Wednesday 27 June 2018

ችኮላ

ጠቅላይ ሚኒስቴር አብይ አህመድ ለውጦችን በአስገራሚ ፍጥነት ነው እያመጡ ያሉት። መቼም አንዳችን በዚህ ፍጥነት ለውጦች ይመጣሉ ብለን ገምተን ነበር የሚል ካለ ይገርመኛል። እርገጥ ኤርሚያስ ለገሰ አብይ አህመድን ስኬታማ ለመሆን ፍጠን ብሏቸው ነበር ግን እርግጠኛ ነኝ እሱም እንደዚህ ይፈጥናሉ ብሎ አልጠበቀም። አንዳችንም አልጠበቅነውም ብለን በትህትና ብናምን ጥሩ ይመስለኛል!

ፈጥኗል ግን ከመጠን በላይ ፈጥኖ ይሆን? ጥሩ ጥያቄ ነው መልሱንም አላውቅም። ከሁላችንም በላይ ከፖለቲካ ጦርነት ውስጥ ያሉት አብይ እና ቡድኑ ነው ያሚያውቁት። ከመጠን በልይ መፍጠን እንደሚቻል ግን ይታወቃል። «ዴሞክራሲ ይስፈን»፤ «ፍትህ ይኑር»፤ «ያለፉት የፖለቲካ እና ሰብዓዊ ወንጀሎች ይጣሩ»፤ «የፖለቲካ ወንጀለኞች ይፈረድባቸው»፤ «ህገ መንግስቱ ይቀየር»፤ «ሀገ መንግስቱ በትክክሉ ይፈጸም» ወዘተ መፈክሮች ምአት ናቸው። የምንፈልገውን በሙሉ አሁኑኑ ይደረግልን የሚሉ አሉ።

ግን የ27፤ የ40፤ የ50፤ የ100 ወዘተ ዓመታት ችግሮች በአንዴ አይፈቱም፤ ይህንን ሁላችንም እናውቃለን። ከብዙ ሰዎች ይህን ጥሩ ምሳሌ ሰምችአለሁ፤ ሀገራችን እንደ ማንኛውም የከባድ በሽታ ህመምተኛ ለህልውናው የሚያሰጋው እና በውቅቱ መታከም የሚችሉ ቁስሎችን ነው በጀመርያ መታከም ያለበት። እነዚህ ህመሞች ሲድኑ ወደሚቀጥሉት መሄድ ነው። የህቅምናውን ቀደም ተከተል በደምብ የሚአቁት ከህመምተኛው ቅርብ ያሉት የሚያክሙት ሐኪሞች ናቸው። ግን እኛ ኢትዮጵያዊዎች ለሐኪሞቹ ተሽሎናል አልተሻለንም ብለን ምልክት መስጠት አለብን። ስለዚህ መፈክሮቹ ጥያቄዎቹ መቀጠል አለባቸው። ግን የነ ጠ/ሚ አብይንም አቅም እና የፖለቲካው ጠቅላላ ሁኔታ መረዳት አለብን። ቢያንስ ለራሳችን ብለን የማይሆን ነገር መጠበቅ የለብንም።

እርግጥ መጠበቅ ከባድ ነው ትእግስት ከባድ ነው። አንድ የሚያቀለው ነገር ግን ስራ ነው። ለለውጥ እንስራ! ጠ/ሚ አብይ ጋብዞናል። ከሰፈራችን፤ ከመስርያቤታችን፤ ከሃይማኖት ስፍራችን ወዘተ ሰላምን እናምጣ። ፍቅር እናምጣ። ሙስናን እና ተመሳሳይ ጎጂ ባህሎችን እንታገል። ከጎረቤታችን ጋር እንፋቀር (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2016/09/blog-post_14.html)። ድሆችን እንርዳ። ብዙ ብዙ ስራ አለ። ጥያቄ ማብዛት ስራ አይደለም፤ ያንንማ ሁላችንም በቀላሉ እናደርገዋለን። እነዚህ የፍቅር ስራዎች ናቸው ከባድ። እነዚህን ስራዎች ብንሰራ ጥያቄዎቻችን እንዲመለሱ ያፈጥናሉ ትእግስትም ይኖረናል!



Tuesday 26 June 2018

ስለ ውጭ ሀገር የተወለዱ ያደጉ ልጆች የእናት ቋንቋቸውን አለመቻል ጉዳይ…

በውጭ ሀገር ኑሮ ደጋግመን ያየነው ታሪክ… በአዋቂ እድሜ ያሉ ኢትዮጵያዊያን በቋንቋቸው እየተነጋገሩ እያሉ አንድ ልጅ ወደነሱ ይመጣል። አዋቂዎቹ ልጁን "Hi, how are you?" ይሉታል ወድያው ንግግራቸውን ወደ እንግሊዘኛ (ጀርመንኛ ወዘተ) ይቀይራሉ! ልጁ አማርኛ፤ ኦሮምኛ፤ ትግርኛ ወይንም ሌላ የኢትዮጵያ ቋንቋ ይችል አይችል አያውቁም ግን ሳያስቡት አይችልም ብለው ገምተው በእንግሊዘኛ ያናግሩታል።

ሁላችንም እንደምናውቀው ውጭ ሀገር የተወለዱ ወይንም በልጅነታቸው ወደ ውጭ ሀገር የሄዱ ልጆቻችን አብዛኞቹ የእናት ቋንቋቸውን አይችሉም። አዎን የተወሰኑ የሚችሉ አሉ ማንበብ መጻፍም የሚችሉ አሉ ግን በርካታው አንዳንድ ቃላት ከመስማት አልፎ አይችልም።

በአንጻሩ በርካታ የሌሎች መጤዎች (ኢሚግራንት) ልጆች የእናት ሀገራቸውን ቋንቋ ይችላሉ። አንዳንዱ ህብረተሰብ የልጅ ልጆቻቸውም ቋንቋቸውን ይችላሉ። ግን አብዛናው ኢትዮጵያዊ ወላጅ ይህንን እውነታ አያውቅም አይገነዘብም። ውጭ የሚኖሩ ልጆች የእናት ቋንቋቸውን አይችሉም ብለን ደምድመናል።

ሆኖም «ለምንድነው ልጆቻችን የእናት ቋንቋቸውን የማይችሉት» ጥያቄ ሁላችንም ደጋግመን እንጠይቃለን። ምዋለ ህጻናት («ዴይኬይር») ስለሚውሉ ነው እንላለን። ትምሕርት ቤት ነው እንላለን። ኑሮ ለማሸነፍ ስለምንሯሯጥ ልጆቻችንን ቋንቋ ለማስተማር ጊዜ ስለሌለን ነው እንላለን። ስንፍነታችን ነው እንላለን። የተለያዩ ምክንያቶች እንሰጣለን።

ግን እነዚህ ምክንያቶች ሁሉን ሌሎች መጤዎችን ይመለከታሉ! ሜክሲካኖች፤ ሌሎች ሂስፓኒኮች፤ ቻይናዎች፤ ህንዶች፤ ጣልያኖች፤ ግሪኮች፤ ሶማሌው፤ አረቦች፤ ቱርኮች ወዘተ ይመለከታቸዋል። እነዚህም ልጆቻቸውን መዋለ ህጻናት እና ትምሕርትቤት  ይልካሉ። እነዚህም እንደኛው ይሰራሉ «ኑሮን ለማሸነፍ» ይጥራሉ ትርፍ ጊዜ የላቸውም። ከነሱ መካከል ሀብታም እና ድሃ አለ። የቀለም ትምሕርት የተማረ ያለተማረ አለ። ከትውልድ ሀገሩ ትንሽ እንግሊዘኛ የተማረ ያልተማረ አለ። አንዳንዱ እንግሊዘኛን እንደ ስልጣኔ የሚቆጥር እና እንደ ጣኦት የሚያመልከው አለ (አንዳንድ ህንዶች) አንዳንዱ ደግሞ ለእንግሊዘኛ ግድ የለውም። ሁሉም አይነት መጤዎች አሉ። ግን እነዚህ በሙሉ ከኛ ኢትዮጵያዊያን በተሻለ መልኩ የእናት ቋንቋቸውን ለጆቻቸው ያስተላልፋሉ።

ታድያ ለምንድነው የኢትዮጵያዊ ልጆች ከነዚህ ሁሉ ተለይተው የእናት ቋንቋቸውን የማይችሉት? መልሱ የሚመስለኝ እንዲህ ነው፤ የልጆቻችን የእናት ቋንቋቸውን አለማወቅ ሳናውቀው ባህል ሆኗል። የመጀመርያ ኢትዮጵያዊ መጤዎች በተለያዩ ምክንያቶች ልጆቻቸውን ቋንቋ ሳያስተምሩ ቀርተው የውጭ ሀገር ልጅ የእናት ቋንቋ አለማወቅ በህብረተሰባችን የተለመደ ሆነ። ይህ "expectation" ባህል ሆነብን።

