Showing posts with label ምዕራብ ዓለም. Show all posts
Showing posts with label ምዕራብ ዓለም. Show all posts

Friday, 3 August 2018

የበታችነት ስሜት

ሰላሳ አርባ ዓመታት በፊት ከሀገሩ የሚሰደድ ኢትዮጵያዊ ወደ ምዕራብ ሀገር ሲሄድ ከሀገሩ ይበልጥ «የሰለጠነ» እና «የበለጸገ» ሀገር አግኝቻለሁ ብሎ ያስቡ ነበር። የምዕራብ ሀገሮች በሀብት፤ በብልጽግና፤ በግብረ ገብነት፤ በቅልትፍና (efficiency)፤ በንፅህና ወዘተ ከኢትዮጵያ የላቁ መሆናቸው አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ያምን ነበር።

ሆኖም ግን ስደተኛው ምዕራብ ሀገሮችን ቢያደንቅም የሚተችባቸው ጉዳዮች ነበሩ። ለምሳሌ «ዘረኝነትን ያራምዳሉ» ይላል። በአዲስ ቅኝ ግዛት ታዳጊ ሀገራትን ያጠቃሉ ይዘርፋሉ። ኢትዮጵያ ለቅኝ ግዛት ስለማትመች እነ አሜሪካ ካዷት እና በደርግ አይነቱ አረመኔ መንግስት በማርክሲዝም እንድትገዛ አደረጉ። በተለያዩ ሀገራት ሕጋዊ የሆኑ መንግስታትን ይገለብጣሉ። ወዘተ። ኢትዮጵያዊ ስደተኛው ልሂቃኑም የምዕራብ ሀገሮችን በዚህ መልኩ ይከሱ ነበር።

በርካታ ስደተኞች እንደዚህ በማለት የምዕራብ ሀገሮችን ተችተው ሀገራቸው ኢትዮጵያ ችግሮች ቢኖሯትም ከነዚህ ሀገሮች በማንነት ደረጃ አታንስም ብለው ያምኑ ነበር። በዚህ ምክንያት የሀገር የማንነት የበታችንነት ስሜት (inferiority complex) ገና ብዙ አላደረባቸውም። በኢትዮጵያዊነቱ ያለው ኩራት ብዙ አልተቦረቦረም ነበር።

ግን ጊዜው ባለፈ ቁጥር ኢትዮጵያ «አልሻሻል» ስትል ባንጻሩ የምዕራብ ሀገሮች በብልጽግና እይናሩ እና አንዳንድ ልውጦች ሲያደርጉ የፕሮፓጋንዳ ስልታቸውም እየዳበረ ሲሄድ ኢትዮጵያዊ ስደተኛው በአሙሮው የምዕራቡን ዓለም እያበለጠ ሀገሩ ኢትዮጵያን እያሳነሰ ሄደ። ቀስ በቀስ የበታችነት ስሜት (inferiority complex) እያደረበት ሄደ። የህ የበታችነት ስሜት ወደ ሀገር ቤትም ገባ።

ወደ ምዕራብ ሀገር የተሰደደ ኢትዮጵያዊ ደህና ገቢ ማግኘት እና ሃብት ማከማቸት ቻለ። ስደተኛው ድሮ ቢገጥመውም ባይገጥመውም የሚያማርረው ዘረኝነቱ እየቀነሰ ሲሄድ አየ። ለነገሩ ዘረኝነቱ ድሮም ኑሮውን ከማሻሻል አልከለከለውም ነበር። አህን ግን ጭራሽ በጥቁርነቱ ስራ ከማጣት ማግኘት ጀመረ! ባሜሪካ ልጆቹ በጉብዝናቸው ብቻ ሳይሆን የጭቁን (ጥቅር) ዘር በመሆናቸው ስኮላርሺፕ ማግኘት ጀመሩ። የአሜሪካ ኑሮ ከድሮም ይበልጥ እየተመቸ ሄደ።

ይህ ስደተኛ ኑሮው «እየተሳካለት» በሄደ ቁጥር አሜሪካ በሱ አይን ይበልጥ እያማረች ሄደች። ፍትሐዊና መሐበራዊ ስነ ሥርዐቱን ከድሮም ይበልጥ ማደነቅ ጀመረ። ለሴቶች፤ ለልጆች፤ ለጥቁሮች ወዘተ ያለው «መብት» እና ጥንቃቄ ከኢትዮጵያ ጋር ሲያነጻጽረው ይገርመዋል። በፖለቲካ ደረጃ «ዴሞክራሲ» አምላኩ ሆነ «ሲኤንኤን» (CNN) መላዕክቱ ሆነ። በአንጻሩ ኢትዮጵያ በስደተኛው አይን እየቀነሰች እየወረደች ሄደች። አልሻሻል አለች እየባሰችም ሄደች። ስደተኛው ሀገሩን በጎበኛት ቁጥር ከአሜሪካ ጋር እያንጻጸረ ዘመዶቹን ያደነቁራል። በአሜሪካ እና ኢትዮጵያ ያለውን ልዩነት ለማሳየት ያህል ዘመዱን ከ«ሀገር ቤት» ለመውጣት በርካታ አስር ሺዎች ዶላር ይከፍላል።

