Showing posts with label ባህል. Show all posts
Showing posts with label ባህል. Show all posts

Thursday, 9 August 2018

የበጎ አድራጎት ድርጅት እና ማህበር ህግ ይበልጥ ይጠንክር

እንደሚታወቀው ኢህአዴግ ዘጠኝ ዓመት በፊት ባሳወጀው ህግ በሰባዊ መብት፤ የብሄር ብሄረሰብ ጉዳዮች፤ የጾታ ልጆች አካል ጉዳተኞች ጉዳዮች ወዘተ የሚሰሩ በጎ አድራጎት ድርጅቶች (በአድ) ከ90% በላይ ገቢአቸውን ከሀገር ውስጥ ማግኘት አለባቸው። ህጉ ሲረቀቅ የተተቸው ምክንያት ኢህአዴግ የሰባዊ መብት ጥሰቶቹ በድርጅቶች እንዳይመረመሩ ኣና ዓለም አቀፍም ሀገራዊም አይን እንዳይበዛበት ነው። እውነትም ህጉ የተመሰረተው ዋና ምክንያት ይህ ነው።

ግን አሁን በመጣው የፖለቲካ ለውጦች መንግሥት የሰባዊ መብት መጣስን እየተወ ነው ለህብረተሰቡም ለድርጅቶችም የመተቸት እና የይግባኝ ማለት ነፃነት ሰጥቷል። እንደ ፍርድ ቤት አይነት መዋቅሮችም እየተሻሻሉ ነው። ፖለቲካውም ወደ ሰላም እየተቀየረ ነው። ስለዚህ ሀገር ውስጥ ያለው ህብረተሰብ ስለ ሰባዊ መብት ወይንም ሌላ ጉዳይ የሚሟገት ድርጅት በሰላም እና አለ ፍርሃት ማቋቋም ይችላል። የውጭ ሀገር ድርጅቶች ወይንም ገንዘባቸውን ከውጭ ሀገር የሚያገኙ ድርጅቶች አስፈላጊ አይደሉም።

አስፈላጊ ባይሆኑም ለምን ገቢያቸውን ከሀገር ውጭ የሚያገኙ ድርጅቶች ይከልከሉ፤ ህጉ ይቀየር እና ይፈቀድላቸው። በዛውኑ ውጭ ሀገር የሚኖሩ ኢትዮጵያዊዎች የሚደጉሟቸው ድርጅቶች በነፃነት ማገልገል ይችላሉ። እንደዚህ የሚሉ አሉ።

ግን ይህ በዙ ሰው የማያስበውን ችግሮች ያመጣል። ብውጭ ገንዘብ የሚመሩ ድርጅቶች የሚያንጸባርቁት የለጋሾቻቸውን ፍላጎት እና አላማ ነው። የሚሰሩት ለኢትዮጵያ ህዝብ ሳይሆን ለለጋሾቻቸው ነው። የለጋሾቻቸው አላማ ደግሞ ከኢትዮጵያ ህዝብ ፈቃድ ውጭ ሊሆን ይችላል።

ለምሳሌ የውጭ ሀገር የፖለቲካ እና ባህል በኢትዮጵያ ሊያስፋፉ ይችላሉ። ጸረ ሃይማኖት ፍልስፍኖችን እና ርዕዮተ ዓለሞችን ሊያስፋፉ ይችላሉ። ጸንፈኛ ጎሰኝነትን ሊደግሙ ይችላሉ በኃይለ ሥላሴ ዘመን እንደተደረገው። ጸንፈኛ ሃይማኖትም እንዲሁ። በተለያየ መንገዶች የውጭ ሀገር ተጽዕኖ በሀገራችን ላይ እንዲጠነክር ማድረግ ይችላሉ። ይህ ደግሞ የኢትዮጵያ ህዝብን ሊከፋፍል እና ሊጎዳ ይችላል እና ኢትዮጵያን ከሌሎች ሀገር አንጻር ሊያደክማት ይችላል።

ማወቅ ያለብን በጎ አድራጎት ድርጅቶች በመጀመርያ ደረጃ የለጋሾቻቸው መሳርያዎች ናቸው እንጂ የበጎ አድራጎት ሰራተኞች አይደሉም። የውጭ ሀገር ድርጅቶች ወይንም ከውጭ ሀገር ገንዘብ የሚያገኙ ድርጅቶች የዛን ውጭ ሀገር መንግስት ወይንም ሌላ ለጋሽ ፍላጎት በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ያንጸባርቃሉ። የዛን ሀገር የውጭ ጉዳይ መሳርያዎች ናቸው።

ግን እንደዚህ ቢሆንም የነዚህ ድርጅቶችን መልእክት መቀበል ፋንታ የኢትዮጵያ ህዝብ ይሁን እና ለምን ይከለከላሉ የሚሉ አሉ። እውነት ነው ህዝብ የመወሰን ነፃነት ሊኖረው ይገባል። ግን ጉዳዩ እንደዚህ ቀላል አይደለም። ለምሳሌ በፖለቲካ ውድድር አንዱ ፓርቲ የሌላው 10 እጥፍ ገንዘብ ካለው የገንዘብ ኃይሉ እንዲያሸንፍ ያደርገዋል። እያንዳንዱ ግለሰብ አንድ ምርጫ ያለው የህዝባ ምርጫ ቢሆንም ገንዘብ ታላቅ ሚና ይጫወታል። ይህ ገንዘብ ለማስታወቅያ እና ለጥቅም (ጉቦ) ይውላል እና በዚህ መንገድ የሰውን ምርጫ ይገዛል። ስለዚህ የገንዘብ ሚና በምርጫ ታላቅ ነው። የበጎ አድራጎት ድርጅቶችም ጉዳይ እንዲሁ ነው። ብር ያለው ህዝብ ላይ ይበልጥ ተጸዕኖ አለው። የሀገራዊ ድርጅቶችን ያፍኗቸዋል።

ሌላው ከውጭ ሀገር ወደ በጎ አድራጎት ድርጅቶች የሚመጣ ገንዘብ መከልከል ጥቅም የሀገሪቷ ህዝብ ድርጅት መደገፍ እና ማቋቋም እንዲለምድ ነው። ለምሳሌ ህዝቡ በልጆች አስተዳደግ ዙርያ ስራ ያስፈልጋል ድርጅት ያስፈልጋል ካለ እራሱ ከኪሱ አውጥቶ ድርጅት ይመስረት። ይህ ድርጅት ሙሉ ለ ሙሉ ህዝብን ይወክላል ማለት ይቻላል። ይህ ድርጅት ህዝብ የሚፈልገውን ያደርጋል እንጂ የውጭ ለጋሾች የሚፈልጉትን አያደርግም። ይህ ነው እውነት «ዴሞክራሲ» ተጠሪነት እና ሃላፊነት።

ስለዚህ በነዚህ ሁለት ምክንያቶች፤ 1) አላግባብ የውጭ ቅኝ ግዛት ተጽዕኖ እና 2) ሀገር በቀል ድርጅቶች እንዲጎለቡ እንዳይታፈኑ ያለው ህግ እንዳለ ይሁን። መሻሻል ካለበትም ሁሉንም በጎ አድራጎት ድርጅቶች ገንዘባቸው በሙሉ ከሀገር ውስጥ ማድረግ ነው።

Thursday, 12 July 2018

የቤት ሰራተኛ

አንድ ጓደኛዬ «የቤት ሰራተኛዬን እንደ ቤተሰብ ነው የምቆጥራት። ካስፈለገ እንጀራ መጋገርም ቤት ማጽዳትም እረዳታለሁ። ግዴታ ትምሕርትቤት እንድትማር አደርጋታለሁ…» ብሎ ነገረኝ። ምን ነው ይህ ያልተለመደ እንክብካቤ ብዬ ስጠይቀው እንዴት ለልጆቼ እንጀራ ጋግራ የምታበላውን አልንከባከባትም አለኝ! እውነት ነው፤ ሌሎቻችን እንዲሁ ቢገባን።

