Showing posts with label ምሁራን. Show all posts
Showing posts with label ምሁራን. Show all posts

Saturday, 29 December 2018

ልሂቃኖቻችን ዛሬም የምዕራባዊነት እስረኞች…

እምብዛም ልሂቃን እና ምሁራኖቻችን ዛሬም በምዕራባዊነት አምልኮ የተለከፍን ነን። እንግሊዝን፤ ጀርማንን፤ አሜሪካንን ገልብጦ እንዳለ ወደ ኢትዮጵያ ከማምጣት ውጭ ሃሳብ የለንም። ምናልባት የኢትዮጵያ ህዝብ ሙሉ ለሙሉ እንደ ምዕራብ ሀገር ለመሆን ዝግጁ ባለመሆኑ ጉዞውን ቀስ በ ቀስ እንጀምራለን እንል ይሆናል። ግን ግቡ አንድ ነው፤ ኢትዮጵያን እንደ «ፈረንጅ» ሀገር ማድረግ ነው።

ይህ አካሄድ ለኔ unimaginative ብቻ ሳይሆን ለሀገራችን የማይሆንም ነው ብዬ አምናለሁ። የኢትዮጵያዊነት ምሁራ ዶናልድ ሌቪን እንደሚያስታውሱን፤
"The vitality of a people springs from feeling at home in its culture and from a sense of kinship with its past. The negation of all those sentiments acquired in childhood leaves man adrift, a prey to random images and destructive impulses…"
ለኔ፤ በግሌ፤ ኢትዮጵያን እስክስታ፤ እንጀራ፤ ወዘተ ያላት ፈረንጅ ሀገር ማድረግ ትርጉም የለውም። ማንነትን ማጣት ነው። ባህላዊን እሴቶችን ማጣት ነው። አብሮነትን አጥተን ብጨኞችን መሆን ነው። ፍቅር አጥተን ነግ በኔዎች መሆን ማለት ነው። እምነት አጥተን እምነት የለሾችን መሆን ማለት ነው። ለኔ ይህ ትሩጉም የለውም።

ግን ልሂቃን እና ምሁራኖቻችን የሀገር ወጋችን ገብቷቸው አክብረውት መራመድ ያቃተን ምክንያት ይገባኛል። በመጀመርያ ወጋችንን በደምብ አላከበርንም። በጃንሆይ ዘመን የነበረው የፍትህ እጦት እና ጭቆና (በምንም ደረጃ ቢሆንም) የመጀመርያ ሀገር በቀል ፈረንጆቻችን እንዲወለዱ አደረገ። በሃይማኖት ተቋሞቻችን የነበረው ግብዝነትም እንዲሁ ጥላቻ ፈጠሮ ምሁራን ወደ ማርክሲዝም እንዲሄዱ ጋበዘ። ይህ ለምሁራኖቻችን ፈረንጅ አምላኪነት አንዱ ምክንያት ነው።

ሌላው ምክንያት ዘመናዊ ትምሕርት አሰጣጡ ነው። ሶሻል ሳየንስ ተማሪዎቻችን ከሞላ ጎደል የሚማሩት የዘመኑ ርዕዮት ዓለም ነው። ርዕዮት ዓለሙ እንደ እውነት ነው የሚሰበክላቸው አብዛኞቹ አለ ጥያቄ ይቀበሉታል። እንደ ምሁራን መቀጠል ከፈጉ ደግሞ ምርጫ የላቸውም። ከዘመኑ ርዕዮት ዓለም የተለየ አስተሳሰብ በባልደረቦቻቸው እንዲናቁ እና እንዲዘለፉ ነው የሚያደርጋቸው። ስራቸውንም ያጣሉ ማንም ዩኒቨርሲቲ ወይም ሌላ ተቋም አይቀጥራቸውም። ስለዚህም የዘመኑን ርዕዮት ዓለምን እንደ ጣኦት ያመልኩታል።

ሶስተኛው ምክንያት የኢትዮጵያ ነባራዊ ችግሮች ናቸው። አስተዋይ ያልሆነ ሰው ሃብታሙ እና ምቾት የተሞላውን ምዕራብ ዓለም ከኢትዮጵያ ጋር አወዳድሮ ምዕራብ ነው ትክክል ይላል። ማስተዋል የማይችል። ጠልቆ ማሰብ እና ማየት የማይችል። መሳደቤ አይደለም፤ እኔም ወደ እንደዚህ አይነት ቀላል ድምዳሜ ተስቤ አውቃለሁ።