ዛሬ በኛ በኢትዮጵያውያን የዝቅተኘት መንፈስ በደምብ አድሮብናል ማለት ከእውነት የራቀ አይመስለኝም። ግን ይህ መንፈስ እውነትን ነው የሚያንጸባርቀው? እውነት ዝቅተኛ ህብረተሰብ ነን? ወይም ሀገራችን ዝቅተኛ ነው? ይበልጥ ታላቅ የሆነው ጥያቄ ሙሉ ሰው ለመሆን ወይንም በዘመኑ ቋንቋ «መሻሻል» ከፈለግን እንደ ምዕራቡ ዓለም መሆን ይኖርብናል? ምናልባት ዘፈናችን ጭፈራችን ምግባችንን ለትዝታ ብለን ጠብቀን በሌላው በሙሉ እንደነሱ እንደ ምዕራባዊያን መሆን ይኖርብን ይሆን?

እዚህ ላይ በቀለም ትምሕርት ከምንማረው በሚዲያ ከምንሰማው ፕሮፓጋንዳና ተራ «እውቀት» ወጥተን እናስብ። በአዲሱ ቅን ግዛት የተገዛውን አእምሮአችንን ነፃ እናውጣው የብዥታ መነጽራችንን እንጣል። በመጀመርያ እስቲ ምንድነው «ስልጣኔ» ብለን እንጀምር። ጥያቄውን በምሳሌ ኃይል ለመመርመር ታዋቂውን የሮሜን ስልጣኔን እንመልከት።

በክርስቶስ ዘመን በርካታ አይሁዶች ወደ ሀገራቸውን ወርሮ የገዛው ሮሜ ይፈልሱ ነበር። አንድ አይሁድ ወደ ሮሜ ሲሄደ ዛሬ ኢትዮጵያዊ ከሀገሩ ወደ አሜሪካ እንደመሄድ እናመሳስለው። ሮሜ ሀብታም ነበረች። «ስደተኞችን» መጤዎችን ትቀበላለች ታስተናግዳለች ታበለጽጋለች። ውጣ ውረድ ቢኖረውም መጤዎች የሮሜ ዜጋ የመሆን እድል አላቸው። የሮሜ ዜግነት አንደ ይሁዳ ዜግነት በጎሳ በብሄር በደም የተወሰነ አይደለም ማንም የሮሜ ዜጋ መሆን ይችላል። የሮሜ ፍርድ ቤቶች በደምብ ይሰራሉ በተለይ ለሮሜ ዜጎች እውነተኛ ፍትሕ ይሰጣሉ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ችግር ባጋጠመው ቁጥር አይሁዶች ሲገሱት ሲሉ የሮሜ ዜግነቱን ተጠቅሞ ፍርድ ይጠይቃል! በሮሜ ፍርድ ቤት ትክክለኛ የፍርድ ሂደት እንደሚጠብቀው ስለሚያውቅ ነው። የሮሜ መንግስታዊ አስተዳደር ፍፁም ባይሆንም ከሌሎች አንጻር «የሰለጠነ» ነበር። «ዴሞክራሲ» አይነት ከነ ምክር ቤት አለው። በሮሜ የማሕበራዊ ብረ ገብ አለ። የሴቶች «መብቶች» ከሌሎች ሀገሮች ከይሁዳ ይልቅ የተከበሩ ናቸው። በስነ ሥርዓት  በኩልም ሮሜ የስለጠነች ናት። መንገዶቿ ንፁ ናቸው። መንገደኛ ለመንገደኛ ጎረቤት ለጎረቤት አገልጋይ ለባለጉዳይ ያለው ግንኙነት በጥቅም የተሳሰረ ሰላማዊና የተቀላጠፈ (efficient) ነው። የድሮ «ሮሜ» ስልጣኔ እንደዚህ ይመስላል።

ለዚህም ነው አይሁዶችም ሌሎችም ወደ ሮሜ የሚፈልሱት ሃብቱን እና ስልጣኔውን ፈልገው። ልክ እንደ ኢትዮጵያውያን ወደ አሜሪካ እንደምንፈልሰው «ህይወትን ለማሻሻል» ወደ በአድ ሀገር ይሄዱ ነበር። ግን ሮሜ የይሁዳ ቅኝ ገዥ ነበረች! አይሁዶች ወደ የሚገዛቸው ሀገር ነበር የሚሄዱት። ወደ ዓለምን በሙሉ በጉልበቷ የተቆጣጠረቹ ሮሜ ነበር ለተሻለ ኑሮ ብለው የሚሄዱት። ግን አይሁዶቹንም ሌሎች መጤዎችንም የሮሜ ስልጣኔ  ክፋነቷን እንዳያዩ አድርጓቸዋል አሳውራቸው። ለነሱ ሮሜ የብልጽግና ሀገር እንጂ የክፋት ሀገር አልነበረትም። ሮሜ ሀገራቸው ይሁዳ የሌላት ነገሮች ሁሉ አላት። በዚህ ምክንያት በራሳቸው ባህልና ማንነት ዝቅጠኝነት ተሰማቸው እንደ ሮሜዎች መሆነ ፈለጉ ወደ ሮሜ ህብረተሰብ ተቀላቀሉ።