አንድ ሰሞን የቤት ሰራተኛ ፍለጋ አዲስ አበባን ከደላላ ወደ ደላላ ዚርን! ደላሎቹ ምን እንርዳችሁ ብለው በጉጉት ይጠይቁናል። የቤት ሰራተኛ ስንላቸው ፈገግራቸው የጠፋል። ሹፌር ወይንም የቀን ሰራተኛ ወዛደር ብንላቸው ይሻላቸው ነበር ብዙ አላቸው። ግን የቤት ሰራተኛ የላቸውም፤ ለነሱም ብርቅ ሆነዋል።

ብዙ የማቃቸው ቤተሰቦች አዲስ አበባም ከገጠር ከተሞችም የቤት ሰራተኞቻቸው በየ ሁለት ሶስት ወር ይለቃሉ አዲስ መቅጠር ይሆንባቸዋል። ወይንም ለመቅተር የገንዘብ አቅም የላቸውም። ወይንም ከመቀቃየር ተስፋ ቆርጠው አለ ሰራተኛ ይኖራሉ።

ዛሬ በአዲስ አበባም በመላው ኢትዮጵያ የቤት ሰራተኛ ጠፍቷል። ወይንም በትክክለኛ አገላለጽ (እጅግ) ተወዷል። ለምን ይሆን? የ ኤኮኖሜ ምክንያቶች አሉ። የሰው ኃይል በጠቅላላው ተወዷል። ዛሬ የቀን የግንባታ ሰራተኛ በወር ወደ 3000 ብር ሊሰራ ይችላል። እንዲሁም የቤት ሰራተኛ ደሞዝ ጨምሯል። ሁለተኛ ምክንያት ዛሬ ሴት ልጆች ከድሮ ይልቅ በትምሕርታቸው ይገፋሉ። የገጠር ወይንም የድሃ ቤተሰብ ልጆቻችው እንዲማሩ ይፈልጋሉ እንጂ በልጅነታቸው ሰራተኛ እንዲሆኑ አይሰጧቸውም። ሶስተኛ ምክንያት ወደ አረብ ሀገር ሄዶ መስራት ነው። የአራብ ሀገር ክፍያ ይበልጣል ወደ «ውጭ» ሀገር መሄድም ምንም ችግር እንደሆነ መረጃ ቢኖርም ያጓጓል ይመስለኛል። በነዚህ ምክንያቶች የቤት ሰራተኞች ተወደዋልም አይገኙምም።

ከኤኮኖሚ ምክንያቶች በተጨማሪ ለቤት ሰራተኛ መጥፋት ማህበረሰባዊ ምክንያር አለ እና እዚህ ላይ ነው ማተኮር የምፈልገው። ዛሬ አንድ ሴት በህንጻ ጽዳት ስራ 2000 ብር በ ወር ታገኛለች። ከዚህ ብር የቤት ኪራይ፤ መጓጓዣ (ትራንስፖርት) እና የምግብ ወጪዎቿን ትከፍላለች። 1000 ከተረፋት ትልቅ ነገር ነው። ነይ በ2000 ብር የቤት ሰራተኛ ሁኚ የቤት ኪራይ፤ የመጓጓዣ እና የምግብ ወጪ አይኖርሽም ብንላት እምቢ ትላለች። ለምን ይሆን? ስራው ከባድ ስለሆነ አይደለም  እትፍ ከባድ አይደለም። ነፃነቱ ይሆን እሱም 1000 ብር የሚያዋጣት አይመስለኝም። ምንም አይነት የሚመች የስራ ሁኔታዎች ብትዋዋልም የቤት ሰራተኛ መሆን አትፈልግም። ታድያ ምንድነው ምክንያቱ?

እኔ እንደሚመስለኝ ዋናው ምክንያት በባህላችን የቤት ሰራተኝነት እንደ ዝቅተኛ የሚናቅ ስራ ስለምንቆጥረው ነው። ይህን የዝቅተኝነት እና የመንናቅ ስሜት እጅግ ብዙ ብር ካልሆነ ብር አይተካውም። ተጎድቼ ውጭ ብሰራ ይሻለኛል ለብዙ ብር ከሰው ቤት ከምሰራ ነው ያለን አስተሳሰብ።

እስቲ ወደ ኋላ ሄደን የቤት ሰራተኞቻችንን እንዴት እንደምንይዝ እንደነበር እናስታውስ። 16 ሰዓት በቀን ይሰራሉ ለሌላው 8 ሰዓት ተጠሪ ናቸው። በወር አንድ ቀን እረፍት ቢኖራቸው ነው ይህም ላይከበር ይችላል። ኦርቶዶክስ ክርስትያን ነን የምንለው እንኳን እሁድ ቀን እረፍት መስጠት ቅዳሴም እንዲያስቀድሱ አንፈቅም (ከዚህ በላይ አሳዛኝ ነገር አላቅም)። እንደ ሰው ሳይሆን እንደ ባርያ እንጮህባቸዋለን እናጎሳቁላቸዋለን። እንደማንም ሰው አድገው ወደፊት ማግባት እና ቤተሰብ ማፍራት እንደሚፈልጉም አንገነዘብም ልንገነዘብም አንፈልግም። ከቤተሰቦቻቸው ርቀው በመኖራቸው እኛ እንደ ሁለተኛ ቤተሰባቸው መሆን እንዳለብን አናስብም። በጠቅላላ ለራሳችን የማንወደውን እናደርግባችዋለን ለራሳችን የምንወደውን አናደርግላቸውም።

ይህ ስር የሰደደ ባህል ሆኖ የቤት ሰራተኛ እጅግ ዝቅተኛ ስራ መሆኑ ሁላችንም አሰሪዎችም ሰራተኞችም እናውቃለን። በዚህ ምክንያት ይመስለኛል በርካታ ሴቶች ከቤት ሰራተኛ ስራ የሚርቁት። ብዙ ብር ቢከፈላቸውም ከገንዘብ አንጻር ቢያዋጣቸውም «ዝቅተኛነቱን» «ውርደቱን» አይፈልጉትም።

የቶሎ የስራ መቀያየር ጉዳይሳ? ለምንድነው ብዙ የዘመኑ የቤት ሰራተኛዎች ገና ወር ሁለት ወር ሳይቆዩ ለቀው ወደ ሌላ ቤት የሚሄዱት። አንዱ ምክንያት የኤኮኖሚው ነው። ብዙ ስራ ስላለ የደሞዝ ጭማሬ ቶሎቶሎ ያገኛሉ። ሌላው ምክንያት ግን እንደሚመስለኝ የቤት ሰራተኝነት የማይፈለግ ስራ በመሆኑ ብዙ ችግር እና የማመዛዘን ድክመት ያላቸውን ሴቶች ናቸው ወደዚህ ስራ የሚገቡት። ይህ ምክንያት የስራ መቀያየራቸውን ብቻ ሳይሆን ሌሊችን ችግሮች እንደ ሌብነት ወዘተ ያስረዳል።

ለረዥም ዘመን የቤት ሰራተኞቻችንን ጎድተናል። በተዟዟሪ ሙሉ መሃበረሰባችንን ጎድተናል። የጎጂ የአሰሪ እና የንቀት ባህላችን ከትውልድ ወደትውልድ አስተላልፈናል። የአሁኑ የሰራተኛ እጥረት እስኩመጣ ድረስ ጥፋቶቻችን አልታዩንም ይሆናል ግን አሁን ጎልተው ሊታየን ይገባል። ጥፋታችንን አይተን አምነን መጸጸት፤ ንስሃ መግባት እና ይቅርታ መጠየቅ የሚኖርብን ይመስለኛል ይህን ጎጂ ባህላችንን በቋሚነት ለማስወገድ። ይህ ለህላችንም ለጠቅላላ ህብረተሰባችን ሰላም እና ፍቅርም አስፈላጊ ይመስለኛል።

Wednesday, 11 July 2018

ንቀት

እኛ ኢትዮጵያዊዎች እንደ መንናቅ የምንጠላው ነገር የለም። ከአንዳንድ ቦታዎች ንቀት እና የተደጋገመ ዝልፍያ እስከ መገዳደል ያደርሳል! መንናቅ እየጠላን ግን መናቅን እንወዳለን  አያስችለንም። ይህ ነውረኛ የንቀት ባህላችን ለበርካታ ሀገራዊ፤ ማህበራዊ እና ፖለቲካዊ ችግሮቻችን  አስተዋጾ አድርጓል። በቀላሉ ለመከፋፈል አጋልጦናል። እርስ በርስ መናናቅን ብናቆም እነዚህ ችግሮችን ለመፍታት ይረዳናል።

