Showing posts with label ኢትዮጵያዊነት. Show all posts
Showing posts with label ኢትዮጵያዊነት. Show all posts

Friday, 17 August 2018

የአማራ ኩራት የት ሄደ?

ለመጀመርያ ጊዜ በአማራ ስም ፋንታ በኢትዮጵያ ስም ብትደራጁ አይሻልም ወይ ብዬ የአማራ ብሄርተኞችን ስጠይቅ ያገኘሁት መልሶች (ስድቦቹን ትተን) አስገራሚ ነበር። ምናልባት 80% ስለ አማራ ላይ ባለፉት 27/40 ዓመት የደረሰበት በደል እና ጭቆና ነው። የአማራ ህዝብ ጥቅም ይበልጥ የሚከበረው በአማራነት በመደራጀት ነው ወይንም በኢትዮጵያዊነት በሚለው ዙርያ ከመወያየት ፋንታ ስለ አማራ መጨቆን የጭቆና ቆጠራ ውስጥ ገባን። ይህን ስል አማራው አልተጨቆነም ማለቴ አይደለም ከሌሎች ይልቅ በመንግስት ብቻ ሳይሆን በግለ ሰብ እና በቡድን በአማራነቱ ተጭቁኗል «መጤም» እየተባለ በትውልድ ሀገሩ ባይተዋር ሆኗል። ይህ ሁሉም የሚያቀው ነው። ግን ይህ በፍፁም የአማራ ማንነት መግለጫ መሆን የለበትም። ላስረዳ…

እንደገባኝ ይህ የ27 ዓመት ጭቆና የዛሬው የአማራ ማንነት መሰረት ሆኗል። እስቲ ስለ አማራ እና አማራነት ንገረኝ ሲባል የዘመኑ አማራ ላለፉት አመታት «እጅግ የተጨቆነ፤ የተበድለ፤ የተፈናቀለ፤ የተዋረደ፤ ባሁሉ የተሰደበ፤ ማንነቱ የተገፈፈ» ወዘተ ነው የሚለው። የድሮ አማራ ይህንን ቢሰማ እጅግ ግራ ነበር የሚገባው። ማን ነው አማራ ምንድነው አማራነት ብለህ የድሮ አማራን ብትጠይቀው 3000 ዓመት ታሪክ ያለው፤ ሃይማኖት ያለው፤ ስልጣኔ ያለው፤ የአፍሪካ ቁንጮ፤ የሰው ልጅ ቁንጮ፤ ፍርሃ እግዚአብሔር ወዘተ ነው የሚለው! ልዩነቱን አያችሁ። አማራ በወጉ መሰረት እራሱን የሚሰይመው ማንነቱን የሚገልጸው በአዎንታዊ መንገድ ነው። ዛሬ ግን እድሜ ለረዥም ዓመት ጫና እና የጎሳ ብሄርተኝነት እና የማርክሲዝም ፕሮፓጋንዳ አማራው ማንነቱን ስቷል።

የዛሬ አማራ የበታችነትን ስሜት (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/07/blog-post_30.html) መቀበል ብቻ ሳይሆን የማንነቱ መሰረት ያደረገው ይመስላል። የሰለባ አመለካከት (victim complex)፤ የበታችነት ስሜት (inferiority complex) አጥቅቶናል። እንደ ጥቁር አሜሪካኖች ወይንም ሌሎች በጭቆና ምክንያት ማንነታቸውን ሙሉ በሙሉ ለ«ጭቁን ነው ማንነቴ» የሚለው አስተሳሰብ እራሳችንን ሰጥተናል።

በራሳችን መተማመን እና መኩራት ቀርቷል። ጣልያን ለአምስት ዓመት ኢትዮጵያ ውስጥ ቆይቶ ተጭቁነናል ተገዝተናል ብለን አናውቅም። የድሮ አማራ ምንም ያህል ቢጭቆን እራሱን «ተጨቋኝ ነኝ» ብሎ አይሰይምም። ጦርነት ላይ ነኝ ነው የሚለው። እንደ አያቶቼ አሸንፋለው ነው የሚለው። እንጂ እጁን ለበታችነት ስሜት አይሰጥም ምን እንደሆነም አያቅም። ለዚህ ነው እስከ ዛሬ ጣልያን ገዝቶናል አንልም። ውግያ ላይ ነበርን ነው የምንለው። ይህ ነበር የድሮ እና ትክክለኛ ተውፊተኛ የአማራ ስለራሱ ማንነት አስተሳሰብ።

ዛሬ ግን ይህ ባለመሆኑ ብዙ አማራ በተለይ ወጣቱ «ጭቁን ብሄረሰብ» ነኝ የሚለው አስተሳሰብ አምኖበት ውጦታል (internalize) ተዋህዶታል። ስለዚህ ይመስለኛል የ«አማራ ብሄርተኝነት» ድሮ ታይቶ የማይተወቀው ዛሬ እንደዚህ መነሳት የጀመረው። በጎሳ ብሄርተኝነት የማናምነው ወንድሞች እና እህቶች ይህ የአማራ ብሄርተኝነት ፖለቲካ ለአማራ ህዝብ ያዋጣል ወይ በሚለው እንነጋገር ስንል ብዙ ጊዜ ስሜታዊ መልስ እና ስድብ ነው የሚጠብቀን። ምክንያቱ የአማራ ብሄርተኛውን ማንነት ጥያቄ ውስጥ ስላደረግን ነው። ማንነቱ «ጭቁን አማራ» ሆኗል። አንድ ሰው ይህ ነው ማንኔቴ ብሎ ከሰየመ አልፎ ተርፎ ቁስል ያለው ከሆነ በዚህ ዙራይ መወያየት አይችልም። ውይይቱ በሃሳብ ሳይሆን በማንነት ስለሆነ በዚህ መደራደር የለም። ስሜት እና ቁጣ ብቻ ነው።

ይህ ክስተት እነ ሻዕቢያ፤ ህወሓት፤ እና ኦነግ ሲመሰረቱ አይተነዋል። ወደነዚህ የሚያዘንብሎ ሰዎችን ድሮ ስናናገር አንዴ እንዲሁም እንዴት ማንነቴን በጥያቄ መልክ ታቀርበዋለሁ ብለው ይናደዱ ነበር። በማንነት ድርድር የለም ይሉ ነበር። መገንጠል አይበጅም ኢትዮጵያዊ ናችሁ ወዘተ አይነት ነበር በፍፁም መስማት ብቻ ሳይሆን ስለዚህ መነጋገርም አይፈልጉም። አንዴ ማንነት ከተቀየረ በአጭር ጊዜ ምንም ማድረግ አይቻልም።

ስለዚህ አሁን ጥንቃቄ ያስፈልጋል። ብዙ በተለይ ልጅ የሆኑ አማራ እህት እና ወንድሞቻችን ባለፈው 27 ዓመት የጎሰኝነት፤ ፀረ አማራ፤ ማርክሲዝም ፕሮፓጋንዳ ቶሞልተው የአማራ ማንነታቸው ተቀይሯል። «ጭቁን» ነኝ ብለው አምነዋል። ለዚህ ጭቆና መልሱ ወደ «አማራነት» ከ«ኢትዮጵያዊነት» ማስቀደም ነው ብለው አምነዋል። ይህን በሰላም መተቸት ማንነትን መተቸት ሆኗል።

ጉዳዩ እንደዚህ ባይሆን እና የበታችንነት እና የ«ጭቁን» አስተሳሰብ ባይህኖር መርሰረታዊ ጥያቄውን በአማራ ስም ነው ወይም በኢትዮጵያ ስም ነው መደራጀት የሚበጀን መወያየት እንችል ነበር። አሁን ግን ለብዙዋች ውይይት አቻልም ስሜት ይነካልና ማንነትን ይነካልና።

አንድ ማረግ የምንችለው የአማራ ባህል እና ወግ በትክክሉ ማስተማር ነው። የአማራ 3000 ዓመት ታሪክ በራሱ መኩራት እና መተማመን ነው። ፍርሃት የለውም። እንደ ጠ/ሚ አብይ (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/08/blog-post_10.html) ማንም አይነት ሰውን አቅፎ ይዞ እግዚአብሔር ልጅ መሆኑን አምኖ ወደ ትክክለኛ መንገድ ማምጣት ነው ባህላችን።  ወደዛ ለመመለስ እንጥራ። መሰረታዊ ማንነቱን ያጣ ህብረተሰብ ይወድቃል።

Wednesday, 15 August 2018

ከአንድ የ«አምራ ብሄርተኛ» ያደረግኩትን ቃለ ምልልስ

ከአንድ የ«አምራ ብሄርተኛ» ያደረግኩትን ቃለ ምልልስ ላቀርብላቹ እወዳለሁ። እኔ አስፋው ጠያቂው ሆኜ እንግዳዬ ደግሞ ግዮናዊት ሀገሬ ትባላለች እራሷን የአማራ ብሄርተኛ ብላ የምትሰይም የ28 ዓመት መምህርት ናት። ቆይታችን እንዲህ ነበር፤

አስፋው፤ ለቃለምልልስ ፈቃደኛ በመሆንሽ አመሰግናለሁ፤ እንኳን ደህና መጣሽ።

ግዮናዊት፤ ምንም አይደለም፤ እኔም አመሰግናለሁ።

አስፋው፤ እስቲ ስለ አማራ ብሄርተኝነት ርዕዮተ ዓለም ትንሽ ንገርኝ።

ግዮናዊት። የአማራ ብሄርተኝነት የአማራ ህዝብ ለአማራ ህዝብ መቆም አለበት የሚል ርዕዮተ ዓለም ነው። የአማራ ህዝብ ባለፉት 27 ዓመት፤ 40 ዓመት ማለት ይቻልም ይሆናል፤ ብዙ ግፍ እና ሰቆቃ የደረሰበት ነው። ክብሩን ከማጣት እስከ ቡድናዊ ግድያ (genocide) ተፈጽሞበታል። ከበየ ኢትዮጵያ ክልሎች ተፈኛቅሏል። ህዝቡ ተገድሏል። የመንግስት በጄቱ ተቀምቷል። አማራ ሀገር ከሁሉም ድኻ ሆኖ ግን በጨቋኝነት ይፈረጃል። እስካሁን እንደ ጨቋኝ ይታያል እንደ ህዝብ መቀጣት አለበት ተብሎ ይሰበክበታል። የአማራ ብሄርተኝነት ይህን ያለፈውንም፤ ያለውንም፤ ወደ ፊት የሚመጣውንም አማራ ላይ ጥቃት ለመቋቋም ነው የሚቆመው። ከዛ አልፎ ተርፎ የአማራ ህዝብ መደራጀት ያለበት እራሱን ለመከላከል ብቻ ሳይሆን ለመቋቋም እና ለመበልጸግ። ልጆቻችን እንዲማሩ፤ እርስ በርስ እንድንረዳዳ፤ ለራሳችን ልማት እንድናመጣ ወዘተ የሚታገል ርዕዮተ ዓለም ነው።

አስፋው፤ ግን እስቲ «አማራ» ከሌላው ይበልት ተጨቁኗል ማለት ይቻላል። ባለፉት 27 ዓመት ሁሉም ትግራይ ያልሆነ ተጨቁኛለሁ ይላል። ኦሮሞ በስመ ኦነግ። ጋምቤላ ለመሬቱ፤ አኟክ ጭራሽ ጄኖሳይድ ተፈጽሞበታል። ሲዳማ በየጊዜው ተመቷል። ወዘተ።

ግዮናዊት። አዎን ህወሓት ሁሉንም መትቷል ግን እንደ አማራ በየ ክልሉ የሚገደል የለም። እንደ አማራ የህዝብ ቁጥሩ እንዲመነምን የተደረገ የለም። እንደ አማራ በየ ክልሉ የሚፈረጅበት ጭቋኝ ተብሎ የሚረገጥ የለም።

አስፋው፤ አዎ ግን ሁሉም ጎሳ እንዲሁ የራሱ እሮሮ አለው እኮ።

ግዮናዊት፤ አይደለም፤ ሁሉም መንግስት ጭቁኖኛል ማለት ይችላል እንበል። በዚህ እንስማማ። ግን አማራ የተጠቃው በመንግስት ብቻ ሳይሆን በሌላው ህዝብም ነው። ይህ ነው ልዩነቱ። ሲገደል ሲፈናቀል መንግስት ብቻ አይደለም ይህን የሚያደርግ የነበረው። መንግስት «ጭቋኝ» ብሎ ሰየመው ከዛ በኋላ የተለያዩ ግለሰብ እና ቡድኖች ይህን ይዘው አማራን በየቦታ ያሰቃያሉ። ይህ ነው ልዩነቱ። አማራ የትጠቃው በመንግስት ብቻ ሳይሆን በህዝብም ነው።

አስፋው፤ ግን እኮ የአርሲ ኦሮሞን ብትጠይቀው የአማራ መንግስት ለ100 ዓመት ጨቁኖኝ ነበር ሰለዚህ እኔም በመንግስት ብቻ ሳይሆን በግለሰቦች ተጨቁኛለሁ ይላል። አማራ ብቻ አይደለም እንደዚህ አይነት ጭቆና ዘመን ያሳለፈው ይላል። የ«ተጨቆንኩኝ» እሽቅድድም አልሆነምን?