ይህ ምሳሌ ስለ «ስልጣኔን» ምን ያስተምረናል? ለብዙዎቻችን ስልጣኔ ሀብት ማለት ነው። ሀብት ካለ ሌሎች ጉድለቶች አያታዩንም። ስልጣኔ «ቴክኖሎጂ» ይመስለናል። የሮሜ የከተማው ቧምቧ እና ፍሳሽ ስራ አይሁዶችን ይገርማቸው ነበር። ስልጣኔ ቅልጥፍና (efficiency) ይመስለናል። የሮሜ የመነግስት መዋቅሮች በተለይ ጦር ሰራዊቱ ግቡን በቀላሉ ያስፈጽም ነበር። ስልጣኔ ፍትሕ ነው። ስልጣኔ ግብረ ገብ እና ስነ መግባር ነው።

እነዚህን ሁሉ ስንመለከት ግን ባጭሩ ስልጣኔ ማለት ነግ በኔን በደምብ ማወቅ ነው። አካባቢዬን አላቆሽሽም ሌሎችን መንገደኞችን ውድጅያቸው ሳይሆን ንፁ አካባቢ ስለሚበጀኝ እኔ ካላቆሸሽኩኝ ሌሎችም ስለማያቆሽሹ ነው። እኔ መኪና የማሽከረክረው ሕግ አክብሬ ነው ሌሎች የመንገድ ተጠቃሚዎችን ስለምወዳቸው ሳይሆን ሁላችንም በትክክል ካሽከረከርን ሁላችንም በፍጥነንት እና በሰላም የምንፈልግበት ቦታ ለመድረስ ስለሚያመችን ነው። መንግስቴ ለደሆች እርዳታ እንዲያደርግ እወዳለሁ ሰላምን ለመጠበቅ እኔም ነገ ብወድቅ እርዳታ እንዳገኝ። ወዘተ። ይህ ነው ስልጣኔ ባጭሩ። ሮሜም አሜሪካም የትም ህዝብ ሰላምና ሀብት እያገኘ ሲሄድ ለራሱ ለግል ምቾቱ የሚሆን አሰራሮች ስነ ምግባሮች እየገባው በተግባር መዋል ይጀምራል።

ግን ይህ ስልጣኔ ከጥሩነት፤ በጎነት፤ ሰላም ወዳድነት እና ከፍቅር ጋር አይገናኝም። ነግ በኔ በጎነትም ፍቅርም አይደለም። «የሰለጠነ» ራስ ወዳድነት ነው። ማንም ከጊዜ በሚያመጣው ልምድ በኋላ የሚደርስበት ነው። ማንም ደግሞ ችግሮች ሲያጋጥሙት ካልተመቸው የሚተወው ነው። ሮሜ ለራሷ የሰለጠነች ነበር ለሌሎች ሀገሮች ግን የክፋት መዓበል ነበረች። ዛሬ አሜሪካም አውሮፓም ሌሎችም ለራሳቸው የሰለጠኑ ናቸው ግን ከጠረፍ ውጭ አይደሉም።

ስለዚህ ይህ ሀገር የሰለጠነ ነው የኔ ሀገር አይደለም ብለን የበታችነት ስሜት ሊኖረን ይግባል? በፍፁም! ስልጣኔ ማንንነት አይደለም። ስልጣኔ ይመጣል ይሄዳል በዓለም ታሪክ በተለያዩ ቦታዎች ተገንብቷል ፈርሷል። ስልጣኔ ከፍቅርና በጎነት አይገናኝም። የሰው ማንነት ግን በጎነት፤ ፍቅር፤ ሰላም ወዘተ ነው። ስለዚህ የሰው ልጅ እነዚህን የሚሽህ እስከሆነ መቼም የበታችነት ሊሰማው አይገባም! ከፍቅር ይልቅ «ብልጭልጭን» ሲያመልክ ነው ችግሩ የሚመጣው።