«ንቅት» ስል ሰውን ወይንም ማህበረሰብን ወደ ታች አድርጎ ማየት ማለቴ ነው። «ምቀኝነት» ሌላውን በመጉዳት ራስን መጥቀም የሚቻል እንደሚመስለው ንቀትም ሌላውን ወደታች በማየት ራስን ከፍ ማድረግ ይቻላል የሚል የውሸት አስተሳሰብ አለው።

ማንን ነው የምንንቀው? ከኛ «ዝቅተኛ» ስራ የሚሰሩትን፤ (ለምሳሌ) የቤት ሰራተኞቻችንን፤ ከኛ ድሃ የሆኑትን፤ ያነሰ ትምሕርት ያላቸውን፤ አማርኛ በደምብ የማይችሉትን፤ እንግሊዘኛ በደምብ የማይችሉትን!፤ ገጠሬዎትን፤ ቀጥቃጭ፤ ቆዳ ፋቂዎች ወዘተ የሆኑትን፤ የሌላ ቋንቋ ተናጋሪዎችን ወዘተ። ዝርዝሩ ረዥም ነው!

ተናቅን የሚል ስሜት ያላቸው ከሚንቋቸው ጋር አንድነት ሳይሆን ልዩነት ይሰማቸዋል። ልዩነት ብቻ ሳይሆን ቂም እና ጥላቻ አከማችተዋል የናቋቸውን ቢበቀሉ ደስ ይላቸዋል። ይህ ማለት ህብረተሰባችን ተከፋፍሏል ነው። እርስ በርስ ጥላቻ አለው ማለት ነው። ታድያ ለረዥም ዓመታት በከፋፍሎ መገዛት ፖለቲካ ብንመራ ለምን ይገርማል። በ«ብሶት ፖለቲካ» መቆየታችን ለምን ይገርመናል? ፖለቲካችን በመጣላት የተመረዘ መሆኑን ምን ይገርማል? የፖለቲካ ውይይቶቻችን በጥይትነና በጡንቻ መካሄዳቸውን ምን ይገርማል?

እስቲ አንዳንድ ተጨባጭ የንቀት ምሳሌዎች ልስጣችሁ፤ በኃይለ ሥላሴ ዘመን ሁላችንም እንደምናውቀው ከመሳፍንቱ እና ባላባቱ መካከል ብዙዎቻችን ገበሬውን፤ ጪሰኞውን፤ ሰራተኞቻችንን ወዘተ እንንቅ ነበር እንደ በታቾቻችን እናያቸው ነበር። አዲሱ «የተማረው» መደብም ራሱ የሚንቀው ቡድን ነበር ይህም ያልተማረውን፤ ሃይማኖታዊውን ወዘተ። ይህ ንቀት ህዝባችንን ከፋፈለ የአንድነት ስሜታችንን ቀነሰ። ሀገራችንን ለኮምዩኒዝም የሚያስተምረው «ጨቋኝ ተጨቋኝ» የክፍፍል ፖለቲካ አጋለጠ። መናናቃችን ለደርግ አብዮት ታላቅ አስተዋጾ አደረገ። አብዮተኞቹ የህዝቡን የመንናቅ ብሶትን እንደ ቤንዚን ተጠቅመው ነው አብዮቱን ያራመዱት። ወዛደሮችን፤ አርሶአደሮችን፤ ሴቶችን፤ «ጭቁን ዘሮችን» ወዘተ እረደሃለሁ እበቀልሃለሁ ብለው ነው ኮምዩኒስቶቻችን የተነሱት። ተናቅን የሚሉትን በሙሉ አቅፍያለሁ እያለ ነው ደርግ የሰበከው። ግን ንቀቱ ባይኖር ብሶቱም አይኖርም ነበር አብዮቱም አይነሳም ነበር።

የኢህአዴግ ዘመንም እንዲሁ ምሳሌ ይሆነናል። ኢህአዴግ ስልጣን ስይዝ የሚናናቅ የተከፋፈለ እርስ በርስ ቂም የያዘ ህብረተሰብ ነው የጠበቀው! ይህን ህብረተሰብ ከፋፍሎ መግዛት እንደሚችል ቶሎ ተረዳ። ልክ እንደ ደርግ ግን በተሻለ ብልጠት ተንቀናል ሊሉ የሚችሉትን ቡድኖች ማፈላለግ እና ማቀፍ ጀመረ! እዚህ ላይ አንድ አስፈላጊ ነጥብ አለ። ኢህአዴግ የተጠቀመበት ክፍፍል አይነት የጎሳን ብቻ አይደለም። ሁሉንም ከላይ የጠቀስቋቸው ክፍፍሎችን፤ ሃብታም እና ድሃ፤ የተማረ ያልተማረ፤ ገበሬ ከተሜ፤ አሰሪ ሰራተኛ፤ ወንድ ሴት፤ ትልቅ ሰው ወጣት ወዘተ ተጥቅሞባቸዋል። እነዚህ ክፍፍሎች አልፈጠራቸውም ተተቀመባቸው እና አስፋፋቸው እንጂ። ስለዚህ ለኢህአዴግም አገዛዝ የንቀት ባህላችን ሙና እንደተጫዋወተ ግልጽ ነው።

ለማጠቃለል ያህል ያለፉት 60 ዓመት ፖለቲካችንን «የብሶት ፖለቲካ» ብለን መሰየም እንችላለን። ቂም እና መከፋፈል የሰፈነበት ፖለቲካ ነው። በ«ጨቋኝ ተጨቋኝ» አስተሳሰብ ተመርዟል። ስለዚህም ነው አብሮ አለመስራት፤ ውግያ፤ ጸብ፤ ቅራኔ አለመፍታት ወዘተ የሰፈነው። ንቀት እና ውጤቶቹ ብሶት እና ቂም ለዚህ ማህበረሰባዊ እና ፖለቲካዊ ችግር ትልቅ ሚና የተጫወቱ ይመስለኛል።

ከ ጠ/ሚ አብይ አህመድ ዋና መፈክሮች አንድነትን ወይንም አለመከፋፈል ነው። አንድ የሆነ ማህበረሰብ ጤነኛ ነው የተከፋፈለ ማህበረሰብ በሽተኛ ነው። የሚናናቅ ማህበረሰብ አንድ ሊሆን አይችልም ስለዚህም ይህ የ«ንቀት» ባህላችንን እንዋጋ እና እናሸንፍ!

አንድ የመጨረሳ ነጥብ ፍቀዱልኝ። ንቀት «አንተ የማትወደውን ለባለእንጀራህ አታድርግ» ስለሚሽር መጥፎ ስነ መግባር መሆኑ ሁላችንም ይገባናል። መንናቅ ስለማንፈልግ መናቅ የለብንም ነው። ግን ይህ ሙሉው ታሪክ አይደለም። ንቀት ኢተፈጥሮ ነው። የሰው ልጅ በእግዚአብሔር አምሳል ስለተፈጠረ ሰውን መናቅ ማለት የሚወደን ፈጣሪአችን እግዚአብሔርን መናቅ ነው። እንደዚህ ስንመለከተው ንቀት እጅግ ከባድ ማጣት ነው።

Monday, 4 June 2018

የዘመናዊነት ዕቅድ (The Modern Project)

ይህ ከቀሲስ/መምህር ስቲፈን (እስቲፋኖስ) ፍሪማን ጽሁፍ (https://blogs.ancientfaith.com/glory2godforallthings/2014/01/10/the-modern-project/) በሰፊው የተረጎምኩት ነው። ቀሲስ ስቲፈን አሜሪካዊ (ምስራቃዊ ወይም ቃልቄዶናዊ) ኦርቶዶክስ ቄስ ናቸው። ከፕሮቴስታንትነት ወደ ኦርቶዶክስ እምነት «ከተመለሱት» በርካታ አሜሪካዊ ካህናት መካከል ናቸው። አሜሪካዊ በመሆናቸው ብቻ ሳይሆን በቀለም ትምሕርት እና በሃይማኖት ታሪካቸው ምክንያት ስለ በዘመናችን የነገሰው ዘመናዊነት ፍልስፍና በደምብ ያውቃሉ ለክርስትና ዋና ጠላት መሆኑንም ይገነዘባሉ። ሆኖም የዘመናዊነት ፍልስፍና የነገሰ ስለሆነ ሳናውቀው ሁላችንም በተወሰነ ደገጃ እንደተቀበልነው ያውቃሉ። ሰለዚህም ነው ቀሲስ ስቲፈን በዚህ ጉዳይ ዙርያ ብዙ የሚጽፉት። ጽሁፋቸው ለሁላችንም ገላጭ እና አስተማሪ ነው ብዬ አምናለው። ብሎጋቸውን ብታነቡ እጅግ ጠቃሚ ይሆናችኋል ብዬ አምናለው።

