Sunday 11 December 2016

ተሃድሶ

ስለ «ተሃድሶ ኦርቶዶክስ» የሚባለውን ንቅናቄ አንዳንድ ሃሳቦች ለማቅረብ እወደለሁ። በመጀመርያ ትሃድሶ በትክክል ምን እንደሆነ አይታወቅም። በጾም ጊዜ አሳ መብላት አግባብ ነው የሚሉ ተሃድሶ ተብለው ሊሰየሙ ይችላሉ። እንደ ፒያኖ ወይም ኦርጋን አይነት የሙዚቃ መሳርያ ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ መተቀም ይቻላል የሚሉም እንደዚሁ ተሃድሶ ተብለው ይሰየማሉ። ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ ጫማ ማድረግ ክልክል አይደለም የሚሉትም እንደዚሁ። በድንግል ማርያም አማላጅነት አምነው ግን በስብከታቸው ስለሷ ብዙ የማይናገሩ ተሃድሶ ይባላሉ። ቅድስት ድንግል ማርያምን እንደ ክርስቶስ የሚያመልኩ አሉና ይህ መሆን የለበትም የሚሉም ሳይገባ ተሃድሶ ይባላሉ። የጋራ ጾም አያስፈልጉም የሚሉም ተሃድሶ ይባላሉ። በቅዱሳን አማላጅነት አናምንም የሚሉም ተሃድሶ ይባላሉ። ወዘተ። «ተሃድሶ» የሚባለው ስያሜ በተለያዩ አግባብ ያላቸውም የሌላቸውም ምክንያቶች እንጠቀማለን።

ከዚህ ጽሁፍ ግን ተሃድሶ ስል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን እምነትንም ስርዓትንም መቀየር - በትንሹም በትልቁም - የሚፈልግ አቋምን ነው። ጫማ ከቤተ ክርስቲያን እናድረግ እስከ የቅዱሳን አማላጅነት የለም የሚሉት። እነዚህ እጅግ የተለያዩ አቋሞች እንደሆኑ እራዳለሁ! ጫማ አለማድረግ የ«ትንሽ» ስረዓት ጉዳይ ነው - የእምነት ጉዳይ ቢሆን ኖሮ ከግብጽ በተ ክርስቲያን ጋር እንለያይ ነበር። ትንሽ ስረዓት ቢሆንም ምክነያት አለው - ይህን ስርዓት ለመቀየር የሚጓጓው መንፈስ በቅዱሳን አማላጅነት አላምንም ከሚለው መንፈስ በተወሰነ ደረጃ ግንኙነት አለው። ላስረዳ...

የኦርቶዶክስ ክርስቲያን እምነት በሶስት መስፈርቶች ሊፈተሽ ይችላል። እምነቱ ከጥንት ጅምሮ ያለ ነው፤ እምነቱ በሁሉም ቦታ ይገኝ ነበር፤ እምነቱ በሁሉም ይታመን ነበር። እነዚህ መስፈርቶች ከክርስቶስ ቀጥሎ ከሃዋሪያቶቹ የወረስነውን እምነት አለማጠፍም አለ«ማደስ»ም ከመንፈቅ ትቆጥበን እምነታችንን እንደተሰጠን ይዘን እንድንጠብቅ የሚገልጹ ናቸው።

የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሃሳብ እንደዚህ ነው። አዲስ ነገርን - ትንሽም ትልቅም - በቀላሉ አታስተናግድም። ቅዱስ አታናሲዮስ መጽሃፍ ቅዱስ የትኞቹን መጸሃፍት እንደሚያካትት ሲናገሩ አዲስ ነገር ነበር። መጸሃፍ ቅዱስ እነዚህ መጸሃፍቶች ናቸው ተብሎ ተሰይሞ አያውቅም ነበር። ታድያ ይህ አዲስ ነገር ነበር ወይ? በፍጹም፤ ቅዱስ አታናሲዮስ የነበረ ሁሉም በሁሉም ቦታ ከመጀመርያ የሚያምኑበትን ነው ያረጋገጡት። ሌሎች መጸሃፍቶችን የተተውበት ምክንያትም የቤተ ክርስቲያን እረኞች ህዝቡ እነዚህን መጸሃፍት በተሳሳተ መልኩ እያነበበ ወደ ኑፋቄ ሲገባ አይተው ነው።