ግዮናዊት፤ ያየድሮ ታሪክ ነው ባለአባቶች መሬታቸውን ከተነጠቁ 44 ዓመት አልፏል። አማራ ላይ ግን አሁንም ነው ጥቃት የሚደረገው።

አስፋው፤ ግን የታሪካዊው ጭቆና አሁንም ርዝራዥ አለው ይሉናል። አማራው ጨቁኗል አሁንም የድሮ ጭቆናው ውጤት ነው የሚያገኘው ይላሉ። መቼም ወደ ኋላ እየተሄደ ሁሉም የግፍ ቆጠራውን ያደርጋል ከሁሉም እበልጣለሁ ይላል አይደለምን?

ግዮናዊት፤ በዚህ አንስማማም። የድሮ የድሮ ነው። ዛሬ ግን ከሁሉም ሰለባ አማራ ነው ብለን ነው በአማራ ብሄርተኝነት የምናምነው።

አስፋው፤ ጥሩ። ግን ከሌሎች ድጋፍ አትጠብቁ። ከኛ በሙሉ እናንተ ናችሁ የተጨቆናችሁት እንዲሏችሁ አትጠብቁ። በዛ መሰረት እንደረደራለን ብላችሁ አታስቡ።

ግዮናዊት፤ ይሁን የራሳቸው ጉዳይ በዚህ መስማማት አያስፈልግም። ግን ለኛ ለአማራ ህዝብ እኛ ዋና ተጨቋኝ እንደሆንን እናምናለን ይህንንም እንደ ምክንያት አድርገን ነው የምንደራጀው።

አስፋው፤ እሺ አማራው ተጎድቷል እየተጎዳ ነው። ለምንድነው በአማራነት መደራጀት የሚያስፈልገው ይህን ጥቃት ለመቋቋም? ለምን በኢትዮጵያ ወይንም በ«ኢትዮጵያ-አማራ» ስም መደራጀት ለዚህ አይበጅም? በኢትዮጵያ ስም ብንደራጅ አማሮች ብቻ ሳይሆን ሌሎችም ለኛ ይቆሙ ነበር።

ግዮናዊት፤ ተጨቋኙ አማራ ነውና። ምን ሌላ ምክንያት አለው። በአማራነቱ እየተሰደበ እየተኮነነ እየተገደለ እያለ እራሱን በአማራነቱ መከላከል አለበት። ማን ሌላ ይከላከልለት? እራሱን ካደራጀ አይጠቃም። ሌላን ከጠበቀ ይጠቃል። ግልጽ ነው እኮ።

አስፋው፤ ማለት የፈለግኩት እንዲህ ነው። የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ እንውሰድ። ይህ ድርጅት እራሱን የ«ኢትዮጵያ ብሄረአዊ ንቅናቄ» ብሎ ቢሰይም አሁን የሚሰራውን መስራት አይችልም ነበር ያውም ሌሎችን አካቶ እና ተጨማሪ ኃይል አከማችቶ?

ግዮናዊት፤ አይችልም። ስሙ «ኢትዮጵያ» ከሆኑ ሁሉንም ማቀፍ ይኖርበታል ለአማራ የተለየ ጭቆና ብቻ መቆም አያችልም። ይህ «ኢትዮጵያዊ» ድርጅት የአማራ ህዝብ ለብቻ የጎደለውን ማሟላት አይችልም። የአማራን ርስት ማስመለስ አይችልም። ወዘተ።

አስፋው፤ ግን በዚህ መልኩ ይችላል። ኢትዮጵያዊ ድርጅት ከሆነ ሁሉንም ለተጨቆነው አማራ ለመቆም ማስተባበር ይችላል። ሁሉንም ለተጭቆነው ኦሮሞ ማስተባበር ይችላል። ይህ ከአማራ በቻ ይበልጥ ትልቅ ኃይል አደለምን?

ግዮናዊት፤ በቴኦሪ ደረጃ ጥሩ ይመስላል ግን በዚህ ዘመን ከአንድ ብሄር በላይ ሲቀላቀል መዘዙ ብዙ ነው። እስካሁኑም አልሆነልንም። አማራ አማራ አትበሉ እንባላለን። ይህ ደግሞ አይመቸንም።

አስፋው፤ እስካሁን አልሆነምን ተይው! የአማራ ብሄርተኝነትም እስካሁን አልሆንም። በደምብ ላልተሞከረ ነገር አልሆነም ማለት ሃሰት ነው። የአንድነት ድርጅቶች ያልተሳካላቸው በአንድነት ስለሚያምኑ አይደለም በእርስ በርስ የጎሳ ፍጭት አይደለም።

ግዮናዊት፤ ምንም ቢሆን እኛ አማሮች ለአማራ መስራት ነው የምንፈልገው።

አስፋው፤ ታድያ ይህ አቋማችሁ ከሌሎች ጎሰኞች እንደ ህወሓት ወዘተ ምን ይለያችኋል?

ግዮናዊት፤ ቅድም እንዳልኩት እኛ ለብቻ ይበልጥ ተጨቁነናል። አልፎ ተርፎ እኛ በኢትዮጵያዊነት እናምናለን። እንገንጠል አንልም። አማራ ኢትዮጵያዊ ነን ነው የምንለው። ይህ ነው ትልቁ ልዩነት።

አስፋው፤ በክልሌ ያለው አማራ «መጤ» ነው የሚለው የኦሮሞ ብሄርተኛውም እንዲሁ ነው የሚለው እኮ። ተበድያለሁ። መገንጠል አልፈልግም (መብቱ አይወሰድብኝ እንጂ) እና እኔ መጀመርያ ኦሮሞ ነኝ ቀጥሎ ኢትዮጵያዊ (የብሄር ፌደራሊዝም እስካለ አለ በለዛ ለቃለው!) ። እንዲሁ ነው የሚሉት። አሁንም ምን ይለያችኋል።

ግዮናዊት፤ እኛ ደግሞ ማንንም አንጨቁንም ከክልላችን ይውጣልን አንልም ብለንም አናውቅም። ይህ ነው ሌላ ልዩነታችን።

አስፋው፤ ግዮናዊት፤ ሌሎቹም እኮ ማንንም አንጨቁንም። ታሪካዊ ጭቆናን እናስተካክላለን ለምሳሌ በaffirmative action አይነት ነገሮች መሬተም ወደ ድሮ የተቀማበት በመመለስ ወዘተ። በክልላችን የኛ ቋንቋ ነው የሚሰፍነው እንላለን በመንግስት በትምሕርት ደረጃ ወዘተ። ሌላው ይህን ካልተቀበለ ይውጣ ከፈለገ ነው የሚሉት። በአማራ ክልልም የአማራ ብሄርተኝነት ከሰፈነ እንዲሁ እይደለም የሚሆነው? በአማራ ክልል ያለው አማራ ያልሆነው ህብረተሰብ ሁለተኛ ዜጋ አይሆንም?

ግዮናዊት፤ አይሆንም ብቻ ነው ማለት የምችለው። አሁን በአማራ ክልል ያሉ የኦሮሞ ዞኖች ውስጥ ነዋሪዎቹ ሙሉ ነፃነት አላቸው በቋንቋቸው በፍላጎታቸው መተዳደር። አገውም እንዲሁ።

አስፋው፤ ስለዚህ አማራው በክልሉ ያሉትን «አናሳ ብሄሮችን» አይጨቁንም የመጨቆን ባህሪውም የለውም እንበል። ጥሩ። ግን ሌሎቹም እንደዚህ እያሉ ግን በደል ያደርሳሉ። ለምሳሌ በኦሮሞ ክልል የአማርኛ ትምሕርት ይቀራል ቢባል አንቺ እንደ ጭቆና ታዪው ይሆናል ግን ኦሮሚያ ቋንቋችን እንዳይሸረሸር ነው ይላል። አማራው በአማራነቱ መደራጀቱ ይህን ጉዳይ እንዴት ያደርገዋል?

ግዮናዊት፤ የአማራ ድርጅት ለዚህ መልስ ይኖረዋል። ከኦሮሚያ ለሚኖረው አማራው መብት ይቆማል ይታገላል።

አስፋው፤ ከመፈክር አልፎ በተግባር ያልሸው ምን ማለት ነው?

ግዮናዊት፤ በአማራ ክልል እንደዛው አይነት ፖሊሲ እናመጣለን። በኛ ኦሮሞ ዞኖችም ትምሕርት ቤት በአማርኛ ብቻ ማድረግ ነው።

አስፋው፤ ግን አማራ በብዛት በየክልሉ አለ። በዚህ ብድር በመመለስ (tit for tat)ተሸናፊ አማራው ነው የሚሆነው። ልክ እንደ ሰርቢያኖች በዩጎስላቪያ በኢትዮጵያ የጎሳ ግጭት ከተነሳ አማራው ነው ከሁሉም በላይ የሚጎዳው አይደለም?

ግዮናዊት፤ አማራው በደምብ ከተደራጀ ሁሉንም አማራ በየ ቦታው ያለውንም መጠበቅ ይችላል። ጦር ይኖረዋል ሄዶ ይከላከላል።

አስፋው፤ የአማራ ጦር አዲስ አበባ ሄዶ የአዲስ አበባ አማራዎችን መብት ሊጠብቅ ነው? ሻሸመኔ ሄዶ አማራውን ሊጠብቅ ነው? ይህ አጉል ፉከራ ከእውነታ የራቀ አይደለም።

ግዮናዊት፤ አዎን ዝም ብዬ የኛ የአማራ ብሄርተኞች ስሜታዊ መልስ ነበር የሰጠውህ! ትክክለኛ መልስ እንዲህ ነው፤ አማራው ተደራጅቶ ሲጠነክር ሌሎች ክልሎች/ብሄሮች ይጠነቀቃሉ ከጸንፈኝነት ይቆጥባቸዋል። ከግጭት ይልቅ ወደ win-win ያመጣቸዋል ነው።

አስፋው፤ ሁሉም አሸናፊ አካሄድ ቢቻል ኖሮማ እስካሁን እናደርገው ነበር! የጎሳ አስተዳደር የሁሉም አሸናፊ ሳይሆን የዚህ ተቃራኒ የሆነው የሁሉም ግጭት ውጤት ነው የሚያመጣው። ያለፈው 27 ዓመት ይህን አሳይቶናል ብለሽ አታምኝም?

ግዮናዊት፤ አዎን ለዚህም ነው የአማራ ብሄርተኞች የጎሳ ፌደራሊዝምን የምንቃወመው። የአማራ ብሄርተኝነት ንቅናቄ (አቤን) አቋሙም እንዲሁ ነው የጎሳ አስተዳደርን ለመቀየር።

አስፋው፤ እንዲህ ከሆነ እንዴት ጠንካራ አማራ ከጎሳዊ ግጭት ያድነናል ትያለሽ? ላለፉት 27 ዓመት በዚህ ክፉ "experiment" እንዳየነው የጎሳ አስተዳደር በጎሳዎች መካከል ግጭት ያመጣል። በሺዎች የሚቆጠሩ ግጭቶች በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ህይወት አልፏል፡ እኔ ሀገር አልባ ሆኛለው።

ግዮናዊት፤ ምን ማለትህ ነው?

አስፋው፤ አንቺ ከደብረ ማርቆስ ከአማራ ክልል በመሆንሽ የኛን ከአምራ ከአዲስ አበባ ውጭ የምንኖረውን አማሮች ታሪክ አትረድቱም። ከኔ ቤተሰቦች ሀገር በምዕራብ ሀረርጌ በጣም ብዙ አማሮች ሁለተኛ ዜጋ ላለመሆን ለህይወታቸው ሁልጊዜ ላለመስጋት ብለው ወደ አዲስ አበባ ተሰድደዋል። ይህ የሆነው ከ1983 ጀምሮ ነው። እስካሁን። ትውልድ ተሰድዷል ሀገር አልባ ሆኗል። ልጆች ሀገሬ ነው ብለው መጎብኘትም አይችሉም። በአካል መሄድ ይችላሉ ግን ሀገርህ አይደለም ስለሆነ የቦታው መንፈስ ዋጋ የለውም። የጎሳ አስተዳደርን በዚህ በተጨባጭ መንገድ ጉዳቱን አይተነዋል ደርሶብናል። ምናልባት እናንተ አምራ ክልል ያላችሁ ምንም ቢደርስባችሁ ሀገር አልባ አልሆናችሁም። የረሳችሁ ከሃዲዎች ናቸው የሚጨቁኗችሁ የነበሩት። ግን ሀገር አላችሁ ዛሬ በነፃነት ዘመን ሀገር አላችሁ። እኛ ግን የለንም። ሰለዚህ ስለ የጎሳ አስተዳደር ጉዳት እናውቃለን። ይህን አውቀን ነው አማራ እራሱን ማደራጀት ለኛ ዋጋ እንደሌለው የምናውቀው።

ግዮናዊት፤ አሳዛኝ ነው ግን መቼስ መደራጀታችን ይጠቅሟችኋል። ቢያንስ በገንዘብ እና ሌላ ነገር ድጋፍ ልንሰጣችሁ እንችላለን።

አስፋው፤ እስቲ ወደ ሌላ ርዕስ እንሂድ… ለምንድነው የአማራ ብሄርተኝነት የሚያስፈልገው ብሄ ስጠይቅሽ በመጀመርያ እና አጥብቀሽ የነገርሽኝ ስለ አማራ ላይ የደረሰው በደል ነው። ሌሎችንም ሳናግር ስለ አማራ ብሄርተኝነት አንድ ገጽ ከጻፉ 70% ስለ አማራ መጨቆን ነው። ይህ የ«ጭቁን» ስነ ልቦና (victim mentality) እንዲሰፍንብን አያደርግም? ይህ አይነት አስተሳሰብ ደግሞ ጎጂ አይደለም እንደ ጥቁር አሜሪካኖች፤ አቦሪጊኖች፤ ኦሮሞ ብሄርተኞች ወዘተ ማንነታችን ከመጨቆን ጋር አቆራኝቶ ወደ ታች አይጎትተንምን?