ስለዚህ ዛሬ በኢትዮጵያ ታላቅ የምሁራን እና ልሂቃን እጥረት (deficit) አለ። እምብዛሙ ውጭ ሀገር የሚያየውን ፎርሙላ ወደ ሀገር ማምጣት ብቻ ነው የሚታየው። ማንነቱን አጥቷል። ማርክሲዝም ይሁን፤ «ሊበራሊዝም» ይሁን፤ ሶሻሊዝም ይሁን፤ «ማርኬት ኤኮኖሚ» ይሁን፤ ሴኩላሪዝም ይሁን፤ ፌሚኒዝም ይሁን፤ ዴሞክራሲ ይሁን ለምሁራኖቻችን ጣኦት ሆነዋል። ለምን ኢትዮጵያዊነት እንደሚያሰኝንም አላውቅም። አሜሪካዊ መሆን ይሻለናል ማንነታችን አሜሪካዊ ከሆነ።

ፋንታሁን ዋቄ እንዳለው ታላቅ paradigm shift ያስፈልገናል። አቢይ አህመድም ደጋግመው እንደሚሉት የሀገራዊ እሴቶቻችንን ተምረን አቅፈን እንራመድ። እሴቶቻችንን እንፈተሽ እና እናሟላ። አንድ አጭር ምሳሌ ልስጥ፤ ሃይማኖታዊ መቻቻል (https://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/04/blog-post_3.html)። የሀገራችንን ወግ የማያውቅ የሀገራችን ሃይማኖቶች መቻቻልን አያውቁም ይላል። ወይን መቻቻል የሚችሉት መሰረታቸውን ትተው ባህል ብቻ ሲሆኑ ነው ይላል። ግን ከላይ እንደጠቀስኩት ጽሁፌ በኦርቶዶክስ ክርስትና ለምሳሌ ከመቻቻል አልፎ ፍቅር ነው ዋናው መርህ! ሙስሊሙን መቻል (አሉታዊ ነገር ነው tolerate) የለብኝም መውደድ ነው ያለብኝ! ግን አብዛኞች ምሁሮቻችን መቻቻልን ከምዕራባዊነት እና ሴኩላሪዝም ያያይዙታል! ይህ ትንሽ ምሳሌ ነው። ወጋችንን እንፈትሽ። የምዕራብ ርዕዮት ዓለም እስረኞች አንሁን። ለራሳችን ማንነት ክብር እና ፍቅር ይኑረን። እራሳችንን እንወቅ።

Thursday, 17 May 2018

የ«አማራ ብሄርተኝነት» ትውፊታዊ ነውን?

የ«አማራ ብሄርተኝነት» ትውፊታዊ ነው ወይስ እንደ ሌሎች የጎሳ ብሄርተኞቻችን (ኤርትራ፤ ትግራይ፤ ኦሮሞ፤ ወዘተ) በፈረንጅ በምዕራባዊ በ«ተራማጅ» በማርክሲስት ፍልስፍና የተመሰረተ ነው?

እርግጥ ብዙ አይነት የአማራ ብሄርተኝነቶች አሉ፤ ለፖለቲካ ስልት ወይንም «ታክቲክ» ብቻ የሆነ አለ፤ በስመ አማራ ላለፉት 27/40 ዓመታት ለተበደሉት ፍትሕ መጠየቅያ የሆነ አለ፤ ዛሬ አማሮች ላይ የሚደርስባቸውን በደል ለመታገል የሆነ አለ፤ በሀገር ደረጃ በፖለቲካ ድርድር ለአማራ ህዝብ የሚቆም አለ፤ በሃሰት የታማው የአማራ ህዝብን ታሪክ እውነቱ እንዲታወቅ የሚንቀሳቀስ አለ፤ የአማራ ህዝብ ክብርና ማንነትን ለመመለስ የሚታገለው አለ፤ ወዘተ። ዛሬ እነዚህ ሁሉ አይነት እንቅስቃሴዎች በስመ አማራ ብሄርተኝነት ይጠራሉ።

ዞሮ ዞሮ ዋናው ነጥብ ይህ የፖለቲካና መሃበራዊ ንቅናቄ እራሱን የ«አማራ ብሄርተኝነት» ብሎ መሰየሙ ነው። አላማው ምንም ቢሆን በዚህ «አማራ ብሄርተኝነት» የሚለው ስም መጠራት ይፈልጋል። በዚህ ስም መጠራቱ ምን ይነግረናል? በተለይ በትውፊትና በተቃራኒው ምዕራባዊ ተራማጅነት ያለው ግንኙነቱ ምንድነው?