የቤተ ክርስቲያን ስረዓትም በተመሳሳይ ቢጠበቅም ትንሽ ላላ ይላል። ስረዓትን «ታናሽ»ና «ታላቅ» ብለን መከፋፈል ይቻላል ግን ይህ ቅፍፍል ወጥ አይደለም - ታናሽና ታላቅ ዳሮች ሆነው ከመካከል ብዙ አሉ። ታናሽ ስረዓቶች ለምሳሌ ጫማ አለማድረግ፤ ታቦት፤ ወዘተ ከኛ ጋር አንድ ከሆነችው የግብጽ ቤተ ክርስቲያን የሉም። እነሱም የራሳቸው እኛ የሌለን ስርዓቶች አሏቸው። ሆኖም ስረዓትም በቀላሉ አይቀየረም። እንደ እምነት ያህል ባይሆንም ከእምነቱ ጋር እጅግ የተያያዘ ስለሆነ መቀየሩ እጅግ አስፈላጊ መሆን አለበት።

ለምሳሌ የቅዳሴአችን ዜማ የተጻፈው በ6ኛው ክፍለ ዘመን በቅዱስ ያሬድ ነው። ከዛ በፊት የነበረው ዜማ የተለየ ነበር ወይም ዜማ አልነበረም። የቅዳሴ ዜማ የስረዓት ለውጥ በቅዱስ ያሬድ ጊዜ ተካሄደ። ይህ የሚያሳየው ስርዓት መቀየር እንደሚቻል ነው። ግን ከዛ በኋላ እስካሁን ለ15 ክፍለ ዘመን አልተቀየረም። ይህ ደግሞ የሚያሳየው ስረዓት መቀየር ቢቻልም (እንደ ስረዓቱ አይነት) እጅግ በጣም ጥቂት ጊዜ ነው የሚቀየረው። የኦርቶዶክስ አስተሳሰብ ለውጥ ስለማይወድና ጥንቱን ስለሚያስቀድም።

ስረዓት ይቀየር ሲባል ለምን ብለን እራሳችንን መጠየቅ አለብን። ኦርቶዶክሳዊ ለውጥ የሚከላከለው አንዱ ታላቅ ምክነያት አብዛኛው ጊዜ ለውጥ የሚፈለገው ለማይሆን ምክነያት ስለሆነ ነው። እንደዚህ አይነት ምክነያቶች ምሳሌዎች እንደ የመንፈቅ አስተሳሰብ፤ ፖለቲካ ወይም የስልጣን ሹኩቻ፤ ፍርሃት አይነቱ ናቸው።

በዛሬው ዘመን - «ዘመናዊነት» ግዥ ርዕዮተ ዓለም በሆነበት ዘመን - የስረዓት ለውጥ (የእምነትም ለውጥ) የሚገፋፋው ከዘመኑ ጋር አብሮ ለመሄድ ነው። ቅዱስ ያሬድን ያነሳሳቸው ጾም ጸሎትና የዳዊት መዝሙርን በመድገም እግዚአብሔርን ይበልጥ ለማመስገን ፈልገው ነው። በዛሬው ዘመን ግን ብንወድም ባንወድም ብናውቀውም ባናውቀም ከዘመኑ ጋር አብሮ የመሄድ ሃሳብ ተጽእኖ ያሳድርብናል ሳናውቀውም ይገፋፋናል። በዚህ ምክነያት ከበፊት ዘመናት - ከቅዱስ ያሬድም - ይበልት ጥንቃቄ ማድረግ አለብን። ምንም አይነት ስርዓትን እንኳን ለመቀየር በጥያቄ ምልክት ውስጥም ማድረግ የለብንም።

ብለላው ቋንቋ እላይ የጠቀኩትን የቤተ ክርስቲያናችንን አስተሳሰብን መርሳት የለብንም - ለውጥን በታቻለው ምከላከልንና መፈተሽን።

ይህ ብዬ ወደ ተሃድሶ እንመለስ። በቤተ ክርስቲያናችን ስንት የሚሰራ ስራ እያለ ለምንድነው ማደስ የሚታሰበው። ንስሃ ገብተናልን? እግዚአብሔርን በሙሉ ልባችን እንድወደዋለን? ያለንን በሙሉ እንሰጠዋለን? በሰው ላይ አንፈርድምን? ገና እንድወድቃለን እንነሳለን መውደቃችን እጅግ ቢበዛም። እረኞቻችን ታድያ ድሮም እንደነበራቸው ዛሬም እንድንነሳና ለክርስቶስ ለመቅረብ ያለንን ፍላጎት ለማዳበር ብዙ ስራ አላቸው። ይህ ሁሉ ስራ እያለ ስለማደስ ማሰብ ምን አስፈለገ?