ግዮናዊት፤ እውነት ከሆነ ተጨቆንኩኝ ማለት ምን ጉዳት አለው? እውነት ነው። መካድ የለበትም። እውነቱን ካላመንን ደግሞ ወደ ፊት ሊደገም ይችላል አጥፊዎቹም ላይማሩ ይችላሉ እኛም ይቅር ማለት ያቅተን ይሆናል።

አስፋው፤ እውነት እማ እውነት ነው። ይካድ አይደለም የምለው። ምን ላይ እናተኩራለን ነው ጥያቄው። አዎን ጥቁር አሜሪካኖች እጅግ ተጨቁነዋል። ግን ያንን ከማመን አልፎ ማንነታቸውን ከመጨቆን ጋር አያይዘው ምንም ነገር ጉዳይ ላይ መጨቆናቸውን እንደ ምክንያት ሰበብ ይጠቀማሉ። (ያው በጅምላ እያወራን ነው ነገሩን ለማቅለል)። ስለዚህ እራሳቸውን አቅም አልባ (disempower) አድርገዋል። ለሚደርስባቸውም ሊሚያደርሱትም ሃላፊነት መውሰድ አቅቷቸው ሃላፊነቱም ምክንያቱም ሁል ጊዜ ጭቆና ይሆናል። ይህ ህብረተሰቡን እንዴት እንደጎዳው እናውቃለን። አምራ ብሄርተኛው ዛሬ ሲያወራም እንዲሁ ነው የሚሰማኝ። ስለደረሰበት ጭቆና በደምብ አሳምሮ ይናገራል። ምን ይመስልሻል?

ግዮናዊት፤ አዎ ስለ victim mentality እና ክብር ማጣት አውቃለሁ። ግን ይህን በኛ አማራ ብሄርተኞች አላይም። ሰለባ ሆነናል እና እንደገና እንዳይደገም መደራጀት እና መስራት አለብን ነው ጉዳዩ።

አስፋው፤ ጥሩ ነው የበታችነት ስሜት ከሌለ። ግን አይመስለኝም። የድሮ አማራ ቢበለም ተበድያለሁ አይልም ጸጥ ብሎ እራሱን ይጎላብታል እንጂ። ሽንፈትን በፍፁም አያምንም፤ ቢያውቀውም አያምንም። ይቅርታ ጠይቁኝ አይልም። የድሮ አማራ በትንሽ ቁጥር የሆኑ ህወሓቶች ተገዛሁኝ በገዛ ሀገሬ ተጨቆንኩኝ አይልም። ይህ እማ ጉድ ነበር የሚባለው! መቼም አያምነውም። የራሴ ጥፋት ነው ብሎ ወደ ራሱን ማስተካከል ቶሎ ይሻገራል። የዛሬው ትውልድ ግን ህወሓት እንዲህ አድርጎናል እያለ ይደጋግማል። እነ ይሄንን እንደ ታላቅ የአዕምሮ ሽንፈት ነው የማየው። ይቅርታ አድርጊልኝ እንጂ ያሳፍረኛል። ዝም ብለን ስራችን ነበር መስራት ያለብን።

ግዮናዊት፤ ታድያ አሁን ስራችንን እየሰራን ነው። ግን ልክ ነህ ቢያንስ ባሁኑ ወቅት ስለበደል ማውራት አቁመን ወደ ስራ መግባት አለብን።

አስፋው፤ ሌላ ጉዳይ… ምንድናቸው እነዚህ ከመካከላችሁ ሆነው ጸንፈኛ ሃሳቦች የሚያራምዱት። የኢትዮጵያ ብሄርተኝነት ዋጋ የለውም እስከ ኢትዮጵያ ፈርሳለች የሚሉ አሉ። አንቀጽ 39 ችግር የለውም የሚሉ አሉ። በጠቅላላ በጎሳ ብሄርተኝነት የሚያምኑ አሉ ከአማራ ጨቋኝ ነው ከሚለው ትርክት በቀር። እነዚህ የአማራ ብሄርተኝነት ምልክቶች ናቸው?

ግዮናዊት፤ ባጭሩ አይደሉም። የሰው ልጅ በተለያየ ምክንያት ወደ ጸንፍ ይሄዳል። አንዳንዱ በስነ ልቦና ምክንያት በደል ወይንም ጭቆና በዝቶበት። እንደምታውቀው ደግሞ ምሁራኖቻችን የጸንፈኝነት ችግር አላቸው። ቀላል መፍትሄ እንደ ዝክተኝነት ይቆጥሩታል። ከባድ እና ውስብስብ መፍትሄ እንደ ሊቅነት ይመስላቸዋል። ለዚህ ነው ወደ ጽንፍ የሚሄዱት እንጂ የአማራ ብሄርተኝነት እንደዚህ አይነቱን ነበር አያምንም። ኢትዮጵያ ከሌለች እማ ምን ዋጋ አለው? ለኛ የአማራ ብሄርተኝነት ኢትዮጵያዊነትን ማጠንከርያ መሳርያ ነው። እንጂ ሌላ ፍልስፍና አይደለም።

ውይይቱ ብሌላ ቀን ይቀጥላል…

Friday, 3 August 2018

የበታችነት ስሜት

ሰላሳ አርባ ዓመታት በፊት ከሀገሩ የሚሰደድ ኢትዮጵያዊ ወደ ምዕራብ ሀገር ሲሄድ ከሀገሩ ይበልጥ «የሰለጠነ» እና «የበለጸገ» ሀገር አግኝቻለሁ ብሎ ያስቡ ነበር። የምዕራብ ሀገሮች በሀብት፤ በብልጽግና፤ በግብረ ገብነት፤ በቅልትፍና (efficiency)፤ በንፅህና ወዘተ ከኢትዮጵያ የላቁ መሆናቸው አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ያምን ነበር።

ሆኖም ግን ስደተኛው ምዕራብ ሀገሮችን ቢያደንቅም የሚተችባቸው ጉዳዮች ነበሩ። ለምሳሌ «ዘረኝነትን ያራምዳሉ» ይላል። በአዲስ ቅኝ ግዛት ታዳጊ ሀገራትን ያጠቃሉ ይዘርፋሉ። ኢትዮጵያ ለቅኝ ግዛት ስለማትመች እነ አሜሪካ ካዷት እና በደርግ አይነቱ አረመኔ መንግስት በማርክሲዝም እንድትገዛ አደረጉ። በተለያዩ ሀገራት ሕጋዊ የሆኑ መንግስታትን ይገለብጣሉ። ወዘተ። ኢትዮጵያዊ ስደተኛው ልሂቃኑም የምዕራብ ሀገሮችን በዚህ መልኩ ይከሱ ነበር።

በርካታ ስደተኞች እንደዚህ በማለት የምዕራብ ሀገሮችን ተችተው ሀገራቸው ኢትዮጵያ ችግሮች ቢኖሯትም ከነዚህ ሀገሮች በማንነት ደረጃ አታንስም ብለው ያምኑ ነበር። በዚህ ምክንያት የሀገር የማንነት የበታችንነት ስሜት (inferiority complex) ገና ብዙ አላደረባቸውም። በኢትዮጵያዊነቱ ያለው ኩራት ብዙ አልተቦረቦረም ነበር።

ግን ጊዜው ባለፈ ቁጥር ኢትዮጵያ «አልሻሻል» ስትል ባንጻሩ የምዕራብ ሀገሮች በብልጽግና እይናሩ እና አንዳንድ ልውጦች ሲያደርጉ የፕሮፓጋንዳ ስልታቸውም እየዳበረ ሲሄድ ኢትዮጵያዊ ስደተኛው በአሙሮው የምዕራቡን ዓለም እያበለጠ ሀገሩ ኢትዮጵያን እያሳነሰ ሄደ። ቀስ በቀስ የበታችነት ስሜት (inferiority complex) እያደረበት ሄደ። የህ የበታችነት ስሜት ወደ ሀገር ቤትም ገባ።

ወደ ምዕራብ ሀገር የተሰደደ ኢትዮጵያዊ ደህና ገቢ ማግኘት እና ሃብት ማከማቸት ቻለ። ስደተኛው ድሮ ቢገጥመውም ባይገጥመውም የሚያማርረው ዘረኝነቱ እየቀነሰ ሲሄድ አየ። ለነገሩ ዘረኝነቱ ድሮም ኑሮውን ከማሻሻል አልከለከለውም ነበር። አህን ግን ጭራሽ በጥቁርነቱ ስራ ከማጣት ማግኘት ጀመረ! ባሜሪካ ልጆቹ በጉብዝናቸው ብቻ ሳይሆን የጭቁን (ጥቅር) ዘር በመሆናቸው ስኮላርሺፕ ማግኘት ጀመሩ። የአሜሪካ ኑሮ ከድሮም ይበልጥ እየተመቸ ሄደ።

ይህ ስደተኛ ኑሮው «እየተሳካለት» በሄደ ቁጥር አሜሪካ በሱ አይን ይበልጥ እያማረች ሄደች። ፍትሐዊና መሐበራዊ ስነ ሥርዐቱን ከድሮም ይበልጥ ማደነቅ ጀመረ። ለሴቶች፤ ለልጆች፤ ለጥቁሮች ወዘተ ያለው «መብት» እና ጥንቃቄ ከኢትዮጵያ ጋር ሲያነጻጽረው ይገርመዋል። በፖለቲካ ደረጃ «ዴሞክራሲ» አምላኩ ሆነ «ሲኤንኤን» (CNN) መላዕክቱ ሆነ። በአንጻሩ ኢትዮጵያ በስደተኛው አይን እየቀነሰች እየወረደች ሄደች። አልሻሻል አለች እየባሰችም ሄደች። ስደተኛው ሀገሩን በጎበኛት ቁጥር ከአሜሪካ ጋር እያንጻጸረ ዘመዶቹን ያደነቁራል። በአሜሪካ እና ኢትዮጵያ ያለውን ልዩነት ለማሳየት ያህል ዘመዱን ከ«ሀገር ቤት» ለመውጣት በርካታ አስር ሺዎች ዶላር ይከፍላል።

ዛሬ በኛ በኢትዮጵያውያን የዝቅተኘት መንፈስ በደምብ አድሮብናል ማለት ከእውነት የራቀ አይመስለኝም። ግን ይህ መንፈስ እውነትን ነው የሚያንጸባርቀው? እውነት ዝቅተኛ ህብረተሰብ ነን? ወይም ሀገራችን ዝቅተኛ ነው? ይበልጥ ታላቅ የሆነው ጥያቄ ሙሉ ሰው ለመሆን ወይንም በዘመኑ ቋንቋ «መሻሻል» ከፈለግን እንደ ምዕራቡ ዓለም መሆን ይኖርብናል? ምናልባት ዘፈናችን ጭፈራችን ምግባችንን ለትዝታ ብለን ጠብቀን በሌላው በሙሉ እንደነሱ እንደ ምዕራባዊያን መሆን ይኖርብን ይሆን?