ይህን ተክትሎ እንደ ምዕራቡ ዓለም መሆን አለብን ብሎ ማሰቡም ተገቢ አይደለም። ለምን ብትሉ የምዕራባዊያን ርዕዮት ዓለም ከኢትዮጵያዊነት ትውፊትና ማንነት 180 ዲግሪ የተቃረነ ነው። የምዕራባዊ አስተሳሰብ የሰው ልጅ የዓለም ቁንጮ አድርጎ ያስቀምጠዋል። እግዚአብሔር የለም ወይንም ምንም ሚና አይጫወትም ይላል። ኢትዮጵያዊ ግን በትውፊታችን ፈጣሪ ነው በአምሳሉ የፈጠረን ብለን እናምናለን ሁሉ ነገራችንም ከዛ ይከተላል። ለዚህም ነው የጠ/ሚ አብይ አህመድ የይቅርታ፤ ፍቅር እና ሰላም መልዕክቶችን በደስታ እና ጉጉት የምንቀበለው። እንደዚህ አይነቱ መልዕክት የተም ምዕራብ ሀገር እንደ ህፃንነት ነበር የሚታየው። ስለ ልማት፤ ነፃነት፤ መብት ነው የምዕራብ ሀገር ውይይት። እግዚአብሔር የለምና።

ታሪክ ረዥም ነው። 500 ዓመት በፊት ቻይና ከሁሉም «የሰለጠነች» ነበር። 60 ዓመት በፊት ቻይና ወደ 40 ሚሊዮን ህዝቦቿን ገደለች ግማሽ ሀገሪቷ በርሃብ እየተሰቃየ ነበር። 2000 ዓመት በፊት ስሜን አውሮፓ በሮሜዎች ዘንድ የያልሰለጠና የአረመኔ ስፍራ ነበር። ዛሬ ደግሞ ከዓለም በሙሉ የሰለጠው ጎራ ይባላል። 60 ዓመት በፊት ኢትዮጵያ በዓለም ደረጃ ታላቅ ክብር ነበራት። ዛሬ እንደ ለማኝ ትታያለች። እኛ ኢትዮጵያዊያን ይህንን ብናስታውስ ጥሩ ይመስለኛል።

እውነት ስልጣኔ ፍቅር እና ሰላም ነው። የኛ የኢትዮጵያዊያን በዚህ ረገድ ከማንም ልናንስም ልንበልጥም እንችላለን የኛ ፋንታ ነው። ግን የሰው ልጅ በመሆናችን ከማንም አናንስም አንበልጥምም። የዝቅተኛ ስሜታችንም በምንም መለክያ ተገቢ አይደለም። እጅግ ጎጂም ነው። ሌላውን ምዕራባዊያንም ለመገልበጥ መሻህ ዋጋ የለውም ጎጂ ነው። ማንነታች ከፈጣሪያችን የተሰጠን ነውና ምንም የምናፍርበት ሊሆን አይገባም። እርግጥም ለሌሎች ምሳሌ ሆነን መገኘት ነው ያለብን ድሮ ሆነን እናውቃለን አሁንም የማንሆንበት ምክንያት የለም።

Monday, 4 June 2018

የዘመናዊነት ዕቅድ (The Modern Project)

ይህ ከቀሲስ/መምህር ስቲፈን (እስቲፋኖስ) ፍሪማን ጽሁፍ (https://blogs.ancientfaith.com/glory2godforallthings/2014/01/10/the-modern-project/) በሰፊው የተረጎምኩት ነው። ቀሲስ ስቲፈን አሜሪካዊ (ምስራቃዊ ወይም ቃልቄዶናዊ) ኦርቶዶክስ ቄስ ናቸው። ከፕሮቴስታንትነት ወደ ኦርቶዶክስ እምነት «ከተመለሱት» በርካታ አሜሪካዊ ካህናት መካከል ናቸው። አሜሪካዊ በመሆናቸው ብቻ ሳይሆን በቀለም ትምሕርት እና በሃይማኖት ታሪካቸው ምክንያት ስለ በዘመናችን የነገሰው ዘመናዊነት ፍልስፍና በደምብ ያውቃሉ ለክርስትና ዋና ጠላት መሆኑንም ይገነዘባሉ። ሆኖም የዘመናዊነት ፍልስፍና የነገሰ ስለሆነ ሳናውቀው ሁላችንም በተወሰነ ደገጃ እንደተቀበልነው ያውቃሉ። ሰለዚህም ነው ቀሲስ ስቲፈን በዚህ ጉዳይ ዙርያ ብዙ የሚጽፉት። ጽሁፋቸው ለሁላችንም ገላጭ እና አስተማሪ ነው ብዬ አምናለው። ብሎጋቸውን ብታነቡ እጅግ ጠቃሚ ይሆናችኋል ብዬ አምናለው።