ደስ የሚለው ነገር የሁሉም አይነት የአማራ ብሄርተኝነት ምልክቶች ትውፊታዊ ናቸው። ለምሳሌ ዓፄ ቴዎድሮስ አንዱ ዋና የአማራ ብሄርተኝነት ንቅናቄ ምልክት ናቸው። የአማራ ታሪክን በትክክሉ ማስተዋወቅና መናገር ሌላው የአማራ ብሄርተኝነት አላማና ምልክት ነው። ግን ዓፄ ቴዎድሮስ እራሳቸውን ወይንም ሀገራቸውን ወይንም አገዛዛቸውን የአማራ ወይንም «አማራ ብሄርተኛ» ብለው ይሰይሙ ይሆን? የአማራ ታሪክ የምንለው በታሪክ ሰሪዎቹ እና በዘጋቢዎች ዘንድ የአማራ ታሪክ ይባል ነበር? የአማራ ብሄርተኝነትን ያንጸባርቅ ነበር?

ለነዚህ ሁለቱም ጥያቄዎች መልሱ «አይደለም» እንደሆነ ነው የማውቀው። ዓፄ ቴዎድሮስ እንደ ሁሉም ንጉሶቻችን በስመ ኢትዮጵያዊነት ነበር እራሳቸውን የሚመለከቱት። ታሪካችም እንዲሁ ኢትዮጵያዊነት ላይ ነው የሚያቶክረው አማራነትን አይደለም። ይህ ማለት «አማራ» የሚባል ህዝብ የለም አልነበረም ማለት አይደለም! መኖሩ በታሪክ በተለያየ ቦታ መመዝገቡ ይታወቃል። ግን እስከማውቀው ማንም በስመ አማራ አልተንቅሳቀስም። ትውፊታችንና ታሪካችን እንደዚህ ከሆነ እንዴት እራሱን «አማራ ብሄርተኝነት» ብሎ የሰየመ ንቅናቄ ትውፊታዊ ነው ማለት ይቻላል?

በሁለተኛ (ወይንም አንደኛ!) ደረጃ ጠቅላላ የጎሳ ብሄርተኝነት የሚባለው ነገር የምዕራባዊ የፖለቲካ ፍልፍና እንደሆነ ይታወሳል። በትውፊታዊ ፖለቲካ «ሀገር» ነው ያለው፤ «ጎሳ» የለም። ይህ አባባሌ ብዙ ነገሮች ስለሚያከማች ሁሉንም በዚህ ጽሁፍ አልጠቅስም ግን በጠቅላላ የ«ጎሳ ብሄርተኝነት» የዘመናዊ የምዕራባዊ ጽንሰ ሐሳብ ነው።

የምፈራው ነገር ይህ አዲሱ የአማራ ብሄርተኝነት ልክ እንደ በፊቶቹ የኤርትራ፤ የትግራይ፤ የኦሮሞ፤ ወዘተ ብሄርተኝነቶች በብሶት እና በበአድ ምዕራባዊ ርዕዮተ ዓለም የተመሰረተ ኢተውፊታዊ ንቅናቄ ይሆናል ብሄ ነው። የኤርትራ እና የትግራይ ብሄርተኝነት በመሰረቱ ጸረ ትውፊት ናቸው። በቀላሉ ምሳሌ ለህዝባቸው መሰረት የሆነው ሃይማኖትና ባህልን የሚጠላ ርዕዮተ ዓለም ነው እነዚህ ብሄርተኝነቶች የተመሰረቱት። የኦሮሞ ብሄርተኝነት እንደዚህም ቢሆን ቢያንስ ወደ ኦሮሞ ትውፊት ለመመልከትና እንደ ገዳ አይነቱን ተውፊት ማክበር ሞክሯል። ሆኖም መሰረቱ የማርሲስት የጨቋኝ ተጨቋኝ የጎሳ ብሄርተኝነት አስተሳሰብ ነው። የአማራ ብሄርተኝነትም እንደዚህ እንዳይሆን መጠንቀቅ ይኖርበታል። ግን እራሱን «አማራ» ብሎ ከሰየመ እዚህ ወጥመድ ውስጥ ቀድሞ ገብቷል ማለት ይመስለኛል።