እዚህ ላይ በቀለም ትምሕርት ከምንማረው በሚዲያ ከምንሰማው ፕሮፓጋንዳና ተራ «እውቀት» ወጥተን እናስብ። በአዲሱ ቅን ግዛት የተገዛውን አእምሮአችንን ነፃ እናውጣው የብዥታ መነጽራችንን እንጣል። በመጀመርያ እስቲ ምንድነው «ስልጣኔ» ብለን እንጀምር። ጥያቄውን በምሳሌ ኃይል ለመመርመር ታዋቂውን የሮሜን ስልጣኔን እንመልከት።

በክርስቶስ ዘመን በርካታ አይሁዶች ወደ ሀገራቸውን ወርሮ የገዛው ሮሜ ይፈልሱ ነበር። አንድ አይሁድ ወደ ሮሜ ሲሄደ ዛሬ ኢትዮጵያዊ ከሀገሩ ወደ አሜሪካ እንደመሄድ እናመሳስለው። ሮሜ ሀብታም ነበረች። «ስደተኞችን» መጤዎችን ትቀበላለች ታስተናግዳለች ታበለጽጋለች። ውጣ ውረድ ቢኖረውም መጤዎች የሮሜ ዜጋ የመሆን እድል አላቸው። የሮሜ ዜግነት አንደ ይሁዳ ዜግነት በጎሳ በብሄር በደም የተወሰነ አይደለም ማንም የሮሜ ዜጋ መሆን ይችላል። የሮሜ ፍርድ ቤቶች በደምብ ይሰራሉ በተለይ ለሮሜ ዜጎች እውነተኛ ፍትሕ ይሰጣሉ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ችግር ባጋጠመው ቁጥር አይሁዶች ሲገሱት ሲሉ የሮሜ ዜግነቱን ተጠቅሞ ፍርድ ይጠይቃል! በሮሜ ፍርድ ቤት ትክክለኛ የፍርድ ሂደት እንደሚጠብቀው ስለሚያውቅ ነው። የሮሜ መንግስታዊ አስተዳደር ፍፁም ባይሆንም ከሌሎች አንጻር «የሰለጠነ» ነበር። «ዴሞክራሲ» አይነት ከነ ምክር ቤት አለው። በሮሜ የማሕበራዊ ብረ ገብ አለ። የሴቶች «መብቶች» ከሌሎች ሀገሮች ከይሁዳ ይልቅ የተከበሩ ናቸው። በስነ ሥርዓት  በኩልም ሮሜ የስለጠነች ናት። መንገዶቿ ንፁ ናቸው። መንገደኛ ለመንገደኛ ጎረቤት ለጎረቤት አገልጋይ ለባለጉዳይ ያለው ግንኙነት በጥቅም የተሳሰረ ሰላማዊና የተቀላጠፈ (efficient) ነው። የድሮ «ሮሜ» ስልጣኔ እንደዚህ ይመስላል።

ለዚህም ነው አይሁዶችም ሌሎችም ወደ ሮሜ የሚፈልሱት ሃብቱን እና ስልጣኔውን ፈልገው። ልክ እንደ ኢትዮጵያውያን ወደ አሜሪካ እንደምንፈልሰው «ህይወትን ለማሻሻል» ወደ በአድ ሀገር ይሄዱ ነበር። ግን ሮሜ የይሁዳ ቅኝ ገዥ ነበረች! አይሁዶች ወደ የሚገዛቸው ሀገር ነበር የሚሄዱት። ወደ ዓለምን በሙሉ በጉልበቷ የተቆጣጠረቹ ሮሜ ነበር ለተሻለ ኑሮ ብለው የሚሄዱት። ግን አይሁዶቹንም ሌሎች መጤዎችንም የሮሜ ስልጣኔ  ክፋነቷን እንዳያዩ አድርጓቸዋል አሳውራቸው። ለነሱ ሮሜ የብልጽግና ሀገር እንጂ የክፋት ሀገር አልነበረትም። ሮሜ ሀገራቸው ይሁዳ የሌላት ነገሮች ሁሉ አላት። በዚህ ምክንያት በራሳቸው ባህልና ማንነት ዝቅጠኝነት ተሰማቸው እንደ ሮሜዎች መሆነ ፈለጉ ወደ ሮሜ ህብረተሰብ ተቀላቀሉ።

ይህ ምሳሌ ስለ «ስልጣኔን» ምን ያስተምረናል? ለብዙዎቻችን ስልጣኔ ሀብት ማለት ነው። ሀብት ካለ ሌሎች ጉድለቶች አያታዩንም። ስልጣኔ «ቴክኖሎጂ» ይመስለናል። የሮሜ የከተማው ቧምቧ እና ፍሳሽ ስራ አይሁዶችን ይገርማቸው ነበር። ስልጣኔ ቅልጥፍና (efficiency) ይመስለናል። የሮሜ የመነግስት መዋቅሮች በተለይ ጦር ሰራዊቱ ግቡን በቀላሉ ያስፈጽም ነበር። ስልጣኔ ፍትሕ ነው። ስልጣኔ ግብረ ገብ እና ስነ መግባር ነው።

እነዚህን ሁሉ ስንመለከት ግን ባጭሩ ስልጣኔ ማለት ነግ በኔን በደምብ ማወቅ ነው። አካባቢዬን አላቆሽሽም ሌሎችን መንገደኞችን ውድጅያቸው ሳይሆን ንፁ አካባቢ ስለሚበጀኝ እኔ ካላቆሸሽኩኝ ሌሎችም ስለማያቆሽሹ ነው። እኔ መኪና የማሽከረክረው ሕግ አክብሬ ነው ሌሎች የመንገድ ተጠቃሚዎችን ስለምወዳቸው ሳይሆን ሁላችንም በትክክል ካሽከረከርን ሁላችንም በፍጥነንት እና በሰላም የምንፈልግበት ቦታ ለመድረስ ስለሚያመችን ነው። መንግስቴ ለደሆች እርዳታ እንዲያደርግ እወዳለሁ ሰላምን ለመጠበቅ እኔም ነገ ብወድቅ እርዳታ እንዳገኝ። ወዘተ። ይህ ነው ስልጣኔ ባጭሩ። ሮሜም አሜሪካም የትም ህዝብ ሰላምና ሀብት እያገኘ ሲሄድ ለራሱ ለግል ምቾቱ የሚሆን አሰራሮች ስነ ምግባሮች እየገባው በተግባር መዋል ይጀምራል።

ግን ይህ ስልጣኔ ከጥሩነት፤ በጎነት፤ ሰላም ወዳድነት እና ከፍቅር ጋር አይገናኝም። ነግ በኔ በጎነትም ፍቅርም አይደለም። «የሰለጠነ» ራስ ወዳድነት ነው። ማንም ከጊዜ በሚያመጣው ልምድ በኋላ የሚደርስበት ነው። ማንም ደግሞ ችግሮች ሲያጋጥሙት ካልተመቸው የሚተወው ነው። ሮሜ ለራሷ የሰለጠነች ነበር ለሌሎች ሀገሮች ግን የክፋት መዓበል ነበረች። ዛሬ አሜሪካም አውሮፓም ሌሎችም ለራሳቸው የሰለጠኑ ናቸው ግን ከጠረፍ ውጭ አይደሉም።

ስለዚህ ይህ ሀገር የሰለጠነ ነው የኔ ሀገር አይደለም ብለን የበታችነት ስሜት ሊኖረን ይግባል? በፍፁም! ስልጣኔ ማንንነት አይደለም። ስልጣኔ ይመጣል ይሄዳል በዓለም ታሪክ በተለያዩ ቦታዎች ተገንብቷል ፈርሷል። ስልጣኔ ከፍቅርና በጎነት አይገናኝም። የሰው ማንነት ግን በጎነት፤ ፍቅር፤ ሰላም ወዘተ ነው። ስለዚህ የሰው ልጅ እነዚህን የሚሽህ እስከሆነ መቼም የበታችነት ሊሰማው አይገባም! ከፍቅር ይልቅ «ብልጭልጭን» ሲያመልክ ነው ችግሩ የሚመጣው።

ይህን ተክትሎ እንደ ምዕራቡ ዓለም መሆን አለብን ብሎ ማሰቡም ተገቢ አይደለም። ለምን ብትሉ የምዕራባዊያን ርዕዮት ዓለም ከኢትዮጵያዊነት ትውፊትና ማንነት 180 ዲግሪ የተቃረነ ነው። የምዕራባዊ አስተሳሰብ የሰው ልጅ የዓለም ቁንጮ አድርጎ ያስቀምጠዋል። እግዚአብሔር የለም ወይንም ምንም ሚና አይጫወትም ይላል። ኢትዮጵያዊ ግን በትውፊታችን ፈጣሪ ነው በአምሳሉ የፈጠረን ብለን እናምናለን ሁሉ ነገራችንም ከዛ ይከተላል። ለዚህም ነው የጠ/ሚ አብይ አህመድ የይቅርታ፤ ፍቅር እና ሰላም መልዕክቶችን በደስታ እና ጉጉት የምንቀበለው። እንደዚህ አይነቱ መልዕክት የተም ምዕራብ ሀገር እንደ ህፃንነት ነበር የሚታየው። ስለ ልማት፤ ነፃነት፤ መብት ነው የምዕራብ ሀገር ውይይት። እግዚአብሔር የለምና።

ታሪክ ረዥም ነው። 500 ዓመት በፊት ቻይና ከሁሉም «የሰለጠነች» ነበር። 60 ዓመት በፊት ቻይና ወደ 40 ሚሊዮን ህዝቦቿን ገደለች ግማሽ ሀገሪቷ በርሃብ እየተሰቃየ ነበር። 2000 ዓመት በፊት ስሜን አውሮፓ በሮሜዎች ዘንድ የያልሰለጠና የአረመኔ ስፍራ ነበር። ዛሬ ደግሞ ከዓለም በሙሉ የሰለጠው ጎራ ይባላል። 60 ዓመት በፊት ኢትዮጵያ በዓለም ደረጃ ታላቅ ክብር ነበራት። ዛሬ እንደ ለማኝ ትታያለች። እኛ ኢትዮጵያዊያን ይህንን ብናስታውስ ጥሩ ይመስለኛል።

እውነት ስልጣኔ ፍቅር እና ሰላም ነው። የኛ የኢትዮጵያዊያን በዚህ ረገድ ከማንም ልናንስም ልንበልጥም እንችላለን የኛ ፋንታ ነው። ግን የሰው ልጅ በመሆናችን ከማንም አናንስም አንበልጥምም። የዝቅተኛ ስሜታችንም በምንም መለክያ ተገቢ አይደለም። እጅግ ጎጂም ነው። ሌላውን ምዕራባዊያንም ለመገልበጥ መሻህ ዋጋ የለውም ጎጂ ነው። ማንነታች ከፈጣሪያችን የተሰጠን ነውና ምንም የምናፍርበት ሊሆን አይገባም። እርግጥም ለሌሎች ምሳሌ ሆነን መገኘት ነው ያለብን ድሮ ሆነን እናውቃለን አሁንም የማንሆንበት ምክንያት የለም።

Tuesday, 26 June 2018

ስለ ውጭ ሀገር የተወለዱ ያደጉ ልጆች የእናት ቋንቋቸውን አለመቻል ጉዳይ…

በውጭ ሀገር ኑሮ ደጋግመን ያየነው ታሪክ… በአዋቂ እድሜ ያሉ ኢትዮጵያዊያን በቋንቋቸው እየተነጋገሩ እያሉ አንድ ልጅ ወደነሱ ይመጣል። አዋቂዎቹ ልጁን "Hi, how are you?" ይሉታል ወድያው ንግግራቸውን ወደ እንግሊዘኛ (ጀርመንኛ ወዘተ) ይቀይራሉ! ልጁ አማርኛ፤ ኦሮምኛ፤ ትግርኛ ወይንም ሌላ የኢትዮጵያ ቋንቋ ይችል አይችል አያውቁም ግን ሳያስቡት አይችልም ብለው ገምተው በእንግሊዘኛ ያናግሩታል።

ሁላችንም እንደምናውቀው ውጭ ሀገር የተወለዱ ወይንም በልጅነታቸው ወደ ውጭ ሀገር የሄዱ ልጆቻችን አብዛኞቹ የእናት ቋንቋቸውን አይችሉም። አዎን የተወሰኑ የሚችሉ አሉ ማንበብ መጻፍም የሚችሉ አሉ ግን በርካታው አንዳንድ ቃላት ከመስማት አልፎ አይችልም።

በአንጻሩ በርካታ የሌሎች መጤዎች (ኢሚግራንት) ልጆች የእናት ሀገራቸውን ቋንቋ ይችላሉ። አንዳንዱ ህብረተሰብ የልጅ ልጆቻቸውም ቋንቋቸውን ይችላሉ። ግን አብዛናው ኢትዮጵያዊ ወላጅ ይህንን እውነታ አያውቅም አይገነዘብም። ውጭ የሚኖሩ ልጆች የእናት ቋንቋቸውን አይችሉም ብለን ደምድመናል።

ሆኖም «ለምንድነው ልጆቻችን የእናት ቋንቋቸውን የማይችሉት» ጥያቄ ሁላችንም ደጋግመን እንጠይቃለን። ምዋለ ህጻናት («ዴይኬይር») ስለሚውሉ ነው እንላለን። ትምሕርት ቤት ነው እንላለን። ኑሮ ለማሸነፍ ስለምንሯሯጥ ልጆቻችንን ቋንቋ ለማስተማር ጊዜ ስለሌለን ነው እንላለን። ስንፍነታችን ነው እንላለን። የተለያዩ ምክንያቶች እንሰጣለን።

ግን እነዚህ ምክንያቶች ሁሉን ሌሎች መጤዎችን ይመለከታሉ! ሜክሲካኖች፤ ሌሎች ሂስፓኒኮች፤ ቻይናዎች፤ ህንዶች፤ ጣልያኖች፤ ግሪኮች፤ ሶማሌው፤ አረቦች፤ ቱርኮች ወዘተ ይመለከታቸዋል። እነዚህም ልጆቻቸውን መዋለ ህጻናት እና ትምሕርትቤት  ይልካሉ። እነዚህም እንደኛው ይሰራሉ «ኑሮን ለማሸነፍ» ይጥራሉ ትርፍ ጊዜ የላቸውም። ከነሱ መካከል ሀብታም እና ድሃ አለ። የቀለም ትምሕርት የተማረ ያለተማረ አለ። ከትውልድ ሀገሩ ትንሽ እንግሊዘኛ የተማረ ያልተማረ አለ። አንዳንዱ እንግሊዘኛን እንደ ስልጣኔ የሚቆጥር እና እንደ ጣኦት የሚያመልከው አለ (አንዳንድ ህንዶች) አንዳንዱ ደግሞ ለእንግሊዘኛ ግድ የለውም። ሁሉም አይነት መጤዎች አሉ። ግን እነዚህ በሙሉ ከኛ ኢትዮጵያዊያን በተሻለ መልኩ የእናት ቋንቋቸውን ለጆቻቸው ያስተላልፋሉ።