ሁለተኛ ዲግሪዬን በ«ቴኦሎጂ» በምማርበት ወቅት (1970 ዎቹ) «የዘመናዊነት ዕቅድ» ('the project of modernity') የውይይት ርዕስ የነበረበት ጊዜ ነበር። ይህ የዘመናዊነት ዕቅድ «ዘመናዊውን» ዓለም ('the modern world') ለመገንባት የሚሰሩትን ማህበራዊ፤ ፍልስፍናዊ፤ ፖለቲካዊ እና ሃይማኖታዊ ስራዎችን ያካትታል። በ17ኛ ክፍለ ዘመን የመነጨው «የብርሃን መብራት» ('the Enlightenment') ፍልስፍና አዲስ የአስተሳሰብ አይነቶች ወደ ምዕራባዊው ዓለም (ከዛ ቀጥሎ ወደ መላው ዓለም) አመጣ። ለምሳሌ ለ«ሀገር» የምንለው ፅንሰ ሃሳብ አዲስ ትርጉም እና አወቃቀር ፈጠረ። የክርስትና ሃይማኖትን በአዲስ መልክ ፈጠረ (ለምሳሌ ፕሮቴስታንትነት)። ከሁሉም በላይ ግን የሰው ልጅ ማንነትን ሌላ ትርጉም ሰጠው።

እኛ የዚህ ዘመን ሰዎች የዚህ ፍልስፍና ወራሾች ነን። የዘመናዊነት እና የዘመናዊነት ዕቅድ ልጆች ነን። ዛሬ ማንም ትምህርት የሌለውም ሰው «የዘመናዊነት ዕቅድ» ያመጣውን አስተሳሰቦችን ሳያውቀውም ቢሆን አድሮበታል አምኖበታልም። በትምህርት ቤትም በሚዲያም በሌሎች መንገዶች አስተሳሰቡን ወርሰነዋል። እኛ «የዘመናዊነት ዕቅዱ» ውጤቶቹ ሆነናል።

ዘመናዊነት ዕቅዱ የሰው ልጅን ማንነት ሲደነግግ እንደዚህ ይላል፤ « የሰው ልጅ በራሱ ብቻ የሚተዳደር ነፍስ ነው፤ ውሳኔዎቹ እና ስራው ብቻ ነው ማንነቱን የሚወስን»። ይህ ማለት፤

1. በራሱ ብቻ የሚተዳደር ነፍስ፤ የሰው ልጅ የማንነቱ መሰረት በማወቅ እና ማሰብ ችሎታው የተወሰነ ነው። «የማሰብ እና ማወቅ ችሎታዬ ብቻ ነው የሰው ልጅ የሚአደርገኝ»። ከዚህ ቀጥሎ በፈቃዴ ከሌሎች ጋር መጋራት እችላለሁ ግን ማንነቴ በራሴ ብቻ ነው የሚወስነው። ከሌሎች ጋር ያለኝን ግንኙነትም እኔ ብቻ ነው የምወስነው። ይህ ነው በዘመናዊው ዓለም የምናየው የ«ግለኝነት» አኗኗር መሰረታዊ ሃሳብ።

2. ውሳኔዎቻችን እና ስራዎቻችን ማንነታችንን እና የህይወት ጉዞዋችንን ይወስናሉ፤ በዚህ ዓለም ያለኝ የማንነት ምደባ የራሴ አመራረጥ፤ ውሳኔዎች እና ያሳለፍኩት ልምዶች ናቸው የሚወስኑት። ውሳኔዎቼ ማንነቴን ይወስናሉ እና መሆን የምፈልገውን መሆን እንድችል ብቸኛ ሚና ይጫወታሉ። የኔ ምርጫ እና ውሳኔዎች ናቸው የህይወቴን ትርጉም እና ማን መሆን እንደምፈልግ የሚወስኑት።

እነዚህን ፅንሰ ሃሳቦች ካሰላሰልናቸው የዘመናችን ታሪክን ወሳኝ ነገር «ነፃነት» ለምን እንደሆነ በቀላሉ እንረዳለን። (ይህ «ነፃነት» የሚባለው የመወሰን እና የመምረጥ «መብት» ነው እንጂ እውነተኛው ነፃነት አይደለም።) የሰው ልጅ ማንነት ትርጉም ከላይ የተጻፈው ከሆነ ይህ «ነፃነት» የግድ ይሆናል። ይህን ነፃነት የሚገድብ ሁሉ የሰው ልጅ ህልውና እና ፍላጎት ጠላት ይሆናል። እንደ ፈለግኩኝ መምረጥ መወሰን ስችል ነው ፍላጎቴን ማምዋላት የምችል ሰው መሆን የምችለው።

ከላይ እንደጠቀስኩት ባሁኑ ዘመን እነዚህ አይነት አስተሳሰቦች ሳናውቀው ሰርቀው አዕምሮአችን ውስጥ ገብተዋል። ዓለም ዙርያ ታውቀዋል። እንደ «ነፃነት» እና «ምርጫ» አይነቶቹ ቃላቶት ምን ማለት እንደሆኑ ብዙሃኑ ተውሕዶታል። እነዚህን ቃላቶችን ስንጠቀም ሁሉም ሰው ትርጉማቸውን «ያውቃል»።

አንዳንድ የክርስቲያን ቡድኖች በተለይም የፕሮቴስታንት ንቅናቄ ይህን አስተሳሰብ አቀናብረው አንጸራጭተውታል። እነዚህ የክርስቲያን ቡድኖች ከአሜሪካ እና አውሮፓ ተነስተው የ«ዘመናዊ» ክርስትና ዓለም ዙርያ አስፋፍተዋል። በጥናታዊ ክርስትና ያልነበሩ አስተያየቶች እና ጥያቂዎችን አስፋፍተው የተለመዱ እንዲሆኑ አደረጉ። ለምሳሌ የህፃንነት ጥምቀት ጥያቄ፤ ዛሬ ሰው ለምን በህፃንነቱ ክርስትና ይነሳል የሚለው ጥያቄ ይጠየቃል። ልበ በሉ ለመጀመርያዎቹ ፕሮቴስታንቶች ይህ ጥያቄ አልነበረም ግን የተከሉት ዘር ወደዚህ አመራ። ጥያቄ የሆነው ምክነያት የህጻንነት ጥምቀት «ነፃነትን» ይሽራል ተብሎ ነው! «ህፃኑ እንዴት አለ «ምርጫው» ይጠመቃል። ለመጠመቅ ላለመጠመቅ ነፃነቱ ሊኖረው አይገባምን?» ይባላል! በዘመናዊነቱ ዕቅድ ምርጫን ወይም የራስ ውሳኔን የሚገድብ ነገር አደገኛ ነው ተብሎ ይሰየማል። በየ «ኤቫንጀሊካል» ፖሮቴስታንት ቤተ ክርስቲያን ክርስቲያን መሆን የ«ነፃ ምርጫ» ጉዳይ ነው ይባላል። «የውሳኔው ስዓት» ሰዎች ክርስቶርስን ጠቀብያለሁ የሚሉበት ጊዜ በዘመናችን ተለምዷል።