እንዳልኩት የዘመኑ ርዕዮተ አለም በፍጹም ሳናውቀው ከባድ ተእጽኖ ያደርግብናል። ካቶሊኩንና ፕሮቴስታንቱን እያየን ሳናውቀው በአፋችን እንደተሳሳቱ እየተናገርንም በልባችን አንዳንድ ነገሮቻቸው በነበር ብለን እንመኛለን። ስነ ስረዓት፤ ንጽህና፤ ፍልስፍና፤ ሃብት፤ ብልጠት፤ ስነ መግባር ወዘተ። ቤተ ክርስቲያናችን ትታደስ ስንልም እንደነዚህ ትንሽ ትሁን ማለታችን ነው። ምንጩ ይህ ነው አደጋውም ይህ ነው።

ታድያ እንደዚህ ስንል ሌላው አብዛኞቻችን በተለይ ካህናቶቻችን በተለይ እናድስ የሚሉት የማናውቀው ነገር ምህ ያህል ካቶሊኩና ፕሮቴስታንቱ - በተለይ ፕሮቴስታንቱ - ችግር ውስጥ እንዳለ ነው። «ፔንጤ» የምንላቸው በትክክሉ «ኤቫንጄሊካል» የሚባሉት ለምሳሌ ባለፉት 50 ዓመታት ኢትዮጵያ ውስጥ ቢያድጉም ባሁኑ ጊዜ በምንጫቸው ሃገር አሜሪካ እየመነመኑና ታላቅ አደጋ ላይ ናቸው። መሰረታው እምነታቸው የግል ስለሆነ - ቤተ ክርስቲያን ሳይሆን ግለ ሰብ ነው ሃይማኖቱን ብቻውን ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እይሚያውቀው ብለው ስለተነሱ - አሁን እስከ 30,000 አይነት ክፍፍሎች አላቸው። ስንቶቻችን ነን ይህን የምናውቀው። የቆዩት ፕሮቴስታንቶች (በኢንግሊዘኛ «ሜይንላይን» ይባላሉ) እንደ አንግሊካን ደግሞ ከሁሉም ክርስቲያን ከሚባሉት የመነመኑና ምእመናን ያጡ ናቸው። ይህን ስንቶቻችን ነው የምናውቀው? አሜሪካን ሀገር ትልቁ የክርስቲያን ፍልሰት ከፕሮቴስታንት ወደ ኦርቶዶክስ እንደሆነ ስንቶቻችን ነን የምናውቀው? ባንዳን የኦርቶዶክስ ሃገረ ስክበቶች አብዛኛ ካህናት ከፕሮቴስታንትነት ውደ ኦርቶዶክስ የተቀየሩ እንደሆነ ስንቶቻችን እናውቃለን? ኦርቶዶክእነሱ ወደ ኦርቶዶክስ ይመጣሉ እኛ ደግሞ ወደነሱ መሄ እንፈልጋለን!

ክሃገራችን ውጭ ብንመለከት ይበጀናል። ውጭ ሃገር ያለነው - በተለይ ካህናት - ስራችን ብለን ዙርያችን እንመልከት። የክርስትና ድርጅቶች አካሄድን እንመልከት። ዛሬ ከምንጩ አሜሪካ እየጠፋ ያለው ፕሮቴስታንት ሃይማኖት ነገ ኢትዮጵያ በዚሁኑ ምክነያት እንደሚጠፋ እንወቅ። ባለፉት ዓመታት በሃገራችን የተከናወነው የኦርቶዶክስ ወደ ጴንጤ ፍልስትን ብቻ አንይ። ሃገራችን ውስጥ እራሱ እነዚህ ድጅጅቶች እንዴት ቀንበቀን እየተፈረካከሱ እንደሆነና እየተባዙ እንደሆነ እንይ።

ምን አልባት ዞር ዞር ብለን ይህን ሁሉ ካየን የፕሮቴስታንት አደጋም የዘመኑ ፈተናንም ልንረዳው እንችላለን። ይህን ተረዳነው ማለት ደግሞ እንታደስ የሚለው ስሜት ይቀንስልናል። አስተያየታችንን ያስተካክላል ሚዛናዊም ያደርጋል።

