። (ያው በጅምላ እያወራን ነው ነገሩን ለማቅለል)። ስለዚህ እራሳቸውን አቅም አልባ (disempower) አድርገዋል። ለሚደርስባቸውም ሊሚያደርሱትም ሃላፊነት መውሰድ አቅቷቸው ሃላፊነቱም ምክንያቱም ሁል ጊዜ ጭቆና ይሆናል። ይህ ህብረተሰቡን እንዴት እንደጎዳው እናውቃለን። አምራ ብሄርተኛው ዛሬ ሲያወራም እንዲሁ ነው የሚሰማኝ። ስለደረሰበት ጭቆና በደምብ አሳምሮ ይናገራል። ምን ይመስልሻል?

ግዮናዊት፤ አዎ ስለ victim mentality እና ክብር ማጣት አውቃለሁ። ግን ይህን በኛ አማራ ብሄርተኞች አላይም። ሰለባ ሆነናል እና እንደገና እንዳይደገም መደራጀት እና መስራት አለብን ነው ጉዳዩ።

አስፋው፤ ጥሩ ነው የበታችነት ስሜት ከሌለ። ግን አይመስለኝም። የድሮ አማራ ቢበለም ተበድያለሁ አይልም ጸጥ ብሎ እራሱን ይጎላብታል እንጂ። ሽንፈትን በፍፁም አያምንም፤ ቢያውቀውም አያምንም። ይቅርታ ጠይቁኝ አይልም። የድሮ አማራ በትንሽ ቁጥር የሆኑ ህወሓቶች ተገዛሁኝ በገዛ ሀገሬ ተጨቆንኩኝ አይልም። ይህ እማ ጉድ ነበር የሚባለው! መቼም አያምነውም። የራሴ ጥፋት ነው ብሎ ወደ ራሱን ማስተካከል ቶሎ ይሻገራል። የዛሬው ትውልድ ግን ህወሓት እንዲህ አድርጎናል እያለ ይደጋግማል። እነ ይሄንን እንደ ታላቅ የአዕምሮ ሽንፈት ነው የማየው። ይቅርታ አድርጊልኝ እንጂ ያሳፍረኛል። ዝም ብለን ስራችን ነበር መስራት ያለብን።

ግዮናዊት፤ ታድያ አሁን ስራችንን እየሰራን ነው። ግን ልክ ነህ ቢያንስ ባሁኑ ወቅት ስለበደል ማውራት አቁመን ወደ ስራ መግባት አለብን።

አስፋው፤ ሌላ ጉዳይ… ምንድናቸው እነዚህ ከመካከላችሁ ሆነው ጸንፈኛ ሃሳቦች የሚያራምዱት። የኢትዮጵያ ብሄርተኝነት ዋጋ የለውም እስከ ኢትዮጵያ ፈርሳለች የሚሉ አሉ። አንቀጽ 39 ችግር የለውም የሚሉ አሉ። በጠቅላላ በጎሳ ብሄርተኝነት የሚያምኑ አሉ ከአማራ ጨቋኝ ነው ከሚለው ትርክት በቀር። እነዚህ የአማራ ብሄርተኝነት ምልክቶች ናቸው?

ግዮናዊት፤ ባጭሩ አይደሉም። የሰው ልጅ በተለያየ ምክንያት ወደ ጸንፍ ይሄዳል። አንዳንዱ በስነ ልቦና ምክንያት በደል ወይንም ጭቆና በዝቶበት። እንደምታውቀው ደግሞ ምሁራኖቻችን የጸንፈኝነት ችግር አላቸው። ቀላል መፍትሄ እንደ ዝክተኝነት ይቆጥሩታል። ከባድ እና ውስብስብ መፍትሄ እንደ ሊቅነት ይመስላቸዋል። ለዚህ ነው ወደ ጽንፍ የሚሄዱት እንጂ የአማራ ብሄርተኝነት እንደዚህ አይነቱን ነበር አያምንም። ኢትዮጵያ ከሌለች እማ ምን ዋጋ አለው? ለኛ የአማራ ብሄርተኝነት ኢትዮጵያዊነትን ማጠንከርያ መሳርያ ነው። እንጂ ሌላ ፍልስፍና አይደለም።

ውይይቱ ብሌላ ቀን ይቀጥላል…

Tuesday 14 August 2018

ተረት ተረት፤ «ጎሰኝነት ዘረኝነት ነው»

ይህም ከፊል እውነታ አለው። አማራ ማየት አማርኛ መስማት የሚጠሉ ጸንፈኛ ኦሮሞ ብሄርተኞች አሉ። ግን ጎሰኝነትን «ዘረኝነት» ብሎ መሰየሙ ችግሩን በትክክል አይገልጸውም ወደ መፍትሄም ለመምጣት አይረዳም። ላስረዳ…

«ዘረኝነት» የሚለው ቃል ብዙ ትርጉም ያለው፤ የተወሳሰበ፤ ኃይል ያለው ቃል ነው። የምንጠቀምበት አንድ ነገርን ወይንም ሰውን ክፉ መጥፎ ነው ብለን ለመሰየም ነው። ከክፉ ጋር ውይይት የለም ድርድር የለም። «ዘረኝነት» ብለን ሰይመን ከዚህ ሀሳብ ጋር ውይይትም ድርድርም አያስፈልግም ነው የምንለው «ዘረኛ» ስንለው። ትክክለኛ አካሄድ አይደለም።

ጎሰኝነትን እስቲ እንደዚህ ብናየው ትክክለኛ ግንዛቤ እንዲኖረን ይረዳል ጎሰኝነትን ለመቀነስ ለማጥፋትም ምን ማድረግ እንዳለብን እንድንረዳ ይረዳናል። ጎሰኝነት ገና ሲጀመር በውይይት፤ በማስረዳት እና በማስተማር ማጥፋት ይቻላል። ግን ጎሰኝነት አንድ ደረጃ ካለፈ ውይይት ከሞላ ጎደል አይሰራም።

ለምሳሌ ጎሰኛው ኦሮሞነቱ እጅግ አይሎ ኢትዮጵያዊነቱ እጅግ ከመነመነ ስለ ታሪክ እና ፖለቲካ ምን ብትሰብከው ለውጥ ሃሳቡን አይቀይርም። «ዘረኛ» ብትለውም ፋይዳ የለውም። ይህ ስወ ዘረኛ ሳይሆን ማንነቴ ሙሉ በሙሉ «ኦሮሞ» ነው ብሎ ወስኗል። ሀገሬ ኦሮሞ ነው ኢትዮጵያ አይደለም ነው የሚለው። ኢትዮጵያን ይጠላ አይጠላ አይደለም ዋናው ጉዳይ። ኦሮሞ ነኝ ማለቱ ነው። ልክ እንደ ኢትዮጵያ እና ሱዳን የተለያዩ ሀገሮች እንደሆኑ ሱዳናዊው በኢትዮጵያ ያለው መብት ውስን እንደሆነ እንዲሁም በተገላቢጦሽ ለኦሮሞ ብሄርተኛው በኦሮሚያ እና ኢትዮጵያ ያለው ልዩነት እንዲሁ ነው። ሌላ ሀገር ንኝ ነው የሚለው። ይህን የማንነት ስሜቱን ደግሞ ልንከለክለው አንችልም። «ዘረኛ» ማለቱ ዋጋ የለውም ምናልባትም ማባባስ ነው።

ታድያ ጎሰኝነት ይህ ከሆነ ምን ችግር አለው ትሉ ይሆናል? የሀገሩ ማንነት መምረጥ የሰው ልጅ «መብት» ከሆነ ምን ክፋት አለው? «ዘረኝነት» ካላልነው መጥፎነቱን እንዴት እንግለጽ? መልሱ ቀላል ነው፤ ጎሰንኘት «መብት» ቢሆንም የታላቅ ግጭት ምንጭ ነው። በአንድ ሀገር ጎሰኝነት በተለይም ጎሰኝነት እና ብሶት (grievance) አብረው ሲኖሩ ከፉ ግጭቶች ይኖራሉ። ይህ በቴኦሪ ወይንም በሌሎች ሀገራት ብቻ የሚታይ ሳይሆን ለ27 ዓመት በኢትዮጵያ የታየ ነው። ለግጭቶች ደግሞ በመንግስት አምባገንነት አናሳብብ፤ መንግስት ያልተሳተፈበት ግጭቶች ብዙ ነበሩ አሁንም አሉ። አልፎ ተርፎ መንግስት በግጭቶቹ ቢሳተፍባቸውም ባለ ክፍተት ነው እየገባ እየበጠበጠ የነበረው እንጂ የሌላ ልዩነት የመፍጠር አቅም አልነበረውም።