ሁለተኛ ዲግሪዬን በ«ቴኦሎጂ» በምማርበት ወቅት (1970 ዎቹ) «የዘመናዊነት ዕቅድ» ('the project of modernity') የውይይት ርዕስ የነበረበት ጊዜ ነበር። ይህ የዘመናዊነት ዕቅድ «ዘመናዊውን» ዓለም ('the modern world') ለመገንባት የሚሰሩትን ማህበራዊ፤ ፍልስፍናዊ፤ ፖለቲካዊ እና ሃይማኖታዊ ስራዎችን ያካትታል። በ17ኛ ክፍለ ዘመን የመነጨው «የብርሃን መብራት» ('the Enlightenment') ፍልስፍና አዲስ የአስተሳሰብ አይነቶች ወደ ምዕራባዊው ዓለም (ከዛ ቀጥሎ ወደ መላው ዓለም) አመጣ። ለምሳሌ ለ«ሀገር» የምንለው ፅንሰ ሃሳብ አዲስ ትርጉም እና አወቃቀር ፈጠረ። የክርስትና ሃይማኖትን በአዲስ መልክ ፈጠረ (ለምሳሌ ፕሮቴስታንትነት)። ከሁሉም በላይ ግን የሰው ልጅ ማንነትን ሌላ ትርጉም ሰጠው።

እኛ የዚህ ዘመን ሰዎች የዚህ ፍልስፍና ወራሾች ነን። የዘመናዊነት እና የዘመናዊነት ዕቅድ ልጆች ነን። ዛሬ ማንም ትምህርት የሌለውም ሰው «የዘመናዊነት ዕቅድ» ያመጣውን አስተሳሰቦችን ሳያውቀውም ቢሆን አድሮበታል አምኖበታልም። በትምህርት ቤትም በሚዲያም በሌሎች መንገዶች አስተሳሰቡን ወርሰነዋል። እኛ «የዘመናዊነት ዕቅዱ» ውጤቶቹ ሆነናል።

ዘመናዊነት ዕቅዱ የሰው ልጅን ማንነት ሲደነግግ እንደዚህ ይላል፤ « የሰው ልጅ በራሱ ብቻ የሚተዳደር ነፍስ ነው፤ ውሳኔዎቹ እና ስራው ብቻ ነው ማንነቱን የሚወስን»። ይህ ማለት፤

1. በራሱ ብቻ የሚተዳደር ነፍስ፤ የሰው ልጅ የማንነቱ መሰረት በማወቅ እና ማሰብ ችሎታው የተወሰነ ነው። «የማሰብ እና ማወቅ ችሎታዬ ብቻ ነው የሰው ልጅ የሚአደርገኝ»። ከዚህ ቀጥሎ በፈቃዴ ከሌሎች ጋር መጋራት እችላለሁ ግን ማንነቴ በራሴ ብቻ ነው የሚወስነው። ከሌሎች ጋር ያለኝን ግንኙነትም እኔ ብቻ ነው የምወስነው። ይህ ነው በዘመናዊው ዓለም የምናየው የ«ግለኝነት» አኗኗር መሰረታዊ ሃሳብ።

2. ውሳኔዎቻችን እና ስራዎቻችን ማንነታችንን እና የህይወት ጉዞዋችንን ይወስናሉ፤ በዚህ ዓለም ያለኝ የማንነት ምደባ የራሴ አመራረጥ፤ ውሳኔዎች እና ያሳለፍኩት ልምዶች ናቸው የሚወስኑት። ውሳኔዎቼ ማንነቴን ይወስናሉ እና መሆን የምፈልገውን መሆን እንድችል ብቸኛ ሚና ይጫወታሉ። የኔ ምርጫ እና ውሳኔዎች ናቸው የህይወቴን ትርጉም እና ማን መሆን እንደምፈልግ የሚወስኑት።

እነዚህን ፅንሰ ሃሳቦች ካሰላሰልናቸው የዘመናችን ታሪክን ወሳኝ ነገር «ነፃነት» ለምን እንደሆነ በቀላሉ እንረዳለን። (ይህ «ነፃነት» የሚባለው የመወሰን እና የመምረጥ «መብት» ነው እንጂ እውነተኛው ነፃነት አይደለም።) የሰው ልጅ ማንነት ትርጉም ከላይ የተጻፈው ከሆነ ይህ «ነፃነት» የግድ ይሆናል። ይህን ነፃነት የሚገድብ ሁሉ የሰው ልጅ ህልውና እና ፍላጎት ጠላት ይሆናል። እንደ ፈለግኩኝ መምረጥ መወሰን ስችል ነው ፍላጎቴን ማምዋላት የምችል ሰው መሆን የምችለው።

ከላይ እንደጠቀስኩት ባሁኑ ዘመን እነዚህ አይነት አስተሳሰቦች ሳናውቀው ሰርቀው አዕምሮአችን ውስጥ ገብተዋል። ዓለም ዙርያ ታውቀዋል። እንደ «ነፃነት» እና «ምርጫ» አይነቶቹ ቃላቶት ምን ማለት እንደሆኑ ብዙሃኑ ተውሕዶታል። እነዚህን ቃላቶችን ስንጠቀም ሁሉም ሰው ትርጉማቸውን «ያውቃል»።