Wednesday 7 December 2016

የተማረ ገደለን

የኢትዮጵያ ወዳጅ ዶናልድ ሌቪን (ነፍሳቸውን ይማረው) ከ50 ዓመታት በፊት ጅምሮ ባህልንና ማንነትን የማያከብርና የሚክድ ህብረተሰባዊ ለውጥ አገር አፍራሽ ነው እያሉ ኢትዮጵያዊያንን ያስጠነቅቁ ነበር። ኃይለ ሥላሴ ወደ ምዕራብ አገር የላኳቸው ተማሪዎች በኢባህላዊ የሆነ  ከራስ ጋር የሚያጣላ ርዕዮት ዓለም ተነክረው ወደ አገራቸው ሲመለሱ በአስተሳሰባቸው ሰውዉን አስተንግጠዋል። አቶ ዶናልድ ሌቪን አንድ ያጋጠማቸውን እንደዚህ አስታወሱ ነበር፤ አንዱን «የተማረ» ምሁራንን እንደዚህ ብለው ጠየቁት «እንደምትመኘው የሶሽያሊስት አብዮት ቢካሄድ በሚሊዮን የሚቆጠር ህዝብ እንደሚሞቱ ታውቃለህን?» ይህ የተማረ ምህር «በ10 ሚሊዮንም ቢሞቱ ይህን ርዕዮት ዓለምን ለማድረስ ስለሆነ ያዋጣል» ብሎ መለሰላቸው። ከራስ ባህል፤ ወግ፤ ትውፊት፤ ምንጭና ማንነት መራቅ እንደዚህ አይነቱን ቅዠታዊ አስተሳሰብ ነው የሚያመጣው።

ዛሬም ይህ አይነት የቀለም ትምህርት አምልኮ ለኢትዮጵያ ዋናው አጥቂና ጠላት ነው። የምዕራብ ዘመናዊ የቀለም ትምህርት በአገራችን እንደ ጣዎት እንደሚመለክ የሚገልጸው በኃይለ ሥላሴ ዘመን የተሰየመው አባባል «የተማረ ይግደለኝ» ነው። ይህ ዛሬም በኢትዮጵያዊያን ጭንቅላት ይንጸባረቃል። ፖለቲካችንን ካየን አብዛኛው የሚንጸባረቁት ሃሳቦችና አስተያየቶች ከኢትዮጵያ ውጭ የመነጩ ናቸው። የኛ ምሁራኖች እነዚህ ሃሳቦችን እየሰገዱላቸው ኢትዮጵያን ወደ እኒዝህ ርዕዮት አለምን ማስተካከል ይፈልጋሉ። ቢያንስ መደረግ የነበረበት እነዚህን ርዕዮት ዓለሞችን ለኢትዮጵያ እንዲሆኑ ማስተካከል።

ይህ አቋሜን የሚደግፉ አንዳንድ ማስረጃዎች እንመልከት። በመጀምርያ ወደ ኋላ ሄደን የኃይለ ሥላሴ መንግስትን ተመልስን እንመልከት። የዛን ጊዜ ውጤቶች ዛሬ ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ ስለሆነ። በሳቸው መንግስት ዘመነ የምዕራብ «ዘመናዊ» ትምህርት በኢትዮጵያ ውስጥ ተስፋፋ። ተማሪዎች በሞላ ጎደል አለምንም መበረዝ ቀጥታ የምዕራብ ትምህርት ነበር የሚማሩት። ስለአገራቸው ጥቂት ውይም ምንም ነገር ሳይማሩ ይመረቁ ነበር። ለምሳሌ ስለ ዓለም ዙርያ መልክአምድር ተምረው ስለኢትዮጵያ መልክአምድር ምንም አያቁም ነበር! ስለራሳቸው ታሪክ፤ ትውፊት፤ ባህልና ሃይማንቶ አይማሩም ነበር። ሳይታወቅ ግራ የገባው ከፊል ኢትዮጵያዊ ከፊል ፈረንጅ የሆነ ትውልድ ተወለደ። የዝቅተኛ መንፈስ ያደረበት ትውለድ ተፈጠሪ። ሳያውቀው እራሱን የሚንቅና የሚጠላም ትውልድ ተፈጠረ። ግን ከዚህ ትውልድ ልጆች መካከል ግማሾቹ ኢትዮጵያዊነታቸው ቢሸረሸርም ለኃይለ ሥላሴ ታማኝ ነበሩ በሳቸውም «የዘመናዊ ስልጣኔ እቅድ» ይስማሙ ነበር። ሌሎቻቸው ግን እንኳን ታማኝ ለመሆን ጠላት ሆነው ተገኙ። አገሪቷን ያስከወሰ አብዮትን አስነሱ። ሁላችንም እንደምናውቀው ይህ አብዮት በአገራችን አስፈላጊ የሆኑ ለውጦችና መስተካከሎች ከማምጣት ፋንታ በጸረ ኢትዮጵያ የሆነውን በምዕራባዊያኑ ርዕዮት ዓለም በኮምዩኒዝም ስር አገራችንን እንድትወድቅ አደረጋት።