ምክነያቱ ከዚህ የሚያልፍ አይመስለኝም። ከላይ እንደጠቀስኩት ከሌሎች መጤዎች ምንም አንለይም። ስለዚህ የባህል ጉዳይ ነው። የአቅም ማጣት ወዘተ አይደለም። ይህን ባህል ከቀየርን እና ልጆቻችን እንደ ማንም ልጆች የእናት ቋንቋቸውን ሊያውቁ ይችላሉ ብልን ከደመደምን አንድ ትልቅ እርምጃ ወሰድን ማለት ነው።

ሁለተኛው እርምጃ ልጆቻችንን በቋንቋችን ብቻ ማናገር ነው። ከተወለዱ ጀምሮ ወላጅ እና ልጅ በማንኛውም ቦታ በቋንቋቸው ብቻ ነው የሚነጋገሩት የሚል ህግ ማውጣት ነው። ቀላል ነው። የተለየ ነገር አያስፈልግም። ቋንቋውን ቅጭ ብሎ ማስተማር አያስፈልግም። ከወላጅ ምንም ትርፍ ስራ አይጠይቅም። ልጆችን በቋንቋ ማነጋገር ብቻ ነው። ሌሎች ሁሉ እንደዚሁ ነው የሚያረጉት። እርግጥ መጻፍ እና ማንበብ መማር ትምሕርት ይጠይቃል ግን በልጅነት ከተጀመረ ትንሽ ጊዜ ነው የሚጠይቀው። ልጆች በትንሽ እድሜ በቀላሉ ፊደሉን መማር ስለሚችሉ ከዛ በኋላ እራሳቸው ይቀጥሉበታል።

በዚህ መልኩ ልጆአቸውን ቋንቋቸውን ያስተማሩ ሰዎች ሁላችንም እናውቃለን። ቁጥራቸው ትንሽ ቢሆንም መጻፍ ማንበብ የሚችሉ አሉ። ግእዝም የሚችል አውቃለሁ! እንደሚቻል መረጃ አለን ትርፍ ስራ እና ጊዜ እንዳማይፈጅም መረጃ አለን። ስለዚህ እንበርታበት!

በመጨረሻ አንድ ነገር ልጨምር እወዳለሁ። የእናት ቋንቋን መቻል ጥቅሙ ምንድነው ብላቸሁ የምትጠይቁ ትኖራላችሁ። ጥሩ ጥያቄ ነው። ልጄን አሜሪካ ወልጄ የማሳድግ ከሆነ አማርኛ መቻሉ ምን ዋጋ አለው? ስፓኒሽ አይሻለው ይሆን? መቼም የእናት ቋንቋችንን ማውቅ አስፈላጊነቱን ሁላችንም ምክንያቱን መደርደር ባንችልም ከልባችን እናውቀዋለን። ግን ምክንያቶቹን እስቲ ልደርድር፤

1. ማንነት፤ ውጭ ሀገር የተውለደ ኢትዮጵያዊ ቢፈልግም ባይፈልግም እራሱን እንደ ሙሉ የውጭ ሀገር ዜጋ ሊቆጥር አይችልም። በሰው ልጅ ተፈጥሮ ምክንያት የአባቶቹ ማንነት ይጫነዋል ከዬት ናቸው ማን ናቸው ማለቱ አይቀርም። ሁላችንም ይህንን በተግባር አይተናል ልንክደው አንችልም። ቋንቋን ማወቅ ይህን የማንነት ስሜትን በተወሰነ ደረጃ ያሟላል።

2. ኢትዮጵያዊ ነን ሀገራችንን እንወዳለን እዚህ ስደተኛ ነን ብለን የምናምን ልጆቻችንን ኢትዮጵያዊ ማድረግ አለብን አይደለ? አይ ልጆቻችንን አሜሪካዊ፤ ጀርማን ወዘተ እናድርግ ይህዱ ከሆነ ጥሩ ግን ምን እያደረግን እንደሆነ እንወቀው። ዜጋን አልፎ መስጠት እንደ ትንሽ ነገር አኑቅጠረው። መብት ቢሆንም ለኢትዮጵያ ኪሳራ ነው።

3. በተዘዋዋሪ በርካታ ጥናቶች እንደሚያሳዩት የራስን ማንነት ማወቅ ለሌላ የኑሮ መስፈርት ይረዳል። ለትምሕርት፤ ከሰው ጋር ለመግባባት፤ ቁም ነገረኛ ለመሆን ወዘተ የራሱን ማንነት እና ከየት የመጣ እንደሆነ የሚያውቅ ልጅ በሁሉም ይሻላል።

ስለዚህ ልጆቻችንን የእናት ሀገር ቋንቋቸውን እናስተምር ወይም ብትክክሉ ለመናገር አንከልክል! በቋንቋቸው እናናግራቸው እና ወደ ፊት ማንነታቸውን የሚያውቁ የሚኮሩ ልጆች እንዲሆኑ እናድርግ።

-------------------------

Friday 22 June 2018

ኤርትራ

የ1991 ኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ስለ ባድሜ ወይንም ድንበር አልነበረም። ጉዳዩ የስልጣን የበላይነት ነበር ተፎካካሪዎቹ ሻዕብያ እና ህወሓት ነበሩ።

ደርግ ከስልጣን ሲወርድ ጀምሮ ለሰባት ዓመት ህወሓት እና ሻዕብያ ከሞላ ጎደል አብረው ኢትዮጵያን ገዝተዋታል። አዎን የኢትዮጵያ መንግስት በህወሓት ነበር የሚመራው ግን በህውሓት ፈቃድ እና ድጋፍ ሻዕብያ እንደ «ሁለተኛ መንግስት» ይንቀሳቀስ ነበር። የኤርትራ መንግስት አካላት ከነ ደህንነት ክፍሉ ኢትዮጵያ ውስጥ በይፋም በስውርም ይሰራ ነበር ስልጣንም ነበረው። የኤርትራ መንግስት እና ባለ ሃብቶች በኢትዮጵያ መንግስት ፖሊሲዎች ታላቅ ሚና ይጫወቱ ነበር። ኤርትራ ከብሄራዊ ባንክ ገንዘብ ታገኛ ነበር። ኤርትራዊ ባለ ሃብቶች በምስና የባንክ ብድር፤ የምንግስት ኮንትራት፤ የቀረጥ ነጻ መብት ወዘተ ያገኙ ነበር። ኤርትራዊያን ቡና አለቀረጥ ከኢትዮጵያ ገዝተው ወደ ውጭ ሀገር ይሸጡ ነበር። ወዘተ፤ ምሳሌዎቹ ማስረጃዎቹ በርካታ ናቸው ተመዝግበዋል በአዲሱ የመንግስት ግልጽነት አካሄድ ደግሞ ይበልጥ ወደ ይፋ ይወጣሉ። ድምዳሜው ግን ከ1983 እስከ 1991 የኤርትራ መንግስት እና ኤርትራዊያን ባለ ሃብቶች ኢትዮጵያ ውስጥ አግባብ ያልሆነ ተጽኖ እና ስልጣን ነበራቸው።

ግን ይህ ሁኔታ ሊቀጥል አይችልም ነበር። ምክንያቱም የሀገር ገዥ የነበረው ህወሓት ኢትዮጵያን ሙሉ በሙሉ መቆጣጠር ይፈልግ ነበር። የሀገር መንግስት ሆኖ ልምንድነው ሌላው ሁለተኛ ምነግስት የሚያስተናግደው? ህወሓት የኢትዮጵያን ስልጣንን እና ከኢትዮጵያ የሚገኘውን ጥቅም ለራሱ ይፈልግ ነበር። ኢህአዴግ ውስጥ ያሉት አጋር ፓርቲዎችም እንዲሁም ኢትዮጵያ ከኤርትራ ተጽኖ ነጻ መሆን አለበት እራሳችን ሙሉ በሙሉ መግዛት አለብን የሚል አቋም ነበራቸው። በዛው መጠን ሻዕብያ በኢትዮጵያ ያለውን ጥቅም እና ስልጣን መልቀቅ አልፈለገም። በዚህ ጉዳይ መደራደር አልተፈለገም ተፎካካሪዎቹ በጡንቻ መጋጠም ወሰኑ። በአጭሩ ይህ ነበር የህወሓት እና የሻዕብያ ግጭት እና የጦርነቱ ምንጭ።