ታድያ ለምንድነው የኢትዮጵያዊ ልጆች ከነዚህ ሁሉ ተለይተው የእናት ቋንቋቸውን የማይችሉት? መልሱ የሚመስለኝ እንዲህ ነው፤ የልጆቻችን የእናት ቋንቋቸውን አለማወቅ ሳናውቀው ባህል ሆኗል። የመጀመርያ ኢትዮጵያዊ መጤዎች በተለያዩ ምክንያቶች ልጆቻቸውን ቋንቋ ሳያስተምሩ ቀርተው የውጭ ሀገር ልጅ የእናት ቋንቋ አለማወቅ በህብረተሰባችን የተለመደ ሆነ። ይህ "expectation" ባህል ሆነብን።

ምክነያቱ ከዚህ የሚያልፍ አይመስለኝም። ከላይ እንደጠቀስኩት ከሌሎች መጤዎች ምንም አንለይም። ስለዚህ የባህል ጉዳይ ነው። የአቅም ማጣት ወዘተ አይደለም። ይህን ባህል ከቀየርን እና ልጆቻችን እንደ ማንም ልጆች የእናት ቋንቋቸውን ሊያውቁ ይችላሉ ብልን ከደመደምን አንድ ትልቅ እርምጃ ወሰድን ማለት ነው።

ሁለተኛው እርምጃ ልጆቻችንን በቋንቋችን ብቻ ማናገር ነው። ከተወለዱ ጀምሮ ወላጅ እና ልጅ በማንኛውም ቦታ በቋንቋቸው ብቻ ነው የሚነጋገሩት የሚል ህግ ማውጣት ነው። ቀላል ነው። የተለየ ነገር አያስፈልግም። ቋንቋውን ቅጭ ብሎ ማስተማር አያስፈልግም። ከወላጅ ምንም ትርፍ ስራ አይጠይቅም። ልጆችን በቋንቋ ማነጋገር ብቻ ነው። ሌሎች ሁሉ እንደዚሁ ነው የሚያረጉት። እርግጥ መጻፍ እና ማንበብ መማር ትምሕርት ይጠይቃል ግን በልጅነት ከተጀመረ ትንሽ ጊዜ ነው የሚጠይቀው። ልጆች በትንሽ እድሜ በቀላሉ ፊደሉን መማር ስለሚችሉ ከዛ በኋላ እራሳቸው ይቀጥሉበታል።

በዚህ መልኩ ልጆአቸውን ቋንቋቸውን ያስተማሩ ሰዎች ሁላችንም እናውቃለን። ቁጥራቸው ትንሽ ቢሆንም መጻፍ ማንበብ የሚችሉ አሉ። ግእዝም የሚችል አውቃለሁ! እንደሚቻል መረጃ አለን ትርፍ ስራ እና ጊዜ እንዳማይፈጅም መረጃ አለን። ስለዚህ እንበርታበት!

በመጨረሻ አንድ ነገር ልጨምር እወዳለሁ። የእናት ቋንቋን መቻል ጥቅሙ ምንድነው ብላቸሁ የምትጠይቁ ትኖራላችሁ። ጥሩ ጥያቄ ነው። ልጄን አሜሪካ ወልጄ የማሳድግ ከሆነ አማርኛ መቻሉ ምን ዋጋ አለው? ስፓኒሽ አይሻለው ይሆን? መቼም የእናት ቋንቋችንን ማውቅ አስፈላጊነቱን ሁላችንም ምክንያቱን መደርደር ባንችልም ከልባችን እናውቀዋለን። ግን ምክንያቶቹን እስቲ ልደርድር፤

1. ማንነት፤ ውጭ ሀገር የተውለደ ኢትዮጵያዊ ቢፈልግም ባይፈልግም እራሱን እንደ ሙሉ የውጭ ሀገር ዜጋ ሊቆጥር አይችልም። በሰው ልጅ ተፈጥሮ ምክንያት የአባቶቹ ማንነት ይጫነዋል ከዬት ናቸው ማን ናቸው ማለቱ አይቀርም። ሁላችንም ይህንን በተግባር አይተናል ልንክደው አንችልም። ቋንቋን ማወቅ ይህን የማንነት ስሜትን በተወሰነ ደረጃ ያሟላል።

2. ኢትዮጵያዊ ነን ሀገራችንን እንወዳለን እዚህ ስደተኛ ነን ብለን የምናምን ልጆቻችንን ኢትዮጵያዊ ማድረግ አለብን አይደለ? አይ ልጆቻችንን አሜሪካዊ፤ ጀርማን ወዘተ እናድርግ ይህዱ ከሆነ ጥሩ ግን ምን እያደረግን እንደሆነ እንወቀው። ዜጋን አልፎ መስጠት እንደ ትንሽ ነገር አኑቅጠረው። መብት ቢሆንም ለኢትዮጵያ ኪሳራ ነው።

3. በተዘዋዋሪ በርካታ ጥናቶች እንደሚያሳዩት የራስን ማንነት ማወቅ ለሌላ የኑሮ መስፈርት ይረዳል። ለትምሕርት፤ ከሰው ጋር ለመግባባት፤ ቁም ነገረኛ ለመሆን ወዘተ የራሱን ማንነት እና ከየት የመጣ እንደሆነ የሚያውቅ ልጅ በሁሉም ይሻላል።

ስለዚህ ልጆቻችንን የእናት ሀገር ቋንቋቸውን እናስተምር ወይም ብትክክሉ ለመናገር አንከልክል! በቋንቋቸው እናናግራቸው እና ወደ ፊት ማንነታቸውን የሚያውቁ የሚኮሩ ልጆች እንዲሆኑ እናድርግ።

-------------------------

Thursday, 17 May 2018

የ«አማራ ብሄርተኝነት» ትውፊታዊ ነውን?

የ«አማራ ብሄርተኝነት» ትውፊታዊ ነው ወይስ እንደ ሌሎች የጎሳ ብሄርተኞቻችን (ኤርትራ፤ ትግራይ፤ ኦሮሞ፤ ወዘተ) በፈረንጅ በምዕራባዊ በ«ተራማጅ» በማርክሲስት ፍልስፍና የተመሰረተ ነው?

እርግጥ ብዙ አይነት የአማራ ብሄርተኝነቶች አሉ፤ ለፖለቲካ ስልት ወይንም «ታክቲክ» ብቻ የሆነ አለ፤ በስመ አማራ ላለፉት 27/40 ዓመታት ለተበደሉት ፍትሕ መጠየቅያ የሆነ አለ፤ ዛሬ አማሮች ላይ የሚደርስባቸውን በደል ለመታገል የሆነ አለ፤ በሀገር ደረጃ በፖለቲካ ድርድር ለአማራ ህዝብ የሚቆም አለ፤ በሃሰት የታማው የአማራ ህዝብን ታሪክ እውነቱ እንዲታወቅ የሚንቀሳቀስ አለ፤ የአማራ ህዝብ ክብርና ማንነትን ለመመለስ የሚታገለው አለ፤ ወዘተ። ዛሬ እነዚህ ሁሉ አይነት እንቅስቃሴዎች በስመ አማራ ብሄርተኝነት ይጠራሉ።

ዞሮ ዞሮ ዋናው ነጥብ ይህ የፖለቲካና መሃበራዊ ንቅናቄ እራሱን የ«አማራ ብሄርተኝነት» ብሎ መሰየሙ ነው። አላማው ምንም ቢሆን በዚህ «አማራ ብሄርተኝነት» የሚለው ስም መጠራት ይፈልጋል። በዚህ ስም መጠራቱ ምን ይነግረናል? በተለይ በትውፊትና በተቃራኒው ምዕራባዊ ተራማጅነት ያለው ግንኙነቱ ምንድነው?

ደስ የሚለው ነገር የሁሉም አይነት የአማራ ብሄርተኝነት ምልክቶች ትውፊታዊ ናቸው። ለምሳሌ ዓፄ ቴዎድሮስ አንዱ ዋና የአማራ ብሄርተኝነት ንቅናቄ ምልክት ናቸው። የአማራ ታሪክን በትክክሉ ማስተዋወቅና መናገር ሌላው የአማራ ብሄርተኝነት አላማና ምልክት ነው። ግን ዓፄ ቴዎድሮስ እራሳቸውን ወይንም ሀገራቸውን ወይንም አገዛዛቸውን የአማራ ወይንም «አማራ ብሄርተኛ» ብለው ይሰይሙ ይሆን? የአማራ ታሪክ የምንለው በታሪክ ሰሪዎቹ እና በዘጋቢዎች ዘንድ የአማራ ታሪክ ይባል ነበር? የአማራ ብሄርተኝነትን ያንጸባርቅ ነበር?

ለነዚህ ሁለቱም ጥያቄዎች መልሱ «አይደለም» እንደሆነ ነው የማውቀው። ዓፄ ቴዎድሮስ እንደ ሁሉም ንጉሶቻችን በስመ ኢትዮጵያዊነት ነበር እራሳቸውን የሚመለከቱት። ታሪካችም እንዲሁ ኢትዮጵያዊነት ላይ ነው የሚያቶክረው አማራነትን አይደለም። ይህ ማለት «አማራ» የሚባል ህዝብ የለም አልነበረም ማለት አይደለም! መኖሩ በታሪክ በተለያየ ቦታ መመዝገቡ ይታወቃል። ግን እስከማውቀው ማንም በስመ አማራ አልተንቅሳቀስም። ትውፊታችንና ታሪካችን እንደዚህ ከሆነ እንዴት እራሱን «አማራ ብሄርተኝነት» ብሎ የሰየመ ንቅናቄ ትውፊታዊ ነው ማለት ይቻላል?

በሁለተኛ (ወይንም አንደኛ!) ደረጃ ጠቅላላ የጎሳ ብሄርተኝነት የሚባለው ነገር የምዕራባዊ የፖለቲካ ፍልፍና እንደሆነ ይታወሳል። በትውፊታዊ ፖለቲካ «ሀገር» ነው ያለው፤ «ጎሳ» የለም። ይህ አባባሌ ብዙ ነገሮች ስለሚያከማች ሁሉንም በዚህ ጽሁፍ አልጠቅስም ግን በጠቅላላ የ«ጎሳ ብሄርተኝነት» የዘመናዊ የምዕራባዊ ጽንሰ ሐሳብ ነው።

የምፈራው ነገር ይህ አዲሱ የአማራ ብሄርተኝነት ልክ እንደ በፊቶቹ የኤርትራ፤ የትግራይ፤ የኦሮሞ፤ ወዘተ ብሄርተኝነቶች በብሶት እና በበአድ ምዕራባዊ ርዕዮተ ዓለም የተመሰረተ ኢተውፊታዊ ንቅናቄ ይሆናል ብሄ ነው። የኤርትራ እና የትግራይ ብሄርተኝነት በመሰረቱ ጸረ ትውፊት ናቸው። በቀላሉ ምሳሌ ለህዝባቸው መሰረት የሆነው ሃይማኖትና ባህልን የሚጠላ ርዕዮተ ዓለም ነው እነዚህ ብሄርተኝነቶች የተመሰረቱት። የኦሮሞ ብሄርተኝነት እንደዚህም ቢሆን ቢያንስ ወደ ኦሮሞ ትውፊት ለመመልከትና እንደ ገዳ አይነቱን ተውፊት ማክበር ሞክሯል። ሆኖም መሰረቱ የማርሲስት የጨቋኝ ተጨቋኝ የጎሳ ብሄርተኝነት አስተሳሰብ ነው። የአማራ ብሄርተኝነትም እንደዚህ እንዳይሆን መጠንቀቅ ይኖርበታል። ግን እራሱን «አማራ» ብሎ ከሰየመ እዚህ ወጥመድ ውስጥ ቀድሞ ገብቷል ማለት ይመስለኛል።

ጎበዝ፤ ጠንካራ፤ ሀገር ወዳድ ምሁራን በተለይ ወጣቶች የአማራ ብሄርተኝነት ያቀፉ አሉ። ምክንያቱ ለሁላችንም ሊገባን ይገባል፤ ለብሶት መልስ ነው። የአስራት ወልደየስ ፖለቲካ የብሶት ሳይሆን እራሳቸው እንዳሉት የግዴታ ነበር። የዛሬው ግን የ27/40 ዓመታት ያመጣው ብሶት ነው። ብሶቱ በህወሓት ላይ ብቻ ሳይሆን በሁሉም፤ በድሮ ምሁራን፤ ልሂቃን፤ ተቃዋሚ፤ ወዘተ ነው። እኔ እንደሚመስለኝ የተማሪው ንቅናቄ ወደ እንደ ማርክሲዝም አይነቱ ምዕራባዊ ፍልስፍና እና ርዕዮተ ዓለም በብሶት ምክንያት እንደገባው የዛሬው ትውልድ በብሶቶች ምክንያት እንደ ቀድሞው ተማሪ ንቅናቄ ወደ ኢ-ትውፊታዊ (ምን አልባት ጸረ ኢትዮጵያዊ) የማይሆን አስተሳሰብ እየገባ ነው። ስለ ተውፊቱ ስላልተማረ በምዕራባዊ የቀለም ትምሕርት የሚሰግድ ህብረተሰብ ውስጥ ስላደገ ሳያውቀው ብዙ ኢ-ትውፊታዊ አስተሳሰቦች አድረውበታል።

