Friday 30 November 2018

የውጭ ሀገር ዜግነት ያለው ኢትዮጵያዊ ለፖለቲካ ስልጣን መወዳደር መቻል የለበትም


ከዚህ የኢሳት እለታዊ ውይይት የጥምር ዜግነት እና የውጭ ሀገር ዜግነት ያላቸው ኢትዮጵያዊ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ተሳታፊነት ጉዳይ ተነስቶ ነበር።

እኔ ከሲሳይ አጌና ሃሳብ ጋር እስማማለሁ። ጉዳዩ በመሰረቱ የሉዓላዊነት (sovereignty)፤ ተጠያቂነት (accountability) እና የባለ ድርሻ (stakeholder) ነው። አሜሪካዊ እና ኢትዮጵያዊ የሆነ ሰው ለሁለቱም ሀገራት ተጠሪነት እና ተጠያቂነት አለው። የሁለቱንም ሀገራት ሉዓላዊነት የመጠበቅ ግዴታ አለበት። የሁለቱም ሀገራት ባለ ድርሻ ነው። ስለዚህ የሁለቱ ሀገራት ጥቅም፤ ሉዓላዊነት፤ «ፍላጎት»፤ የሚለያዩ ወይንም የሚቃረኑ ከሆነ ይህ አሜሪካዊ እና ኢትዮጵያዊ የሆነ ሰው ከራሳቸው ጋር ይጣላል። የየትኛውን ሀገር ሉዓላዊነት ይጠብቅ? አልፎ ተርፎ ይህ ሰው ከአሜሪካ ንብረት እና ቤተሰብ ካለው ይህን ከራስ መጣላቱን ያብሰዋል። ስለዚህ ነው የፖለቲካ መሪነት እና የመምረጥ መብት ሊኖረው አይገባም የሚባለው። አንድ ሰው የአንድ ሀገር ሉዓላዊነት ብቻ ነው (በዛሬው ዓለም) መጠበቅ የሚችለው።

ልሰ ተሳትፎ አወራን ግን የገንዘቡ ጉዳይስ? ማለትም የዲያስፖራ ኢትዮጵያዊዎች ነገ ለግንቦት ሰባት ወይንም ለኦፌኮ 10 ሚሊዮን ዶላር ሰብስበው ቢሰጡ በሀገር ሉዓላዊነት ምን ሚና ይጫወታል። በእርጥ ሉዓላዊነትን ይቀንሳል። በዚህ ምክንያት መከልከል አለበት። አብዛኞች ሀገራት የፖለቲካ ፓርቲዎች ከውጭ ሀገራት ገንዘብ ማግኘት አይችሉም የሚል ህገጋት አላቸው። ግን እንደሚታወቀው ገንዘብ፤ እንዳ ውሃ፤ መንገድ አያጣም። በሌላ ድርጅት ወይንም ንግድ ገብቶ ከዛ ያ ኢትዮጵያዊ ድርጅት ወይንም ንግድ ለፖለቲካ ፓርቲ ገንዘቡን ይለግሳል። ሆኖም መከልከሉ አሁንም አስፈላጊ ነው። ቢያንስ ግድብ ይሆናል። በፖለቲካችን ያለው የውጭ ሀገር ሚናን ይቀንሳል (minimize ያደርጋል)።

ጉዳዩን በአጭሩ እንዲህ ነው የማየው። እንደ ድሮ የዛሬውም ዓለም በሀገራት ታላቅ የአቅም ልዩነት አለ። የሀገራችንን ፖለቲካ ለውጭ ሀገር ገንዘብ እና ተሳትፎ ክፍት ካረግን በቀላሉ እንዋጣለን። የዜጎቻችን ጥቅም ከሚከበር ይልቅ የውጭ ሀገር ዜጎች፤ ድርጅቶች፤ ኩባኒያኦች እና መንግስቶች ጥቅም የሚከበርበት ፖለቲካ ይኖረናል። ሉዓላዊነታችንን አጣን ማለት ነው። ዜጎቻችን ሀገር አልባ ሆኑ ማለት ነው። ይህ እንዳይሆን በሚገባው ደረጃ አጥር እና ግድብ ማብጀት ግድ ነው።

No comments:

Post a Comment

ለሀሳብዎ አመሰግናለሁ!