ከጦርነቱ በኋላ በህወሓት እና ኢህአዴግ ክፍፍል ምክንያት ወደ «ጦርነትም ሰላምም የለም» ("no war no peace") ዘመን ገባን። ለምን እስከ መጨረሻ ሄደን አሰብን አልወሰድንም ሻዕብያን አላፈርሰንም የሚሉ ነበሩ። ስለዚህ የህወሓት የፖለቲካ ስምምነት ያንን ባናደርግም ኤርትራን በማግለል ሻዕብያን እንጎዳለን ሆነ። ሻዕብያ በኢትዮጵያ አሳቦ የሀገራቸውን ኤኮኖሚ እና የህዝብ ሞራል ይገላል እና ቀስ ብሎ ይወድቃል ነበር በኢትዮጵያ መንግስት የነበረው አስተሳሰብ። ከዛ በኋላ ከኢትዮጵያ ጋር በተሻለ መልኩ ለመደራደር ዝግጁ የሆነ መንግስት ኤርትራ ውስጥ ስልጣን ይይዝ እና ከነሱ ጋር እንደራደራለን ነበር የኢህአዴግ አቋም።

ስለዚህ ባጭሩ የ«ጦርነትም ሰላምም የለም» ፖሊሲ ሁለት አላማ ነበረው፤ 1) ሻዕብያን ከስልጣን ማውረድ ለኢትዮጵያ ወይንም ለህወሓት የሚመች መንግስት እንዲመጣ እና 2) ኤርትራ እንደ ሀገር ኃይሏ ከኢትዮያ አንጻር እንዲመነምን እና በዚህ ምክንያት ለኢትዮጵያ አመቺ የሆነ የድርድር ሁኔታ እንዲፈጠር።

ዛሬ አንደኛው ግብ አልተመታም ግን ሁለተኛው ተመቷል ወይንም ከዚህ በላይ ሊመታ አይችልም። ማለተም ካሁን ወድያ ኤርትራን ለማድከም ተብሎ ይህ ፖሊሲ ቢቀጥል ጉዳቱ ከጥቅሙ ይበልጣል። ሻዕብያ እና ኤርትራ የሚማሩት ትምሕርትሮች ከነበሩ ተምረውታል። የኤኮኖሚ ችግር በቂ አይተውታል። ሻዕብያ መሪው ኢሳያስ አፈወርቂ ከህውየት እስኪለዩ መግዛት መቀጠሉ ግልጽ ሆኗል። ከዛ በኋላ ደግሞ ትርምስ የሚመጣ ይመስላል የሻዕብያን የመገንጠል ጦርነትን የማያስታውስ ጭቆና ብቻ የሚያስታውስ አዲስ ትውልድ ወደ ፊት እየመጣ ሲሄድ። ስለዚህ ነው የአብይ አህመድ መንግስት ይበቃል ወደ ሰላም እና ድርድር እንግባ ያለው። ትርምስ ሳይመጣ ጠላት ሀገሮች እጃቸውን አለ ቁጥጥር ኤርትራ ውስጥ መክተት ከሚጀምሩ በፊት ካሁኑኑ የቀረውን የወንድማማቾች ስሜትን ተጠቅመን እንደራደር ነው።

ይህ ጥሩ አካሄድ ይመስለኛል። እንዳልኩት የ «ጦርነትም ሰላምም የለም» ፖሊሲ በቂ ሰርቷል ምቀጠሉ ለኢትዮጵያ አይጠቅማትም። ከዚህ አልፎ ተርፎ የኤርትራ ችግር ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ የቅርብ የፖለቲካ ለውጦች የሁለቱን ሀገራት የኃይል ሚዛን እጅግ ወደ ኢትዮጵያ አመዝኖታል። በህወሓት ዘመን የኢትዮጵያ ህዝብ የሚጠላው ከፋፋይ መንግስት ስለነበር ሀገሪቷን የተከፋፈለች ከሚገባት ደካማ ኃይል እንዲኖራት አድርጓል። በዛን ጊዜ ኢትዮጵያ ከኤርትራ ጋር ድርድር ብትገጥም ውጤቱ ደካማ ነበር የሚሆነው። አሁን ግን ህዝቡ በሙሉ አንድ ስለሆነ እነ አብይ አህመንድ ወደ ድርድር ሲገቡ ያንን ሁሉ ኃይል ይዘው ስለሚገቡ ታላቅ ድል ማድረስ ይችላሉ። እንደ ድሮ የሻዕብያን ብልጠት መፍራት የለም። እንደ ድሮ ኤርትራ እና ኢትዮጵያ እንደ እኩለኛማቾች አደሉም። ኢትዮጵያ ታላቅ፤ ግዙፍ እና ባለ ኃይል ናት ኤርትራ እንደሚገባት የኢትዮጵያ አንድ አስረኛ ናት። ይህ ለድርድር ጥሩ ሜዳ ነው። በእውነታ የተመሰረተ ትክክል እና ዘላቂ ስምምነት እንዲኖር የሚያደርግ ሜዳ ነው።

ባጭሩ የጠቅላይ ሚኒስቴር አብይ አህመድ የ«ጦርነትም ሰላምም የለም» የሚለውን ፖሊሲ ያቆመው ምክንያት ጥቅሙ ስላለቀ እና ለኢትዮጵያ አሁኑኑ ከኤርትራ ጋር ድርድር መግባት አዋጪ ስለሆነ ነው። እዚህ ላይ ማለት የምፈልገው አንድ ነገር አለ። ለኔ ኤርትራ እና ኢትዮጵያ አንድ ናቸው። የኤርትራ ህዝብ ኢትዮጵያዊ አይደለሁም ለማለት ሙሉ መብት አሉ በዚህ መብት አምናለሁ። ግን ለኔ ኤርትራኖች ሀገሬዎች ወንድሞቼ ናቸው። ከዛም አልፎ ከኢትዮጵያ የተገነጠሉት በኔ በኛ ጥፋት እንጂ በነሱ ክፋት አይደለም ብዬ ነው የማምነው። ስለዚህ ለኔ ይህ ድርድር ስለኤኮኖሚ ብቻ ሳይሆን ስለ ህዝባዊ ግንኙነተና ትሥስር ነው። የመለያየታችን ቁስሎች፤ ትዕቢቶች፤ ውሸቶች፤ ወዘተ የማስወገድ መጀመርያ ነው። እነ አብይ አህመድ ይህንን ለማድረግ እግዚአብሔር ይርዳቸው ይድራን!

Thursday 14 June 2018

አማራ ብሄራዊ ንቅናቄ

ስለ አማራ ፖለቲካዊ ንቅናቄ ለኢትዮጵያ ህልውና ያለው አስፈላጊነት (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2016/09/blog-post_23.html) ሁለት ዓመት በፊት ጽፌ ነበር። ያኔ አንዳንዶች  ከዚህ ንቅናቄ ተነስተው በአማራ ስም የተሰየመ የፖለቲካ ድርጅት ያቁቁማሉ ብዬ አልጠበቅሁም። ግን እንሆ «የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ» (አብን) ተወልዷል!

ዛሬ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ሁኔታ በፍጥነት እየተቀያየረ ነው። በየቀኑ ያልተጠበቁ ለውጦች እየተካሄዱ ነው። የሀገር ግንባታ ወቅት ነው (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/02/blog-post_20.html)። የጥያቄ፤ ውይይት፤ ምርምር፤ ድርድር እና ስምምነት ምመስረት ወቅት ነው። ይህን እድል ለማግኘታችን ተመስገን ማለት ያለብን ይመስለኛል፤ ማንናችንም ሁለት ዓመት በፊት ይህንን የተነበየ የለም። በዚህ የውይይት መንፈስ ነው ስለ «አማራ ብሄራዊ ንቅናቄ» ይህን  ጽሁፍ የማቀርበው።

የአማር ብሄራዊ ንቅናቄ አቋሙን፤ ፖሊሲዎቹን እና መመርያዎቹን አርቅቆ ባይጨርስም ሁለት ዋና ግቦቹን አሳውቋል። እነዚህ፤

1. የአማራ ህዝብን ከደረሰበት ያለው ግፍ እና ወንጀል ከነ መፈናቀል፤ መገደል፤ የተለያዩ ጥቃቶች፤ ታሪኩ እና ክብሩ በሃሰት መተቸቱ ወዘተ መከላከል እና ማዳን።

2. የጎሳ አስተዳደርን ማጥፋት። የህወሓትን ጎሰኛ ህገ መንግስትን ብዚህ መልኩ መቀየር፤ መሰረቱ «ብሄር ብሄረሰቦች ህዝቦች» ሳይሆን «ዜጋ» እንዲሆን፤ «ብሄር» ወይንም «ጎሳ» በህገ መንግስት ደረጃ እውቅና እንዳይኖረው (ቋንቋ ሊኖረው ይችላል)፤ ክልሎች የዜጎች እንዲሆኑ፤ ወዘተ።

ጥሩ ግቦች ናቸው። ብዙዎቻችን የምንስማማባቸው ይመስለኛል።

ግቦቹን እንደተቀበልን ወደ ዋናው ጥያቄ እንምጣ፤ እነዚህን ግቦች ለማሳካት በስመ «አማራ ብሄር» መደራጀት ነው የሚሻለው ወይንም በስመ «ኢትዮጵያ» በ«ህብረ ብሄራዊ» መልክ መደራጀት ነው የሚሻለው? እነዚህን ግቦች ለመምታት በህብረ ብሄራዊ መልክ መደራጀቱ ከበጀ ያ መንገድ ይሻላል ማለት ነው። አለበለዛ የ«አብን» መንገድ ነው የሚያስፈልገው ማለት ነው።