ጎበዝ፤ ጠንካራ፤ ሀገር ወዳድ ምሁራን በተለይ ወጣቶች የአማራ ብሄርተኝነት ያቀፉ አሉ። ምክንያቱ ለሁላችንም ሊገባን ይገባል፤ ለብሶት መልስ ነው። የአስራት ወልደየስ ፖለቲካ የብሶት ሳይሆን እራሳቸው እንዳሉት የግዴታ ነበር። የዛሬው ግን የ27/40 ዓመታት ያመጣው ብሶት ነው። ብሶቱ በህወሓት ላይ ብቻ ሳይሆን በሁሉም፤ በድሮ ምሁራን፤ ልሂቃን፤ ተቃዋሚ፤ ወዘተ ነው። እኔ እንደሚመስለኝ የተማሪው ንቅናቄ ወደ እንደ ማርክሲዝም አይነቱ ምዕራባዊ ፍልስፍና እና ርዕዮተ ዓለም በብሶት ምክንያት እንደገባው የዛሬው ትውልድ በብሶቶች ምክንያት እንደ ቀድሞው ተማሪ ንቅናቄ ወደ ኢ-ትውፊታዊ (ምን አልባት ጸረ ኢትዮጵያዊ) የማይሆን አስተሳሰብ እየገባ ነው። ስለ ተውፊቱ ስላልተማረ በምዕራባዊ የቀለም ትምሕርት የሚሰግድ ህብረተሰብ ውስጥ ስላደገ ሳያውቀው ብዙ ኢ-ትውፊታዊ አስተሳሰቦች አድረውበታል።

ስለዚህ ጉዳዩን ወደ ኋላ ወደ መሰረታችን ተመልሰን አመለካከታችንን በሙሉ ከ«ሀ» ብንገመግም ጥሩ ይመስለኛል። ከዛ በኋላ ነው የአማራ ብሄርተኝነት ትውፊታዊ ነው ወይ የሚለውን ጥያቄ በትክክሉ ልንመልሰው የምንችል የሚመስለኝ።


Friday, 6 April 2018

የህዝብ ብዛት

የኢትዮጵያ ህዝብ ቁጥር በዝቷል በተለያዩ መንገዶች የህዝብ ቁጥር እድገትን መቀነስ አለብን ሲባል እጅግ አዝናለሁ። በተለይ የኛ ምሁራን ልሂቃን እንደዚህ ሲሉ ስለ ሀገራችን ህልውና እሰጋለሁ። ሀገራችን ብዙ የፖለቲካ የኤኮኖሚ የመሐበረሰብ ችግሮች አሉትና ከነዚህ ሁሉ የሰው ቁትር መብዛት «ችግር» ከተባለም ትንሹ ነው። የሰው ቁጥር አለ አግባብ ጨምሯል ከተባለም ምክንያቱ የእርግዝና መከላከያ እጦት ሳይሆን ሌሎች የኤኮኖሚና የፖለቲካ ችግሮች ናቸው።

እስቲ አንዳንድ እውነታዎች እንመልከት፤

1. በገጠር ሴቶች በአማካይ ስድስት ልጆች ይወልዳሉ። በአዲስ አበባ በአማካይ ሁለት ልጆች ይወልዳሉ። ላለፉት 43 ዓመት የመንግስታችን የመሬት ፖሊሲ ህዝባችን ከገጥር እንዳይወጣ አድርጓል። ምክንያቱም አንድ ገበሬ ገጠርን ትቶ ወደ ከተማ መምጣት ከፈለገ መሬቱን መሸጥ ስለማይችል ከሞላ ጎደል ባዶ እጁን ወደ ከተመ መምጣት ስለሚሆንበት አያደርገውም። በዚህ ምክንያት 43 ዓመት በፊት የህዝባችን 85% የገጠር ነዋሪ ነበር አሁንም ወደ 80% የገጠር ነዋሪ ነው። የመሬት ፖሊሲው ባይኖር ይህ ቁጥር ዛሬ ምናልባት 60% ይሆን ነበር። እንደዚህ ቢሆን ኖር 80% ፋንታ 60% ነበር ስድስ ልግ የሚወልድው 20% ፋንታ 40% ሁለት ልግ ይወልዳል። በዚህ ምክንያት የጠቅላላ የህዝብ ቁጥር እድገት ይቀንስ ነበር።

