Wednesday 19 September 2018

ታላቅ ጥላቻ ባይኖር የከቡራዩ እልቂት አይከሰትም ነበር

ስለቡራዩ የዘር ማጥፋት እልቂት ብዙ ይባላል። ጸንፈኛ የኦሮሞ ብሄርተኞች የቀሰቀሱት እና ያስተባበሩት ነው ይባላል። በተለያዩ የኦሮሞ ሚዲያዎች በተለይም ኦኤምኤን የጥላቻ ፕሮፓጋንዳ የተቀሰቀሰው ነው ይባላል። ሁከት ለመፍጠር እና ኦሮሞ እና አማራን «ለማጣላት» የህወሓት ሰዎች ናቸው ያደረጉት ይባላል። ህወሓት ከያኮረፉት ኦህዴዶች እና ጸንፈኛ ብሄርተኞች አብሮ ያስተባበረው ነው ይባላል። አሁን ደግሞ አንዳንድ የህወሓት ጸንፈኞች እና የኦሮሞ ብሄርተኞች የጎሳ ብሄርተኝነትን የጥላ እሸት ለመቀባት ተብሎ ግንቦት ሰባት ያሴረው ክስተት ነው ይላሉ። ብዙ ይባላል መንግስት ቀስ ብሎ እውነታውን በይፋ እንደሚያወጣው ተስፋ አለኝ።

ይህ ሁሉ ሲባል አንድ እውነታን መካድ አይቻልም። ይህን የህዝብ ማጥፋት እልቂትን የፈጸሙት ሰዎች በዘር ጥላቻ የተሞሉ መሆናቸው ግልጽ ነው። ሰለቦችም መስካሪዎችም የመሰከሩት የዘር ማጥፋትን ነው። ገዳዮቹ ዘርን እየሰደቡ፤ ውነድ ልጅን ለመግደል እየፈላለጉ፤ ሴቶችን እየደፈሩ፤ ጥይት ወይንም ድብደባ ሳይሆን አጸያፊ የግድያ መንገዶች እየተጠቀሙ ወዘተ መሆኑ ይታወቃል። ይህ ክስተት መሆን የሚቻለው በዘር ጥላቻ ያላቸው ሰዎች ናቸው። ክስተቱ ሙሉ በሙሉ ግልጽ የሆነ የዘር ማጥፋት (ethnic cleansing) በሃሪ ነው ያለው።

ዝም ብሎ ቅጥረኛ ገዳይ ይህንን አይነት ድርጊት ማድረግ አይችልም። ቅጥረኛ ገዳይ በቀጥታ ነው ተግባሩን የሚፈጽመው። ግደል እና ዝረፍ ከሆነ ይገላል ይዘርፋል እንጂ የዘር ማጥፋት ዘመቻ ያለው ክስተት ሊፈጽም አይችልም።

በተዘዋዋሪ በሌሎች በኢትዮጵያ ስፍራዎችም ያየናቸው የዘር ማጥፋት ዘመቻዮች እንዲሁ በዘር ጥላቻ ያላቸው ኃይሎች እንደተፈጸመ ግልጽ ነው። በጊዴኦ/ጉጂ፤ ኦሮሞ/ሶማሌ፤ አማራ/ቤኒሻንጉል የተከሰቱት የዘር ማጥፋት ዘመቻ ምክልቶች (pattern) አላቸው። ምንም የፖለቲካ እና የገንዘብ ኃይል ከበስተጀርባቸው ቢኖርም አለዘር ጥላቻ መፈጸም የማይችሉ ተግባሮች ናቸው።

ስለዚህ ዋናው ችግር የዘር ጥላቻው ነው! እና የዘር ጥላቻን የሚያራግቡ ናቸው! ገንዘቡ፤ ሴራው፤ ወዘተ ባለው የዘር ጥላቻ ላይ ነው ስራውን የሚሰራው። ችግሩን ለመፍታት ሴራውን የሚሰሩት እና የሚያቀናበሩትን ማስቆም ያስፈልጋል። ግን ይህ መሰረታዊ ችግሩን አይፈታም። በዋናነት የዘር ጥላቻን የሚያራግቡትን ማስቆም ያስፈልጋል። ቀጥሎ በህዝብ መካከል ያለውን ጥላቻ ማጥፋት ያስፈልጋል።

እንዴት ነው በህዝቡ መካከል ያለው የዘር ጥላቻን ማጥፋት የሚቻለው። መንግስት ትህምህርት ቤትን፤ ሚዲያን እና ሌሎች ተመሳሳይ መዎቅሮችን በተገቢ ሁኔታ መቆጣጠር አለበት። የ27 ዓመታት የዘር ጥላቻ ፕሮፓጋንዳን ለመመለስ ሙሉ ዘመቻ ማድረግ አለበት። ጉዳዩ አስርት ዓመታት ይፈጃል ግን አማራጭ የለም። ሌላው የዚህ ዘመቻ ዋና ተግባር ደግሞ ህዝብ እንዲ ቀላቀል ማድረግ ነው። የእርስ በርስ ቋንቋ እንዲማር እና እንዲጋባ እና እንዲዋህድ ማድረግ ነው። ዘላቂው መፍትሄ ይህ ነው።

No comments:

Post a Comment

ለሀሳብዎ አመሰግናለሁ!