በ«አማራነት» ወይንም በ«ኢትዮጵያዊነት» የመደራጀት ጥቅም እና ጉዳት

በስመ «አማራ» መደራጀት ዋና ጥቅሙ የብሄራዊ ወይንም ጎሳዊ ስሜትን ሃይል እና አቅም ለመገንባት መጠቀም ነው። በስመ አማራ ከተደራጀን በ«ኢትዮጵያዊነት» ከምንደራጅ ይልቅ ህዝቡ በአማራነት ስሜት ይበልጥ ይሳተፋል ነው።  በታሪካችን ዛሬም ያሉት ሌሎቹ የጎሳ ድርጅቶች ይህ አንዱ ለመፈጠራቸው የሚሰጡት ምክንያት ነው። ሰውዉን በ«ኢትዮጵያዊነት» ይልቅ በ«ጎሳዊነት» መቀስቀስ ይቀላል ነው።

በስመ አማራነት መደራጀት ሁለተኛ ጥቅም የአማራ ህዝብ «አጄንዳ» ላይ ማተኮር ነው። ህብረ ብሄራዊ ድርጅት የሁሉንም ጉዳዮች ማስተናገድ አለበት። በዚህ መካከል የአማራው ጉዳይ አንዱ ይሆናል። ለምሳሌ በአማራ መፈናቀል ስራ መስራት ከተፈለገ የሁሉንም ትብብር ይጠይቃል። በአማራ ላይ የተለጠፈውን ሃሰተኛ ታሪክ ማስተካከል ከሆነም የሁሉን ትብብር ይጠይቃል። ወዘተ። ግን የአማራ ብቻ ድርጅት እነዚህን ስራዎች አትኩሮ መስራት ይችላል።

የህብረ ብሄር አደረጀት ዋና ጥቅም ኃይል እና አቅም (capacity) ነው። በማንኛውም ጉዳይ ላይ የአማራ ብቻ ሳይሆን የሌሎችም አቅም ማሳተፍ ይችላል። ለምሳሌ አማራ ከቤኒሻንጉል ሲፈናቀሉ አማራዎች ብቻ ሳይሆኑ ሌሎችም የዚህ ህብረ ብሄር ድርጅት አባሎች አቅማቸውን ሰምስበው ጉዳዩ ላይ ይሰራሉ። ባጭሩ ትልቅ ድርጅት በመሆኑ ትልቅ አቅም ይኖረዋል።

ሌላው ጥቅሙ በአንድ ብሄር የተወሰነ ባለመሆኑ በርካታ አቋማቸው ያልሰከነ ሰዎችን የመሰብሰብ አቅም ነው። እንደሚታወቀው ከጎሳኝነት እና አንድነት ፖለቲካ የሚዋዥቁ በርካታ ኢትዮጵያዊያን አሉ። እነዚህ ጸንፈኛ ጎሰኛ ያልሆኑት በውይይት እና መግባባት ወደ አንድነት አቋም ሊመጡ ይችላሉ እና የህብረ ብሄር ፓርቲ አባል ሊሆኑ ይችላሉ። የህብረ ብሄር ድርጅት ይህንን ማድረግ ይችላል ግን መቼም የአማራ ድርጅት አይችልም።

ሶስተኛው ልጠቅስ የምወደው በህብረ ብሄራዊ መልክ መደራጀቱ ጥቅም ይህ ነው፤ በመአላው ኢትዮጵያ በተለይም በአማራ ህዝብ መካከል በኢትዮጵያዊነት መደራጀት የተለመደ ነው። በኢትዮጵያዊነት መደራጀት ረዥም እና የሰከነ ታሪክ አለው። ይህ አይነት አደረጃጀት ክርክር የለውም ተቃውሞ የለውም (ከጎሰኞች በቀር)። በታሪካችን የተለመደ ነው። ትክክል ቢሆንም ባይሆንም በስመ አማራ መደራጀት ግን ሁልጊዜ አከራካሪ ነው ግጭት እና ጥል ያመጣል። አቅምን ይጎዳል ሰውን ይከፋፍላል። ይህን ታሪክ ከዚህ በፊት አይተነዋል ዛሬም እያየነው ነው።

ግቦቻችንን ለመምታት የትኛው መንገድ ይሻላል

የመጀመርያ የ«አብን» ግብ አማራን ባለበት ቦታ ማዳን እና ለመብቱ መከራከር እና መታገል ነው። እንደ ቅንጅት አይነቱ በስመ «ኢትዮጵያ» የተመሰረተ የህብረ ብሄራዊ ድርጅት ይበልጥ ያአማራ መብትን ማስከበር ይችላል ብዬ ገምታለሁ። በመጀመርያ ደረጃ ይህ ድርጅት ከአማራነት የሰፋ ስለሆን ከላይ እንደጠቀስኩት በርካታ አማራ ያልሆኑ የሌላ ብሄር ሰዎች፤ ቅኝት (ከአንድ በላይ ጎሳ) የሆኑ ሰዎች፤ ጎሰኝነትን የማይወዱ ግን አማራ ወይንም አማራ ብቻ ያልሆኑ ሰዎች ወዘተ ያሳትፋል። ይህ በርካታ አቅም በአማራ የሚደርሰውን ግፍ ላማስቆም ታላቅ ሚና ይጫወታል። ለምሳሌ ከኦሮሚያ ክልል አማሮች ከተፈናቀሉ አማሮች ብቻ ሳይሆኑ ኦሮሞዎችም በአንድ በህብረ ብሄራዊ ድርጅት ስም ይህን ወንጀል ይታገሉታል። ኦሮሞ ከሶማሌ ክልል ሲፈናቀል እንዲሁም። ይህ አካሄድ አንድነትን ይጎለብታል።

ግን እንደ «አብን» የሆነ የአማራ ድርጅት አማሮችን ብቻ በጉዳዩ ማሳተፍ ስለሚችል አቅሙ ውስን ይሆናል። በስመ አማራ እራሱን የገለለ (exclusive) ስለሆነ ወይንም ለሁሉም ክፍት ስላልሆነ  የሌሎች ትብብር ለማግኘት ይከብደዋል። እራሳችሁ ተወጡት ይባላል። እኛ እና እነሱ አይነት ስሜትን ያጎለብታል።

አይ የአማራ ድርጅት ከሊሎች ብሄራዊ ድርጅቶች ለምሳሌ ከኦሮሞ ብሄራዊ ድርጅቶች ጋር አብሮ መስራት ከሆነ ለምን መጀመርያዉኑ በሰፊ በጎሳ ሳይሆን በዜግነት የተመሰረተ ጥላ አይሰራም! ይህ አስተሳሰብ አንዱ የጎሳ አስተዳደር ርዕዮት ዓለም ምሶሶ ነው አይደለምን? ጎሰኞቹ የሚሉት የኢትዮጵያ ፖለቲካ በጠቅላላ ጥሩ ሁኔታ ላይ የሚደርሰው ሁሉም በጎሳ ከተደራጀ ነው። እና ግን እምንለው ሰፊው (ህብረ ብሄራዊ ድርጅት) ጥላ የጎሰኝነት ስሜትን ያበርዳል ትብብርን ያመቻል ግን ሁለት የብሄራዊ ድርጅቶች ሲደራደሩ የጎሳ ስሜት እና አደገኛ የግሳ ውድድር ስለሚቀድም አዋጪ እና ዘላቂ ትብብር ለመፍጠር ከባድ ይሆናል።

በዚህ ምክነያቶች የአማራ ህዝብን ከጥቃት ለማዳን ህብረ ብሄራዊው መንገዱ ይሻላል።

እስቲ የሁለተኛውን ግብ እንመልከት፤ ጎሳዊ አስተዳደርን አፍርሶ ዜጋዊ አስተዳደርን እንዲሰፍን ማድረግ። ይህ ጉዳይ ብዙ ተሳታፊዎች በሚገኙበት ፖለቲካዊ ድርድር ላይ ነው የሚፈታው።  እንደ «አብን» አይነቱ የአማራ ድርጅት ለዚህ ድርድር ምን ሚና ይጫወታል። የአማራ ህዝብን በበርካታ ደረጃ ወክሏል እንበል። አብን ከዚህ ድርድር ማለት የሚችለው የአማራ ህዝብን ወክዬ ህገ መንግስታችን ከጎሰኝነት ወደ ዜጋዊነት እንዲቀየር እጠይቃለሁ ነው። ሌሎች ደግሞ የኦሮሞ ህዝብን ወክዬ ወይንም የቲግራይን ህዝብ ወክዬ ወዘተ ይህንን አንፈልግም ይላሉ። ከዚህ ድርድር የሚሳተፈው የህብረ ብሄር ድርጅቶች ደግሞ እንደግፋለን ይላሉ። ስለዚህ አንዱ «ሴናሪዮ» የአማራው እና የህብረ ብሄር ድርጅቶች ባንድ ወገን ሆነው ህገ መንግስቱ ይቀየር ይላሉ ሌሎቹ የጎሳ ድርጅቶች አይቀየር ይላሉ።

እዚህ ላይ የማን ድምጽ ያሸንፋል (ማስተዋል ያለብን እንደዚህ አይነት የሀገር ግንበታ ድርድር ላይ 50%+1 አይነት ሳይሆን ቢያንስ 70% በላይ ያስፈልጋል ለዘላቂ ስምምነት)። ህገ መንግስቱ አይቀየር የሚሉት ያሸንፋሉ። ለምን?