ቤተ ክርስቲያን ስለ ገብረ ግብ የምታስተምረውም በዘመናዊነት ዕቅዱ ምክንያት በጥርጣሬ ላይ ወድቋል። ዘመናዊ ሰዎች እራሳቸውን «ካቶሊክ»፤ «ኦርቶዶክስ»፤ «ጴንጤቆስጣል»፤ «ፕሬስቢቴሪያን» ወዘተ ብሎ ቢሰይምም ቤተ ክርስቲያናቸው ስለ ግብረ ገብ ወይም ስነ መግባር ኑሮዋቸው መወሰን የለባትም ብለው ያምናሉ። እራሳቸውን «ካቶሊክ» ብለው ቢሰይሙም በካቶሊክ እምነት አይገዙም። ለምሳሌ አብዛኞች አሜሪካዊ ካቶሊኮች ቤተ ክርስቲያናቸው በተለይ ስለ ቤተሰብ እና ጋብቻ የምታስተምረውን ሌሎችም ትምህርቶቿንም ይክዳሉ! ከቤተ ክርስቲያናቸው እምነቶች የሚፈልጉትን ይመርጣሉ የግል ምርጫዬ ነው የነፃነት ጉዳይ ነው ብለው ያምናሉ። ግን ይህ «የግል ሃይማኖታቸውን» በራሳቸው «ነፃነት» እና ምርጫ «ካቶሊክ» ብለው ይሰይማሉ። በዚህ አስተሳሰብ «ካቶሊክ»፤ «ኦርቶዶክስ»፤ «ሉቴራን» ወዘተ ሰው የሚመርጠው ማንነት ነው እንጂ ማንነትን እና ህይወትን የሚወስን ጉባኤ አይደለም።

የዘመናዊነት ዕቅዱ የጥንታዊ ክርስትና ጠላት ነው።

በጥንታዊ አመለካከት የሰው ልጅ ለራሱ ብቸኛ ወሳኝ አይደለም። በዚህ ዓለም የምንገኘው ከራሳችን ሌላ በሆነው በእግዚአብሔር ፈቃድ ነው። ህይወታችን የእግዚአብሔር ስጦታ ነው። የህይወታችን አላማው፤ ትርጉሙ እና አቅጣጫው በእግዚአብሔር የተሰጠ ነው። የሰው ልጅ የሚያደርገን እና ዋጋ የሚሰጠን በእግዚአብሔር ምሳሌ መፈጠራችን ነው እንጂ ውሳኔዎቻችን ወይም የመወሰን አቅም ስላለን አይደለም። የሁላችንም ታናሾች አቅም የሌላቸው፤ ችሎታ የሌላቸው፤ ከአልጋ ተኝተው መንቀሳቀስ የማይችሉት፤ ወዘተ በኢግዚአብሔር ምሳሌ በመፈጠራቸው ክብር እና ዋጋ አላቸው።

ማንነታችን በህይወት ምርጫዎቻችን እና ውሳኔዎቻችን ብቻ አይደለም የሚወሰነው። ህይወታችን እና ማንነታችን ከእግዚአብሔር ያገኘነው ስጦታ ነው። እሰረታዊ ማንነታችን በተወሰነ ደረጃ የተመደበ ነው። ይህ ማንነት በክርስትና ህይወት የሚገለጽ እና የሚለወት ነው እንጂ አንድ ሰው በግሉ የሚፈጥረው አይደለም። ምርጫዎቻችን እና ውሳኔዎቻችን ሚና ይጫወታሉ ግን ከእግዚአብሔር ውሳኔ ስር ነው ሚናቸው። ዞሮ ዞሮ የእግዚአብሔር ፍጥረቶች ነን ስለዚህ ውሳኔዎቻችን ትርጉም ያላቸው ከሱ ጋር ባለን ግንኝነት ነው።

በዘመናዊነት ዕቅዱ እና በጥንታዊው አመለካከት ያለው ጦርነት በደምብ የሚታየው በተለይም በምዕራቡ ዓለም በስነ ህይወት (biology) እና የሰው ግንኝነት ዙርያ። ጥንታዊ የክርስትና አመለካከት ስነ ህይወታችን፤ ማለትም ሰውነትና አካላችን ወዘተ፤ የተሰጠን ነው። እንደ አባት፤ እናት፤ ወንድም፤ እህት ወዘተ ያለን ከሰው ጋር ያለን ግንኙነቶችም የተሰጡን ናቸው። ጾታ ምርጫ አይደለም። ቤተሰብም የደም ተፈጥሮ ነው እንጂ በምርጫ አይደለም። በባለና ሚስት መካከል ወይም ሌሎች ወሰባዊ ግንኙነቶች የተሰጠ አላማ አላቸው እንጂ የግል ፍላጎት ማምዋያ አይደሉም። ግን የዘመናዊነት ዕቅዱ «ነፃነትን» እና «ምርጫን» እንዲሰፍኑ ማድረግ ነው የሚፈልገው። የሰው ተፈጥሮ እውነት ነው ግን ወሳኝ አይደለም ይላል (ለዚህም ነው ዛሬ አንዳንዶች ጾታቸውን የሚመርጡት)። ቤተሰብ የምርጫ ጉዳይ ነው የምንፈልገውን ግንኙነቶችን እንመርጣለን። የደም ትሥሥር የተሰጠ መሆኑ እና በደም ትሥሥር ምክንያት ሃላፊነቶች መኖራቸው በምዕራባዊ ሀገራት መንግስታት እና ፍርድ ቤቶች እየተካደ ነው። ለዚህም ነው በእግዚአብሔር ፈቃድ የተጸነሰው ከ«ነፃነት» ጋር መወዳደር ያልቻለው እና ጽንስን ማስወረድ የሰፈነው።

ዛሬ «እውነት» የሚባለው ነገር አሻሚ ሆኗል። የኔ እውነት ካንተ እውነት ይለያል ግን ሁለቱም እውነቶች ናቸው ይባላል። እውነትም የምርጫ ጉዳይ ሆኗል። አንድ የሆነ እውነት የለም ይባላል። በዚህ ዘመናዊ ዓለም እውነት አንድ ነው ማለት እንደ ጭቆና ነው የሚቆጠረው። የጥንታዊ ክርስትና አስተያየት ከነ ህግ እና እምነቱ የማይመች እና መጥፋት ያለበት ሆኖ ነው የሚታየው። ዘመናዊው ዕቅድ «ለምን እግዚአብሔርንም በራሳችን ምርጫ በራሳችን ምናብ አንፈጥረውም አንወስነውም» ይለናል።

መጨረሻው

ከመጀመርያ ጀምሮ ለ400 ዓመታት በላይ የዘመናዊው ዕቅድ የጥንታዊ ክርስትናን ተዋግቶ ከሰው ልጅ ከህዝብ ማስወገድ ነው አላማው። የዘመናዊነት ጥያቄ «እግዚአብሔር እንዴት ነው የፈጠረን» ሳይሆን «ዓለምን ምን እንዲመስል ነው የምንፈልገው?» ነው። የዓለም ሁኔታ የሰው ምርጫ ጉዳይ ነው ብሎ ነው የሚያምነው። ስለዚህ ነው የዘመናዊ ዕቅዱ ልጅ የሆነው የፕሮቴስታንት ስነ መለኮት (ቴኦሎጂ) የክርስትናን ትውፊት እና ወግን ከመመርመር እና ማጥናት ይልቅ ወንጌልን በራሱ ምናብ መተርጎም የፈለገው።

ማርቲን ሉተር «በመጻሐፍት ብቻ» ('Sola Scriptura') የሚባለው የፕሮቴስታንት አቋምን ሲፈጥር ማንም ሰው መጸሀፍ ቅዱስን አንብቦ አለ እርዳታ አለ ቤተ ክርስቲያን አለ ሃዋርያት በትክክሉ ይተረጉመዋል ለማለት ነው። ማርቲን ሉተር የሮሜ ጳጳስን ወይም የሮሜ ቤተ ክርስቲያን ችግሮችን በመቃወም ስበብ ክርስትናን በራሱ ውሳኔ እና ምርጫ መቅረስ ፈለገ። በዝህ መልክ ይህ «በመጸሐፍት ብቻ» የሚባለው አስተያየት በመጀመርያ ቤተ ክርስቲያንን እና ትውፊቷን ለመለየት የተጠቀሙበት መሳርያ ነበር። ግን ባልታሰበበት (ግን ሊታሰብበት) መልክ ይህ አስተሳሰብ ሰዎች መጸሀፍ ቅዱስን በግላቸው እንተርጉም እያሉ ከአንድ ከሉተር ከሁለት የሉተር ተፎካካሪ ዝዊንግሊ ወደ 30 ሺ አተረጓገም (ዛሬ ዓለም ዙርያ ያሉት የፕሮቴስታንት ቡድኖች ቁጥር) ደርሷል።

ግን «የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም» እና ዛሬም የጥንታዊ ክርስትና አለች የዘመናዊነቱን ዕቅድን የስጋው መውግያ ናት። የዘመኑ ሚዲያ ቫቲካንን አትኩረው ያያሉ ገና ለገና መሰረቷን ሸርሽራ ትጨርሳለች እጇን ሙሉ በሙሉ ለዘመናዊነቱን ዕቅድ ትሰጣለች ብለው። በሩስያ ከሞት የተነሳችው ኦርቶዶክስ እምነት ደግሞ ከፖለቲካዊ «አምባገነን» ጋር የተያያዘ እና «ኋላ ቀር» ብለው ይሰይሙታል! ጦርነት ነው!