በደርግ ዘመነ መንግስት ደግሞ አብዛኛው የኢትዮጵያ የፖለቲካ ንቅናቀዎች የጸረ ኢትዮጵያ አቋምና ርዕዮት ዓለም ይዘው ነበር የሚራመዱት። ጸረ ሃይማኖት ነበሩ። ጸረ ባህልና ጸረ ትውፊት ነበሩ። እርግጥ በዛን ዘመን ሙዚቃ ጭፈራ ወዘተ «ትስፋፍቷል»። ግን የተስፋፋው በምዕራባዊያን አመለካከት ዘንድ ነው - ስር የሰደደ የማንነት የሆነ ሳይሆን እንደ ልብስ ከላይ የሚለበስ ወይም እንደ ቴአትር የሚታይ ነበር። በመጀመርያ ኮምዩኒስት ነን፤ ግን እስክስታ የምንጨፍር ኮምዩኒስት ነን! በጠቅላላ አብዛኛው ፖለቲከኞችና ምሁራንም የኢትዮጵያ ማንነት መቀየር አለበት ብለው የሚያምኑ ነበሩ።

በኢህአዴግ ዘመን ይህ ወደ ውጫዊ አመለካከት ማድላት ወደ ጸንፍ ደረሰ። በሶሺአሊዝም የተሞላ በጎሳ የተመሰረተ ጸንፈኛ ህገ መንግስት በኢትዮጵያ ተጫነባት። ይህ ክስተት ከኢትዮጵያዊ «የተማረ» ኃይል በተደጋጋሚ የሚታይ አንድ ጸባይን በደምብ ያብራራል። ይህ ጸባይ ጸንፈኝነት ነው። የኢትዮጵያ መሰረታዊ ችግር የብሄር እኩልነት ነው ብሎ ቢታመንም ቋንቋ፤ ባህል፤ መልክአ ምድር፤ ጎሳም የሚያካተት ግን ለዘብተኛ የሆነ ህገ መንግስት ሊመሰረት ይቻል ነበር። ግን ያኔ የነበሩት ኃይሎች ጸንፍ ካልያዝን አሉ! በምድረ ዓለም ታይቶ የማይታውቅ አይነት ህገ መንግስት - ከሶሺያሊስት በላይ ሶሺያሊስት የሚያሰኝ ህገ መንግስት ካልደነገግን አሉ። ጭራሽ ከደቡብ አፍሪካ በቀር የሌለውን ጎሳ በመታወቅያ ጀመሩ! ሁላችንም እንደምናውቀው እስካሁን ይህ መርዝ ነው እያሳመመን ያለው።

ይህ ሁሉ ሆኖ የአገራችን ገዥም ተቃዋሚም ፖለቲከኞችና ምሁራን አሁንም ውጫዊ በተለይ ምእራባዊ አመለካከት ነው ያላቸው። ገዝ ፓርቲ «ዘመናዊነት» የሚባለው አመለካከት ነው ያለው። ሃይማኖት ኋላ ቀር ነው። እግዚአብሔር ሳይሆን ሰው ነው የዓለም ቁንጮ። ባህል፤ ትውፊትና ወግ ውሸት ናቸው። ህዝብ ባህልን ትቶ ወደዚህ አይህነት አመለካከት እስኪ ገባ ድረስ እንደ ያላደገ ህጻን ነውና እኛ ስልጣን ተቆጣጥረን ልናሳድገው ይገባል። ካደገ በኋላ፤ ማለት እንደኛ የ«ዘመናዊ» አስተሳሰብ ካደረበት በኋላ - ስልጣናችንን እንለቃለን። በሌላ አባባል ኢትዮጵያዊነቱን አርግፎ ከኛ ይበልጥ «ያደጉትንና የሰለጠኑትን» ምእራባዊያን ከመሰለ በኋላ ነው ሰው የሚሆነው። ይህ ራስን ማንነትን መጥላት ካልሆነ ምንድነው?

ተቃዋሚው ደግሞ እንደ አሜሪካ ወይም እንደ አውሮፓ እንሁን ነው! (በጅምላ እየተናገርኩኝ ስለሆነ ይቅርታ።) የኢትዮጵያዊነት ራዕይ የለውም። እርግጥ አንዳንድ ጥሩ የሆነ ሃሳቦች እንደ ገዳ አሰራር አጥንቶ በተወሰነ መጠቅም ተነስተዋል። አንዳንዱም ደፋር የንጉሳዊ አስተዳደር (በወግ ደረጃ ብቻ ቢሆንም) ይመለስ የሚሉ አሉ። እነዚህ ሃሳቦች በርካታ ውይይትና ክትትል ያስፈልጋቸዋል ከነዚህ አይነቱ ባህላዊ መንገድ ነውና የአገራችን ውበት የሚመለሰው።

በብዙሃኑ ደረጃ ደግሞ ቤተሰብ ልጁን የምእራባዊ ባህልና ቋንቋ ለማስተማር ይሯሯጣል! ለልጁ ከቀለም ትህምሕርት በላይ በዚህ ዓለም ምንም የለም የሚል መልክት ነው ደጋግሞ የሚያስተላልፍለው። ልጁም የቀለም ትምሕርትን ጣኦት አድርጎታል። ከዛ በኋላ የልጁ አኗኗር ግራ የገባው ሲሆን፤ ትምሕርትና ስራ አለው ግን በሌላው ንሩው ያልተረገጋ መሰረተ ቢስ የሆነ ሲሆን - ወላጅ ግራ ይገባዋል። የዛሬው ትውልድ እንደዚህ ነው እንደዛ ነው ብሎ ያማርራል። ታድያ ባህሉን ያልወረሰ ሰው ሁልጊዜ ኑሮው እንደሚናወጥ አናውቅምን?