በአንድ ወገን ያሉት የአማራ እና የህብረ ብሄር ድርጅቶች ድምራቸው ደካማ ነው የሚሆነው። ለምን ብትሉ የአማራ ድርጅት በመፈጠሩ የተነሳው ክርክር እና ጥል የዚህ ወገንን አቅም (capacity) በታላቅ ደረጃ ይመነምናል። ይህንን በመላው አማራ እና መላው ኢትዮጵያ ክርክር ጊዜ አይተነዋል። አሁንም ለተወሰነ ዓመት በአማራ ብሄርተኝነት የሚያራምዱ እና በግንቦት 7 መካከል አይተነዋል። የታወቀ ነገር ነው ጉዳዩ ከፋፋይ ነው ቂም እና ቁስል ትቶ ነው የሚሄደው። ሁለቱ ድርጅቶች ሁለት ከሚሆኑ አንድ ቢሆኑ እጅግ ይበልጥ ተንካራ ይሆናሉ። ግን ለብቻ ሆነው አንድ አቋም ቢኖራቸውም ህገ መንግስቱን ለማስቀየር በቂ አቅም አይኖራቸውም። ህገ መንግስቱን ለመቀየር ግብ አይመታም ማለት ነው።

በተቃራኒው አማራው እንዳለ በህብረ ብሄር ድርጅቱ ስር ቢገባ ይህ ጎጂ ህዝብ ከፖለቲካእና ከመሳተፍ የሚያርቅ ክርክር ይቀራል። ለዚህ ውጤት ማስራጃ እንደ ናሙና ምርጫ 97ን መመልከት ይቻላል። እውነት ነው ረዝም ዓመት በፊት ነበር ሁኔታዎችም ተቀይረዋል ግን ያለን ናሙና ይህ ነው። ህብረ ብሄራዊ ቅንጅት ምርጫውን ጠረገው። ከአማራ ክልል ውጭ በርካታ ድጋፍ አግኝቶ አሸነፈ። ይህ የሚያሳየው አማራው በህብረ ብሄራዊ መልክ ሲጠቃለል የህብረ ብሄራዊ ድርጅቱ አቅም ግዙፍ እንደሚሆን ነው። በቀላል ቋንቋ የአማራ ድርጅት ሲደመር የህብረ ብሄራዊ ድርጅት አቅሙ "2" ነው ካልን አንድ ላይ በአንድ ህብረ ብሄራዊ ድርጅት ስር ቢሆኑ የዚህ ትልቅ ድርጅት አቅም "3" ነው የሚሆነው። እና ይህ ግዚፍ ድርጅት በህገ መንግስት ድርድር ላይ ታላቅ ሚና መጫወት ይችላል ግቡን በቁጥር ሃይል ሊአስፈጽም ይችላል።

በአጭሩ ለሁለቱም ከዚህ ጽሁፍ የገለጽኳቸው የ«አብን» ግቦች አንድ የሆነ የሌሎች ብሄር ሰዎች የሚያጠቃልል በህብረ ብሄር በኢትዮጵያዊነት የተመሰረተ ድርጅት ይበልት ይመረጣል። ይህ ድርጅት በግዙፍነቱ እና ሁሉን አቀፍ በመሆኑ ምክንያት የአማራ መብትን ለማስከበርም ህገ መንግስቱን ለመቀየርም አቅሙ ይኖረዋል።

በተጨማሪ አንድ ነጥብ ላነሳ እወዳለሁ። ከላይ እንደጠቀስኩት አንዱ በአማራነት መደራጀት ጥቅሙ በጎሰኝነት ስሜት ምክነያት ተጨማሪ የአማራ ህዝብ ደጋፍ እና ተሳትፎ ለማግኘት ነው። በ«ኢትዮጵያዊነት» ከምንደራጀት በ«አማራነት» መደራጀት ከአማራ ህዝብ ይበልጥ ተሳትፎ እንደሚያመጣ እና የሚፈጠረውን ድርጅት ይበልጥ የሚያጠነክር ከሆነ የአማራ ህዝብ ለጎሳው ያለው ስሜት ለሀገሩ ካለው ስሜት ይበልጣል ማለት ነው! ወይንም በበቂ ቅስቀሳ እና ፕሮፓጋንዳ የአማራ ህዝብ ከኢትዮጵያዊነት ወደ ጎሰኝነት ስሜት እንዲያድል ማድረግ ይቻላል ማለት ነው። የአማራ ህዝብ እውነታ እንደዚህ ነው? አይመስለኝም። ምናልባት የተወሰነውን ይሳተፋል ሌላው በሚመጣው ጭቅጭቅ ምክነያት ወይንም በጎሳ አደረጃጀት ባለማመን ምክነያት ይቀራል አይሳተፍም።

ግን የህዝቡ ጎሰኝነት ስሜቱ አይሎ ጠንክሮ «አብን» ይጠነክራል እንበል። ይህ ድርጅት በስመ አማራ ተደራጅቶ በአማሮች ድጋፍ አግኝቶ ጠንክሮ እንዴት ነው ህገ መንግስቱ እንዲቀየር መታገል የሚችለው? የጎሳ አስተዳደር ጠፋ ማለት አብን ይጠፋል ነው። ድርጅት እራሱን አያጠፋም። ያቋቋሙት ሰዎች የህገ መንግስቱ መቀየርን ቢፈልጉም እንዴት አንድ ፓሪቲ ህልውናውን አውቆ ያጠፋል? ድርጅቱ አንዴ ከተቋቋመ እና መዋቅር ከሆነ በኋላ እራሱን ለማዘጋት ዝግጁ አይሆንም። በሌላ ቋንቋ አብን እንደዚህ ይላል፤ «የጎሳ ችግር የጎሳ አስተዳደር ነው እንድፈጠር ያደረገኝ፤ የጎሳ አስተዳደር ከጠፋ እኔም እጠፋለሁ፤ ስለዚህ ህገ መንግስቱ እንዳለ ይቀጥል!»

ለዚህ ነው እንደ አብን አይነቱ የጎሳ ወይንም የብሄር ድርጅት ማቋቋም እና የጎሳ አስተዳደር ይቅር ማለት ተቃራኒ ጉዳዮች የሚመስሉት። አብን የተቁቁመው ጎሰኝነት ስላለ ይህ ጎሰኝነት አማራን ስላጠቃ ነው። የአብን «ቤንዚን» ወይንም ኃይል ለጎሳው የተቆረቆረ አማራ ነው። አብን ከህብረ ብሄራዊ ድርጅት ይሻላል የተባለው ይህ የአማራ ተቆርቋሪ በህብረ ብሄራዊ መንገድ ከሚታገል በስመ አማራ ቢታገል ይሻለዋል ተሳትፎውን ይጨምራል ተባሎ ነው። ስለዚህ ጎሰኝነቱ በአማራውም አድሯል ማለት ነው። እንዴት አብን ይህ በንዚኑ ይቅር ይላል። አይለም። የጎሳ አስተዳደሩ ቢቀጥል ነው የሚጠቀመው። ይህ ነው «ፓራዶክሱ»።

Friday 8 June 2018

ሃይማኖታዊዋ ትግራይ እንዴት በፀረ ሃይማኖት ፓርቲ ትመራለች?