ዛሬ የጥንታዊ ክርስትና መንገድ ከባድ ነው። አታላዩ መንገድ ዝም ብሎ ጸረ የዘመናዊው አብዮት መሆን ነው። ከዘመናዊነት ዕቅዱ እኩል እንደ አማራጭ መወዳደር። ግን ክርስትና እንዳዚህ ካረገች እጇን ለዘመናዊው ዕቅድ ሰጠች ማለት ነው። ሌላ «ምርጫ» ሆነች ማለት ነው። ግን ጥንታዊ ክርስትና የምርቻዎቻን ውጤቶች አይደለንም ህይወቶቻችን በእግዚአብሔር ጸጋ እና ስጦታ ነው የሚወሰነው ሁሉም ነገር ከእግዚአብሔር አኳያ ነው የምንመለከተው ነው። የቤተ ክርስቲያን ተውፊት የለ የተሰጠ ነገር ነው እንጂ ምርጫ አይደለም። ስለዚህ እራሱን እንደ አንድ አማራጭ አያቀርብም ሊያቀርብም አይችልም።

የጥንትዊ ክርስትና መንፈስ ስለ በራስ መምርጥ ሳይሆን እራስን ባዶ ማድረግ። ማለት የራስን ፍላጎት ትቶ የእግዚአብሔርን ፍላጎት ማወቅ እና ማክበር። እጅን ለእግዚአብሔር ሙሉ በሙሉ መስጠት። ጥንታዊ ክርስትና ህይወት የተሰጠ እንደሆነ ይረዳል። የተፈጥሮ የደም ትሥሥር፤ ቤተ ሰብ እና ዝምድና ተጭባጭ ናቸው እና ህይወታችን ላይ ተገቢ ሚና ይጫወታሉ ሃላፊነት ይሰጡናል። ዓለም እንደዚህ ትሁን እንደዛ ትሁን ብለን ማለም ከለት ለለት ከባድ የሆነ የክርስትና ኑሮአችን እንድንርቅ እንድንሰንፍ ፈተና ነው። የዓለም ድሃ ይረዳ እያልኩኝ እየተፈላሰፍኩኝ ድሃ ባለንጀራዬን ዞር ብዬ አላየውም! ግን የዘመናዊነት ዕቅድ እንደዚህ ነው የሚያስበው። ዓለምን አሻሽላለው ይላል። ከ«ነፃነት» በደምብ ማትረፍ የሚችሉትን ባለ ሃብቶች እና በትምሐርት ጎበዞች በደምብ አትርፈዋል። ግን ይህ የዘመናዊነት ዕቅድ ፉከራ ባዶ ነው ህይወታችንን በራሳችን መወሰን ስለማንችል። እራሳችንን ከእውነታችን በላይ ታላቅ አርገን ብናስብም መጨረሻ ላይ ሞት ምርጫችንን አያከብርም! ምናልባትም የዛሬው ታላቅ አሽሙር የዘመናዊነት ዕቅዱ የ«መሞት መብት»ን ማራመዱ ነው አለመሞት ምርጫ እንደሆነ!

Thursday, 17 May 2018

የ«አማራ ብሄርተኝነት» ትውፊታዊ ነውን?

የ«አማራ ብሄርተኝነት» ትውፊታዊ ነው ወይስ እንደ ሌሎች የጎሳ ብሄርተኞቻችን (ኤርትራ፤ ትግራይ፤ ኦሮሞ፤ ወዘተ) በፈረንጅ በምዕራባዊ በ«ተራማጅ» በማርክሲስት ፍልስፍና የተመሰረተ ነው?

እርግጥ ብዙ አይነት የአማራ ብሄርተኝነቶች አሉ፤ ለፖለቲካ ስልት ወይንም «ታክቲክ» ብቻ የሆነ አለ፤ በስመ አማራ ላለፉት 27/40 ዓመታት ለተበደሉት ፍትሕ መጠየቅያ የሆነ አለ፤ ዛሬ አማሮች ላይ የሚደርስባቸውን በደል ለመታገል የሆነ አለ፤ በሀገር ደረጃ በፖለቲካ ድርድር ለአማራ ህዝብ የሚቆም አለ፤ በሃሰት የታማው የአማራ ህዝብን ታሪክ እውነቱ እንዲታወቅ የሚንቀሳቀስ አለ፤ የአማራ ህዝብ ክብርና ማንነትን ለመመለስ የሚታገለው አለ፤ ወዘተ። ዛሬ እነዚህ ሁሉ አይነት እንቅስቃሴዎች በስመ አማራ ብሄርተኝነት ይጠራሉ።

ዞሮ ዞሮ ዋናው ነጥብ ይህ የፖለቲካና መሃበራዊ ንቅናቄ እራሱን የ«አማራ ብሄርተኝነት» ብሎ መሰየሙ ነው። አላማው ምንም ቢሆን በዚህ «አማራ ብሄርተኝነት» የሚለው ስም መጠራት ይፈልጋል። በዚህ ስም መጠራቱ ምን ይነግረናል? በተለይ በትውፊትና በተቃራኒው ምዕራባዊ ተራማጅነት ያለው ግንኙነቱ ምንድነው?

ደስ የሚለው ነገር የሁሉም አይነት የአማራ ብሄርተኝነት ምልክቶች ትውፊታዊ ናቸው። ለምሳሌ ዓፄ ቴዎድሮስ አንዱ ዋና የአማራ ብሄርተኝነት ንቅናቄ ምልክት ናቸው። የአማራ ታሪክን በትክክሉ ማስተዋወቅና መናገር ሌላው የአማራ ብሄርተኝነት አላማና ምልክት ነው። ግን ዓፄ ቴዎድሮስ እራሳቸውን ወይንም ሀገራቸውን ወይንም አገዛዛቸውን የአማራ ወይንም «አማራ ብሄርተኛ» ብለው ይሰይሙ ይሆን? የአማራ ታሪክ የምንለው በታሪክ ሰሪዎቹ እና በዘጋቢዎች ዘንድ የአማራ ታሪክ ይባል ነበር? የአማራ ብሄርተኝነትን ያንጸባርቅ ነበር?

ለነዚህ ሁለቱም ጥያቄዎች መልሱ «አይደለም» እንደሆነ ነው የማውቀው። ዓፄ ቴዎድሮስ እንደ ሁሉም ንጉሶቻችን በስመ ኢትዮጵያዊነት ነበር እራሳቸውን የሚመለከቱት። ታሪካችም እንዲሁ ኢትዮጵያዊነት ላይ ነው የሚያቶክረው አማራነትን አይደለም። ይህ ማለት «አማራ» የሚባል ህዝብ የለም አልነበረም ማለት አይደለም! መኖሩ በታሪክ በተለያየ ቦታ መመዝገቡ ይታወቃል። ግን እስከማውቀው ማንም በስመ አማራ አልተንቅሳቀስም። ትውፊታችንና ታሪካችን እንደዚህ ከሆነ እንዴት እራሱን «አማራ ብሄርተኝነት» ብሎ የሰየመ ንቅናቄ ትውፊታዊ ነው ማለት ይቻላል?