አንዳንድ የክርስቲያን ቡድኖች በተለይም የፕሮቴስታንት ንቅናቄ ይህን አስተሳሰብ አቀናብረው አንጸራጭተውታል። እነዚህ የክርስቲያን ቡድኖች ከአሜሪካ እና አውሮፓ ተነስተው የ«ዘመናዊ» ክርስትና ዓለም ዙርያ አስፋፍተዋል። በጥናታዊ ክርስትና ያልነበሩ አስተያየቶች እና ጥያቂዎችን አስፋፍተው የተለመዱ እንዲሆኑ አደረጉ። ለምሳሌ የህፃንነት ጥምቀት ጥያቄ፤ ዛሬ ሰው ለምን በህፃንነቱ ክርስትና ይነሳል የሚለው ጥያቄ ይጠየቃል። ልበ በሉ ለመጀመርያዎቹ ፕሮቴስታንቶች ይህ ጥያቄ አልነበረም ግን የተከሉት ዘር ወደዚህ አመራ። ጥያቄ የሆነው ምክነያት የህጻንነት ጥምቀት «ነፃነትን» ይሽራል ተብሎ ነው! «ህፃኑ እንዴት አለ «ምርጫው» ይጠመቃል። ለመጠመቅ ላለመጠመቅ ነፃነቱ ሊኖረው አይገባምን?» ይባላል! በዘመናዊነቱ ዕቅድ ምርጫን ወይም የራስ ውሳኔን የሚገድብ ነገር አደገኛ ነው ተብሎ ይሰየማል። በየ «ኤቫንጀሊካል» ፖሮቴስታንት ቤተ ክርስቲያን ክርስቲያን መሆን የ«ነፃ ምርጫ» ጉዳይ ነው ይባላል። «የውሳኔው ስዓት» ሰዎች ክርስቶርስን ጠቀብያለሁ የሚሉበት ጊዜ በዘመናችን ተለምዷል።

ቤተ ክርስቲያን ስለ ገብረ ግብ የምታስተምረውም በዘመናዊነት ዕቅዱ ምክንያት በጥርጣሬ ላይ ወድቋል። ዘመናዊ ሰዎች እራሳቸውን «ካቶሊክ»፤ «ኦርቶዶክስ»፤ «ጴንጤቆስጣል»፤ «ፕሬስቢቴሪያን» ወዘተ ብሎ ቢሰይምም ቤተ ክርስቲያናቸው ስለ ግብረ ገብ ወይም ስነ መግባር ኑሮዋቸው መወሰን የለባትም ብለው ያምናሉ። እራሳቸውን «ካቶሊክ» ብለው ቢሰይሙም በካቶሊክ እምነት አይገዙም። ለምሳሌ አብዛኞች አሜሪካዊ ካቶሊኮች ቤተ ክርስቲያናቸው በተለይ ስለ ቤተሰብ እና ጋብቻ የምታስተምረውን ሌሎችም ትምህርቶቿንም ይክዳሉ! ከቤተ ክርስቲያናቸው እምነቶች የሚፈልጉትን ይመርጣሉ የግል ምርጫዬ ነው የነፃነት ጉዳይ ነው ብለው ያምናሉ። ግን ይህ «የግል ሃይማኖታቸውን» በራሳቸው «ነፃነት» እና ምርጫ «ካቶሊክ» ብለው ይሰይማሉ። በዚህ አስተሳሰብ «ካቶሊክ»፤ «ኦርቶዶክስ»፤ «ሉቴራን» ወዘተ ሰው የሚመርጠው ማንነት ነው እንጂ ማንነትን እና ህይወትን የሚወስን ጉባኤ አይደለም።

የዘመናዊነት ዕቅዱ የጥንታዊ ክርስትና ጠላት ነው።

በጥንታዊ አመለካከት የሰው ልጅ ለራሱ ብቸኛ ወሳኝ አይደለም። በዚህ ዓለም የምንገኘው ከራሳችን ሌላ በሆነው በእግዚአብሔር ፈቃድ ነው። ህይወታችን የእግዚአብሔር ስጦታ ነው። የህይወታችን አላማው፤ ትርጉሙ እና አቅጣጫው በእግዚአብሔር የተሰጠ ነው። የሰው ልጅ የሚያደርገን እና ዋጋ የሚሰጠን በእግዚአብሔር ምሳሌ መፈጠራችን ነው እንጂ ውሳኔዎቻችን ወይም የመወሰን አቅም ስላለን አይደለም። የሁላችንም ታናሾች አቅም የሌላቸው፤ ችሎታ የሌላቸው፤ ከአልጋ ተኝተው መንቀሳቀስ የማይችሉት፤ ወዘተ በኢግዚአብሔር ምሳሌ በመፈጠራቸው ክብር እና ዋጋ አላቸው።

