Thursday 11 April 2019

የምኞት ፖለቲካ ሲቀጥል...

የኢሳት የኤላታዊ ተንታኞች ምኞጣጨው ጥሩ ነው፤ የጎሳ ጥላቻ በሀገራችን ያመጣው አደጋ እንዲቀረፍ ወደ ርዋንዳ መስመር ከመግባታችን በፊት። የባህል እና ቋንቋ ብዙሃነት ያለበት ግን የጎሳ አስተዳደር እና ፖለቲካ የሌለበት ሀገር ነው ምኞታቸው። ጥሩ ምኞት ነው፤ የኔም የብዙዎቻችን ነው።

ግን «ጠ/ሚ አቢይ፤ ጎሰኞቹን በአዋጅ አግታቸው፤ የመንግስት መዋቅርን በሹመት ተቆጣጠር፤ የክልል ጦሮችን በአዋጅ ህገ ወጥ አድርግ፤ ወዘተ» በማለት ይህ ምኞት ሊፈጸም አይችልም። የሀገራችን የፖለቲካ ነባራዊ ሁኔታ ይህን አይፈቅድም። የጎሳ ብሄርተኛ ጎራው የ«ፖለቲካ ኃይል» አለው። ይህ ጎራ የተዋቀረ እና የተቀነባበረ ኃይል፤ በመንግስት መዋቅሮች የተሰገሰገ ኃይል፤ የገንዘብ ኃይል፤ ወዘተ ኃይል አለው። ጠ/ሚ ዓቢይ የእለታዊ ተንታኞች የሰቡትን እርምጃዎች ልውሰድ ካለ የጎሳ ብሄርተኛው ጎራ ቀውስ ያስነሳል። ጠ/ሚ ዓቢይ እንደዚህ አይነት እርምጃዎች ከመውሰዳቸው በፊት በስልት እና ዘዴ የጎሳ ብሄርተኛውን ኃይል ማድከም አለበት። አለበለዛ ነባራዊ ሁኔታን የማይመጥን እርምጃ ይሆናል እና ሁኔታውን ያባብሳል።

የጎሳ ብሄርተኛ ጎራውን ከማድከም እና ማከፋፈል አልፎ ሌላ ዋና እርምጃ ያስፈልጋል፤ ይህ የ«መሃል ፖለቲካው» ወይንም የዜግነት ፖለቲካ ጎራው እጥፍ ድርብ መጠንከር አለበት። ይህ ጎራ መዋቅር፤ ቅንብር፤ የገንዘብ፤ የመንግስት መዋቅር ከውስጥ በኔትወርክ መአስር ኃይል ሊኖረው ይገባል። የዜግነት ፖለቲካ ጎራው እንደዚህ አይነት «የፖለቲካ ኃይል» ሲኖረው የጎሳ ፖለቲካን ለመቀነስ የሚወሰዱ እርምጃዎች ሲወሰዱ የጎሳ ብሄርተኞች የሚነሳውን ሁከቶች መቋቋም ይቻላል። የጠ/ሚ ዓቢይ መንግስት በጎሳ ብሄርተኞች ሲጫን የዜግነት ጎራው ይደፍገዋል። ቀደም ተከተሉ እንዲህ ነው መሆን ያለበት።

ግን አሁን የዜግነት ፖለቲካ ጎራው ገና በቂ አልተደራጀም። ለዚህ ነው የጠ/ሚ ዓቢይ መንግስት አሁንም ከባድ ሁኔታ ውስጥ ያለው። ለዚህ ነው «ከባድ እርምጃ ውሰድ» የሚለው ሃሳብ አጉል ምኞት የሆነው። መጀመርያ የዜግነት ፖለቲካ ጎራው ማለትም «መሃሉ» ጠንክሮ መገኝነት አለበት የጎሳ ብሄርተኞቹን ጫና ለመቋቋም።

ስለዚህ የእለታዊ ተንጣኞች በሙሉ ኃይላቸው ይህ የዜግነት ፖለቲካ ጎራ መደራጀት እና መጠንከር ዋና ተልዕኮአቸው ማድረግ አለባቸው። ለሀገራችን ሰላም ቀድመ ሁኔታ ነው። ማለት ይህ ካልሆነ ምንም አይነት የፖለቲካ መሻሻል ሊመጣ አይችልም።

No comments:

Post a Comment

ለሀሳብዎ አመሰግናለሁ!