በሁለተኛ (ወይንም አንደኛ!) ደረጃ ጠቅላላ የጎሳ ብሄርተኝነት የሚባለው ነገር የምዕራባዊ የፖለቲካ ፍልፍና እንደሆነ ይታወሳል። በትውፊታዊ ፖለቲካ «ሀገር» ነው ያለው፤ «ጎሳ» የለም። ይህ አባባሌ ብዙ ነገሮች ስለሚያከማች ሁሉንም በዚህ ጽሁፍ አልጠቅስም ግን በጠቅላላ የ«ጎሳ ብሄርተኝነት» የዘመናዊ የምዕራባዊ ጽንሰ ሐሳብ ነው።

የምፈራው ነገር ይህ አዲሱ የአማራ ብሄርተኝነት ልክ እንደ በፊቶቹ የኤርትራ፤ የትግራይ፤ የኦሮሞ፤ ወዘተ ብሄርተኝነቶች በብሶት እና በበአድ ምዕራባዊ ርዕዮተ ዓለም የተመሰረተ ኢተውፊታዊ ንቅናቄ ይሆናል ብሄ ነው። የኤርትራ እና የትግራይ ብሄርተኝነት በመሰረቱ ጸረ ትውፊት ናቸው። በቀላሉ ምሳሌ ለህዝባቸው መሰረት የሆነው ሃይማኖትና ባህልን የሚጠላ ርዕዮተ ዓለም ነው እነዚህ ብሄርተኝነቶች የተመሰረቱት። የኦሮሞ ብሄርተኝነት እንደዚህም ቢሆን ቢያንስ ወደ ኦሮሞ ትውፊት ለመመልከትና እንደ ገዳ አይነቱን ተውፊት ማክበር ሞክሯል። ሆኖም መሰረቱ የማርሲስት የጨቋኝ ተጨቋኝ የጎሳ ብሄርተኝነት አስተሳሰብ ነው። የአማራ ብሄርተኝነትም እንደዚህ እንዳይሆን መጠንቀቅ ይኖርበታል። ግን እራሱን «አማራ» ብሎ ከሰየመ እዚህ ወጥመድ ውስጥ ቀድሞ ገብቷል ማለት ይመስለኛል።

ጎበዝ፤ ጠንካራ፤ ሀገር ወዳድ ምሁራን በተለይ ወጣቶች የአማራ ብሄርተኝነት ያቀፉ አሉ። ምክንያቱ ለሁላችንም ሊገባን ይገባል፤ ለብሶት መልስ ነው። የአስራት ወልደየስ ፖለቲካ የብሶት ሳይሆን እራሳቸው እንዳሉት የግዴታ ነበር። የዛሬው ግን የ27/40 ዓመታት ያመጣው ብሶት ነው። ብሶቱ በህወሓት ላይ ብቻ ሳይሆን በሁሉም፤ በድሮ ምሁራን፤ ልሂቃን፤ ተቃዋሚ፤ ወዘተ ነው። እኔ እንደሚመስለኝ የተማሪው ንቅናቄ ወደ እንደ ማርክሲዝም አይነቱ ምዕራባዊ ፍልስፍና እና ርዕዮተ ዓለም በብሶት ምክንያት እንደገባው የዛሬው ትውልድ በብሶቶች ምክንያት እንደ ቀድሞው ተማሪ ንቅናቄ ወደ ኢ-ትውፊታዊ (ምን አልባት ጸረ ኢትዮጵያዊ) የማይሆን አስተሳሰብ እየገባ ነው። ስለ ተውፊቱ ስላልተማረ በምዕራባዊ የቀለም ትምሕርት የሚሰግድ ህብረተሰብ ውስጥ ስላደገ ሳያውቀው ብዙ ኢ-ትውፊታዊ አስተሳሰቦች አድረውበታል።

ስለዚህ ጉዳዩን ወደ ኋላ ወደ መሰረታችን ተመልሰን አመለካከታችንን በሙሉ ከ«ሀ» ብንገመግም ጥሩ ይመስለኛል። ከዛ በኋላ ነው የአማራ ብሄርተኝነት ትውፊታዊ ነው ወይ የሚለውን ጥያቄ በትክክሉ ልንመልሰው የምንችል የሚመስለኝ።


Wednesday, 7 December 2016

የተማረ ገደለን

የኢትዮጵያ ወዳጅ ዶናልድ ሌቪን (ነፍሳቸውን ይማረው) ከ50 ዓመታት በፊት ጅምሮ ባህልንና ማንነትን የማያከብርና የሚክድ ህብረተሰባዊ ለውጥ አገር አፍራሽ ነው እያሉ ኢትዮጵያዊያንን ያስጠነቅቁ ነበር። ኃይለ ሥላሴ ወደ ምዕራብ አገር የላኳቸው ተማሪዎች በኢባህላዊ የሆነ  ከራስ ጋር የሚያጣላ ርዕዮት ዓለም ተነክረው ወደ አገራቸው ሲመለሱ በአስተሳሰባቸው ሰውዉን አስተንግጠዋል። አቶ ዶናልድ ሌቪን አንድ ያጋጠማቸውን እንደዚህ አስታወሱ ነበር፤ አንዱን «የተማረ» ምሁራንን እንደዚህ ብለው ጠየቁት «እንደምትመኘው የሶሽያሊስት አብዮት ቢካሄድ በሚሊዮን የሚቆጠር ህዝብ እንደሚሞቱ ታውቃለህን?» ይህ የተማረ ምህር «በ10 ሚሊዮንም ቢሞቱ ይህን ርዕዮት ዓለምን ለማድረስ ስለሆነ ያዋጣል» ብሎ መለሰላቸው። ከራስ ባህል፤ ወግ፤ ትውፊት፤ ምንጭና ማንነት መራቅ እንደዚህ አይነቱን ቅዠታዊ አስተሳሰብ ነው የሚያመጣው።

ዛሬም ይህ አይነት የቀለም ትምህርት አምልኮ ለኢትዮጵያ ዋናው አጥቂና ጠላት ነው። የምዕራብ ዘመናዊ የቀለም ትምህርት በአገራችን እንደ ጣዎት እንደሚመለክ የሚገልጸው በኃይለ ሥላሴ ዘመን የተሰየመው አባባል «የተማረ ይግደለኝ» ነው። ይህ ዛሬም በኢትዮጵያዊያን ጭንቅላት ይንጸባረቃል። ፖለቲካችንን ካየን አብዛኛው የሚንጸባረቁት ሃሳቦችና አስተያየቶች ከኢትዮጵያ ውጭ የመነጩ ናቸው። የኛ ምሁራኖች እነዚህ ሃሳቦችን እየሰገዱላቸው ኢትዮጵያን ወደ እኒዝህ ርዕዮት አለምን ማስተካከል ይፈልጋሉ። ቢያንስ መደረግ የነበረበት እነዚህን ርዕዮት ዓለሞችን ለኢትዮጵያ እንዲሆኑ ማስተካከል።

ይህ አቋሜን የሚደግፉ አንዳንድ ማስረጃዎች እንመልከት። በመጀምርያ ወደ ኋላ ሄደን የኃይለ ሥላሴ መንግስትን ተመልስን እንመልከት። የዛን ጊዜ ውጤቶች ዛሬ ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ ስለሆነ። በሳቸው መንግስት ዘመነ የምዕራብ «ዘመናዊ» ትምህርት በኢትዮጵያ ውስጥ ተስፋፋ። ተማሪዎች በሞላ ጎደል አለምንም መበረዝ ቀጥታ የምዕራብ ትምህርት ነበር የሚማሩት። ስለአገራቸው ጥቂት ውይም ምንም ነገር ሳይማሩ ይመረቁ ነበር። ለምሳሌ ስለ ዓለም ዙርያ መልክአምድር ተምረው ስለኢትዮጵያ መልክአምድር ምንም አያቁም ነበር! ስለራሳቸው ታሪክ፤ ትውፊት፤ ባህልና ሃይማንቶ አይማሩም ነበር። ሳይታወቅ ግራ የገባው ከፊል ኢትዮጵያዊ ከፊል ፈረንጅ የሆነ ትውልድ ተወለደ። የዝቅተኛ መንፈስ ያደረበት ትውለድ ተፈጠሪ። ሳያውቀው እራሱን የሚንቅና የሚጠላም ትውልድ ተፈጠረ። ግን ከዚህ ትውልድ ልጆች መካከል ግማሾቹ ኢትዮጵያዊነታቸው ቢሸረሸርም ለኃይለ ሥላሴ ታማኝ ነበሩ በሳቸውም «የዘመናዊ ስልጣኔ እቅድ» ይስማሙ ነበር። ሌሎቻቸው ግን እንኳን ታማኝ ለመሆን ጠላት ሆነው ተገኙ። አገሪቷን ያስከወሰ አብዮትን አስነሱ። ሁላችንም እንደምናውቀው ይህ አብዮት በአገራችን አስፈላጊ የሆኑ ለውጦችና መስተካከሎች ከማምጣት ፋንታ በጸረ ኢትዮጵያ የሆነውን በምዕራባዊያኑ ርዕዮት ዓለም በኮምዩኒዝም ስር አገራችንን እንድትወድቅ አደረጋት።

