Wednesday 14 September 2016

ከጎረቤቱ ጋር የተጣላ «ወያኔ» ነው!

2009/1/4 ዓ.ም. (2016/9/14)

የጎረቤታሞቾ ልጆች ይጣላሉ። አንዱ ሌላውን የትምህርት ቤት መጸሐፌን ሰረቀ ብሎ ይከሰዋል። ወሬው ወደ ወላጅ ጆሮ ይደርሳል። የተከሳሹ ቤተሰብ እንዴት ልጃቸው ልጃችንን ሌባ ይላል ብለው ጎረቤቶቻቸውን ይቀየማሉ። በዚህ ተነስቶ የሁለቱ ጎረቤታሞቾ ግንኙነት መበላሸት ይጀምራል። ሐሜትና ክስ መመላለስ ይጀምራሉ። በተዘዋዋሪም በቀጥታም መሰዳደብ ይጀምራሉ። አንዱ ሌላውን እንደ «ጠላት» ይቆጥራል። ጓደኞቻቸውም ይወግናሉ።

አብዮቱ ከነበልባል ወደ እሳት እየተፋፋመ ነው። አንዱ ቤተሰብ የጠላት ጎረቤታቸውን ልጅ ኢህአፓ ነው እያሉ ማስወራት ይጀምራሉ። ልጁ ታስሮ ይወሰዳል ይሰቃያል ይገደላልም። ታሪክ ልጁን የደርግ ሰለባ አድርጎ ይመዘግበዋል። እውነቱ ግን የጎረቤት ሰለባ መሆኑ ነው። ደርግ መሳርያ ብቻ ነበር።

በትምህርት ቤቱ ሰራተኞች መካከል ምንጩ የተረሳ የቆየ ጸብ አለ። ሰራተኞቹ ለሁለት ተከፍለዋል፤ ዋናው አስተዳዳሪው አንድ ወገን ይዟል፤ ምክትል አስተዳዳሪው ሌላውን ወገን ይዟል። ጦርነት አይደለም፤ ትምህርት ቤቱ ይሰራል ልጆቹም ይማራሉ። ግን ውስጥ ለውስጥ ችግር አለ፤ ትምህርት ቤቱ በሐሜትና ሹክሹክታ መንፈስ ተይዟል።

ኢህአዴግ ስልጣን በቅርብ ይዞ ለአብዮታዊ ዴሞክራሲ እንቅፋት ለሆኑትን «ነፍጠኖች» ከመንግስት ስራ እያባረረ ነው። ምክትል አስተዳዳሪው የሱ «ጠላት» ጎራ የሆኑትን በውሸት ትምክህተኞች ነፍጠኞች ብሎ ለመንግስት ይጠቁማቸዋል ከሰራም ይባረራሉ። ኢህአዴግ አባረራቸው ተብሎ ታሪክ የሚዘግበዋል። ግን ይህን ጉዳት ያደረሱባቸው ባልደረቦቻቸው ናቸው። ኢህአዴግ መሳርያ ብቻ ነበር።

ትምህርት አይሆነውም የሚባል ልጅ ከሰፈራችን አለ። ቤተሰቡም ዘመዶቹም ትምህርት ቤቱም ካህኑም አይረዱትምም አይረዱትም። ጭራሽ ይለቅፉታል ይሰድቡታል ይተቹታል። ልጁ እያደገ ሲሄድ ብሶትና ምሬት ያለው ከራሱ ጋር የተጣላ የዝቅተኝነት ስሜት ያለው ጎረምሳ ይሆናል።

ከምርጫ 97 በኋላ ሰላማዊ ሰልፎች እየተካሄዱ እያለ ፌዴራል ፖሊስ እየዞሩ ህዝብን እያሰሩ ነው። ይህንን ብሶት የተሞላው ልጅ ከሰፈርህ የሰልፉን አስተባባሪዎች የሆኑትን ጠቁምልን በቋሚነትም ጠቋሚያችን ሁንልን ብለው ይጠይቁታል። ልጁ ተስማምቶ በርካታ የሰፈር ልጆችን ይጠቁማል። እስረኞቹም ቤተሰቦቻቸውም ይሰቃያላኡ። የታሰሩት የተሰቃዩት ታሪክ ሲመዘገብ እንደ ኢህአዴግ ሰለቦች ይመዘግባቸዋል። ግን ጠቋሚው ባይጠቁማቸው ምንም አይደርስባቸውም ነበር። ልጁ አሁንም የሰፈሩ «ጠቋሚ» ትብሎ ይታወቃል።