ማንነታችን በህይወት ምርጫዎቻችን እና ውሳኔዎቻችን ብቻ አይደለም የሚወሰነው። ህይወታችን እና ማንነታችን ከእግዚአብሔር ያገኘነው ስጦታ ነው። እሰረታዊ ማንነታችን በተወሰነ ደረጃ የተመደበ ነው። ይህ ማንነት በክርስትና ህይወት የሚገለጽ እና የሚለወት ነው እንጂ አንድ ሰው በግሉ የሚፈጥረው አይደለም። ምርጫዎቻችን እና ውሳኔዎቻችን ሚና ይጫወታሉ ግን ከእግዚአብሔር ውሳኔ ስር ነው ሚናቸው። ዞሮ ዞሮ የእግዚአብሔር ፍጥረቶች ነን ስለዚህ ውሳኔዎቻችን ትርጉም ያላቸው ከሱ ጋር ባለን ግንኝነት ነው።

በዘመናዊነት ዕቅዱ እና በጥንታዊው አመለካከት ያለው ጦርነት በደምብ የሚታየው በተለይም በምዕራቡ ዓለም በስነ ህይወት (biology) እና የሰው ግንኝነት ዙርያ። ጥንታዊ የክርስትና አመለካከት ስነ ህይወታችን፤ ማለትም ሰውነትና አካላችን ወዘተ፤ የተሰጠን ነው። እንደ አባት፤ እናት፤ ወንድም፤ እህት ወዘተ ያለን ከሰው ጋር ያለን ግንኙነቶችም የተሰጡን ናቸው። ጾታ ምርጫ አይደለም። ቤተሰብም የደም ተፈጥሮ ነው እንጂ በምርጫ አይደለም። በባለና ሚስት መካከል ወይም ሌሎች ወሰባዊ ግንኙነቶች የተሰጠ አላማ አላቸው እንጂ የግል ፍላጎት ማምዋያ አይደሉም። ግን የዘመናዊነት ዕቅዱ «ነፃነትን» እና «ምርጫን» እንዲሰፍኑ ማድረግ ነው የሚፈልገው። የሰው ተፈጥሮ እውነት ነው ግን ወሳኝ አይደለም ይላል (ለዚህም ነው ዛሬ አንዳንዶች ጾታቸውን የሚመርጡት)። ቤተሰብ የምርጫ ጉዳይ ነው የምንፈልገውን ግንኙነቶችን እንመርጣለን። የደም ትሥሥር የተሰጠ መሆኑ እና በደም ትሥሥር ምክንያት ሃላፊነቶች መኖራቸው በምዕራባዊ ሀገራት መንግስታት እና ፍርድ ቤቶች እየተካደ ነው። ለዚህም ነው በእግዚአብሔር ፈቃድ የተጸነሰው ከ«ነፃነት» ጋር መወዳደር ያልቻለው እና ጽንስን ማስወረድ የሰፈነው።

ዛሬ «እውነት» የሚባለው ነገር አሻሚ ሆኗል። የኔ እውነት ካንተ እውነት ይለያል ግን ሁለቱም እውነቶች ናቸው ይባላል። እውነትም የምርጫ ጉዳይ ሆኗል። አንድ የሆነ እውነት የለም ይባላል። በዚህ ዘመናዊ ዓለም እውነት አንድ ነው ማለት እንደ ጭቆና ነው የሚቆጠረው። የጥንታዊ ክርስትና አስተያየት ከነ ህግ እና እምነቱ የማይመች እና መጥፋት ያለበት ሆኖ ነው የሚታየው። ዘመናዊው ዕቅድ «ለምን እግዚአብሔርንም በራሳችን ምርጫ በራሳችን ምናብ አንፈጥረውም አንወስነውም» ይለናል።

መጨረሻው

ከመጀመርያ ጀምሮ ለ400 ዓመታት በላይ የዘመናዊው ዕቅድ የጥንታዊ ክርስትናን ተዋግቶ ከሰው ልጅ ከህዝብ ማስወገድ ነው አላማው። የዘመናዊነት ጥያቄ «እግዚአብሔር እንዴት ነው የፈጠረን» ሳይሆን «ዓለምን ምን እንዲመስል ነው የምንፈልገው?» ነው። የዓለም ሁኔታ የሰው ምርጫ ጉዳይ ነው ብሎ ነው የሚያምነው። ስለዚህ ነው የዘመናዊ ዕቅዱ ልጅ የሆነው የፕሮቴስታንት ስነ መለኮት (ቴኦሎጂ) የክርስትናን ትውፊት እና ወግን ከመመርመር እና ማጥናት ይልቅ ወንጌልን በራሱ ምናብ መተርጎም የፈለገው።