2. ሀብት ምቾት ድሎት ከትመት (urbanization) በጠቅላላ ብልጽግና (development) በጨመረ ቁጥር የቤተሰብ መጠን ይቀንሳል። ይህ ንድፈ ሐሳብ (theory) ሳይሆን ያለፈው የ100 አመት የዓለም ታሪክ የመሰከረው እውነታ ነው። በሀገርም በህብረተሰብም ደረጃ ይህ እውነታ ይታያል። ሀብታም ሀገሮች ብዙ አይወልዱም ከነሱም የሚወልዱት ካልበለጸጉ ሀገሮች የመጡ መጤዎች ናቸው። ማንኛውም ሀገር አማካይ ሀብቱ በጨመረ ቁጥር የቤተሰብ መጠኑ ይቀንሳል። ስለዚህ በኢትዮጵያም «ብልጽግና» በጨመረ ቁጥር የሚወለደው ቁጥር ይቀንሳል። ስለዚህ አሁን እንቀንሰው ብሎ መርሯሯጥ አያስፈልግም።

3. የህዝብ ብዛት ሀብት ነው። የምዕራብ ሀገሮች ፍልሰትን (immigration) የሚጋብዙት ምክንያት የሰው እጥረት ስላላቸው ኤኮኖሚያቸው እየተጎዳ ስለሆነ ነው። የአዲስ አበባ ኤኮኖሚ የሚንርበት አንዱ ምክንያት ከገጠር ወደ ከተማ ያለው ፍልሰት ነው። የሰው ኃይልና የሸማች (consumer) ቁጥር በመጨመረ ቁጥር የኤኮኖሚ እንቅሳሴ ይጨምራል። በውጭ ግንኙነት አንጻርም ብዙ ህዝብ ያለው ሀገር በዓለም ላይ ያለው ኃይልና ሚና ይጨምራል። የኢትዮጵያ የዝብን ቁጥር በአባይ ግድብ ላይ ያለው ሚና ትንሽ አይደለም። ስለዚህ የህዝብ ብዛት እንደ እንቅፋት ብቻ መታየት የለበተም።

4. ኢትዮጵያ ገና ብዙ የህዝብ ቁጥር ማስተናገድ የምትችል ሀገር ናት። ካላት ለም መሬትና ሌሎች የተፈጥሮ ምንጮች አንጻር ምናልባት እስከ 200 ሚሊዮን ትችላለች። ጃፓን የኢትዮጵያ አራት እጥፍ ሰው በካሬ ኪሎሜትር አላት። ስለዚህ ኢትዮጵያ ትጨናነቃለች ብለን ልንሰጋ አይገባም።

ከዚህ አልፎ ተርፎ እንደ ኦርቶዶክስ ክርትያን የህዝብ ቁጥርን «መቆጣጠር» የሚባለው ነገር ያሳስበኛል። በተለይ የወሊድ መቆጣጠርን ማስፋፋት ያሳስበኛል። እንደዚህ አይነት ጉዳይ ውስጥ መግባት ትዕቢትን ነው የሚጋበዘው። እራሳችንን እንደ አምላክ እንድናይ ይፈትነናል። ከእግዚአብሔር የሰጠንን የተፈጥሮ ተልእኮ እንድንወጣ ይፈትነናል። ለዚህም ነው የሃይማኖት አባቶቻችን በሙሉ የቃወሙታ። ይህን መጠቀም ከሰው ተልእኮና ማንነት ይጋጫል ማጣት ነው ይላሉ። እርግጥ ካህናት በእረኝነት ሚናቸው በአንዳንድ አጋጣሚዎች የሃይማኖት ልጆቻቸውን እንዲጠቀሙ ሊፈቅዱ ይችላሉ ግን በጠቅላላ ከተቻለ አይመከርም። የስጋ ግንኙነትና መውለድ በተፈጥሮ የተገናኙ ናቸው ማለያየት ለሰው ልጅ ጎጂ ነውና።