ምርጫ 97 ሊደርስ አቅራብያ አቋማቸው ተመሳሳይ የሆኑት የተቃዋሚ ፓርቲዎች አንድ ግንባር ፈጥረው እራሳቸውን «ቅንጅት» ብለው ሰይመው ምርጫውን ይወዳደራሉ። አሸንፉም። መንግስት ግን አላሸነፋችሁም አመጽም ማስነሳት ሞክራችኋል ብሎ ያስራቸዋል። ከዓመት በላይ ታስረው ከእስር ቤት ሲወጡ ባመረረ የእርስ በርስ ጥል ይለከፋሉ። በጸባቸው ምክንያት የነፃነት ንቅናቄውንም እንዲፈርስ ያደርጋሉ። እርስ በርስ ቢጣሉም የነፃነት ትግሉን ብያከሽፉትም «ውያኔ» በድሎናል ብለው ያለቅሳሉ።

አምባገናናዊ መንግስት በካላሉ ካስቀመጥነው «አምባገነን» የሚባለው የአብዛኛው የህዝብ ድጋፍ ስለሌለው ነውና የራሱን ፍላጎት ህዝቡ ላይ ስለሚጭንባቸው ነው። አብዛኛውን ቢወክልማ ምን «አምባገነን» ያስብለዋል። ኢህአዴግ አምባገነናዊ ነው ካልን የትንሽ ሰው ቁጥር ድጋፍ ነው ያለው ማለት ነው። የትንሽ የሰው ቁጥር ድጋፍ ያለው መንግስት ደግሞ አብዛኛ የሆነውን ህብረተሰብ መግዛት የሚችለው ይህ ህዝብ እርስ በርስ ለመከፋፈልና ለመገዛት ፈቃደኛ ከሆነ ብቻ ነው! «ፈቃደኛ» የሚለውን ቃል የተጠቀምኩት አውቄ ነው። ምክንያቱም አንድ ህብረተሰብ «ተከፋፈል» ትብሎ መታዘዝ አይቻልም። እራሱ ነው ልከፋፈል ውይም አልከፋፈል ብሎ የሚወስነውና።

ይህ መከፋፈል ነው ኢህአዴግን እስካሁን በስልጣን ላይ ያቆየው። ስለዚህ የኢህአዴግ ኢትዮጵያን እስካሁን መግዛት ሃላፊነቱን መሸከም ያለበት በገዛው ፈቃድ የተከፋፈለው የአገሪቷ ህብረተሰቡ ነው። 

ከላይ ያስቀመጥኳቸው ምሳሌ ታሪኮች ይን ይገልጻሉ። እርስ በርስ ሲጣላ ሲጠላ ሲቃረን የዋለ ህዝብ እንዲህ ይላል «ለጎረቤቴ ወይም ለወንድሜ ያለኝ ጥላቻ ለአምባገነኑና ለአምባገነኑ ጭካኔ ካለኝ ጥላቻ ይበልጣል፤ አምበገነኑ ይግዛኝ!» ታድያ የፖለቲካ ችግር ምንጭና ሃላፊነት ዬት ነው? ከ«ዎያኔ» ነው ወይስ ከኛ ኢትዮጵያ ህዝብ ነው?። ከኛ እንደሆነ ግልጽ የሆነ ይመስለኛል። የችግሩ መንጭም እኛው ነን፤ ሃላፊነቱም የኛው ነው፤ መፍትሄውም ከኛው ነው።

የታወቁት የሶቪዬት (የሩሲያ) ጸሃፊ አሌክሳንደር ሶልዠኒትሲን ለረጅም ዓመታት በ«ጉላግ» ከሚባለው የሶቪዬት «የሞት» እስር ቤቶች በፖለቲካ ምክንያት ታስረው ነበር። የሶቪዬት የኮምዩኒስት አምባገነናዊ መንግስት እስከ 20 ሚሊዮን ሰዎች (ከ160 ሚሊዮን የህዝብ ቁጥር) ወደነዚህ የጉልበት ስራ የስቃይና የሞት እስርቤቶች ልኮ ነበር።

ሶልዠኒትሲን ጀግና የሆኑ ሀገራቸውን ያገለገሉ ወታደር ነበሩ። ቢሆንም መንግስቱና በተለይ ሹማምንቱን ወቀስክ ተብለው ታሰሩ። ከእስር ቤት ሆነው እንደማንኛውም የህሊና እስረኛ «ለምን ታስረርኩኝ» «ምን አይነት ጭካኞች ናቸው» የሚሉትን ሃሳቦች ያንሸራሽሩ ነበር። ግን ከእስር ቤት ሆነው ስለ እስራ ዘመናቸው ሲመዘግቡ ከታች የተጠቀሰውን ታላቅ ሃሳብ ተገለጸላቸው፤ በታወቀው «የጉላግ አርኪፔላጎ» መጸሃፍ ሳፉት (ትርጉም የኔ ነው)፤