ስለዚህ ጉዳዩን ወደ ኋላ ወደ መሰረታችን ተመልሰን አመለካከታችንን በሙሉ ከ«ሀ» ብንገመግም ጥሩ ይመስለኛል። ከዛ በኋላ ነው የአማራ ብሄርተኝነት ትውፊታዊ ነው ወይ የሚለውን ጥያቄ በትክክሉ ልንመልሰው የምንችል የሚመስለኝ።


Sunday, 25 March 2018

ስለ «አማራ» ያከው ውይይት

ስለ አማራ ማንነት ይሆን ወይም በሌላም አርእስት ስነወያይ ነገሮችን በጥራት እንድናይ ለመወያየት ለመከራከር ለመተቻቸት ብቻ ሳይሆን ግብ ለመምታት ከሆነ ከውይይታችን ከአስተሳሰባችን በስተ ጀርባ ዙርያውን ያለውን ሁኔታ አስተሳሰባችን መመልከት አለብን። ይህን ለማድረግ ዘንድ እስቲ እነዚህን ነጥቦች በደምብ እንመልከታቸው።

1. ሁሉም ውይይት "context" (ዐውደ ሁኔታ?) አለው። ዛሬ ያለው ሁኔታ ምንድነው? 60 ዓመት በፉት ይህ ውይይት ይኖር ነበር ቢኖርስ ምን ይመስል ነበር።

2. ለውይይቱ ምን አይነት አመለካከት ርዕዮት ዓለም እምነት ወዘተ ይዘን ነው የምንከራከረው? በጎሰኝነት ("identity") ፒለቱካ እናምናለን? ወይም የአገር ብሄርተኖች ("nationalist") ነን?

3. የምንጠቀምበት ቋንቋ ቃላቶች ምን ትርጉም አላቸው? «ጎሳ» ምንድንደው? «ህዝብ» ምንድነው? «አማራ» ምንድነው? «ማንንነት» ምንድነው?

4. የውይይታችን አላማ ምንድነው? ውይይቱን ማሸነፍ ነው? መስማማት ነው? እውነት ላይ መድረስ ነው?

5. የጠቅላላ አላማችን ምንድነው? ከአገራችን ሽኩቻ አድሎ ኢፍትሃዊነት እንዲጠፋ ሰላምና ፍትህ እንዲኖር ነው? ህወሓትን ከስልጣን ማውረድ ነው? ስልጣን መያዝ ነው? ጥሩ የሚመስለንን ሥርዓትን ማስፈን ነው?

6. ውይይታችን አቋማችን ከህዝቡ ዝንባሌ ጋር በተወሰነ ድረጃ ብቻ ቢሆንም ይሄዳል ወይ? ይህ ታላቅ ጥያቄ ነው። የ«ፌስቡክ» ብቻ ውይይት ነው? የልሂቃን ብቻ ውይይት ነው? የአዲስ አበባ ብቻ ውይይት ነው? የተማሪዎች? ወይም ከብዙኃኑ ምካከል ይህ ጉዳይ እንደ ቁም ነገር ይቆጠር ይሆን?

ሁላችንም እራሳችንን እነዚህን ጥያቄዎች ጠይቀን በአግባቡ መልሰን ነው ፍሬአማ ውይይት ሊኖርን ይሚችለው። 

እስቲ የኔን መልሶች ልስጣችሁ፤

1. ዛሬ የምዕራባዊ የማርክሲዝም የጎሳ ወይም ብሄሮች አስተሳሰብ ኢትዮጵያ ውስጥ ገብቶ በደምብ ሰክኗል። በ ኃይለ ሥላሴ ዘመን ተማሪዎቻችን ወደ ውጭ አገር ትምሕርትቤት ሄድው ያመጡት ርዕዮት ዓለም አገር ውስጥ መሰረት ጥሎ ጭርሽ ህገ መንግስታችንን በክሎታል የፖለቲካ መዋቀራችንን በይኗል። በመሀበረሰብ ደረጀ በፊት ከ«ልሂቃን» ያልወጣ አስተሳሰብ አሁን አማራ ኦሮሞ ሲዳማ ትግሬ ብዙኃኑም ያውቀዋል። ግን በትክክሉ ምንድነው የሚያውቀው? ቋንቋ ነው? «ዘር» ነው? «ቦታ» ነው? ማንነት ነው? የፖለቲካ ክፍል ነው? ብዚህ ዙርያ  የተለያዩ አመለካከቶች ቢኖሩም አብዛኞቻችን «አማራ» የሚለውን ቃል ድሮ የማንጠቀምበት ዛሬ እንጠቀምበታለን። ድሮ የፖለቲካ ትርጉም ያልነበረው ዛሬ አለው። ዛሬ ሰዎች በአማርነት ይከሰሱበታል። ይወነጀሉበታል። አንዳንዱ አማራ በመሆኔ ተጎጂ ነኝ ብሎ ያስባል። እጨቆናለሁ መብት የለኝም የሚል አለ። ባጭሩ ይህ ሁኔታ ላይ ነው ዛሬ የምንገኘው። 

2. ማንነት የሰው ተፈጥሮ ባህሪ ነው ብዬ አምናለው። በመንደር ካልሆነ በጠቅላይ ግዛት ካልሆነ በጎሳ ካልሆነ በአገር ሁላችንም አንዱ የማንነታችንን ክፍል ይህ ነው። እስቲ አንድ ምሳሌ እናስብ። አንድ ኢትዮጵያዊ አሜሪካ ለ20 ዓመት ኖሮ ዜግነት ተቀብሎ አሜሪካው ነኝ ይላል። ኢትዮጵያዊ ነኝም ይላል። ለምን ኢትዮጵያዊነቱን አይተወውም። ልም ልጆቹን የኢትዮጵያ ቋንቋ ያስተምራል ቢችልም የኢትዮጵያ ትምሕርትቤት ይልካል? ለመሆኑ አሜሪካና ኢትዮጵያ በሆነ ጉዳይ ቢቃረኑ ማንን ይሆን የሚደግፈው? ኢትዮጵያን ቢደፍግ ሌላው አሜሪካዊ ከሃዲ አይለውም ይሆን? ለሌላው አሜሪካዊ «ኢትዮጵያዊ-አመሪካዊ» ማለት ጎሳ ነው። አያችሁ የጎሳ ስሜት እንዴት የተፈጥሮ እንደሆነ። የተፈጥሮ ቢሆንም ብዙ ጎሳዎች ያሉበት አገር ውስት የጎሰኝነት ስሜት ከአገር ብሄርተኝነት ስሜት ከበለጠ የጎሳ ፉክክር ("ethnic competition") በፖለቲካ ምድር ውስጥ ያበዛና ለአገሪቷ ህልውና ለሰላም ለፍትህ አደገኛ ነው ይሚሆነው። ይህን ነው ዛሬ በኢትዮጵያ የምናየው። ይህ ምክነያት የአገር ብሄርተኛ ነኝ። ማለት ለሁላችን ሰላምና ለአገሪቷ ብልጽግና የጎሰኘት ስሜት ከአገር ስሜት በታች መሆን አለበት ብዬ ነው የማምነው። «ኢትዮጵያዊ ነኝ ቀጥሎ ኦሮሞ» ትሩ ነው። «ትግሬ ነኝ ቀጥሎ ኢትዮጵያዊ» ወደ ችግር ይመራል።

3. «ጎሳ» «ህዝብ» «ማንንነት» «አማራ» ለሁላችንም የተለያዩ ትርጉሞች አላቸው። ከላይ እንዳልኩት ለኔ የሰው ልጅ ማንነት ውስጥ አንድ የአገር ወይ ጎሳ ወይ መንደር ወዘተ ክፍል አለ። ስለዚህ ለኔ ይህ የማንነት ክፍል በ«ኢትዮጵያዊነት» ወይም «ኦሮሞነት» ወይም «ኦሮሞ-ኢትዮጵያዊነት» ወይም «ኢትዮጵያ-አማራነት» ወይም «ጎጃምነት» ወይም «አፍሪካነት» ሊሞላ ይችላል። ግን ሰውው «ጎሳ» እና «ህዝብ» እና «አገር» ሲለይ የፖለቲካ አቋምን ነው የሚገልጸው። ለምሳሌ አውሮፓ ከትናንሽ የንጉስ ግዛቶች «ጎሳዎች» ወደ አገሮች ("nation state") ሲቀየር «ጎሳ» የኋላ ቀር ነው ብለው ሰየሙ። ግን በጎስኝነት ዘመን የሚያራምዱት ጥላቻን ጦርነትን አሁን በ«አገር» ደረጃ በከፍ ያለ አቀም አራመዱት! ወደ «አማራ» የምንለው ቃል እንምጣ። የቃላቱ ትርጉም በመቶዎች ዓመታት እነደተቀየሩ ግልጽ ነው። የታሪቅ መጽሐፍቶች የድሮ አጠቃቀም ካሁኑ እንደሚለው ያሳያሉ። በቅርብ ዓመታት እራሱ ለምሳሌ ከሃረር እስከ ሸዋ መካከል «ነባር» ሙስሊም ኦሮሞዎች በቀር ሌላው «ክርስትያን» ነበር የሚባለው። ግን ነገሮች ይቀየራሉ። አሁን ከላይ እንደጠቀስኩት የማርክሲዝም ፖለቲካ ሰፍኖ ሁላችንም አማራ እንላለን ወይም ታግለን እራሳችንን እንቆጥባለን።

4. ስወያይ በተቻለ ቁጥር እውነት ላይ ለመድረስ ነው የምወያየው። አዎን አንድ አንድ ጊዜ ፍተናው ያሸንፈኛልና ትቢት ተሞልቼ ማሸነፍ ፈልጋለው አቋሜ ትክክል ቢሆንም ባይሆንም። ውይም ፈርቼ ወይም ለይሉኝታ መስማማት እፈልጋለሁ ስምምነት በውሸት የተመሰረተ ቢሆንም። ግን ደካማ ወገኔን ትቻ አላማየ እውነት ነው። ባልወደውም። ለምን እውነንት? እውነት ነው ለሁሉም የሚበጀው። አላማ እውነት ነው ማለት ለታክቲክ ወይም ለጊዜያዊ ሰላም ቁስል እስኪድን ወዘተ ተብሎው ዝም አይባልም ወይም አይዋሽም ማለት አይደለም። ገን የመጨረሻ ግቡ እውነት ነው።

5. እኔ ሰላምና ፍትህ ነው የምወደው። (አድሎ ሙስና አይኖር ማለት ፍትህ ይኑር ነው።) ሰው እንዳይጎዳ። ሰው ሌላውን ጉዳ እንዳይባል መጉዳት ከመጎዳት ይበልጥ ጎጂ ነውና። ከዛ ውጭ ማን ይግዛ ምን ሥርዓት ይኖር ግድ የለኝም። እንደ ኦርቶዶክስ ክርስትያንነቴ ወደ ንጉሳዊ አገዛዝ አደላለው ከሰው ወይም ሰዎች ይልቅ እግዚአብሔር መሪ ቢሾም ይሻላል ስለሚመስለኝ። ግን ይህ ሀሳብ ለ«ዘመናዊ» ሰው አይገባውም እንተወው። ለማንኛውም ሰላም ፍቅር ፍትህን የሚያበዛ ትልና ሽኩጫን የሚያሳንስ ሥርዓት ከተባለ ከሞላ ጎደል ምን መምሰል እንዳለበት እናውቃለን። 

6. እውነቱን ለመናገር ይህ ሀአማራ ማንነት ጉዳይ ከዲያስፖራና ፌስቡክ ውች ያን ያህል ትኩረት ያለው አይመስለኝም። በኔ እይታ (በኢህአዴግም ይመስለኛል!) ያለፉት ሶስት አራት ዓመት የህዝብ ተቃውሞ በመጀመርያ ደረጃ አድሎን በተለይ የ«ትግሬ አድሎን» ተመስርቶ ነው። ይህ በአማራ ክልል የተካሄደውን ተቃውሞንም ያካትታል። መፈከሩ ትግሬ አይግዛን ነው እንጂ አማራ ይከበር አይመስለኝም። በግሌ ያየሁት የሰማሁት እንደዚህ ነው። እንደሚመስለኝ ዛሬ አማራ የምንለው ህዝብ አሁንም በጣም ወደ ኢትዮጵያዊነት ያመዝናል ከአማራነት ይልቅ። ነገ አማራ ክልል በንዚን ቢገኝ ለአማራ ክልል ብቻ ይውል የሚል ጥቂት መሰለኝ። ትግሬ ምንም አያገኝ የሚሉ ብዙ ይኖራሉ ያሳዝናል እንጂ። ጥቃት ያመታው ችግር ነው። ግን አብዛኛው አማራ በለጸገች ከማለት ኢትዮጵያ በለጸገች ነው የሚለው።

