Monday 14 January 2019

ስለ ራያ ማንነት ውይይት፤ ዳር ዳሩን ከማለት ወደ ቁምነገሩ ካልገባን ችግሮችን አንፈታም


ይህን ስለ ራያ ማንነት ጉዳይ ቃለ ምልልስ ስመለከት ጠያቂውም እንግዶቹም ስለ ህግ አፈጻጸም እና ሂደታዊ (procedural) ጉዳዮች ከዓንድ ሰዓት በላይ ተወያይተው ዋናው መሰረታዊ የሆነው ጉዳይ ላይ ምናልባት 10 ደኪካ ነው ያዋሉት። «በግልጽ እንነጋገር ከተባለ…» ማለቱ ለምን ያስፈልጋል፤ መጀመሪያኑ በግልጽ ስለ መሰረታዊ ጉዳዩ መነጋገር ነው።

በግጭት መፍታት (conflict resolution) መሰረታዊ ችግር እንዳለ መገንዘብ፤ ከዛ ችግሩን ማወቅ፤ ከዛ ችግሩን ለመፍታት መስራት አብዛኛው ጊዜ የግድ የሆነ አስፈላጊ ሂደት ነው። አለበለዛ የችግሮቹ ውጤቶች ላይ እየተተኮረ እሳት እየተለኮሳ እሳት እያጠፋን እንቀጥላለን። መሰረታዊ ችግሩ እየተባባሰ ይሄዳል። እርግጥ የግጭቱ አካሎች ስለ መሰረታዊ ጉዳዩ ማውራት ማሰብም አይወዱ ይሆናል ግን አማራጭ የለም። ክስ ብሎ አለስልሶ ወደዛ መግባት ግድ ነውና።

የራያ መሰረታዊ ጉዳይ የራያ ማንንነት ኮሚቴ(ዎች) መቼ አመለከቱ ለማን አመለከቱ አይደለም። ይህ ሁለተኛ ጉዳይ ነው እና ብዙ የውይይት ጊዜ ሊፈጅ አይገባም። መሰረታዊ ችግር እና ጥያቄው እንደገባኝ ከሆነ እንዲህ ነው፤

1) እኛ ከትግሬ የተለየ የራያ ማንነት አለን እና አለፍላጎታችን በትግሬ ክልል ተካለልን፤
2) ሰባዊ መብታችን በትግራይ ክልላዊ መንግስት ለ27 ዓመት ትጥሷል እና ተጭቁነናል፤
3) መጀመሪያውኑ የጎሳ አስተዳደር ባይሆን ኖሮ ይህ የማንነት ጉዳያችን በዚህ መልኩ አይነሳም ኖሮ፤
4) አማራ ክልል ብንገባ መብታችን እና ሰላማችን ይከበራል እና የአምባገናን ትግራይ ክልልውስጥ መሆን አንፈልግም።

በርካታው የውይይቱ ጊዜ በነዚህ ጥያቄዎች ዙርያ መሆን ነበረበት ብዬ አስባለው። በዛሬው የፖለቲካ ሁኔታ ጥያቄዎቹ እጅግ ከባድ ናቸው እና ብዙ ውይይት ያስፈልጋቸዋል። ይህን ትቶ ስለ ደብዳቤ እና ግልባጭ ማውራት ትንሽ priority ማጣት ይመስለኛል።

No comments:

Post a Comment

ለሀሳብዎ አመሰግናለሁ!