ማርቲን ሉተር «በመጻሐፍት ብቻ» ('Sola Scriptura') የሚባለው የፕሮቴስታንት አቋምን ሲፈጥር ማንም ሰው መጸሀፍ ቅዱስን አንብቦ አለ እርዳታ አለ ቤተ ክርስቲያን አለ ሃዋርያት በትክክሉ ይተረጉመዋል ለማለት ነው። ማርቲን ሉተር የሮሜ ጳጳስን ወይም የሮሜ ቤተ ክርስቲያን ችግሮችን በመቃወም ስበብ ክርስትናን በራሱ ውሳኔ እና ምርጫ መቅረስ ፈለገ። በዝህ መልክ ይህ «በመጸሐፍት ብቻ» የሚባለው አስተያየት በመጀመርያ ቤተ ክርስቲያንን እና ትውፊቷን ለመለየት የተጠቀሙበት መሳርያ ነበር። ግን ባልታሰበበት (ግን ሊታሰብበት) መልክ ይህ አስተሳሰብ ሰዎች መጸሀፍ ቅዱስን በግላቸው እንተርጉም እያሉ ከአንድ ከሉተር ከሁለት የሉተር ተፎካካሪ ዝዊንግሊ ወደ 30 ሺ አተረጓገም (ዛሬ ዓለም ዙርያ ያሉት የፕሮቴስታንት ቡድኖች ቁጥር) ደርሷል።

ግን «የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም» እና ዛሬም የጥንታዊ ክርስትና አለች የዘመናዊነቱን ዕቅድን የስጋው መውግያ ናት። የዘመኑ ሚዲያ ቫቲካንን አትኩረው ያያሉ ገና ለገና መሰረቷን ሸርሽራ ትጨርሳለች እጇን ሙሉ በሙሉ ለዘመናዊነቱን ዕቅድ ትሰጣለች ብለው። በሩስያ ከሞት የተነሳችው ኦርቶዶክስ እምነት ደግሞ ከፖለቲካዊ «አምባገነን» ጋር የተያያዘ እና «ኋላ ቀር» ብለው ይሰይሙታል! ጦርነት ነው!

ዛሬ የጥንታዊ ክርስትና መንገድ ከባድ ነው። አታላዩ መንገድ ዝም ብሎ ጸረ የዘመናዊው አብዮት መሆን ነው። ከዘመናዊነት ዕቅዱ እኩል እንደ አማራጭ መወዳደር። ግን ክርስትና እንዳዚህ ካረገች እጇን ለዘመናዊው ዕቅድ ሰጠች ማለት ነው። ሌላ «ምርጫ» ሆነች ማለት ነው። ግን ጥንታዊ ክርስትና የምርቻዎቻን ውጤቶች አይደለንም ህይወቶቻችን በእግዚአብሔር ጸጋ እና ስጦታ ነው የሚወሰነው ሁሉም ነገር ከእግዚአብሔር አኳያ ነው የምንመለከተው ነው። የቤተ ክርስቲያን ተውፊት የለ የተሰጠ ነገር ነው እንጂ ምርጫ አይደለም። ስለዚህ እራሱን እንደ አንድ አማራጭ አያቀርብም ሊያቀርብም አይችልም።

የጥንትዊ ክርስትና መንፈስ ስለ በራስ መምርጥ ሳይሆን እራስን ባዶ ማድረግ። ማለት የራስን ፍላጎት ትቶ የእግዚአብሔርን ፍላጎት ማወቅ እና ማክበር። እጅን ለእግዚአብሔር ሙሉ በሙሉ መስጠት። ጥንታዊ ክርስትና ህይወት የተሰጠ እንደሆነ ይረዳል። የተፈጥሮ የደም ትሥሥር፤ ቤተ ሰብ እና ዝምድና ተጭባጭ ናቸው እና ህይወታችን ላይ ተገቢ ሚና ይጫወታሉ ሃላፊነት ይሰጡናል። ዓለም እንደዚህ ትሁን እንደዛ ትሁን ብለን ማለም ከለት ለለት ከባድ የሆነ የክርስትና ኑሮአችን እንድንርቅ እንድንሰንፍ ፈተና ነው። የዓለም ድሃ ይረዳ እያልኩኝ እየተፈላሰፍኩኝ ድሃ ባለንጀራዬን ዞር ብዬ አላየውም! ግን የዘመናዊነት ዕቅድ እንደዚህ ነው የሚያስበው። ዓለምን አሻሽላለው ይላል። ከ«ነፃነት» በደምብ ማትረፍ የሚችሉትን ባለ ሃብቶች እና በትምሐርት ጎበዞች በደምብ አትርፈዋል። ግን ይህ የዘመናዊነት ዕቅድ ፉከራ ባዶ ነው ህይወታችንን በራሳችን መወሰን ስለማንችል። እራሳችንን ከእውነታችን በላይ ታላቅ አርገን ብናስብም መጨረሻ ላይ ሞት ምርጫችንን አያከብርም! ምናልባትም የዛሬው ታላቅ አሽሙር የዘመናዊነት ዕቅዱ የ«መሞት መብት»ን ማራመዱ ነው አለመሞት ምርጫ እንደሆነ!