እሺ በመጨረሻ ለ«ትግሉ» ተብሎ በአማራነት መታገሉ አይሻልም ወይ የሚለው ከመምህር ሐዚም አስራት ወልደየስ ዘመን ጀምሮ ያለ ጥያቄ አለ። ያኔ አልሰራም ከላይ እንደጠቀስኩት «አማራ» የሚባለው ስሜቱ ከአማራነት ይልቅ ኢትዮጵያዊነት እጅግ ስለሚበልት። አናሳ ብሄርም ስላልሆነ። የተጭቋኝ ስሜትም ስላልነበረው። ዛሬ ሁኔታው ጠቀይሯል በተወሰነ ደረጃ ግን አሁን ስኬታማ የ«አማራ የጎሳ» ትግል ለማካሄድ የህዝቡ ሁኔታ የሚፈቅድ አይመስለኝም።

እውነት ነው እንደዚህ አይነቱ ትግል ያስጎመዣል። እነ ሻዕብያ ህወሓት ኦነግ እንዳረጉት ስኬታማ ትግል ማድረግ ነው። የጎሳን የተፈጥሮ የማሰባሰብ ኃይል መጠቀም ነው። ግን ሁኔታው ካልፈቀደ ህዝቡ ማንነቱ ከዚ አይነት አስተሳሰብ ጋር የማይሄድ ከሆነ አሁንም አይሳካም። ሰከን ብሎ ማሰብ ነው።

በመጨረሻ ላስታውሳችሁ የምወደው ምሳሌዎቹ ወይም "template" የሆኑት እነ ሻዕብያ ህወሓት እጅግ አናሳ ስለሆኑ ለማሸነፍ ጎሰኝነትን ግድ መጠቀም አለብን ብለው ያምኑ ነበር። ግን እስካማውቀው ኢ-ህወሓት የሆንነው ወይም «ተቃዋሚ» የሆንነው የአገሪቷ 90% ወይም 80% ወይም 70% ነን። የጎሰኝነት የፖለቲካ ኃይል መሰብሰብያ "ethnic leverage" አስፈላጊ ነው ልንል አይገባም። ትንሽ የፖልቲካ ብስለት ትብብር አብሮ መስራት መተማመን ጉዳዩን ትላንት ይጨርሰው ነበር።

Wednesday, 21 March 2018

«ሴኩላሪዝም»

ትንሽ አመታት በፊት አንድ የመንግስት ስራተኛ የሆነ ዘመዴ የኦርቶዶክስ መዝሙር ከመስሪያቤት ኮምፕዩተሩ ላይ ማዳመጥ ክልክል እንደተደረገ ነገረኝ። ለምን ብዬ ስጠይቀው ክርስትያኑም ሙስሊሙም የሚፈልገውን መዝሙር፤ ስብከት፤ ትምሕርት እያዳመጠ እና ኮምፕዩተሩ ላይ ሥዕል እየለጠፈ የሰራተኞች እርስ በርስ ግጭት ሊፈጥር ይችላል ተብሎ ተከለከለ አለኝ። የሚገርመው ነገር ግን 1) ከመስሪያቤቱ እንደዚህ አይነት ግጭቶች አልነበሩም እና 2) ክልከላው በተራ ትዛዝ ሳይሆን ከከፍ ያለ የአስተዳደር ደረጃ በመመርያ ምልክ የተላለፈ ነበር። የመመርያው ርዕስ ደግሞ «ሴኩላሪዝም» ነበር።

ይህን ታሪክ ስሰማ እጅግ አዘንኩኝ። መቼ ነው መንግስቶቻችን፤ ምሁሮቻችን እና ልሂቆቻችን የምዕራብ ዓለም ርዕዮት ዓለምና ፍልስፍና ይዘው አገራችን ላይ መጫን የሚያቆሙት? ካለፉት የ100 ዓመታት ታሪካችን አይማሩምን?

እስቲ «ሴኩላሪዝም» ባጭሩ ምን እንደሆነ እንመልከት። «ሴኩላሪዝም በዓለማችን እግዚአብሔር የለም/አይሳተፍም ብሎ ማሰብ ነው»። ሴኩላሪዝም እግዚህብሔር ሊኖር ላይኖርም ይችላል ግን ከዓለማችን ከሕይወታችን ከለት ኑሮአችንም አይሳተፍም የሚለው አመለካከት ነው። እግዚአብሔር ካለ እዛው ከዙፋኑ ወይንም ገነቱ ተቀምጦ ይመለከተናል። በሃይማኖት እና በእግዚአብሔር በግል ምርጫችን ልናምንባቸው የምንችል የእምነት ሥርዓቶች ናቸው። በሀሳብ ደረጃ ነው የምናምንባቸው ካላሰኘን ደግሞ ከሀሳባችን እናስወግዳቸዋለን!

ይህ አስተሳሰብ በተለያየ መንገድ ወደ ክርስትያን የሆነውን አስተሳሰብ ገብቷል። «ዓለማዊ» እና «መንፋሳዊ» የምንላቸው ቃላት በተሳሳተ መንገድ እንጠቀማለን። ዓለማዊ ስንል ስራችን፤ ትምሕርታችን፤ ገበያችን፤ ንግዳችን ወዘተ ነው። እግዚአብሔር እነዚ ነገሮች ውስጥ እንዳለ አናምንም። ስለዚህም ነው በነዚህ የህይወት ዘርፎቻችን ኢ-ክርስትያናዊ ነገሮች እያደረግን እያለን አማኞች ነን የምንለው። እሁድ እሁድ ግን ቤተ ክርስትያን ሄደን ወደ መንፈሳዊስ ዓለም እንሸጋገራለን። እዛ ጨዋ ነን፤ ጥሩ ስነ መግባር አለን፤ ጭንቀቶቻችንን አስተንፍሰን ወደ ዓለማችን እንመለሳለን።

ይህ ግን የውሸት ክርስትና ነው። በእምነታችን እግዚአብሔር በሁሉም ቦታ በሁሉም ነገር አለ። «እኔ የቅርብ አምላክ ነኝ እንጂ የሩቅ አምላክ አይደለሁም። ሰው በስውር ቢሸሸግ፥ እኔ አላየውምን? ሰማይንና ምድርንስ የሞላሁ እኔ አይደለሁምን? ይላል እግዚአብሔር።» ኤር 23:23-24።

ስለዚህ ትምሕርት ቤት ብሄድ፤ መስሪያ ቦታ ብሄድ፤ እርሻዬ ላይ ብሆን፤ ትራንስፖርት ላይ ብሆን፤ መጠጥ ቤት ብሄድ፤ በሁሉም ቦታ እግዚአብሔር አለ። ሕይወታችንን እግዚአብሔር ያለበትና የሌለበት ብለን ልንከፋፍለው አንችልም። በሁሉም ቦታ በሁሉ ደቂቃ ከኛ ጋር ነውና።

ይህ የሚያሳየን የሰው ልጅ ክርስትያንም ሴኩላሪስትም አብሮ ሊሆን አይችልም። ብዙዎቻችን ወደዚህ ስህተት ብንገባም ሊሆን የማይችል ነገር ነው። ለክርስትያኖች እግዚአብሔር ልኬት የለውምና። በተጨማሪ ሴኩላሪዝም እግዚአብሔርን ከለት ኑሮአችን ማጥፋት ስለሚፈልግ የክርስትና ተቃራኒ ብቻ ሳይሆን ጠላት እንደሆነ ግልጽ ነው።

«እናንተ ኦርቶዶክሶች፤ ሙስሊሞች፤ ፕሮቴስታንቶች አብሮ መኖር አትችሉም። ስለዚህም (እግዚአብሔራን ተክቼ!) ከላያችሁ ሆኜ አስተዳድራችኋለሁ» ይላል ሴኩላሪዝም / ሴኩላሪስቱ። «እኔ ነኝ ስልጡኑ፤ ከማንም ጋር የማልጋጨው፤ ከሁሉም ጋር የምግባባው፤ ሁሉንም የማከብረው» ይላል። እውነቱ ግን ሴኩላሪስቱ እንደዚህ ሲል ሁሉንም በሰላም ለመጠበቅ ሳይሆን አላማው ይህን አስመስሎ «እግዚአብሔር የለም» የሚባለውን ሃይማኖትን ለማስፋፋት ነው። እግዚአብሔር ከአዕምሮአችን ብቻ ነው ያለው እንጂ ከስራ ቦታችን፤ ገበያ ቦታችን፤ መንገዶቻችን፤ ሚዲያዎቻችን፤ ከለት ኑሮአችን የለም ብለን ካመንን ቀጥሎ እግዚአብሔር የትም የለም ማለት የሚቀጥለው ቀላል እርምጃ ነውና!

በተጨማሪ እግዚአብሔር ከለት ኑሮአችን ከሌለ የማህበረሰብ የአገራችን ድንጋጌዎች ከየት ሊመጡ ነው? ከሴኩላሪዝም ርዕዮት ዓለም ከ«እግዚአብሔር የለም» ሃይማኖት ሊመጡ ነው! አያችሁ ሴኩላሪዝም እራሱን ገለልተኛ አድርጎ እንዴት «እግዚአብሔር የለም» ሃይማኖትን ሰተት ብሎ እንደሚያሰፍን።

ኢትዮጵያ የሃይማኖት አገር ናት። ታሪካችን ትውፊታችን ከዚህ የተያያዘ ነው። ማንነታችን ይህ ነው። ሴኩላሪዝም ደግሞ የህን አፍርሶ «እግዚአብሔር የለም» ሃይማኖትን ነው ማስፈን የሚፈልገው። ይህ ሂደት እንዴት እንደሚሰራ ለማወቅ የምዕራብ ዓለሙን ያለፈውን 400 መቶ ዓመት ታሪክ መመልከት ነው። ስለዚህ ሴኩላሪዝም ኢ-ኢትይጵያዊ እንደሆነ ተረድተን ወደ አገራችን ሰተት ብሎ እንዳይገባ መጠንቀቅ አለብን። በተለይ ደግሞ ወደ ልባችን ሰተት ብሎ እንዳይገባ መጠንቀቅ አለብን።

Friday, 2 March 2018

የምዕራባዊያን አገራት አምልኮ

የአባቴ ትውልድ የምዕራባዊያን አገሮችን የሚተቹባቸው በርካታ ጉዳዮች ነበሩ። ዘረኛ ናቸው። ታላቂቷ ምዕራባዊ አገር አሜሪካ አሁንም በጥቁር ዜጎቿ ታላቅ ግፍ እያደረሰችባቸው ነው። ዓለምን በቅኝ ግዛት አሰቃይተዋል። ቅኝ ግዛታቸውን እየተውዉ ቢሆንም አሁንም በ«አዲሱ ቅኝ ግዛት» መርህ ዘንድ ጥቅማቸውን የማያስከብሩ መንግስታትን በመፈንቀለ መንግስትና የተለያዩ ዘዴዎች ያፈርሳሉ።

የአሁኑ ትውልድ ደግሞ የምዕራባዊያን አገሮችን እንደ ጣዖት የሚያመልክ ይመስላል። ነፃነት ከነሱ ጎራ ነው የሚገኘው። ተራማጅነት ከነሱ ነው። ሀብት ከነሱ። ዴሞክራሲ ከነሱ። ቴክኖሎጂ ከነሱ። ስነ መግባር ከነሱ። ወዘተ።

በኔ ኢይታ ይህ አምልኮ ለአገራችን ለያንዳንዳችንም አደገኛ ነው። ለምን ብትሉኝ ይህ አመለካከት ከባህላችን፤ ትውፊታችን፤ ማንነታችን ነጥቆ እንደ ስሩ የተነቀለ አትክልት ነው የሚያደርገን።

ስለዚህም ቢዚህ ርእስ ዙርያ የተወሰኑ ጽሁፎች ለማዘጋጀት አቅጅያለሁ። የኢትዮጵያዊነት፤ የሰውነት፤ የማንነት ጉዳይ የተሳሰረበት ርእስ ነው። የምዕራባዊው ፕሮፓጋንዳ እጅግ ከባድ ነው። በመሰረታዊ አስተሳሰባችንን፤ አስተያየታችንን፤ አስተነፋፈሳችንንም ታላቅ ሚና ተጫውቷል። መሰራታዊ ሃሳቦቻችንና ቋንቋችንም ቀይሯል መቀየሩንም አናውቀውም! ይህ ሁሉ በደምብ ልናየው ይገባል።

ጽሁፎቼን ስጽፍ በተለምዶ በመጀመርያ እንደ ክርስቲያን በማቀው ክርስቲያናዊ አመለካከት ነው የምጽፋቸው። እምነቴ በሁሉ ነገር ኢግዚአብሔር አለ ብሎ ሰለሚያስተምር እንቋን የማንነት ጉዳይ ምንም ነገር ከዚህ መነጽር ውጭ ማየት አይቻልም።