ስለዚህ ጎሰኝነት ወይንም የጎሳ እና ሀገር ሚዛን ከልክ በላይ ወደ ጎሳ ሲያመዝን ችግሩ ጎሰኝነት «ዝረኝነት» መሆኑ ሳይሆን የግጭት ምንጭ መሆኑ ነው። መፍትሄውም የግጭት ምንጭ ነው ብለን ጎሳን እንደ ጽንሰ ሀሳብ ከሀገሪቷ ህገ መንግስት ማውጣት እና በ«ቋንቋ እና ባህል» ጽንሰ ሀሳቦች መተካት ነው።

ተረት ተረት፤ አዲስ አበባ የሰፋችው ኦሮሞ ገበሬን በማፈናቀል ነው

እንደ አብዛኛው ውሸት «አዲስ አበባ የሰፋችው ኦሮሞ ገበሬን በማፈናቀል ነው» የሚለው የተወሰነ እውነታ አለው። አዎን በኢህአዴግ አገዛዝ በአዲስ አበባ ዙርያ ያሉ ገበሬዎች ለመሬታቸው ከሚገባው እጅግ ዝቅተኛ የሆነ ካሳ ተከፍሏቸው በግዴታ ከመሬታቸው ተባረዋል። ግን ይህ ሙሉ ታሪኩ አይደለም።

እንደሚታወቀው በሀገራችን መሬት የመንግስት ነው የሚል አሳዛኝ ህግ ነው ያለው። ይህ ህግ ሲተገበር ስናይ መንግስት ባሰኘው ጊዜ የከተማም ይሁን የገጠር መሬት ከነዋሪዎች ይወስዳል። ሲወስድ ደግሞ የሚከፍለው ካሳ የ«ገበያ» ዋጋ ሳይሆን መንግስት እራሱ የሚተምነው እጅግ አናሳ ካሳ ነው። ልምሳሌ አዲስ አበባ ውስጥ ለ«ልማት» ተብሎ መሬትን መንግስት ሲወስድ የሚከፍለው ካሳ የቤትና የጊቢው አብሮ ዋጋ ሳይሆን የቤቱ (የግንቡ) ዋጋ ብቻ ነው። ለምሳሌ 100 ካሬ ላይ ቤት አለኝ ከሸጥኩት 500,000 ብር ያመጣል እንበል። መንግስት ሊወስደው ከፈለገ ግን የቤቱ ግምብ ዋጋ ብቻ እራሱ (ሶስተኛ ወገን ሳይሆን) ገምቶ ምናልባት 50,000 ብር ከፍሎኝ በግድ ይወስደዋል። በገጥር ደግሞ እንደ ክልሉ እና ዞኑ ቢለያይም አንድ ምሳሌ ልስጣችሁ። መንግስት ከገበሬ መሬቱን ሲወስድ የሶስት ዓመት ገቢውን ለካሳ ይከፍለዋል። ገጠር መሬት መሸጥ ባይኖርም የዚህ መሬት ዋጋ ከዚህ በላይ እንደሚሆን መገመት ይቻላል። የሶስት ዓመት ገቢ ሳይሆን ቢያንስ የአስር ነው መታሰብ የነበረበት።

ከዚም አልፎ ተርፎ ይግባኝ የለም። መንግስት አንዴ ትፈናቀላላችሁ ካለ ይህን ውሳኔ መታገል አይቻልም። ከመሬት ንትቅያው በስተጀርባ ያለው የገንዘብ እና የፖለቲካ ኃይል እጅግ ከባድ ነው። የኢህአዴግ ባለሟሎች አሉ፤ ኢነቬስተር ዩኖራል፤ ጉቦኛ መንግስት ሰራተኛው አለ፤ ባለ ስልጣን አለ። ባለ መሬቱ ከነዚህ ጋር መጋፋት አይችልም እና ተዛዙ ሲመጣ እሺ ጌታዬ ብሎ መንግስት የሚሰጠውን ካሳ ተቀብሎ መሄድ ነው።

ይህ ሁኔታ ያለው በመላው ሀገሪቷ ነው በአዲስ አበባ ብቻ አይደለም። ከመሬታቸው አለ አግባብ የሚፈናቀሉት ኦሮሞ ብቻ ሳይሆኑ ሌሎች ሁሉ ናቸው። ገበሬዎች ብቻ ሳይሆን ከተሜዎችም ናቸው። አዲስ አበባን ከመሬታቸው የሚፈናቀሉትን ካየን ከአዲስ አበባ ዙርያ ካሉት ገበሬዎች ይልቅ የከተማው ተፈናቃይ ነው ይበልጥ መፈናቀል የሚጎዳው። ለምን? አራት ኪሎ 100 ካሬ ላይ የሚኖር ቤቱን ከነ ጊቢው ቢሸጠው አንድ ሚሊዮን ያገኝበት ነበር 50,000 ተሰጥቶ ይባረራል። ገበሬው ግን ሰፋ ያለ መሬት ቢኖረውም ከከተማ ሩቅ በመሆኑ ዋጋው ያን ያህል ውድ አይደለም በሚሰጠው ካሳ እና በመሬቱ እውነተኛ ዋጋ ያለው ልዩነት እንደ ከተማው መሬት አይሆንም። ስለዚህ አዲስ አበባ እና ዙርያ ሁሉም በመንግስት ከመሬታቸው የተፈናቀሉ ቢጎዱም በአማካይነት የከተማው ከገበሬው ይበልጥ ተጎድቷል።

በመጨረሻ ማን ነበር እነዚህን ገበሬዎች የሚያፈናቅለው ብለን ከጠየቅን የኦሮሚያ የኦህዴድ ቀበሌ እና ውረዳ ሰራተኞች እና የነሱ አዛዦች ናቸው። ለምሳሌ ባለ ሃብት ወይንም የአዲስ አበባ መንግስት በኢህአዴግ ድጋፍ መጥተው የለገጣፎን ባለስልጣኖች መሬት እንፈልጋለን ይላሉ። እነዚህ የኦህዴድ ባለ ስልጣኖች አላማቸው ትንሽ ካሳ ለገበሬው ሰጥቶ በትልቅ ዋጋ ለአዲስ አበባ ወይንም ለባለ ሃብት መስጠት እና በመካከል ከዋጋ ልዩነቱ ጉቦ መብላት ነው። አዲስ አበባ ውስጥም ይህ ነበር አሰራሩ። በጠቅላላ ላለፉ 27 ዓመት መሬት ለመንግስት ሹማምንት ታላቅ የጉቦ የገቢ ምንጭ እና ለኢህአዴግ ታላቅ የካድሬ መያዣ መንገድ ነበር። ስለዚህ አዲስ አበባ ሳይሆን የራሱ የኦህዴድ ካድሬ ነው አዲስ አበባ ዙርያ ያለውን ኦሮሞ ገበሬ አለ አግባብ ያፈናቀለው። አዲስ አበባ ናት ያፈናቀለቻቸው ማለት ሃሰት ነው።

ሙሉ እውነታው ይህ ነው፤ አዲስ አበባ ዙርያ ሳይሆን አዲስ አበባ ውስጥም ሀገር ዙርያም በየቀኑ ዜጎቻችን ከመሬታቸው አለ አግባብ እና አለ በቂ ካሳ ይፈናቀላሉ። የሚፈናቀሉት ደግሞ ኦሮሞዎች ብቻ ሳይሆኑ ሁሉም ነው። ችግሩ በአዲስ አበባ እና በኦሮሚያ መካከል ሳይሆን የመሬት የመንግስት ነው የሚለው ፖሊሲ (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/03/blog-post_47.html) ነው። መሬት የግል ቢሆን እነዚህ ገበሬዎች በነፃነት በሚያስደስታቸው ዋጋ መሬታቸውን ሽጠው ነበር።

ተረት ተረት፤ የትግራይ ገዥ መደብ አገዛዝ እና የ«አማራ ገዥ መደብ» አገዛዝ አንድ ናቸው

«የትግራይ ገዥ መደብ አገዛዝ እና የ«አማራ ገዥ መደብ» አገዛዝ አንድ ናቸው»። ይህ ተረት ተረት (myth) በበርካታ ሰዎች ሲደጋገም ወደ እውነታ እያማራ ነው። በቅርቡ ባደረጉት ኑዛዜአቸው የቀድሞ ጠ/ሚ ታምራት ላይኔም ደግመውታል። «የአማራ ገዥ መደብ ብይ አማራ ብዙሃን እንደነገዱት ነው ህወሓት የትግራይ ገዥ መደብ በትግራይ ብዙሃን የነገዱት» ብለዋል። ይህ አስተያየት እጅግ የተሳሳተ ነው።

የሁለቱ አገዛዞች መሰረታዊ ልዩነት ይህ ነው፤ በደርግ እና በንጉሳዊው ስርዓት ጎሳ፤ ዘውግ፤ ብሄር አይነት ጽንሰ ሀሳቦች በህግ ደረጃ አልነበሩም። አገዛዙ በህግ ደረጃ ከጎሳ እና ከጎሰኝነት ውጭ ነበር። በህወሓት አገዛዝ ግን ጎሳ እና ጎሰኝነት በህግ የተደነገገ ነው። ጎሰኝነቱ በልምድ ወይንም በባህል ደረጃ ሳይሆን ህጋዊ ነው። ይህ መሰረታዊ ልዩነት ነው።