የትግዳይ ህዝብ ረዥም ታሪክ እንዳለው ወግ እና ትውፊቱን እንደሚወድ እንደሚአከብር ይታወቃል። ለምሳሌ ሃይማኖቶቻቸውን የሚአስቀድሙ እንደሚአጠብቁ ይነገራል ይታያል። በክብረ በአልም በዘውትር ጊዜም አክሱምን የጎበኘ ክርስቲያን ይህንን ሊመሰክር ይችላል። የህዝቡ አምልኮት ልዩ እና ጠንካራ መሆኑ ይታያል።

ታድያ እንደዚህ አይነቱ ህዝብ እንዴትቢሆን ነው በ ፀረ ሃይማኖት የሆነ የፖለቲካ ኃይል የሚገዛው እንዴት ይህን ኃይል ለዓመታት ከሌሎች ለይቶ ይደግፋል የሚለው ጥያቄ እንዴት ነው የማይጠየቀው። ፀረ ሃይማኖት ስል ከህወሓት አባላት መካከላማኞች የሉም ማለቴ ሳይሆን ግን የፓርቲው ርዕዮት ዓለም ፀረ ሃይማኖት መሆኑ ግልጽ ነው። አጀማመሩም እንደዚሁ ነው ዛሬም እንደዚህ ነው። አንድቀላል ምሳሌ ስለ ጎሰኝነት ያላቸው አመለካከት ቀትታ ከማርክሲዝም የመጣ ነው። የ «ጨቋኝ ተጨቋኝ» አመለካከታቸውም እንደዚሁም። እነዚህ «ከ ሃይማኖት ነፃ» የሆኑ አመለካከቶች ሳይሆኑ ፀረሃይማኖት ፀረ ትውፊት ናቸው።

እርግጥ ሃይማኖታዊ ትውፊት አክባሪ የሆነ ህብረተሰብ እንዴት በፀረ ሃይማኖት ወይም ሃይማ ኦት የለሽ ገዥ መደብ ወይም ልሂቃን ይመራል የሚለው ጥያቄ ትግራይን ብቻ ሳይሆን መላ ኢትዮጵያን ይመለከታል። ከኦርቶዶክስ ክርስቲያን አንፃር መልሱ ቀላል ነው፤ የህዝቡ የኛ ሐጢአት ነው ምክንያቱ። በጾቪዬት እስር ቤት የተሰቃዩት አለክሻንደር ሶልዠኒትሲን ከእስር ቤት ሆነው የጻፉትን እንደገና ልጥቀስ
ከእስርቤታችን አልጋ የሆነው የበሰበሰው ገለባ ላይ ጋደም ብዬ ነው ለመጀመርያ ከውስጤ የበጎ መንፈስ የተሰማኝ። ቀስ በቀስ መረዳት የጀመርኩት ይህ ነው፤ ጥሩና ክፉን የሚለየው መስመር በሀገሮች፤ መደቦች፤ የፖለቲካ ፓርቲዎችም መካከል አይደለም የሚያልፈው፤ ይህ መስመር የሚያልፈው በያንዳንዱ የሰው ልብ መኻል ነው። መስመሩእድሜአችን በሙሉ ከውስጣችን ወደፊት ወደኋላ ይላል። በክፉ የተሞሉ ልቦችም ቢያንስ ቅንጣት ያህል ጥሩነት ይኖራል፤ ከሁሉም ጥሩ ከሚባለውም ልብ ከአንድ ጥጓ ትንሽ ክፉነት ይኖራል።
በየቦታው እየዞሩ ያሉ ክፉ ስራ የሚሰሩ ክፉ ሰዎች ቢኖሩና እነሱን ከኛ መለየትና ማጥፋት ብቻ ቢሆን ኖሮ እንዴት ቀላል ነበር? ግን ጥሩና ክፉን የሚለየው መስመር ከያንዳንዱ የሰው ልጅ ልብ መካከል ነው የሚያልፈውና ማን አለ ከራሱ ልብ ቁራጭ ቆርጦ ለማጥፋት ፈቃደኛ ይሆነ?
እያንዳንዶቻችን ልብ ውስጥ ያለው ክፋት ተጠራቅሞ ነው በመሪዎቻችን ላይ የሚታየው።

ሆኖም አሁን የህወሓት ስልጣን በሚገባው እየመነመነ ስለሆነ የትቭራይ ህዝብ ስለማንነታቸው ስለ ሃይማኖት እና ትውፊታቸው ስለ ፀረ ሃይማኖት መሪዎቻቸው እራሳቸውን ለመመርመር ጥሩ ጊዜ ይመስለኛል። የትግራይ ህዝብ በመጀመርያ ኮሙዩ ኢስት ነው ወይንም ሃይማኖተኛ። ልጎቹ ሃይማኖት የለሽ ገንዘብ እና ስልጣን አምላኪዎች ሆነው እንዲያድጉ ነው የሚፈልጉት? መሪዎቻቸው እየወደቈየተነሱምቢሆን ሃይማኖታዊ ቢሆኗይሻልም ወይ። ይህ ነው ወይም ካርል ማርክስ ወዘተ ነው የ ትግራይ ትውፊት? እነዚህን ጥያቄዎችን ለመጠየቅ ትክክለኛው ጊዜ ይመስለኛል።

እኔ በትክክሉ ይር ትግራይ ሰው ባልሆንም እንደ ኢትዮጵያዊነቴ ይበልጥ እንደ ኦርቶዶክስ ክርስቲያን መሆኔ ይህ ጉዳይ የ ኤርትራም ተመሳሳይ በማርክሲስት ሻብያ መገዛቱ ጉዳይ እጅግ ያሳዝነኛል። እነዚህ ቦታዎች ለክርስትናችን ቁልፍ ምናልባትም ምንጭ ቦታዎች ናቸው። እንዴት ሐጢአተኞች ብንሆን ነው ወደ ፀረ ሃይማኖታዊ አገዛዝ የሸጥናቸው። እግዚአብሔር ይቅር ይበለን።

Monday 4 June 2018

የዘመናዊነት ዕቅድ (The Modern Project)

ይህ ከቀሲስ/መምህር ስቲፈን (እስቲፋኖስ) ፍሪማን ጽሁፍ (https://blogs.ancientfaith.com/glory2godforallthings/2014/01/10/the-modern-project/) በሰፊው የተረጎምኩት ነው። ቀሲስ ስቲፈን አሜሪካዊ (ምስራቃዊ ወይም ቃልቄዶናዊ) ኦርቶዶክስ ቄስ ናቸው። ከፕሮቴስታንትነት ወደ ኦርቶዶክስ እምነት «ከተመለሱት» በርካታ አሜሪካዊ ካህናት መካከል ናቸው። አሜሪካዊ በመሆናቸው ብቻ ሳይሆን በቀለም ትምሕርት እና በሃይማኖት ታሪካቸው ምክንያት ስለ በዘመናችን የነገሰው ዘመናዊነት ፍልስፍና በደምብ ያውቃሉ ለክርስትና ዋና ጠላት መሆኑንም ይገነዘባሉ። ሆኖም የዘመናዊነት ፍልስፍና የነገሰ ስለሆነ ሳናውቀው ሁላችንም በተወሰነ ደገጃ እንደተቀበልነው ያውቃሉ። ሰለዚህም ነው ቀሲስ ስቲፈን በዚህ ጉዳይ ዙርያ ብዙ የሚጽፉት። ጽሁፋቸው ለሁላችንም ገላጭ እና አስተማሪ ነው ብዬ አምናለው። ብሎጋቸውን ብታነቡ እጅግ ጠቃሚ ይሆናችኋል ብዬ አምናለው።

ሁለተኛ ዲግሪዬን በ«ቴኦሎጂ» በምማርበት ወቅት (1970 ዎቹ) «የዘመናዊነት ዕቅድ» ('the project of modernity') የውይይት ርዕስ የነበረበት ጊዜ ነበር። ይህ የዘመናዊነት ዕቅድ «ዘመናዊውን» ዓለም ('the modern world') ለመገንባት የሚሰሩትን ማህበራዊ፤ ፍልስፍናዊ፤ ፖለቲካዊ እና ሃይማኖታዊ ስራዎችን ያካትታል። በ17ኛ ክፍለ ዘመን የመነጨው «የብርሃን መብራት» ('the Enlightenment') ፍልስፍና አዲስ የአስተሳሰብ አይነቶች ወደ ምዕራባዊው ዓለም (ከዛ ቀጥሎ ወደ መላው ዓለም) አመጣ። ለምሳሌ ለ«ሀገር» የምንለው ፅንሰ ሃሳብ አዲስ ትርጉም እና አወቃቀር ፈጠረ። የክርስትና ሃይማኖትን በአዲስ መልክ ፈጠረ (ለምሳሌ ፕሮቴስታንትነት)። ከሁሉም በላይ ግን የሰው ልጅ ማንነትን ሌላ ትርጉም ሰጠው።

እኛ የዚህ ዘመን ሰዎች የዚህ ፍልስፍና ወራሾች ነን። የዘመናዊነት እና የዘመናዊነት ዕቅድ ልጆች ነን። ዛሬ ማንም ትምህርት የሌለውም ሰው «የዘመናዊነት ዕቅድ» ያመጣውን አስተሳሰቦችን ሳያውቀውም ቢሆን አድሮበታል አምኖበታልም። በትምህርት ቤትም በሚዲያም በሌሎች መንገዶች አስተሳሰቡን ወርሰነዋል። እኛ «የዘመናዊነት ዕቅዱ» ውጤቶቹ ሆነናል።