በትህትና ባይመስልም ግን የትህትና ምክሬ እንደዚህ ነው። በመጀመርያ የዘመናዊ ትምህርት ምን ያህል ጸረ ባህል፤ ጸረ ትውፊት፤ ጸረ ማንነት፤ ጸረ ኢትዮጵያ እንደሆነ እንረዳ። ሞያ፤ ሳየንስና ቴክኖሎጊ ችግር የለውም ከጥንትም የነበሩ ዘርፎች ናችሀው ከምንምም ጋር አይጋጭም። አደገኛው ግን «ዘመናዊነት» የሚባለው ርዕዮት ዓለም ነው። ቅድም የጠቀስኩት ጸረ ሃይማኖትና ጸረ ባህል የሆነ አስተሳሰብን እንደ መርፌ ይወጋል። ይህን አውቀን ስንዴውን ከንክርዳዱን መለየት አለብን። ጠቃሚውን ትምህርት እየተማርን ጎጂውን እራሳችንን እንድንጠላ የሚያደርገውን ለይተን አውቀን እንተው። የምንማረውን በባህልና ሃይማኖታችን መነጽር ወይም አመለካከት እንማረው። ለልጆቻችንም እንደዚሁ።

ይህ ነው ምክሬ። ዶናልድ ሌቪን እንዳሉት - ክሁሉ ጥቅሳቸው ይህን ነው እጅግ የምወደው - "The vitality of a people springs from feeling at home in its culture and from a sense of kinship with its past. The negation of all those sentiments acquired in childhood leaves man adrift, a prey to random images and destructive impulses…" ከኔ የምትሻሉት ተርጉሙት!

Sunday 4 December 2016

መደጋገም አለመሻሻል

እንደጠበኩት የ2008-2009 የህዝብ ዐመፅ ተረጋግቷል። የተረጋጋው መንግስት የአስሸኳይ አዋጅ ስላወጀ፤ የማይሸነፍ ኃይልና አቅም ስላለው፤ ህዝቡ አቅም ስለሌለው፤ ህዝቡ ስለተከፋፈለ፤ አብዛኛው ህዝብ ኢህአዴግን ስለሚደግፍ፤ ወዘተ አይደለም። ዐመፁ የመነመነው ህዝቡ በተለይም የፖለቲካ መደቡ የኢትዮጵያ የመንገስት አገዛዝን ለመቀየር የሚያስፈልጉ ቀድመ ዝግጅቶች ስላላሟሉ ነው።

እነዚህ ቀድመ ዝግጅቶች ምንድናቸው? አንድ አገዛዝን ለመቀየር በመጀመርያ አማራጭ መቅረብ አለበት። አማራች የፖለቲካ ራዕይ ወይም ሰፊ አመለካከት፤ ርዕዮት ዓለም፤ መዋቅርና ኃይል ያስፈለጋል። ከዛ በኋላ ነው ህዝቡ በሰላም ወይም በዐመፅ፤ በቀስታ ወይም (ቢቀርብን ይሻላልንጂ) በአብዮት፤ ካሉት የመንግስት አስተዳደር አማራቾች የሚመርጠው።