በኃይለ ሥላሴ መንግስት ማንኛውም ግለሰብ በጎሳ ምክንያት ከመንግስታዊ ስልጣን እና ሹመት አይከለከልም ነበር። አይከለከልም ብቻ ሳይሆን ጎሳው ጭራሽ እንደ ጉዳይ አይነሳም፤ በህግ እና ስረዓት ደረጃ ጎሳ የሚባል ጸንሰ ሀሳብ የለም። በዚህም ምክንያት በኃይለ ሥላሴ መንግስት በርካታ ከተለያዩ ጎሳ የሆኑ ባለ ስልጣኖች ነበሩ።

ሆኖም የአስተዳደር ቋንቋው አማርኛ ነበር። ይህ ከጅማ ለተወለደው ኦሮሞ መሰናከል ነበር። የገዥ ስረዓቱ ንጉሳዊ ነበር። ይህ ከኮንሶ የተወለዱት ባዕዳዊ ስረዓት ነበር። በነዚህ አይነት ምክንያቶች አማራ ያልሆኑ ወደ ስልጣን ለመቅረብ ከአማራ ይልቅ ይከብዳቸው ነበር ማለት ይቻል ይሆናል። አማራ ቋንቋውን በማወቅ ከሌላው ይበልጥ እድል ነበረው ማለት ይቻላል። እንዲሁም የአዲስ አበባ ተወላጅ ይበልጥ እድል ነበረው ማለት ይቻላል። በዚህ ደረጃ በተለያዩ የጎሳ ተወላጆች የስልጣን እና ሹመት እድል ልዩነት መኖሩን መካድ አይቻልም። ግን ይህ ልዩነት የታሪክ አጋጣሚ ነው እንጂ በህግ የተደነገገ አልነበረም። ስለዚህ አማራ ያልሆነው ቢከብደውም ወደ ስልጣን መምጣት ይችል ነበር። አድሎ ነበር ግን አድሎው ህጋዊ አልነበረም ስለዚህ ሊቀለበስ የሚችል አድሎ ነበር።

የህወሓት አገዛዝ ግን መሰረቱ ጎሰኝነት ነበር። ህወሓት የትግራይ ድርጅት ለትግራይ ህዝብ ነው። አማራው በአማራነቱ ቦታ የለውም። ቋንቋ ባለመቻሉ ወይንም የፖለቲካ ባህሉን ባለማወቁ ሳይሆን በአማራነቱ ምክንያት ስልጣን ሊይዝ አይችልም። በህወሓት ዘመን አድሎ መቀልበስ የማይችል የጎሳ የደም አድሎ ነበር።

ይህን የ«ትግራይ ገዥ መደብ» እና የ«አማራ ገዥ መደብ» አገዛዝ ልዩነት ስንመለከት አንድ ትልቅ ትምሕርት እንማራለን። ይህ ስለ የጎሳ አገዛዝ አደገኝነት ነው። ጎሳ የትውልድ የደም ጉዳይ ስለሆነ በመሰረቱ ህዝብን የሚለይ እና አድሎ (discrimination) የሚያመጣ ነው። በዚህ ምክንያት ነው የጎሳ አገዛዝ የግጭት (conflict) ፋብሪካ የሚሆነው።

የጎሳ መብቶችን ለማስተናገድ የጎሳ አስተዳደርን ከመጠቀም ወይንም የጎሳ መብቶች በህግ ከማወጅ የቋንቋ እና የባህል መብቶችን ማደንገድ ይሻላል። ቋንቋ እና ባህል ማንም መማር መቀየር የሚችለው ስለሆነ መሰረታዊ አድሎ የላቸውም። በዚህ ምክንያት በአድሎ የተነሳ የተጨቋኝ ስሜቶችን አያዳብርም ስለዚህ ግጭትን አያበዛም።

ይህን ተመስርተን ነው የኢትዮጵያ ህገ መንግስት ጸንፈኛ ነው የምንለው። ዓለም ዙርያ ሀገራት የቋንቋ እና ባህል መብቶችን በህጋቸው ያስተናግዳሉ። የጎሳ መብቶችን በዚህ መንገድ ያስተናግዳሉ። ግን የትም ሀገር ጎሳን በህጋቸው አያስተናግዱም። በጎሳ እና በቋንቋና ባህል ያለውን ልዩነት በግጭት መጋበዝ አኳያ በድምብ የታወቀ ስለሆነ ነው እንዲህ የሆነው። ግን ኢትዮጵያ ብቸኛዋ ጎሳን በህግዋ ውስጥ ያካተተች ናት። ለሀገራችን ህልውና ይህን መቀየሩ አስፈላጊ ነው።

Monday 13 August 2018

አጸያፊ ግጭቶች ለተወሰነ ጊዜ ይቀጥላሉ

ብዙዎቻችን ለ27 ዓመታት በየ ክልሉ በዘውትር የሚካሄደውን የምናውቅ አይመስለኝም። የቤተሰቦቼ ሀገር ጨርጨር (ምዕራብ ሀረርጌ) እንደ ምሳሌ ተጠቅሜ ላስረዳ። ኢህአዴግ ስልጣን ክተቆጣጠረ ጀምሮ በየጊዜው «ነባሮቹን» (የጨርጨር ሙስሊም ኦሮሞዎች) እንወክላለን የሚሉ ጸንፈኛ ጎሰኛ እና ሙስሊም ተነስተው «መጤዎቹን» (ሙስሊም ኦሮሞ ያልሆኑት አማራ፤ ጉራጌ፤ ሶማሌ ወዘተ) በግድ ሙስሊም ሁኑ፤ ከሀገራችን ውጡ ወዘተ እያሉ ይነሳሉ። በሳውዲዎች ገንዘብ የሚደገፉ «ማድራሳዎች» (የጸንፈኛ እስልምና ትምሕርትቤትዎች) ይከፈታሉ ጽንፈኛ እስልምና ያስፋፋሉ። ጸንፈኛ ጎሰኝነት በስውር በየመንግስት መስሪያቤቱም ይንቀሳቀሳል «መጤውን» አባሩ ግደሉ ብሎ ይሰብካል። ይህ ጸንፈኝነት በየወቅቱ «መጤዎች» ላይ ጫና ይፈጠራል እስከ ሞት ያህል ጉዳት በየጊዜው ይደርሳል። እንደዚህ አይነት ክስተቶች ሲበዙ ፌደራል ፖሊስ ወይንም መከላከያ ይመጡና ጸንፈኞቹን አድነው አግኝነተው ያስሯቸዋል ግን አብዛኛው ጊዜ ይረሽኗቸዋል። ምርመራ፤ ፍርድ ቤት ወዘተ የለም። ዋና አቀነባባሪዎቹን ፈልገው ያጠፏቸዋል። ከዛ በኋላ ለተወሰነ ጊዜ ሁኔታው ይረጋጋል «መጤው» ትንሽ ሰላም ያገኛል። ግን ከትወሰነ ጊዜ በኋላ ጸንፈኞቹ እንደገና ይነሳሉ። አላለፉት 27 ዓመት ይህ ነበር የሚደጋገመው።

ከዚም አልፎ ተርፎ በለት ኑሮዋቸው «መጤዎች» ስለ ደህንነታቸው በትወሰነ ደረጃ ሁል ጊዜ ይጨንቃሉ። አባቶቻቸው ጭቋኝ የነበሩ ያማይፈለጉ «እንግዶች» እንደሆኑ እንዲሰማቸው ይደረጋል። እንደ ሁለተኛ ዜጋ ነው የሚታዩት። ማህበራዊ ችግር ከተፈጠረ ወይንም የህግ አስከባሪ ጉድለት ከመጣ ጉዳት ይደርስብናል ብለው ነው «መጤዎቹ» የለት ኑሮዋቸውን የሚኖሩት። በስጋት ነው የሚኖሩት። የከፋ ጊዜ ከመጣ ፌደራል ፖሊስ ወይንም መከላከያ ነው የሚያድንን ብለው ነው የሚያስቡት።

የህወሓት አሰራር እንዲህ ነበር በኦሮሚያ፤ ደቡብ፤ ቤኒሻንጉል፤ ሶማሌ ወዘተ ክልሎች። ፖሊሲአቸውን «ያዝ ለቀቅ» ብሎ መሰየም ይቻላል። ጎሰኝነትን በፖሊሲ ደረጃም ያራምዳሉ ጸንፈኛ ጎሰኝነት እንዲፈጠር እንዲኖር ያደርጋሉ። ግን ከቁጥጥራቸው ሲወጣ የወለዷቸውን ጸንፈኞች ያጠፏቸዋል እና እራሳቸውን እንደ የ«መጤው» ጠባቂ አድርገው ያቀርባሉ። «መጤውም» ምርጫ የለውም ለደህንነቱ ሁልጊዜ ወደ ፌደራል መንግስት ይመለከታል። ህወሓት የኖረው ይህን ክፉ ሚዛን ገንብቶ በመጠበቅ ነው።