በደርግ ዘመነ መንግስት ደግሞ አብዛኛው የኢትዮጵያ የፖለቲካ ንቅናቀዎች የጸረ ኢትዮጵያ አቋምና ርዕዮት ዓለም ይዘው ነበር የሚራመዱት። ጸረ ሃይማኖት ነበሩ። ጸረ ባህልና ጸረ ትውፊት ነበሩ። እርግጥ በዛን ዘመን ሙዚቃ ጭፈራ ወዘተ «ትስፋፍቷል»። ግን የተስፋፋው በምዕራባዊያን አመለካከት ዘንድ ነው - ስር የሰደደ የማንነት የሆነ ሳይሆን እንደ ልብስ ከላይ የሚለበስ ወይም እንደ ቴአትር የሚታይ ነበር። በመጀመርያ ኮምዩኒስት ነን፤ ግን እስክስታ የምንጨፍር ኮምዩኒስት ነን! በጠቅላላ አብዛኛው ፖለቲከኞችና ምሁራንም የኢትዮጵያ ማንነት መቀየር አለበት ብለው የሚያምኑ ነበሩ።

በኢህአዴግ ዘመን ይህ ወደ ውጫዊ አመለካከት ማድላት ወደ ጸንፍ ደረሰ። በሶሺአሊዝም የተሞላ በጎሳ የተመሰረተ ጸንፈኛ ህገ መንግስት በኢትዮጵያ ተጫነባት። ይህ ክስተት ከኢትዮጵያዊ «የተማረ» ኃይል በተደጋጋሚ የሚታይ አንድ ጸባይን በደምብ ያብራራል። ይህ ጸባይ ጸንፈኝነት ነው። የኢትዮጵያ መሰረታዊ ችግር የብሄር እኩልነት ነው ብሎ ቢታመንም ቋንቋ፤ ባህል፤ መልክአ ምድር፤ ጎሳም የሚያካተት ግን ለዘብተኛ የሆነ ህገ መንግስት ሊመሰረት ይቻል ነበር። ግን ያኔ የነበሩት ኃይሎች ጸንፍ ካልያዝን አሉ! በምድረ ዓለም ታይቶ የማይታውቅ አይነት ህገ መንግስት - ከሶሺያሊስት በላይ ሶሺያሊስት የሚያሰኝ ህገ መንግስት ካልደነገግን አሉ። ጭራሽ ከደቡብ አፍሪካ በቀር የሌለውን ጎሳ በመታወቅያ ጀመሩ! ሁላችንም እንደምናውቀው እስካሁን ይህ መርዝ ነው እያሳመመን ያለው።

ይህ ሁሉ ሆኖ የአገራችን ገዥም ተቃዋሚም ፖለቲከኞችና ምሁራን አሁንም ውጫዊ በተለይ ምእራባዊ አመለካከት ነው ያላቸው። ገዝ ፓርቲ «ዘመናዊነት» የሚባለው አመለካከት ነው ያለው። ሃይማኖት ኋላ ቀር ነው። እግዚአብሔር ሳይሆን ሰው ነው የዓለም ቁንጮ። ባህል፤ ትውፊትና ወግ ውሸት ናቸው። ህዝብ ባህልን ትቶ ወደዚህ አይህነት አመለካከት እስኪ ገባ ድረስ እንደ ያላደገ ህጻን ነውና እኛ ስልጣን ተቆጣጥረን ልናሳድገው ይገባል። ካደገ በኋላ፤ ማለት እንደኛ የ«ዘመናዊ» አስተሳሰብ ካደረበት በኋላ - ስልጣናችንን እንለቃለን። በሌላ አባባል ኢትዮጵያዊነቱን አርግፎ ከኛ ይበልጥ «ያደጉትንና የሰለጠኑትን» ምእራባዊያን ከመሰለ በኋላ ነው ሰው የሚሆነው። ይህ ራስን ማንነትን መጥላት ካልሆነ ምንድነው?

ተቃዋሚው ደግሞ እንደ አሜሪካ ወይም እንደ አውሮፓ እንሁን ነው! (በጅምላ እየተናገርኩኝ ስለሆነ ይቅርታ።) የኢትዮጵያዊነት ራዕይ የለውም። እርግጥ አንዳንድ ጥሩ የሆነ ሃሳቦች እንደ ገዳ አሰራር አጥንቶ በተወሰነ መጠቅም ተነስተዋል። አንዳንዱም ደፋር የንጉሳዊ አስተዳደር (በወግ ደረጃ ብቻ ቢሆንም) ይመለስ የሚሉ አሉ። እነዚህ ሃሳቦች በርካታ ውይይትና ክትትል ያስፈልጋቸዋል ከነዚህ አይነቱ ባህላዊ መንገድ ነውና የአገራችን ውበት የሚመለሰው።

በብዙሃኑ ደረጃ ደግሞ ቤተሰብ ልጁን የምእራባዊ ባህልና ቋንቋ ለማስተማር ይሯሯጣል! ለልጁ ከቀለም ትህምሕርት በላይ በዚህ ዓለም ምንም የለም የሚል መልክት ነው ደጋግሞ የሚያስተላልፍለው። ልጁም የቀለም ትምሕርትን ጣኦት አድርጎታል። ከዛ በኋላ የልጁ አኗኗር ግራ የገባው ሲሆን፤ ትምሕርትና ስራ አለው ግን በሌላው ንሩው ያልተረገጋ መሰረተ ቢስ የሆነ ሲሆን - ወላጅ ግራ ይገባዋል። የዛሬው ትውልድ እንደዚህ ነው እንደዛ ነው ብሎ ያማርራል። ታድያ ባህሉን ያልወረሰ ሰው ሁልጊዜ ኑሮው እንደሚናወጥ አናውቅምን?

በትህትና ባይመስልም ግን የትህትና ምክሬ እንደዚህ ነው። በመጀመርያ የዘመናዊ ትምህርት ምን ያህል ጸረ ባህል፤ ጸረ ትውፊት፤ ጸረ ማንነት፤ ጸረ ኢትዮጵያ እንደሆነ እንረዳ። ሞያ፤ ሳየንስና ቴክኖሎጊ ችግር የለውም ከጥንትም የነበሩ ዘርፎች ናችሀው ከምንምም ጋር አይጋጭም። አደገኛው ግን «ዘመናዊነት» የሚባለው ርዕዮት ዓለም ነው። ቅድም የጠቀስኩት ጸረ ሃይማኖትና ጸረ ባህል የሆነ አስተሳሰብን እንደ መርፌ ይወጋል። ይህን አውቀን ስንዴውን ከንክርዳዱን መለየት አለብን። ጠቃሚውን ትምህርት እየተማርን ጎጂውን እራሳችንን እንድንጠላ የሚያደርገውን ለይተን አውቀን እንተው። የምንማረውን በባህልና ሃይማኖታችን መነጽር ወይም አመለካከት እንማረው። ለልጆቻችንም እንደዚሁ።

ይህ ነው ምክሬ። ዶናልድ ሌቪን እንዳሉት - ክሁሉ ጥቅሳቸው ይህን ነው እጅግ የምወደው - "The vitality of a people springs from feeling at home in its culture and from a sense of kinship with its past. The negation of all those sentiments acquired in childhood leaves man adrift, a prey to random images and destructive impulses…" ከኔ የምትሻሉት ተርጉሙት!