ላለፉት 25 ዓመታት ግን የኢህአዴግ ተቃዋሚዎች፤ ማለት ህዝብም የፖለቲካ መደቡም፤ እነደዚህ አይነት የፖለቲካ አማራጭ ማዘጋጀት አልቻለም። በመጀመርያ የፖለቲካ አመለካከቱም ርዕዮት ዓለሙም የተበታተነና ያልሰከነ ነው። የተለያዩ አመለካከቶች አሉ ከጎሰኝነት እስከ አንድነትና ሌሎች ከመካከል። ይህ ልዩነቶች ተገቢ ቢሆንም እነዚህ አመለካከቶች እንደሆነው ሆኖ ለመስማማት ተስማምተው አብሮ መስራት አልቻሉም። ይባስ ተመሳሳይ የፖለቲካ አስተያየት ያላቸው እርስ በርስ በተራ ምክነያቶች እየተጣሉ አይስማሙም። በኦሮሞ ብሄርተኞች መካከል ወይም በኢትዮጵያ ብሄርቶኞች ወይም የአንድነት ፖለቲካ ደጋፊዎች መካከል ያለው አለመስማማትና አብሮ አለመስራት ነው ዋናው ችግር። ለመድገም ያህል በጎሳና በአንድነት አመለካከት ያለው አለመስማማት አደለም ትሉቁ ችግራችን። ዋናው ችግራችን አንድ አመለካከት ያላቸው ወገኖች ትስማምተው መስራት አለመቻላችን ነው። የኢትዮጵያ የፖለቲካ ችግር በአንድ አረፍተ ነገር ለመቋጨት ከተፈለገ ይህ ነው። በዚህ ምክነያት የኢህአዴግ ተቃዋሚ አንድ የሆነ ወይም ሁሉን አቀፍ የሆነ የፖለቲካ አማራጭ አመለካከትና ርዕዮት ዓለም ለ25 ዓመት መገንባት አልቻለም።

አንድ የአማራጭ አመለካከት ከሌለ ደግሞ መዋቅር ሊኖር አይችልምና ለዚህም እስከ ዛሬ አማራጭ መዋቅር የለም። ሻእቢያና ህወሃት በደርግ ጊዜ የነበራቸውን መዋቀር እናስታውስ። የዘመኑ ተቃዋሚ እነደዚህ አይነት ነገር በኢትዮጵያ ውስጥም ውጭም የለውም። እነ ሻእቢያ በጄታቸው በሚሊዮን ብር ሲቆጠር የዛሬ የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች በሺዎች ይቆጠራሉ! እንደዚህ አይነት መዋቅሮች ምን ብለው ነው መንግስት የሚወርሱት?

መዋቅር ስለሌለ ደግሞ ኃይል የለም። የተቃዋሚ የህዝቡም ኃይል በሺዎች ነው የሚቆጠረው። በፊሊፒንስ ሀገር የህዝብ አብዮት ሲነሳ ህዝቡ በሚሊኦን ነበር ወደ ሰልፍ የወጣው። አንድ ጥይት ሳይተኮስ  መንግስት በሰላም ተቀየረ። ኢትዮጵያ ግን ውስን ቁጥር ነው ሰልፍ የሚወጣው። የተቃዋሚ የጦርም ኃይል ኢሚንት ነው። ረብሻ ለመፍጠር ያህል አቅም ቢኖራቸው ነውንጂ በዚህ ሁኔታ ከዛ አልፎ የተም አይደርስም።

እሺ፤ የፖለቲካ አመለካከት ወይም ርዕዮት ዓለም የለም። መዋቅርም የለም። ኃይልም የለም። ታድያ ምንድነው የሚጠበቀው? ከ25 ዓመታት በኋላ ተቃዋሚው ጎራ በሞላ ጎደል ምንም መሻሻል አላሳይምም የበፊቱንም ስህተቶች ደጋግሞ ይደጋግማል።

የዛሬውን የምሁራንና የተቃዋሚ መሪዎች ውይይት ሲታይ ከ25 ዓመት በፊት ከነበረው ብዙ ለውጥ የለውም። ምናልባትም ወደ ኋላ ሄደናል። 25 ዓመት በፊት የታተመ ኢትዮጵያን ሪቭዩ መጽየትን ብንመለከት ያው ዛሬም የምንወያይበት ጉዳዮች ያኔም (ያኔ በተሻለ ቋንቋና ብስለት) እየተወያየን ነበር። በውይዩቱ ውይም በመግባባቱ ምንም ለውጥ አይታይም!

ገጣሚው አቶ ፍቅሬ ቶሎሳ 25 ዓመት በፊት በገጣሚ አቅሙ ስለኦሮሞና አማራ ግንኙነት የሚገጥሙትን ዛሬም ይጽፋሉ ያኔም ዛሬም በቂ የተረዳቸው ስለሌለ። አንድ ኦሮሞ ብሄርተኛ ኢትዮጵያ መገነጣጠል አለባት ሲሉ ጉዳዩን እንደተለመደ አድርጎ በበሰለና በሰከነ መንገድ ተመልክቶ የሚገባውን መልስ ከመስጠት ልክ እንደ 25 ዓመት በፊት በድንጋጤ - ይህ ያላሰብነው የጎሳ ብሄርተኝነት እውነት ሊመጣብን ነው እንጂ እያልን - የተበታተነና መላ የሌለው መልስ መለስን ፍረሃትንም አንጸባረቅን። ትናንሽ የስራ አለመግባባት ሲያጋጥማቸው «የአማራ ንቅናቄ ደጋፊዎች» በፖለቲካ አመለካከት የሚጋሩትን ግንቦት 7 ደግሞም ኢሳትን መሳደብ ጀመሩ ልክንደ 25 ዓመት የአንድነት ደጋፊዎች ከላይ የጠቀስኩትን ታላቅ ኢትዮጵያን ሪቪዩ መጽየት ተጣልተው እንዳፈረሱት። ለማስታውስ ያህል ከዛም በኋላ መላው ኢትዮጵያ ወይም መላው አማራ ትብሎ ኃይለኛ ፍጅት ተቅሄደ። ቀጥሎ የቅንጅት ፍጅቶች፤ የአንድነት ፓርቲ ፍጅት፤ ዛሬም የሰማያዊ ፓርቲ ፍጅት! እንሆ ከ25 ዓመት በኋላ ታሪክ እየተደገመ ነው!