አሁን በነ ጠ/ሚ አብይ አህመድ ዘመን ይህ አካሄድ አብቅቷል። በመጀመርያ ደረጃ ጎሰኝነትን ለመቀነስ ተነስተዋል። ሁለተኛ ደግሞ ሰላም፤ ፍቅር እና ፍትህ እንዲመጣ ነው የረዥም እቅዳቸው። በዚህ መሰረት ወንጀሎች እና ግጭቶች ሲፈጠሩ እንደ ድሮ የህወሓት አገዛዝ ገብተው አይረሽኑም። በህጋዊ መንገድ ጉዳዩን አጣርተው ፍትህ እና መፍትሄ በትክክሉ መንገድ ማድረስ ነው የሚፈልጉት። በዚህ መካከል ጸንፈኞች ፍርሃታቸው ቀንሶ ድሮ የማይደፍሩትን ያደርጋሉ። ወንጀሎች እና ግጭቶች ወዲያው አይቋረጡም መፍትሄ ቀስ ብሎ ይሆናል የሚገኝላቸው። በቅርቡ በሶማሌ፤ ቤኒሻንጉል፤ ሻሸመኔ ወዘተ የምናየው ይህ ነው። አልፎ ተርፎ በጠ/ሚ አብይ የግድያ ሙከራ ወይንም በስመኘው በቀለ ግድያ ዙርያም እንዲሁም ወደያው የፈጣን መልስ አልተገኘለትም። በህጋዊ ስነ ስርዓት እየተጣራ ነው (https://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/07/blog-post_6.html)።

ከዚህ ሁሉም መካከል ደግሞ የአዲሱ ስርዓት አቅምን ማወቅ አለብን። የድሮ የህወሓት ርዝራዦች ገና ከመንግስት፤ መከላከያ፤ ፌደራል ፖሊስ፤ በተለይም ደህንነት ገና አልጸዱም ለማጽዳትም ረዥም ጊዜ ይፈጃል። እንኳን ሌላ የጠ/ሚ አብይን ደህንነት መጠበቅ እራሱ ከባድ ሆኗል። ስለዚህም ነው እነ አብይ በማንኛውም ስራ እንቅፋቶች እያገጠማቸው የሚሰሩት።

ስለዚህ ባሁኑ ጊዜ ከህወሓት የጠብ መንጃ ፍትህ-ቢስ አገዛዝ ወደ ጠ/ሚ አብይ አገዛዝ መሸጋገርያ ወቅት ገና ብዙ ወንጀል፤ ዘር ማጥፋት ሙከራዎች፤ ህዝባዊ ግጭቶች፤ ግድያዎች፤ ወዘተ ሳይቀጥሉ አይቀሩም። የጠ/ሚ አብይ መንግስት እስኪጠነክር ድርስ፤ የክልል ፖሊሶች እስኪጠነክሩ ድርስ፤ ህዝቡ እስኪረጋጋ ድርስ፤ ፖለቲከኞች እና ሌሎች መሪዎች እስኪረጋጉ እና ለጥያቄዎች መልስ እና አቅታጫ ማስያዝ እስኪችሉ ድርስ ይቀጥላል። የድሮ እንቅፋቶች እስኪነሱ ድርስ በርካታ ጉዳቶች ያጋጥሙናል። ከመታገስ እና አዲሱን መንግስት ባለን አቅም በተለይ በአቅም ግንባታ ደረጃ ከመርዳት በቀር ምንም ማድረግ አይቻልም።

ለተጎዱት ለተገደሉት በሙሉ ጸሎታችን ከነሱ ጋር ይሁን። የሁላችንም የተከማቸ የረዥም ዓመታት ኃጢአት ነውና ሀገራችንን በዚህ ሁኔታ እንድትሆን ያደረገው።

Friday 10 August 2018

ጠ/ሚ አብይ አህመድ፤ የድሮ ሰው

ዓመት በፊት ማንኛውም ኢትዮጵያዊን ምን አይነት የፖለቲካ ለውጥ ትፈልጋለህ ቢባል፤ «ዴሞክራሲ፤ ነፃነት፤ ፍትህ፤ እኩልነት» ይል ነበር። ጠ/ሚ አብይ ስልጣን ሲይዙ እንደዚህ አይነት መልእክቶች እና መፈክሮች ነበር የሚጠበቅባቸው። ግን እሳቸው «ፍቅር፤ ሰላም፤ ይቅር ማለት» አሉ። መንፈሳዊ መረጋጋትን ከፖለቲካ መረጋጋት አስቀደሙ። ይህን የድሮ ሰው ብቻ ነው የሚለው፤ የዘመኑ ሰዎች ምን ማለት እንደሆነም ሊገባን ያስቸግረናል።

ጠ/ሚ አብይ የፖለቲካ ለውጡን ሲጀምሩ በሀገራችን መልካም አስተዳደር እና ብልጽግና እንዴት እንደሚያመጡ ይነግሩናል ብለን ሁላችንም እንጠብቅ ነበር። በነዚህ ጉዳዮች ሲናገሩ ግን እኛ ካሰብነው አልፎ ሄዱ። እሳቸው እንኳን ለኢትዮጵያ ለምስራቅ አፍሪካ ቀጥሎም ለጠቅላላው አፍሪካ ምሳሌ የሚሆን እና የሚያስተምር መልካም አስተዳደር እና ብልጽግና እናመጣለን አሉ! እኛ ስለሀገራችን ኢትዮጵያ ብቻ ነው ያሰብነው። በዛሬ ዝቅተኛ ሞራላችን ከሀገራችን ውጭ ምሳሌ መሆን እንደምንችል በፍጹም አናስብም። ጠ/ሚ አብይ ግን ዛሬ የጊዜያዊ ድክመቶች ቢኖራትም ኢትዮጵያ የአፍሪካ መሪ ናተና ይህንን ተእልኮዋን አንረሳም ብቻ ሳይሆን እናሟላለን አሉ። እንዲህ ሲሉ 60 ዓመት በፊት የነበሩ ጀግና የኢትዮጵያ ልሂቃን የማዳምጥ መሰለኝ!

ጠ/ሚ አብይ አብዛኞቻቸው ትንተናቸውን የሚጀምሩት የኢትዮጵያ ታሪክ እና ወግ በመጥቀስ ነው። ለምሳሌ ስለ «ፍቅር፤ ሰላም፤ ይቅርታ» ሲያወሩ ወጋችን ነው ብለው ነው። ታሪካችን ጥላቻ፤ ጦርነት፤ እና ቂም በደምብ እንዳለበት አልተሳኑም ግን የታሪክ እና ወጋችን የመጨረሻ ግብ እና ፍጻሜ ፍቅር፤ ሰላም እና ይቅርታ እንደሆነ ያውቃሉ። በድክመታችን ላይ ሳይሆን በጥሩ ጎናችን ያቶኩራሉ። በዚህ ዘመን ማን እንዲህ ይላል? በዚህ ዘመን ብዙዎቻችን በዝቅተኛ መንፈስ የተሞላን ስለሆነን ከታሪክ እና ወጋችን ጥሩ ነገር አይታየንም። ግን ጠ/ሚ አብይ ታሪክ እና ወጋቸውን በሚገባው በእውነተኛ ፍቅር ነው የሚያዩት።

በኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ሁላችንም የጠበቅነው ጠ/ሚ አብይ መንግስት ካሁን ወድያ በቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ጣልቃ እንዳይገባ ያደርጋሉ ነው። ምናልባትም ይህን በይፋ ለህዝብ ይናገራሉ ነው። ግን እሳቸው እንደገና ከጠበቅነው አልፈው ቤተ ክርስቲያንን ነፃ መተው ብቻ ሳይሆን ወደ መርዳት ገቡ! መንግስት ላበላሸው ሃላፊነት አለበት ማስተካከል አለበት ብለው በሲኖዶሶቹ እርቅ እንዲኖር ምኞታቸውን ተናገሩ። መናገር ብቻ ሳይሆን ስልጣናቸውን እንደ ህሊና ግፊት በመጠቀም እርቁ እንደፈጸም አስተዋጾ አደረጉ። ጭራሽ ካልሆነ እግራችሁ ላይ ወድቄ እንድትታረቁ እለምናችኋለሁ አሉ! ማናችንም ይህን አልጠበቅንም።