ዘመናዊነት ዕቅዱ የሰው ልጅን ማንነት ሲደነግግ እንደዚህ ይላል፤ « የሰው ልጅ በራሱ ብቻ የሚተዳደር ነፍስ ነው፤ ውሳኔዎቹ እና ስራው ብቻ ነው ማንነቱን የሚወስን»። ይህ ማለት፤

1. በራሱ ብቻ የሚተዳደር ነፍስ፤ የሰው ልጅ የማንነቱ መሰረት በማወቅ እና ማሰብ ችሎታው የተወሰነ ነው። «የማሰብ እና ማወቅ ችሎታዬ ብቻ ነው የሰው ልጅ የሚአደርገኝ»። ከዚህ ቀጥሎ በፈቃዴ ከሌሎች ጋር መጋራት እችላለሁ ግን ማንነቴ በራሴ ብቻ ነው የሚወስነው። ከሌሎች ጋር ያለኝን ግንኙነትም እኔ ብቻ ነው የምወስነው። ይህ ነው በዘመናዊው ዓለም የምናየው የ«ግለኝነት» አኗኗር መሰረታዊ ሃሳብ።

2. ውሳኔዎቻችን እና ስራዎቻችን ማንነታችንን እና የህይወት ጉዞዋችንን ይወስናሉ፤ በዚህ ዓለም ያለኝ የማንነት ምደባ የራሴ አመራረጥ፤ ውሳኔዎች እና ያሳለፍኩት ልምዶች ናቸው የሚወስኑት። ውሳኔዎቼ ማንነቴን ይወስናሉ እና መሆን የምፈልገውን መሆን እንድችል ብቸኛ ሚና ይጫወታሉ። የኔ ምርጫ እና ውሳኔዎች ናቸው የህይወቴን ትርጉም እና ማን መሆን እንደምፈልግ የሚወስኑት።

እነዚህን ፅንሰ ሃሳቦች ካሰላሰልናቸው የዘመናችን ታሪክን ወሳኝ ነገር «ነፃነት» ለምን እንደሆነ በቀላሉ እንረዳለን። (ይህ «ነፃነት» የሚባለው የመወሰን እና የመምረጥ «መብት» ነው እንጂ እውነተኛው ነፃነት አይደለም።) የሰው ልጅ ማንነት ትርጉም ከላይ የተጻፈው ከሆነ ይህ «ነፃነት» የግድ ይሆናል። ይህን ነፃነት የሚገድብ ሁሉ የሰው ልጅ ህልውና እና ፍላጎት ጠላት ይሆናል። እንደ ፈለግኩኝ መምረጥ መወሰን ስችል ነው ፍላጎቴን ማምዋላት የምችል ሰው መሆን የምችለው።

ከላይ እንደጠቀስኩት ባሁኑ ዘመን እነዚህ አይነት አስተሳሰቦች ሳናውቀው ሰርቀው አዕምሮአችን ውስጥ ገብተዋል። ዓለም ዙርያ ታውቀዋል። እንደ «ነፃነት» እና «ምርጫ» አይነቶቹ ቃላቶት ምን ማለት እንደሆኑ ብዙሃኑ ተውሕዶታል። እነዚህን ቃላቶችን ስንጠቀም ሁሉም ሰው ትርጉማቸውን «ያውቃል»።

አንዳንድ የክርስቲያን ቡድኖች በተለይም የፕሮቴስታንት ንቅናቄ ይህን አስተሳሰብ አቀናብረው አንጸራጭተውታል። እነዚህ የክርስቲያን ቡድኖች ከአሜሪካ እና አውሮፓ ተነስተው የ«ዘመናዊ» ክርስትና ዓለም ዙርያ አስፋፍተዋል። በጥናታዊ ክርስትና ያልነበሩ አስተያየቶች እና ጥያቂዎችን አስፋፍተው የተለመዱ እንዲሆኑ አደረጉ። ለምሳሌ የህፃንነት ጥምቀት ጥያቄ፤ ዛሬ ሰው ለምን በህፃንነቱ ክርስትና ይነሳል የሚለው ጥያቄ ይጠየቃል። ልበ በሉ ለመጀመርያዎቹ ፕሮቴስታንቶች ይህ ጥያቄ አልነበረም ግን የተከሉት ዘር ወደዚህ አመራ። ጥያቄ የሆነው ምክነያት የህጻንነት ጥምቀት «ነፃነትን» ይሽራል ተብሎ ነው! «ህፃኑ እንዴት አለ «ምርጫው» ይጠመቃል። ለመጠመቅ ላለመጠመቅ ነፃነቱ ሊኖረው አይገባምን?» ይባላል! በዘመናዊነቱ ዕቅድ ምርጫን ወይም የራስ ውሳኔን የሚገድብ ነገር አደገኛ ነው ተብሎ ይሰየማል። በየ «ኤቫንጀሊካል» ፖሮቴስታንት ቤተ ክርስቲያን ክርስቲያን መሆን የ«ነፃ ምርጫ» ጉዳይ ነው ይባላል። «የውሳኔው ስዓት» ሰዎች ክርስቶርስን ጠቀብያለሁ የሚሉበት ጊዜ በዘመናችን ተለምዷል።

ቤተ ክርስቲያን ስለ ገብረ ግብ የምታስተምረውም በዘመናዊነት ዕቅዱ ምክንያት በጥርጣሬ ላይ ወድቋል። ዘመናዊ ሰዎች እራሳቸውን «ካቶሊክ»፤ «ኦርቶዶክስ»፤ «ጴንጤቆስጣል»፤ «ፕሬስቢቴሪያን» ወዘተ ብሎ ቢሰይምም ቤተ ክርስቲያናቸው ስለ ግብረ ገብ ወይም ስነ መግባር ኑሮዋቸው መወሰን የለባትም ብለው ያምናሉ። እራሳቸውን «ካቶሊክ» ብለው ቢሰይሙም በካቶሊክ እምነት አይገዙም። ለምሳሌ አብዛኞች አሜሪካዊ ካቶሊኮች ቤተ ክርስቲያናቸው በተለይ ስለ ቤተሰብ እና ጋብቻ የምታስተምረውን ሌሎችም ትምህርቶቿንም ይክዳሉ! ከቤተ ክርስቲያናቸው እምነቶች የሚፈልጉትን ይመርጣሉ የግል ምርጫዬ ነው የነፃነት ጉዳይ ነው ብለው ያምናሉ። ግን ይህ «የግል ሃይማኖታቸውን» በራሳቸው «ነፃነት» እና ምርጫ «ካቶሊክ» ብለው ይሰይማሉ። በዚህ አስተሳሰብ «ካቶሊክ»፤ «ኦርቶዶክስ»፤ «ሉቴራን» ወዘተ ሰው የሚመርጠው ማንነት ነው እንጂ ማንነትን እና ህይወትን የሚወስን ጉባኤ አይደለም።

የዘመናዊነት ዕቅዱ የጥንታዊ ክርስትና ጠላት ነው።

በጥንታዊ አመለካከት የሰው ልጅ ለራሱ ብቸኛ ወሳኝ አይደለም። በዚህ ዓለም የምንገኘው ከራሳችን ሌላ በሆነው በእግዚአብሔር ፈቃድ ነው። ህይወታችን የእግዚአብሔር ስጦታ ነው። የህይወታችን አላማው፤ ትርጉሙ እና አቅጣጫው በእግዚአብሔር የተሰጠ ነው። የሰው ልጅ የሚያደርገን እና ዋጋ የሚሰጠን በእግዚአብሔር ምሳሌ መፈጠራችን ነው እንጂ ውሳኔዎቻችን ወይም የመወሰን አቅም ስላለን አይደለም። የሁላችንም ታናሾች አቅም የሌላቸው፤ ችሎታ የሌላቸው፤ ከአልጋ ተኝተው መንቀሳቀስ የማይችሉት፤ ወዘተ በኢግዚአብሔር ምሳሌ በመፈጠራቸው ክብር እና ዋጋ አላቸው።

ማንነታችን በህይወት ምርጫዎቻችን እና ውሳኔዎቻችን ብቻ አይደለም የሚወሰነው። ህይወታችን እና ማንነታችን ከእግዚአብሔር ያገኘነው ስጦታ ነው። እሰረታዊ ማንነታችን በተወሰነ ደረጃ የተመደበ ነው። ይህ ማንነት በክርስትና ህይወት የሚገለጽ እና የሚለወት ነው እንጂ አንድ ሰው በግሉ የሚፈጥረው አይደለም። ምርጫዎቻችን እና ውሳኔዎቻችን ሚና ይጫወታሉ ግን ከእግዚአብሔር ውሳኔ ስር ነው ሚናቸው። ዞሮ ዞሮ የእግዚአብሔር ፍጥረቶች ነን ስለዚህ ውሳኔዎቻችን ትርጉም ያላቸው ከሱ ጋር ባለን ግንኝነት ነው።