ለጽሁፎቼ እንደ መግብያና ሀሳብ ማንሸራሸርያ እስቲ እነዚህን ቃላቶችን እናስባቸው፤

ዘመናዊነት (modernity)
መሻሻል ወይም እድገት (progress)
ዴሞክራሲ (democracy)
ነፃነት (freedom)
ሰው (Man)
ፍትህ (justice)
ልማት (development)
አገር (nation)
ጎሳ (tribe - in the neutral sense)
ተፈጥሮ (nature)
ፍቅር (love)
ስልጣኔ (civilization)
ሴኩላሪዝም (secularism)

Friday, 16 February 2018

ጨቋኝና ተጨቋኝ

እንደተረዳሁት ባለፈው ባወጣው መግለጫ ኦህዴድ የኢትዮጵያ መሰረታዊ የጭቆና ታሪክ የ«መደብ ጭቆና» ነበር እንጂ የ«ብሄር ጭቆና» አልነበረም ብሏል። ለዚህ አቋማቸው ኦህዴድን አደንቃለው አመሰግናለውም። ከረዥም ዓመታት የተሳሳተ እምነታቸው መቀየር ከባድ ነውና ጥንካሬና ህሊና ይጠይቃል። ዛሬ በሃገራችን ያለውን ከፍተኛና ኢ-ጤናማ የጎሳ ውጥረትንም ተገንዝበው የተሳሳተ ርእዮተ ዓለማቸውን ገምግመው ሃሳባቸውን ቀይረው ይህንን በይፋ ማውጣታቸው ትልቅ ነገር ነው። ደግሞ ከሌሎች አጋር ፓርቲዎቻቸው ቀድመው ይህን ማድረጋቸውም ሊደነቅላቸው ይገባል። እነ ለማ መገርሳ ለኢትዮጵያዊነት ታላቅ አስተዋጾ እያደረጉ ነው።

ሆኖም ይህ ዜና በሃገራችን መሰረታዊ የሆነ አሳዛኝ አስተሳሰብ አሁንም እንዳለ ይገልጻል? «ጨቋኝ» እና «ተጨቋኝ» እራሱ የተሳሳተ ቋንቋ ነው። ጽንሰ ሃሳብ የመጣው ከውሸትና ኢባህላዊ የሆነ የምእራባዊ የኮምዩኒስት አስተሳሰብ የመነጨ ነው። እስቲ አንድ እርምጃ ወደ ኋላ ተመልሰን ለምንድነው የሰው ታሪክ በ«ጨቋኝና ተጨቋኝ» የሚለው አስተሳሰብ መወሰን ያለበት? እንደዚህ አይነቱ አስተሳሰብ በሃሳብም ደረጃ በተግባርም ግጭት፤ ቅሬታ፤ ቂም፤ ጦርነት፤ ግድያ፤ አብዮት ወዘተ የሚያስገድድ ነው። አንድነት፤ ፍቅር፤ ይቅርታ፤ ትህትና፤ መስማማት ወዘተ የሚቃረን አስተሳሰብ ነው።

አልፎ ተርፎ ማን ግለሰብም ህብረተሰብም ፍፁም ንፁሃን ፍፁም ጥፋተኛ የሆነ የለም። እያንዳዳችን ጨቁነናል ተጭቁነናል፤ በድለናል ተበድለናል፤ ወደናል ተወደናል፤ ተስማምተናል ተጣልተናል፤ ተሳስተናል ስታታችንን አምነን ይቅርታ ጠይቀናል፤ ቂም ይዘናል ይቅርታን ተቀብለናል። በዚህ ዓለም እኔ ነኝ ንጹ ተጨቋኝ የሚል የራሱን ጥፋት ስለማይመለከት ወደ ከባድ ጥፋጡስት ይገባል ሰፊ በደልም ይፈጽማል።

በዚህ ጉዳይ ታላቅ የሩሲያ ደራሲ አለክሳንደር ሶልዠኒትሲን ያሉትን በደምብ ሊገባን ይገባል፤
ከእስርቤታችን አልጋ የሆነው የበሰበሰው ገለባ ላይ ጋደም ብዬ ነው ለመጀመርያ ከውስጤ የበጎ መንፈስ የተሰማኝ። ቀስ በቀስ መረዳት የጀመርኩት ይህ ነው፤ ጥሩና ክፉን የሚለየው መስመር በሀገሮች፤ መደቦች፤ የፖለቲካ ፓርቲዎችም መካከል አይደለም የሚያልፈው፤ ይህ መስመር የሚያልፈው በያንዳንዱ የሰው ልብ መኻል ነው። መስመሩ እድሜአችን በሙሉ ከውስጣችን ወደፊት ወደኋላ ይላል። በክፉ የተሞሉ ልቦችም ቢያንስ ቅንጣት ያህል ጥሩነት ይኖራል፤ ከሁሉም ጥሩ ከሚባለውም ልብ ከአንድ ጥጓ ትንሽ ክፉነት ይኖራል።
በየቦታው እየዞሩ ያሉ ክፉ ስራ የሚሰሩ ክፉ ሰዎች ቢኖሩና እነሱን ከኛ መለየትና ማጥፋት ብቻ ቢሆን ኖሮ እንዴት ቀላል ነበር? ግን ጥሩና ክፉን የሚለየው መስመር ከያንዳንዱ የሰው ልጅ ልብ መካከል ነው የሚያልፈውና ማን አለ ከራሱ ልብ ቁራጭ ቆርጦ ለማጥፋት ፈቃደኛ ይሆነ?
ሶልዘኒትሲን ኮምዩኒስት የነበሩ ወታደር የነበሩ ስታሊን ለዓመታት በሞት እስር ቤት (ጉላግ) ያሰራቸው ከሩሲያ ወደ ኦርቶዶክስ ሃይማኖታቸው የተመለሱ የሩሲያ ጀግና ነበሩ። ተጨቋኝ ነኝ ማለት የሚገባቸው ነበሩ። ለሃገረቸው ጦርነት ተዋግተው በማግስቱ የታሰሩ ናቸው። አለምንም ጥርጥር ተጨቋኝ ነኝ ማለት የሚገባቸው ነበር። ግን እስር ቤት የሌሎችን ሳይሆን የራሳቸውን ኃጢያት እንዲገለጽላቸው አደረገ! የሰው ልጅ እውነተኛ ባሕርይ እንዲረዱ አደረገ። የሰው ልጅ ችግርም እንዴት መቅረፍ እንደሚቻል ገባቸው። በጦርነት፤ በማስወገድ፤ በማባረር፤ በመወገን ሳይሆን በንስሃ፤ በመስማማት፤ በመከባበር፤ በመቻቻል ነው።

ይህ ሩሲያዊ ሶልዠኒትሲን የዘመኑን «ጭቋኝና ተጨቋኝ» አስተሳሰብን ትተው የእውነትን ባህላዊ የኢትዮጵያዊ አስተሳሰብ ነው የገለጹት። ሩሲያዊው ኦርቶዶክስ ባህላችንን ያስታውሱን። ለምንናውም የኢትዮጵያ ባህል፤ ማንኛውም ሃይማኖት፤ ይህ የ«ጨቋኝና ተጨቋኝ» ርእዮተ ዓለም በአድ ነው። በአድ ነው። ሚስኪኖቹ የጃንሆይ ተመሪዎች ወደ ሃገራችን ከምእራብ ሃገራት ያመጡት መርዝ ነው። መርዙን እናውጣው። ወደ እራሳችን እንመለስ።

Thursday, 28 December 2017

ስለ የለማ መገርሳ ምሳሌ የሆነ ንግግር

ለማ መገርሳን አላውቃቸውምም ባውቃቸውም ስለማንነታቸው ምንም ማለት አልችልም፤ ይህ የእግዚአብሔር ጉዳይ ነውና።
ሆኖም አቶ ለማ ይሚሰጡትን ንግግሮች አድምጬ እጅግ ጥሩና አስተማሪ እንደሆኑና ለሉላችንም አስፈላጊ መልክቶች እንደሚያስተላልፉ ተገንዝብያለው።

ከባህር ዳር በበአዴን ስብሰባ የተናገሩትን እኚህን ዋና ነጥቦችን ላተንትን፡

1. ትህትና፡ አቶ ለም አንድም እሳቸውም ድርጃታቸውም የሰራውን ነገር አልወደሱም። አንድች። በአንጻሩ ያሉትን ችግሮች አለ ህፍረት ሙሉ በሙሉ ዘርዝረው በተዘዋዋሪ ሙሉ ሃላፊነት ተቀብለዋል። ማን ፖለቲከኛ ነው እንደዚህ የሚለው? ይህ ለሁላችንም እጅግ ታላቅ ምሳሌ ነው። ጣት ከመጥቆም ወደ ራስ ማየት ነው የችር መፍቴ።

2. ሃላፊነት፡ ላሉት ችግሮች ሃላፊነት ወሰደው ለመፍትሄውም ሃላፊነት ወስደዋል። እንደዚህ መደረግ አለበት ወይም እነዛህ እንደዚህ ማድረግ አለባቸው ሳይሆን እንደዚህ ማድረግ አለብን ነው ያሉት። ታልቅ ምሳሌ የሆነ አባባል ነው።

3. ኢትዮጵያዊነት፡ አቶ ለማ የኢትዮጵያዊነት እንዳለና እንዳልጠፋ፤ ለሰላምና ብልጽግና እንደሚያስፈልግ አስረግጠው ተናገሩ። 20 ዓመት በፊት ነውር የነበረውን «ኢትዮጵያዊነት» አኩሪ እንደሆነ ገለጸ። ይህ አባባል፤ በተለይ ከአንድ ኦህዴድ መሪ፤ እጅግ ጥንካሬንና ለእውነትና ሰላም መሻትን ያሳያል። ሌሎቻችንም እንደዚህ ብናስብ ይበጅ ነበር!

4. መልካም አስተዳደር (ሙስና)፡ የመንግስት ሹማምንት «ብቸኛይ ስልጣን» ስላላቸው ነው ችግሩ ብለዋል አቶ ለማ። ሚዛን ከህዝብ ወደ ሹማምንት ከመጠን በላይ አመዝኗል አሉ። ይህ ኢሃዴግን በተለይ የ100% ውሳኔውን የሚተች አነጋገር ነው። ኢህአዴግ ብችኛ ስልጣን ሊኖረው አይገባም። ወይም የፖለቲካ ውድድር በተወሰና ደረጃ ቢሆን ግድ ነው ማለቱ ነው። ከአንድ የኢህአዴግ አመራር አስደናቂ አባባል ነው።

5. ስለ ወጣቶች ሲናገሩ ከፖለቲካ ወደ ማህበራዊ ጉዳይ ከፍ አሉ። ወጣቱን ለቴለቪዥንና ኢንተርኔት መተው ሳይሆን ማሳደግ እንዳለብን አስታወሱን። ከዛም በላይ ግን የወደኩላቸው ቤተሰብ ዋና መሆኑን ማስረዳታቸው ንው። ማንም ኢትዮጵያዊ ምህር ቤተሰብን ከትምህርት በዚህ ማንገድ ሲያስቀድም ስምቼ አላውቅም። ትምህርት ትምህርት ትምህርት ነው የሁላችንም ጭህወት። ግን ትምህርት መሳርያ ነው ቤተሰብ ማንነት ነው የሚለውን  ከዚህ በፊት ማንም ሲል ሰምቼ አላውቅም። እጅግ ጠንካራ ምልክት ነው ያስተላለፉት፡

6. በእህአዴግ ዘመን በተለያየ መድረክ የተዘለፉት ምሁራን እንዳ ማንኛውም የህዝብ ዘርፍ ለሃገሪቷ አስፈላጊ እንደሆኑ ሲያሳስበን አቶ ለማ አንድ ጉዳትን ያመጣ ቁስል አዳነ።

7. የጎሰኝነት ለሁሉም ያለው አደጋ አስረግጠው ተናገሩ። ያመጣው ጥላቻና ቅሬታ ለሁሉ ሰውና ለሃገሪቱ ጎጂ መሆኑን ማስረገጣቸው ለሁላችንም ታላቅ ማስተንቀቂያና ምሳሌ ነው። አንድነት ደግሞ የሁሉ ችግራችን ቀድሞ መፍቴ መሆኑን ገለጹ። እውነት ነው። ማንም ችግር አለአንድነት ሊፈታ አይችልም፡

8. በታሪካችን ማፈር ሳይሆን ኮርተን ጥሩውን እንደምሳሌ ወስደን መጥፎውን አስወግደን ግን ሃላፊነቱን በጋራ ተቀብለን መኖራለብን። ይህ ታላቅ የአንድነት መንገድ ነው። ታሪቅ የኔ ወይም የሱ ሳይሆን የጋራ አድረግን መያዝ አንድነትን ይየሚያዳብር ነው።

እግዚአብሄር አቶ ለማ እንዳለው ያድርግለት። ከባድ ስራ ነው ያለው። የኦህዴድ መሪነት ከባድ ስራ ነው ከጎሰኞች ጋር የሚያጋፍጥ ነውና ሚዛን ጠብቆ ነው መራመድ የሚችለው። በዚህ ጉዞአው ሁላችንም ፍርድ ሳይሆን ድጋፍ እንድንሰጠው ይገባል ብዬ አስባለው።