ጠ/ሚ አብይ ለሀገራችን ባህላዊ ሃይማኖቶች ታላቅ ክብር አላቸው። እኛ የዘመኑ ሰዎች እንዚህን መዋቅሮች ከፖለቲካ ውጭ የሆኑ ኋላ ቀር ነገሮች ይመስሉናል። እሳቸው ግን ለሀገራችን ደህንነት እና ጤንነት አስፍላጊ እና መሰረታዊ እንደሆኑ ይገባቸዋል። እነሱን ትቶ ኢትዮጵያዊነት በአሸዋ የተመሰረተ ቤት እንድሆነች ያውቃሉ ይናገራሉ ያስተምራሉ። እንደዚህ አይነት አስተሳሰብ ከልሂቃኖቻችን ድሮ ነው የጠፋው።

ጠ/ሚ ዱባይ ሄደው ከአረብ ህብረት መሪ ጋር ሲወያዩ አረቡ ልንረዳችሁ አስበናል ምናልባትም ትምሕርት ቤቶች በኢትዮጵያ ለማቋቋም እያሰብን ነው አሉ። ጠ/ሚ አብይ እሺ አላሉም። ወይንም ጥሩ ነው ግን የኤኮኖሚ ኢንቬስትሜንት ይሻለናል አላሉም። እናንተ እምነታችሁን እያጣችሁ ስለሆነ እኛ አረብኛ ተምረን ሃይማኖትን መልሰን እናስተምራችኋለን አልዋቸው (https://www.youtube.com/watch?v=b3GUI1rD9-M)! እዩ በራሳቸው እና በሀገራቸው ምን ያህል እንደሚተማመኑ። ማናችን በዚህ ዘመን ያለነው ኢትዮጵያዊ እንደዚህ እናስባለን? ይህ የጠ/ሚ አብይ ንግግር ኢትዮጵያን በትክክለኛ በሚገባት ቦታ የሚያስቀምጥ ነው። እውነትም ነው። ግን ስንቶቻችን እንደዚህ አይነት አስተሳሰብ ከልባችን ይገባን ይሆን?

ጠ/ሚ አብይ መንግስታቸው ለፈጸማቸው በደሎች በቡድናቸው በኢህአዴግ ስም ሳይሆን በግላቸው ይቅርታ ጠይቀዋል። ይቅርታ የሚጠይቅ ሰው በራሱ የሚተማመን ነው (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/07/blog-post.html)። በራሱ የማይተማመን ሰው ወይንም የዝቅተኛ መንፈስ ያለው ሰው ይቅርታ ማለት ድክመቱን ለሁሉም የሚገልጥ ይመስለዋል። ጠ/ሚ አብይ ግን ትንሽ ይቅርታ ሳይሆን ለኢህአዴግ ኃጢአት በሙሉ ግዙፍ ይቅርታ ጠየቁ።

ከዚም አልፎ ከተለያዩ በአንድ ወቅት እንደ ጠላት የሚቆጠሩ ሰዎች ጋር በሂሊና ነፃነት ይገናኛሉ ይወያያሉ። ከኢሳያስ አፈዎርቂ፤ አብዴል እል-ሲሲ፤ ግንቦት ሰባት፤ ታማኝ በየነ፤ ጀዋር መሃመድ፤ የተለያዩ የህወሓት ሹማምንት ወዘተ በሰላም ተገናኝተው በህዝብ ፊት አብሮ ይቀርባሉ። ከነዚህ ጋር አብሮ መታየቴ እና መወያየቴ ማንነቴን በግምት ያስገባዋል እና አጉል እተቻለሁ ብለው አያስቡም። ይህም በራስ የመተማመን ምልክት ነው። ምንም አይበረግገዋቸውም። ከማንም ጋር መነጋገር እችላለሁ "on my own terms" ነው አስተሳሰባቸው።

ጠ/ሚ አብይ በራሳቸው የሚተማመኑት በሰው ልጅነታቸው ብቻ ሳይሆን ከፖለቲካ አንጻር በኢትዮጵያዊነታቸው ሙሉ በሙሉ ስለሚኮሩ ነው። በዚህ በኩል የድሮ ሰው ናቸው። እንደ በምኒልክ ዘመን የነበሩት ከአውሮፓዊያን ጋር በእኩልነት ሳይ በበላይነት ስሜት የሚደራደሩ። እንደ በኃይለ ሥላሴ ዘመን ለኢትዮጵያ በዓለም ደረጃ እንደሚደራደሩት አልፎ ተርፎ ለአፍሪካ የሚዋጉት። የሰለባነት አስተሳሰብ (victim mentality)፤ በዝቅተኝነት መንፈስ (inferiority complex)፤ በልመና፤ ሌሎችን መለመን ወይንም እንደ ሌሎች መሆን መፈለግ የለም። ይህ አስተሳሰብ ድንቅ ነው በአሁኑ ዘመን ከሀገራችን ብዙ የማይገኝ ነው። ግን ኢትዮጵያ እንደገና እንደዚህ አይነት እንደ ጠ/ሚ አብይ አይነቱን ሰው ማፍረት መቻሏ ተመስገን ነው። ሁላችንም የሳቸውን አስተሳሰብ (mindset) ያኑርብን። የሀገራችን ብጎ ህልውና ከዚህ ነው የምጀረውና።

Thursday 9 August 2018

የበጎ አድራጎት ድርጅት እና ማህበር ህግ ይበልጥ ይጠንክር

እንደሚታወቀው ኢህአዴግ ዘጠኝ ዓመት በፊት ባሳወጀው ህግ በሰባዊ መብት፤ የብሄር ብሄረሰብ ጉዳዮች፤ የጾታ ልጆች አካል ጉዳተኞች ጉዳዮች ወዘተ የሚሰሩ በጎ አድራጎት ድርጅቶች (በአድ) ከ90% በላይ ገቢአቸውን ከሀገር ውስጥ ማግኘት አለባቸው። ህጉ ሲረቀቅ የተተቸው ምክንያት ኢህአዴግ የሰባዊ መብት ጥሰቶቹ በድርጅቶች እንዳይመረመሩ ኣና ዓለም አቀፍም ሀገራዊም አይን እንዳይበዛበት ነው። እውነትም ህጉ የተመሰረተው ዋና ምክንያት ይህ ነው።

ግን አሁን በመጣው የፖለቲካ ለውጦች መንግሥት የሰባዊ መብት መጣስን እየተወ ነው ለህብረተሰቡም ለድርጅቶችም የመተቸት እና የይግባኝ ማለት ነፃነት ሰጥቷል። እንደ ፍርድ ቤት አይነት መዋቅሮችም እየተሻሻሉ ነው። ፖለቲካውም ወደ ሰላም እየተቀየረ ነው። ስለዚህ ሀገር ውስጥ ያለው ህብረተሰብ ስለ ሰባዊ መብት ወይንም ሌላ ጉዳይ የሚሟገት ድርጅት በሰላም እና አለ ፍርሃት ማቋቋም ይችላል። የውጭ ሀገር ድርጅቶች ወይንም ገንዘባቸውን ከውጭ ሀገር የሚያገኙ ድርጅቶች አስፈላጊ አይደሉም።

አስፈላጊ ባይሆኑም ለምን ገቢያቸውን ከሀገር ውጭ የሚያገኙ ድርጅቶች ይከልከሉ፤ ህጉ ይቀየር እና ይፈቀድላቸው። በዛውኑ ውጭ ሀገር የሚኖሩ ኢትዮጵያዊዎች የሚደጉሟቸው ድርጅቶች በነፃነት ማገልገል ይችላሉ። እንደዚህ የሚሉ አሉ።

ግን ይህ በዙ ሰው የማያስበውን ችግሮች ያመጣል። ብውጭ ገንዘብ የሚመሩ ድርጅቶች የሚያንጸባርቁት የለጋሾቻቸውን ፍላጎት እና አላማ ነው። የሚሰሩት ለኢትዮጵያ ህዝብ ሳይሆን ለለጋሾቻቸው ነው። የለጋሾቻቸው አላማ ደግሞ ከኢትዮጵያ ህዝብ ፈቃድ ውጭ ሊሆን ይችላል።

ለምሳሌ የውጭ ሀገር የፖለቲካ እና ባህል በኢትዮጵያ ሊያስፋፉ ይችላሉ። ጸረ ሃይማኖት ፍልስፍኖችን እና ርዕዮተ ዓለሞችን ሊያስፋፉ ይችላሉ። ጸንፈኛ ጎሰኝነትን ሊደግሙ ይችላሉ በኃይለ ሥላሴ ዘመን እንደተደረገው። ጸንፈኛ ሃይማኖትም እንዲሁ። በተለያየ መንገዶች የውጭ ሀገር ተጽዕኖ በሀገራችን ላይ እንዲጠነክር ማድረግ ይችላሉ። ይህ ደግሞ የኢትዮጵያ ህዝብን ሊከፋፍል እና ሊጎዳ ይችላል እና ኢትዮጵያን ከሌሎች ሀገር አንጻር ሊያደክማት ይችላል።