መፍትሄው ምንድነው? በዋና ጉዳዩ ላይ ስራ መስራት ነው። የሰው ልጅ ችግር እንዳለውና ማስተካከል ካልፈለገ ለመሸሽ ያህል ሌሎች ላይ ወይም በሌላ ጉዳይ ያተኩራል። ዋናው ችግሩ እንዳለ ወይም እየባሰ ይቀጥላልም። እስካሁን የኢትዮጵያ የተቃዋሚ ጎራ  እንደዚህ ነን። በዋናው ጉዳይ ስራ ከመስራት መጣላትና መናቆር ላይ ቆይተናል። ግን ወደ ግብ የምሄድ ፍላጎት ካለን እነዛን አሳሳች ተግባሮችን ትተን ወደ ስራ መግባት አለብን።

እነዚህ ስራዎች ምንድናቸው? የፖለቲካ አመለካከትን ተወያይቶ ቀስ ብሎ ጨምቆ ሰፊ ግን አንድ የሆነ የአገዛዝ አመለካከት አዘጋጅቶ በዚ ላይ መስማማት። ይህ ስምምነት መዋቅር ለመዘርጋት ዋና ቀድመ ዝግጅት ነው። መተዋወቅ፤ መግባባት፤ መስማማትና አንድ ልብ መሆን ግድ ናቸው። ይህ ደግሞ ረጅም ጊዜ የሚወስድ ሂደት ነው። በቅርቡ ባደረጉት ቃለ ምልልስ አቶ ጁኔዲ ሳዶ በአንድ ወቅት ኦኸድድ የ20 የሙሉ ቀን ውይይት ከወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ጋር እንዳካሄደ ተናግረዋል። ይህ ረጅም ውይይት በተዋቀረ ድርጅት ውስጥ ነበርና አዲስ ድርጅት ወይም ስብስብ ምን ያህል ውይይት እንደሚያስፈልገው እናስብ።

አንድ ሰፊ ግን አስማሚ አመለካከት ላይ ከተደረሰ በኋላ መዋቅር መዘርጋት ነው የሚቀጥለው እርምጃ። ይህ በተነጻጻሪ ቀላሉ እርምጃ ነው የሚሆነው። አንድ ልብ የሆነ ሰው እጅግ ስኬታማ ይሆናልና። ይህ መዋቅር አንድ ድርጅት ብቻ ሊሆን አይገባም። የተለያዩ መዋቅሮች - የታወቁም የህቡ - በተለያዩ የህብረተሰብ ዘርፍ ይቋቋማሉ። በርካታ ሰዎችም ዛሬ ባሉት የሀገሪቱ መዋቅሮች ከነ ኢህአዴግ ውስጥ ሰተት ብሎው ገብተው የራሳቸውን የሚያምኑበትን አቋም በድብቅ ያራምዳሉ።

ይህ መደራጀት እይጠነከረ ሲቀጥል በራሱ ትልቅ ኃይል ዪሆናል። በዚህ ወቅት የጠመንጃ ኃይል አያስፈልግም! እያንዳኑ የሀገሪቷ ዘርፍ በነዚህ የተቃዋሚው ጎራ ሰዎች ሞልቶ ይገኛልና ትንሿ እንቅስቃሴ አገዛዙን በሰላም ግልብጥ ያረገዋል። የነባር መንግስቱ ተራም ቀንደኛም ባለስልጣኖች በግድ ቢሆንም በተቃዋሚው ብስለት ምክንያት አለ ፍርሃት ለውጡን ይቀበላሉ።

በኔ እምነት የኢትዮጵያ የፖለቲካ መሻሻል ቀደም ተከተል እንዲህ ነው መሆን ያለበት። የተሻለ ምርጫ የለም። ግን ከ25 ዓመት በኋላ አሁንም በተወሰነ ደረጃ ገና አንደኛ እርምጃው ላይ ነን። ስራችንን እንጀምር።