በዘመናዊነት ዕቅዱ እና በጥንታዊው አመለካከት ያለው ጦርነት በደምብ የሚታየው በተለይም በምዕራቡ ዓለም በስነ ህይወት (biology) እና የሰው ግንኝነት ዙርያ። ጥንታዊ የክርስትና አመለካከት ስነ ህይወታችን፤ ማለትም ሰውነትና አካላችን ወዘተ፤ የተሰጠን ነው። እንደ አባት፤ እናት፤ ወንድም፤ እህት ወዘተ ያለን ከሰው ጋር ያለን ግንኙነቶችም የተሰጡን ናቸው። ጾታ ምርጫ አይደለም። ቤተሰብም የደም ተፈጥሮ ነው እንጂ በምርጫ አይደለም። በባለና ሚስት መካከል ወይም ሌሎች ወሰባዊ ግንኙነቶች የተሰጠ አላማ አላቸው እንጂ የግል ፍላጎት ማምዋያ አይደሉም። ግን የዘመናዊነት ዕቅዱ «ነፃነትን» እና «ምርጫን» እንዲሰፍኑ ማድረግ ነው የሚፈልገው። የሰው ተፈጥሮ እውነት ነው ግን ወሳኝ አይደለም ይላል (ለዚህም ነው ዛሬ አንዳንዶች ጾታቸውን የሚመርጡት)። ቤተሰብ የምርጫ ጉዳይ ነው የምንፈልገውን ግንኙነቶችን እንመርጣለን። የደም ትሥሥር የተሰጠ መሆኑ እና በደም ትሥሥር ምክንያት ሃላፊነቶች መኖራቸው በምዕራባዊ ሀገራት መንግስታት እና ፍርድ ቤቶች እየተካደ ነው። ለዚህም ነው በእግዚአብሔር ፈቃድ የተጸነሰው ከ«ነፃነት» ጋር መወዳደር ያልቻለው እና ጽንስን ማስወረድ የሰፈነው።

ዛሬ «እውነት» የሚባለው ነገር አሻሚ ሆኗል። የኔ እውነት ካንተ እውነት ይለያል ግን ሁለቱም እውነቶች ናቸው ይባላል። እውነትም የምርጫ ጉዳይ ሆኗል። አንድ የሆነ እውነት የለም ይባላል። በዚህ ዘመናዊ ዓለም እውነት አንድ ነው ማለት እንደ ጭቆና ነው የሚቆጠረው። የጥንታዊ ክርስትና አስተያየት ከነ ህግ እና እምነቱ የማይመች እና መጥፋት ያለበት ሆኖ ነው የሚታየው። ዘመናዊው ዕቅድ «ለምን እግዚአብሔርንም በራሳችን ምርጫ በራሳችን ምናብ አንፈጥረውም አንወስነውም» ይለናል።

መጨረሻው

ከመጀመርያ ጀምሮ ለ400 ዓመታት በላይ የዘመናዊው ዕቅድ የጥንታዊ ክርስትናን ተዋግቶ ከሰው ልጅ ከህዝብ ማስወገድ ነው አላማው። የዘመናዊነት ጥያቄ «እግዚአብሔር እንዴት ነው የፈጠረን» ሳይሆን «ዓለምን ምን እንዲመስል ነው የምንፈልገው?» ነው። የዓለም ሁኔታ የሰው ምርጫ ጉዳይ ነው ብሎ ነው የሚያምነው። ስለዚህ ነው የዘመናዊ ዕቅዱ ልጅ የሆነው የፕሮቴስታንት ስነ መለኮት (ቴኦሎጂ) የክርስትናን ትውፊት እና ወግን ከመመርመር እና ማጥናት ይልቅ ወንጌልን በራሱ ምናብ መተርጎም የፈለገው።

ማርቲን ሉተር «በመጻሐፍት ብቻ» ('Sola Scriptura') የሚባለው የፕሮቴስታንት አቋምን ሲፈጥር ማንም ሰው መጸሀፍ ቅዱስን አንብቦ አለ እርዳታ አለ ቤተ ክርስቲያን አለ ሃዋርያት በትክክሉ ይተረጉመዋል ለማለት ነው። ማርቲን ሉተር የሮሜ ጳጳስን ወይም የሮሜ ቤተ ክርስቲያን ችግሮችን በመቃወም ስበብ ክርስትናን በራሱ ውሳኔ እና ምርጫ መቅረስ ፈለገ። በዝህ መልክ ይህ «በመጸሐፍት ብቻ» የሚባለው አስተያየት በመጀመርያ ቤተ ክርስቲያንን እና ትውፊቷን ለመለየት የተጠቀሙበት መሳርያ ነበር። ግን ባልታሰበበት (ግን ሊታሰብበት) መልክ ይህ አስተሳሰብ ሰዎች መጸሀፍ ቅዱስን በግላቸው እንተርጉም እያሉ ከአንድ ከሉተር ከሁለት የሉተር ተፎካካሪ ዝዊንግሊ ወደ 30 ሺ አተረጓገም (ዛሬ ዓለም ዙርያ ያሉት የፕሮቴስታንት ቡድኖች ቁጥር) ደርሷል።

ግን «የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም» እና ዛሬም የጥንታዊ ክርስትና አለች የዘመናዊነቱን ዕቅድን የስጋው መውግያ ናት። የዘመኑ ሚዲያ ቫቲካንን አትኩረው ያያሉ ገና ለገና መሰረቷን ሸርሽራ ትጨርሳለች እጇን ሙሉ በሙሉ ለዘመናዊነቱን ዕቅድ ትሰጣለች ብለው። በሩስያ ከሞት የተነሳችው ኦርቶዶክስ እምነት ደግሞ ከፖለቲካዊ «አምባገነን» ጋር የተያያዘ እና «ኋላ ቀር» ብለው ይሰይሙታል! ጦርነት ነው!

ዛሬ የጥንታዊ ክርስትና መንገድ ከባድ ነው። አታላዩ መንገድ ዝም ብሎ ጸረ የዘመናዊው አብዮት መሆን ነው። ከዘመናዊነት ዕቅዱ እኩል እንደ አማራጭ መወዳደር። ግን ክርስትና እንዳዚህ ካረገች እጇን ለዘመናዊው ዕቅድ ሰጠች ማለት ነው። ሌላ «ምርጫ» ሆነች ማለት ነው። ግን ጥንታዊ ክርስትና የምርቻዎቻን ውጤቶች አይደለንም ህይወቶቻችን በእግዚአብሔር ጸጋ እና ስጦታ ነው የሚወሰነው ሁሉም ነገር ከእግዚአብሔር አኳያ ነው የምንመለከተው ነው። የቤተ ክርስቲያን ተውፊት የለ የተሰጠ ነገር ነው እንጂ ምርጫ አይደለም። ስለዚህ እራሱን እንደ አንድ አማራጭ አያቀርብም ሊያቀርብም አይችልም።

የጥንትዊ ክርስትና መንፈስ ስለ በራስ መምርጥ ሳይሆን እራስን ባዶ ማድረግ። ማለት የራስን ፍላጎት ትቶ የእግዚአብሔርን ፍላጎት ማወቅ እና ማክበር። እጅን ለእግዚአብሔር ሙሉ በሙሉ መስጠት። ጥንታዊ ክርስትና ህይወት የተሰጠ እንደሆነ ይረዳል። የተፈጥሮ የደም ትሥሥር፤ ቤተ ሰብ እና ዝምድና ተጭባጭ ናቸው እና ህይወታችን ላይ ተገቢ ሚና ይጫወታሉ ሃላፊነት ይሰጡናል። ዓለም እንደዚህ ትሁን እንደዛ ትሁን ብለን ማለም ከለት ለለት ከባድ የሆነ የክርስትና ኑሮአችን እንድንርቅ እንድንሰንፍ ፈተና ነው። የዓለም ድሃ ይረዳ እያልኩኝ እየተፈላሰፍኩኝ ድሃ ባለንጀራዬን ዞር ብዬ አላየውም! ግን የዘመናዊነት ዕቅድ እንደዚህ ነው የሚያስበው። ዓለምን አሻሽላለው ይላል። ከ«ነፃነት» በደምብ ማትረፍ የሚችሉትን ባለ ሃብቶች እና በትምሐርት ጎበዞች በደምብ አትርፈዋል። ግን ይህ የዘመናዊነት ዕቅድ ፉከራ ባዶ ነው ህይወታችንን በራሳችን መወሰን ስለማንችል። እራሳችንን ከእውነታችን በላይ ታላቅ አርገን ብናስብም መጨረሻ ላይ ሞት ምርጫችንን አያከብርም! ምናልባትም የዛሬው ታላቅ አሽሙር የዘመናዊነት ዕቅዱ የ«መሞት መብት»ን ማራመዱ ነው አለመሞት ምርጫ እንደሆነ!