ማወቅ ያለብን በጎ አድራጎት ድርጅቶች በመጀመርያ ደረጃ የለጋሾቻቸው መሳርያዎች ናቸው እንጂ የበጎ አድራጎት ሰራተኞች አይደሉም። የውጭ ሀገር ድርጅቶች ወይንም ከውጭ ሀገር ገንዘብ የሚያገኙ ድርጅቶች የዛን ውጭ ሀገር መንግስት ወይንም ሌላ ለጋሽ ፍላጎት በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ያንጸባርቃሉ። የዛን ሀገር የውጭ ጉዳይ መሳርያዎች ናቸው።

ግን እንደዚህ ቢሆንም የነዚህ ድርጅቶችን መልእክት መቀበል ፋንታ የኢትዮጵያ ህዝብ ይሁን እና ለምን ይከለከላሉ የሚሉ አሉ። እውነት ነው ህዝብ የመወሰን ነፃነት ሊኖረው ይገባል። ግን ጉዳዩ እንደዚህ ቀላል አይደለም። ለምሳሌ በፖለቲካ ውድድር አንዱ ፓርቲ የሌላው 10 እጥፍ ገንዘብ ካለው የገንዘብ ኃይሉ እንዲያሸንፍ ያደርገዋል። እያንዳንዱ ግለሰብ አንድ ምርጫ ያለው የህዝባ ምርጫ ቢሆንም ገንዘብ ታላቅ ሚና ይጫወታል። ይህ ገንዘብ ለማስታወቅያ እና ለጥቅም (ጉቦ) ይውላል እና በዚህ መንገድ የሰውን ምርጫ ይገዛል። ስለዚህ የገንዘብ ሚና በምርጫ ታላቅ ነው። የበጎ አድራጎት ድርጅቶችም ጉዳይ እንዲሁ ነው። ብር ያለው ህዝብ ላይ ይበልጥ ተጸዕኖ አለው። የሀገራዊ ድርጅቶችን ያፍኗቸዋል።

ሌላው ከውጭ ሀገር ወደ በጎ አድራጎት ድርጅቶች የሚመጣ ገንዘብ መከልከል ጥቅም የሀገሪቷ ህዝብ ድርጅት መደገፍ እና ማቋቋም እንዲለምድ ነው። ለምሳሌ ህዝቡ በልጆች አስተዳደግ ዙርያ ስራ ያስፈልጋል ድርጅት ያስፈልጋል ካለ እራሱ ከኪሱ አውጥቶ ድርጅት ይመስረት። ይህ ድርጅት ሙሉ ለ ሙሉ ህዝብን ይወክላል ማለት ይቻላል። ይህ ድርጅት ህዝብ የሚፈልገውን ያደርጋል እንጂ የውጭ ለጋሾች የሚፈልጉትን አያደርግም። ይህ ነው እውነት «ዴሞክራሲ» ተጠሪነት እና ሃላፊነት።

ስለዚህ በነዚህ ሁለት ምክንያቶች፤ 1) አላግባብ የውጭ ቅኝ ግዛት ተጽዕኖ እና 2) ሀገር በቀል ድርጅቶች እንዲጎለቡ እንዳይታፈኑ ያለው ህግ እንዳለ ይሁን። መሻሻል ካለበትም ሁሉንም በጎ አድራጎት ድርጅቶች ገንዘባቸው በሙሉ ከሀገር ውስጥ ማድረግ ነው።

Friday 3 August 2018

የበታችነት ስሜት

ሰላሳ አርባ ዓመታት በፊት ከሀገሩ የሚሰደድ ኢትዮጵያዊ ወደ ምዕራብ ሀገር ሲሄድ ከሀገሩ ይበልጥ «የሰለጠነ» እና «የበለጸገ» ሀገር አግኝቻለሁ ብሎ ያስቡ ነበር። የምዕራብ ሀገሮች በሀብት፤ በብልጽግና፤ በግብረ ገብነት፤ በቅልትፍና (efficiency)፤ በንፅህና ወዘተ ከኢትዮጵያ የላቁ መሆናቸው አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ያምን ነበር።

ሆኖም ግን ስደተኛው ምዕራብ ሀገሮችን ቢያደንቅም የሚተችባቸው ጉዳዮች ነበሩ። ለምሳሌ «ዘረኝነትን ያራምዳሉ» ይላል። በአዲስ ቅኝ ግዛት ታዳጊ ሀገራትን ያጠቃሉ ይዘርፋሉ። ኢትዮጵያ ለቅኝ ግዛት ስለማትመች እነ አሜሪካ ካዷት እና በደርግ አይነቱ አረመኔ መንግስት በማርክሲዝም እንድትገዛ አደረጉ። በተለያዩ ሀገራት ሕጋዊ የሆኑ መንግስታትን ይገለብጣሉ። ወዘተ። ኢትዮጵያዊ ስደተኛው ልሂቃኑም የምዕራብ ሀገሮችን በዚህ መልኩ ይከሱ ነበር።

በርካታ ስደተኞች እንደዚህ በማለት የምዕራብ ሀገሮችን ተችተው ሀገራቸው ኢትዮጵያ ችግሮች ቢኖሯትም ከነዚህ ሀገሮች በማንነት ደረጃ አታንስም ብለው ያምኑ ነበር። በዚህ ምክንያት የሀገር የማንነት የበታችንነት ስሜት (inferiority complex) ገና ብዙ አላደረባቸውም። በኢትዮጵያዊነቱ ያለው ኩራት ብዙ አልተቦረቦረም ነበር።

ግን ጊዜው ባለፈ ቁጥር ኢትዮጵያ «አልሻሻል» ስትል ባንጻሩ የምዕራብ ሀገሮች በብልጽግና እይናሩ እና አንዳንድ ልውጦች ሲያደርጉ የፕሮፓጋንዳ ስልታቸውም እየዳበረ ሲሄድ ኢትዮጵያዊ ስደተኛው በአሙሮው የምዕራቡን ዓለም እያበለጠ ሀገሩ ኢትዮጵያን እያሳነሰ ሄደ። ቀስ በቀስ የበታችነት ስሜት (inferiority complex) እያደረበት ሄደ። የህ የበታችነት ስሜት ወደ ሀገር ቤትም ገባ።

ወደ ምዕራብ ሀገር የተሰደደ ኢትዮጵያዊ ደህና ገቢ ማግኘት እና ሃብት ማከማቸት ቻለ። ስደተኛው ድሮ ቢገጥመውም ባይገጥመውም የሚያማርረው ዘረኝነቱ እየቀነሰ ሲሄድ አየ። ለነገሩ ዘረኝነቱ ድሮም ኑሮውን ከማሻሻል አልከለከለውም ነበር። አህን ግን ጭራሽ በጥቁርነቱ ስራ ከማጣት ማግኘት ጀመረ! ባሜሪካ ልጆቹ በጉብዝናቸው ብቻ ሳይሆን የጭቁን (ጥቅር) ዘር በመሆናቸው ስኮላርሺፕ ማግኘት ጀመሩ። የአሜሪካ ኑሮ ከድሮም ይበልጥ እየተመቸ ሄደ።

ይህ ስደተኛ ኑሮው «እየተሳካለት» በሄደ ቁጥር አሜሪካ በሱ አይን ይበልጥ እያማረች ሄደች። ፍትሐዊና መሐበራዊ ስነ ሥርዐቱን ከድሮም ይበልጥ ማደነቅ ጀመረ። ለሴቶች፤ ለልጆች፤ ለጥቁሮች ወዘተ ያለው «መብት» እና ጥንቃቄ ከኢትዮጵያ ጋር ሲያነጻጽረው ይገርመዋል። በፖለቲካ ደረጃ «ዴሞክራሲ» አምላኩ ሆነ «ሲኤንኤን» (CNN) መላዕክቱ ሆነ። በአንጻሩ ኢትዮጵያ በስደተኛው አይን እየቀነሰች እየወረደች ሄደች። አልሻሻል አለች እየባሰችም ሄደች። ስደተኛው ሀገሩን በጎበኛት ቁጥር ከአሜሪካ ጋር እያንጻጸረ ዘመዶቹን ያደነቁራል። በአሜሪካ እና ኢትዮጵያ ያለውን ልዩነት ለማሳየት ያህል ዘመዱን ከ«ሀገር ቤት» ለመውጣት በርካታ አስር ሺዎች ዶላር ይከፍላል።

ዛሬ በኛ በኢትዮጵያውያን የዝቅተኘት መንፈስ በደምብ አድሮብናል ማለት ከእውነት የራቀ አይመስለኝም። ግን ይህ መንፈስ እውነትን ነው የሚያንጸባርቀው? እውነት ዝቅተኛ ህብረተሰብ ነን? ወይም ሀገራችን ዝቅተኛ ነው? ይበልጥ ታላቅ የሆነው ጥያቄ ሙሉ ሰው ለመሆን ወይንም በዘመኑ ቋንቋ «መሻሻል» ከፈለግን እንደ ምዕራቡ ዓለም መሆን ይኖርብናል? ምናልባት ዘፈናችን ጭፈራችን ምግባችንን ለትዝታ ብለን ጠብቀን በሌላው በሙሉ እንደነሱ እንደ ምዕራባዊያን መሆን ይኖርብን ይሆን?