ከእስርቤታችን አልጋ የሆነው የበሰበሰው ገለባ ላይ ጋደም ብዬ ነው ለመጀመርያ ከውስጤ የበጎ መንፈስ የተሰማኝ። እውነቱን ቀስ በቀስ እንደዚህ እንደሆነ መረዳት ጀመርኩኝ፤ ጥሩና ክፉን የሚለየው መስመር የሚያልፈው በሀገሮች፤ በመደቦች፤ በፖለቲካ ፓርቲዎችም መካከል አይደለም፤ ይህ መስመር የሚያልፈው በያንዳንዱ የሰው ልብ መኻል ነው። መስመሩ እድሜአችን በሙሉ ከውስጣችን መለስ ከለስ ይላል። በክፉ የተሞሉ ልቦችም ቢያንስ ቅንጣት ያህል ጥሩነት ይኖራቸዋል፤ ከሁሉም ጥሩ ከሚባለውም ልብ ከአንድ ጥጓ ትንሽ ክፋት ይኖራታል።

በየቦታው እየዞሩ ያሉ ክፉ ስራ የሚሰሩ ክፉ ሰዎች ቢኖሩና እነሱን ከኛ መለየትና ማጥፋት ብቻ ቢሆን ኖሮ እንዴት ቀላል ይሆን ነበር! ግን ጥሩና ክፉን የሚለየው መስመር ከያንዳንዱ የሰው ልጅ ልብ መካከል ነው የሚያልፈውና ማን አለ ከራሱ ልብ ቁራጭ ቆርጦ ለማስወጣት ፈቃደኛ ይሆነ?

በዚህ አባባላቸው ሶልዠኒትሲን የሚሉት የአምባገነናዊ ስረዓት የገዢና የመሪ ውጤት ሳይሆን የያንዳንዱ ሰው ድክመትና ጠፋት ውጤት ነው። ይህ አስተማሪ አባባል የዛሬውን የኢትዮጵያ ፖልቲካ ሁነታ በደምብ ይገልጻል።

ቅድም እንዳልኩት ኢህአዴግ አናሳ ድጋፍ ነው ያለው። በተጨማሪ ከለሎች አምባገነናዊ ስረዓት አናሳነቱ የተለየ ነው። ለምሳሌ የሶቪዬት መንግስት አናሳ ድጋፍ ቢኖረውም ይህ ደጋፍ በጎሳ የተመሰረተ አልነበረም። ስለዚህ የሶቪዬት ህዝብ ተጨቆኛለሁ ሲል በራሴ ወገን በሶቪዬቶች ነው የተጭቆንኩት ብሎ ነበር የሚያስበው። የኢህአዴግ አገዛዝ ግን አናሳ ብቻ ሳይሆን በጎሳ የተመሰረተ ነው። ህገ መንግስቱም አስተምረውም እንደዚህ ነው። ህዝቡም እንደዚህ ነው የሚመለከተው። የሰው ልጅ ባህሪ ደግሞ በራሱ ወገን ቢገደል ይሻለዋል በሌላ ወገን ወይም ጎሳ ከሚጨቆን! ስለዚህ የኢህአዴግ የጎሳ አገዛዝ ከሌላው አማገነናዊ ስረዓት ይበልጥ ህዝብ ቅራኔና አመጽ የተጋለጠ መሆን ነበረበት።

ይህን አመዛዝነን ከተረዳን ለኢህአዴግ በስልጣን መቆየት እኛ ኢትዮጵያዊያን ዋና ምክንያት መሆናችንን ይገባናል። አንድነት ያለው ህብረተሰብ ብንሆን እርስ በርስ ብንስማማ ብንተሳሰብ ብንፋቀር ኢህአዴግ ድሮ ወድቆ ነበር። በተጨማሪ ማለት የምንችለው ኢህአዴግ በኃይል ሊገዛን አይችልም በኃይል ገዝቶንም አያውቅም! በኛ እርዳታ፤ ትብብርና ፈቃድ ነው እየገዛን ያለው። የኛ ጥፋትና ሃጥያት ነው የኢህአዴግ አገዛዝ ምሶሶ። ስለዚህም ኢህአዴግን የፈጠርነው የምናቆመውም እኛ ከሆንን የምናፈርሰውም የምናጠፋውም እኛው ነን የምንሆነው። ውግያና ተመሳሳይ ቀውጥ አያስፈልግም፤ ከጎረቤቴ ጋር አልጣላም ማለት ብቻውን በቂ ነው። እንደዚህ ካረግን የኢህአዴግ ይፈርሳል። እርግጠኛ ነኝ በርካታ የኢህአዴግ አባላትም ያንን ሸክማቸውን የሚያወርዱበትን ቀን በጉጉት የጠብቁታል!

No comments:

Post a Comment

ለሀሳብዎ አመሰግናለሁ!