እዚህ ላይ በቀለም ትምሕርት ከምንማረው በሚዲያ ከምንሰማው ፕሮፓጋንዳና ተራ «እውቀት» ወጥተን እናስብ። በአዲሱ ቅን ግዛት የተገዛውን አእምሮአችንን ነፃ እናውጣው የብዥታ መነጽራችንን እንጣል። በመጀመርያ እስቲ ምንድነው «ስልጣኔ» ብለን እንጀምር። ጥያቄውን በምሳሌ ኃይል ለመመርመር ታዋቂውን የሮሜን ስልጣኔን እንመልከት።

በክርስቶስ ዘመን በርካታ አይሁዶች ወደ ሀገራቸውን ወርሮ የገዛው ሮሜ ይፈልሱ ነበር። አንድ አይሁድ ወደ ሮሜ ሲሄደ ዛሬ ኢትዮጵያዊ ከሀገሩ ወደ አሜሪካ እንደመሄድ እናመሳስለው። ሮሜ ሀብታም ነበረች። «ስደተኞችን» መጤዎችን ትቀበላለች ታስተናግዳለች ታበለጽጋለች። ውጣ ውረድ ቢኖረውም መጤዎች የሮሜ ዜጋ የመሆን እድል አላቸው። የሮሜ ዜግነት አንደ ይሁዳ ዜግነት በጎሳ በብሄር በደም የተወሰነ አይደለም ማንም የሮሜ ዜጋ መሆን ይችላል። የሮሜ ፍርድ ቤቶች በደምብ ይሰራሉ በተለይ ለሮሜ ዜጎች እውነተኛ ፍትሕ ይሰጣሉ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ችግር ባጋጠመው ቁጥር አይሁዶች ሲገሱት ሲሉ የሮሜ ዜግነቱን ተጠቅሞ ፍርድ ይጠይቃል! በሮሜ ፍርድ ቤት ትክክለኛ የፍርድ ሂደት እንደሚጠብቀው ስለሚያውቅ ነው። የሮሜ መንግስታዊ አስተዳደር ፍፁም ባይሆንም ከሌሎች አንጻር «የሰለጠነ» ነበር። «ዴሞክራሲ» አይነት ከነ ምክር ቤት አለው። በሮሜ የማሕበራዊ ብረ ገብ አለ። የሴቶች «መብቶች» ከሌሎች ሀገሮች ከይሁዳ ይልቅ የተከበሩ ናቸው። በስነ ሥርዓት  በኩልም ሮሜ የስለጠነች ናት። መንገዶቿ ንፁ ናቸው። መንገደኛ ለመንገደኛ ጎረቤት ለጎረቤት አገልጋይ ለባለጉዳይ ያለው ግንኙነት በጥቅም የተሳሰረ ሰላማዊና የተቀላጠፈ (efficient) ነው። የድሮ «ሮሜ» ስልጣኔ እንደዚህ ይመስላል።

ለዚህም ነው አይሁዶችም ሌሎችም ወደ ሮሜ የሚፈልሱት ሃብቱን እና ስልጣኔውን ፈልገው። ልክ እንደ ኢትዮጵያውያን ወደ አሜሪካ እንደምንፈልሰው «ህይወትን ለማሻሻል» ወደ በአድ ሀገር ይሄዱ ነበር። ግን ሮሜ የይሁዳ ቅኝ ገዥ ነበረች! አይሁዶች ወደ የሚገዛቸው ሀገር ነበር የሚሄዱት። ወደ ዓለምን በሙሉ በጉልበቷ የተቆጣጠረቹ ሮሜ ነበር ለተሻለ ኑሮ ብለው የሚሄዱት። ግን አይሁዶቹንም ሌሎች መጤዎችንም የሮሜ ስልጣኔ  ክፋነቷን እንዳያዩ አድርጓቸዋል አሳውራቸው። ለነሱ ሮሜ የብልጽግና ሀገር እንጂ የክፋት ሀገር አልነበረትም። ሮሜ ሀገራቸው ይሁዳ የሌላት ነገሮች ሁሉ አላት። በዚህ ምክንያት በራሳቸው ባህልና ማንነት ዝቅጠኝነት ተሰማቸው እንደ ሮሜዎች መሆነ ፈለጉ ወደ ሮሜ ህብረተሰብ ተቀላቀሉ።

ይህ ምሳሌ ስለ «ስልጣኔን» ምን ያስተምረናል? ለብዙዎቻችን ስልጣኔ ሀብት ማለት ነው። ሀብት ካለ ሌሎች ጉድለቶች አያታዩንም። ስልጣኔ «ቴክኖሎጂ» ይመስለናል። የሮሜ የከተማው ቧምቧ እና ፍሳሽ ስራ አይሁዶችን ይገርማቸው ነበር። ስልጣኔ ቅልጥፍና (efficiency) ይመስለናል። የሮሜ የመነግስት መዋቅሮች በተለይ ጦር ሰራዊቱ ግቡን በቀላሉ ያስፈጽም ነበር። ስልጣኔ ፍትሕ ነው። ስልጣኔ ግብረ ገብ እና ስነ መግባር ነው።

እነዚህን ሁሉ ስንመለከት ግን ባጭሩ ስልጣኔ ማለት ነግ በኔን በደምብ ማወቅ ነው። አካባቢዬን አላቆሽሽም ሌሎችን መንገደኞችን ውድጅያቸው ሳይሆን ንፁ አካባቢ ስለሚበጀኝ እኔ ካላቆሸሽኩኝ ሌሎችም ስለማያቆሽሹ ነው። እኔ መኪና የማሽከረክረው ሕግ አክብሬ ነው ሌሎች የመንገድ ተጠቃሚዎችን ስለምወዳቸው ሳይሆን ሁላችንም በትክክል ካሽከረከርን ሁላችንም በፍጥነንት እና በሰላም የምንፈልግበት ቦታ ለመድረስ ስለሚያመችን ነው። መንግስቴ ለደሆች እርዳታ እንዲያደርግ እወዳለሁ ሰላምን ለመጠበቅ እኔም ነገ ብወድቅ እርዳታ እንዳገኝ። ወዘተ። ይህ ነው ስልጣኔ ባጭሩ። ሮሜም አሜሪካም የትም ህዝብ ሰላምና ሀብት እያገኘ ሲሄድ ለራሱ ለግል ምቾቱ የሚሆን አሰራሮች ስነ ምግባሮች እየገባው በተግባር መዋል ይጀምራል።

ግን ይህ ስልጣኔ ከጥሩነት፤ በጎነት፤ ሰላም ወዳድነት እና ከፍቅር ጋር አይገናኝም። ነግ በኔ በጎነትም ፍቅርም አይደለም። «የሰለጠነ» ራስ ወዳድነት ነው። ማንም ከጊዜ በሚያመጣው ልምድ በኋላ የሚደርስበት ነው። ማንም ደግሞ ችግሮች ሲያጋጥሙት ካልተመቸው የሚተወው ነው። ሮሜ ለራሷ የሰለጠነች ነበር ለሌሎች ሀገሮች ግን የክፋት መዓበል ነበረች። ዛሬ አሜሪካም አውሮፓም ሌሎችም ለራሳቸው የሰለጠኑ ናቸው ግን ከጠረፍ ውጭ አይደሉም።

ስለዚህ ይህ ሀገር የሰለጠነ ነው የኔ ሀገር አይደለም ብለን የበታችነት ስሜት ሊኖረን ይግባል? በፍፁም! ስልጣኔ ማንንነት አይደለም። ስልጣኔ ይመጣል ይሄዳል በዓለም ታሪክ በተለያዩ ቦታዎች ተገንብቷል ፈርሷል። ስልጣኔ ከፍቅርና በጎነት አይገናኝም። የሰው ማንነት ግን በጎነት፤ ፍቅር፤ ሰላም ወዘተ ነው። ስለዚህ የሰው ልጅ እነዚህን የሚሽህ እስከሆነ መቼም የበታችነት ሊሰማው አይገባም! ከፍቅር ይልቅ «ብልጭልጭን» ሲያመልክ ነው ችግሩ የሚመጣው።

ይህን ተክትሎ እንደ ምዕራቡ ዓለም መሆን አለብን ብሎ ማሰቡም ተገቢ አይደለም። ለምን ብትሉ የምዕራባዊያን ርዕዮት ዓለም ከኢትዮጵያዊነት ትውፊትና ማንነት 180 ዲግሪ የተቃረነ ነው። የምዕራባዊ አስተሳሰብ የሰው ልጅ የዓለም ቁንጮ አድርጎ ያስቀምጠዋል። እግዚአብሔር የለም ወይንም ምንም ሚና አይጫወትም ይላል። ኢትዮጵያዊ ግን በትውፊታችን ፈጣሪ ነው በአምሳሉ የፈጠረን ብለን እናምናለን ሁሉ ነገራችንም ከዛ ይከተላል። ለዚህም ነው የጠ/ሚ አብይ አህመድ የይቅርታ፤ ፍቅር እና ሰላም መልዕክቶችን በደስታ እና ጉጉት የምንቀበለው። እንደዚህ አይነቱ መልዕክት የተም ምዕራብ ሀገር እንደ ህፃንነት ነበር የሚታየው። ስለ ልማት፤ ነፃነት፤ መብት ነው የምዕራብ ሀገር ውይይት። እግዚአብሔር የለምና።

ታሪክ ረዥም ነው። 500 ዓመት በፊት ቻይና ከሁሉም «የሰለጠነች» ነበር። 60 ዓመት በፊት ቻይና ወደ 40 ሚሊዮን ህዝቦቿን ገደለች ግማሽ ሀገሪቷ በርሃብ እየተሰቃየ ነበር። 2000 ዓመት በፊት ስሜን አውሮፓ በሮሜዎች ዘንድ የያልሰለጠና የአረመኔ ስፍራ ነበር። ዛሬ ደግሞ ከዓለም በሙሉ የሰለጠው ጎራ ይባላል። 60 ዓመት በፊት ኢትዮጵያ በዓለም ደረጃ ታላቅ ክብር ነበራት። ዛሬ እንደ ለማኝ ትታያለች። እኛ ኢትዮጵያዊያን ይህንን ብናስታውስ ጥሩ ይመስለኛል።

እውነት ስልጣኔ ፍቅር እና ሰላም ነው። የኛ የኢትዮጵያዊያን በዚህ ረገድ ከማንም ልናንስም ልንበልጥም እንችላለን የኛ ፋንታ ነው። ግን የሰው ልጅ በመሆናችን ከማንም አናንስም አንበልጥምም። የዝቅተኛ ስሜታችንም በምንም መለክያ ተገቢ አይደለም። እጅግ ጎጂም ነው። ሌላውን ምዕራባዊያንም ለመገልበጥ መሻህ ዋጋ የለውም ጎጂ ነው። ማንነታች ከፈጣሪያችን የተሰጠን ነውና ምንም የምናፍርበት ሊሆን አይገባም። እርግጥም ለሌሎች ምሳሌ ሆነን መገኘት ነው ያለብን ድሮ ሆነን እናውቃለን አሁንም የማንሆንበት ምክንያት የለም።

Wednesday 1 August 2018

ስለ አማራ ብሄርተኝነት አንድ የውይይት ምዕራፍ

1. አማራ የተጠቃው በብሄር ስም ስላልተደራጀ ነው ከሆነ የጎሰኝነትን ፍልስፍና አምነንበታል ማለት ነው። አማራ 60 ዓመት በፊት በተለየ መልኩ እየተጠቃ ነበርን? አይደለም ከሆነ መልሱ ጥቃቱ የተጀመረው የጎሳል ፖለቲካ ሀገር ውስጥ ሲገባ ነው ማለት ነው። ይሄውን ያጠቃንን ፍልስፍና መቀበል ሽንፈት እና ይበልጥ ጥቃት ነው።

2. አማራ በብሄር መደራጀቱ የአማራን ጥቅም አያስከብርም ብዬ ነው የማምነው። ለምን? በብሄር ተደራጀን ማለት ክልላችንን አስከበርን ማለት ነው በዛሬው ፖለቲካ ሌላ ትርጉም የልውም። ከአማራ ክልል ውጭ ያለውን አማራ አዲስ አበባም ላለው አማራ ምንም ልናደርግለት አንችልም። ነገ በኦሮሚያ የአማርኛ ትምሕርትቤቶች ሁሉ ይዘጋሉ ቢባል (በዴሞክራሲያዊ ምርጫ በድምጽ ብልጫ ማለት ነው) አማራው ምን ሊያደርግ ነው። ኦሮምኛ በአማራ ክልል መከልከል?! በሶማሌ ክልል ጅግጅጋ ሶማሌ ተናጋሪ በመንግስትም ሌሎችም ስራዎች ቀድሞ የሚቀጠረው ቢባል አማራው ምን ያደርጋል። ድምጽ ብልጫ የለውም። አዲስ አበባ አተሰፋም ቢባል አማራው ድርጅት ምን ያደርጋል? ከአማራ ክልል ውጭ ያሉት አማሮች የአማራ ድርጅቱ አባል ቢሆኑ ምን ይጠቅማቸዋል ጥቃት ብቻ ይሆናቸዋል እንጂ። ግን አማራው በስመ ኢትዮጵያዊነት ቢደራጅ ከሌሎች (የዘር ቅልቅሎች እና ሌሎች ብሄሮች) ስምምነት ( alliance) እያደረገ ይበልጥ ኃይል ይኖረዋል። ይህ ይበልጥ መላው ሀገር ውስጥ ያለውን አማራ መብት ያስከብራል።

3. «ውሸት አንድነት ይብቃ፡፡ ስንቴ እንታለል፡፡» ይህ በትክክል የጎሰኞቹ አቋም ነው። አቋማቸው እንዲህ ነው 1) ኢትዮጵያ ስለካደችን ወደ ጎሳችን እንመለስ 2) ኢትዮጵያ የካዳችን የፈረሰችበት ምክንያት መጀመርያውኑ ሀገር ሳይሆን የጎሳዎች እስር ቤት ስለሆነች ነው። መፍረስዋ ይህን ነው የሚያመለክተው ነው አቋማቸው። አሁንም የአማራ ብሄርተኝነት እንዲህ ነው የሚለው። እራስህን መጠየቅ ያለብህ «አንድነት» እንደምትለው «ውሽት» ወይም ውድቅ የሆነው በኛ በአስፈጻሚው ድክመት ነው ወይንም «አንድነት» የሚለው ጽንሰ ሀሳብ ከመጀመርያ ውሸት ስለሆነ ነው? የመጨረሻው ከሆነ መልስህ መጀመርያውኑ ያጠቃህ የጎሰኝነትን ፍልስፍና ጠቀብለሃል ማለት ነው። የመጀመርያ ከሆነ መልስህ ማድረግ ያልብን አንድነትን መተው ሳይሆን መትክክሉ ማስፈጸም ነው። «አንድነት» የተበላሸው እኛ የአንድነት ደጋፊዎች ከነ ሁሉም አማራ (በዛን ጊዜ) እርስ በርስ በፈረንጅ ፍልፍና ተለክፈን ስለተከፋፈልን ነው እንጂ አንድነቱ ራሱ ችግር ኖሮት አይደለም። አይደለምን?

4. ለላይ ጠቅሼዋለሁ እንጂ የራሱ ነጥብ ይገባዋል፤ በስመ አማራ መደራጀት ከሌሎች «ኢትዮጵያዊ ነን» ከሚሉ ጋር ለመጋራት ያለንን እድል ይቀንሳል። ለምሳሌ አዲስ አበባ ወይንም ናዝረት የህብረ ብሄር ድርጅት በቀላሉ ምርጫ ያሸንፋል ግን የአማራ ድርጅት አያሸንፍም። የህብረ ብሄር ድርጅቱ ያአማራውን መብት በደምብ ያስከብራል። የሚበጀን ምን እንደሆነ ግልጽ ነው።

5. መጠቃት ስሜትን ይነካል ይገባኛል። ግን ስሜታዊ ሆኖ ላለ ችግር ወደ ተሳሳተ መፍትሄ መግባት ጎጂ ነው ባለፉት 60 ዓመት የሀገራችን ታሪክ ነው። «መሬት ላራሹ» ብለን መሬትን ለመንግስት ሰጥተን። አንባገንነት ብለን ወደ ጎስኝነት ገባን። ወዘተ። አሁንም አማሮች ተጠቃን እንላለን መፍትሄው ግን በኢትዮጵያዊነት መደራጀት ነው።

6. በኢትዮጵያዊነት መደራጀት ያልቻልንበት ምክንያት እንደጠቀስኩት ከ60 ዓመት በፊት በፈረንጅ ፍልስፍና ተወክፈን እርስ በርስ መፋጀታችን ነው። ይህ የሆነው በኢትዮጵያዊነት ስለተደራጀን አይደለም። አሁንም በስመ አማራ እንደራጅ በኢትዮጵያዊነት ከመደራጀት ይቀላል የሚለው እጅግ የተሳሳተ ነው። በርካታው አማራ በስመ አማራ መደራጀት አይፈልግም። ምናልባት ከመቂ ፕሮፓጋንዳ በኋላ ቁጥሩ ይጨምር ይሆናል ግን ዛሬ የአማራ ብሄርተኝነት ከፋፋይ ሀሳብ ነው። ባሁኑ ወቅት አንድ በመሆናችን ጊዜ ከፋፋይ አቋምን መግፋት ምን ማለት ነው። የግቡን ተቃራኒ ነው።