ይህን እያወቅን የህዝብ ቁጥር እድገት እንዲቀንስ ተግባራዊ ስራዎች እናካሄድ ማለት ይከብደኛል። በተለይ በወሊድ መቆጣጠርያን በመጠቀም እንቀንስ ማለት ይከብደኛል። ለተጠቃሚው መንፈስ ጎጂ ነው ብዬ የማምነው ነገርን ማስፋፋት ህሊናዬ አይፈቅድልኝም። ሰዎች በገዛ ፍቃዳቸው ቢጠቀሙ ልፈርድባቸው አይገባም አልችልም «መብታቸው» ነው። ግን እንደ መንግስት መርህ ይህን ማስተዋወቅና ማስፋፋት ጎጂ ነው ብዬ ነው የማምነው። የቤተሰብ መጠንን ይቀንሳል ግን የመንፈሳዊ ጉዳቱ በምዕራቡ ዓለም የምናየው ኢትዮጵያ ውስጥ ማየት አልፈልግም። አዎ ዛሬ በሀገራችን በደምብ ተስፋፍቷል ግን መንግስት ከዚህ ጉዳይ እራሱን ቢያወጣ እወዳለሁ።

አልፎ ተርፎ ከላይ እንደጠቀስኩት በኔ እምነት የህዝብ ቁጥራችን አሳሳቢ ጉዳይም አይደለም። ክትመት ብልጽግና በጨመሩ ቁጥር የህዝብ ቁጥር እድገት ይቀንሳል። ቻይና ለ40 አመት ህዝቧ እንዳይወልዱ አድርጋ አሁን የህዝብ ቁጥራችን አንሶ አሳስቦናል ትላለች! እንማር!

ሀገራችን ገና «አልሞላችም»። ስለዚህ ትኩረታችንን ወደ ሌሎች የኤኮኖሚ የፖለቲካ የመሐበረሰብ ጉዳዮች ይሁን። እነዚህን ጉዳዮች በማሸነፍ የህዝብ ብዛት ጉዳያችንም በራሱ ይስተካከላል።

Wednesday, 4 April 2018

ዜና (ወሬ) ያጃጅላል ባርያ ያደርጋል!

በ2017/11 የተጻፈን ትርጓሜ

አባቴ ኢትዮጵያዊ ምሁር ነበር ማለት ይቻላል። ቤታችን እንደሌሎች የኢትዮጵያዊ ምሁራን ቤቶች የፖለቲካ የፍልስፍና ውይይት ስፍራ ነበር። እኔና አባቴ ብቻችን ሆነንም ከጓደኞች ከእንግዶች ጋርም ምሳ እራት ዝግጅት ሲኖርም «ሁለት ወይም ሶስት» ሆነን በተገኘን ቁጥር ፖለቲካ አብሮን ነበር!

የፖለቲካ ዜናም በቴሌቪዥን እንከታተል ነበር። ከጥቂት ኮሜዲዎች ወይንም የካውቦይ ፊልሞች በቀር ዜና ብቻ ነበር የምንከታተለው። ዋናው ዜና ነበር። ወደ ሰሜን አሜሪካ ስንፈልስ ደግሞ ዜና እስከሚበቃን ማየት ቻልን! የፖለቲካ ትንታኔ ፕሮግራሞችም በሽ ነበሩ።

ዜናን በመከታተላችን እራሳችንን የተማርን ሊቆች ብለን እንቆጥር ነበር። እንደሌሎች ሰዎች የማይረቡ ትርዒቶች አናይ! የሰለጠንን ምሁራን ቁም ነገረኞች ነበርን! ጎረቤቶቻችን ሜክሲኮም እንኳን የት እንደሆነ የማያውቁ ሲሆን እኛ አብዛኞቹ የዓለም ዋና ከተሞችን እናውቃለን። የአሜሪካ የፕሬዚደንት ምርጫ ክርክሮችንም እንከታተላለን። ያውም ምርጫው ገና በእጪ ደረጃም ሆኖ! ስልጣኔአችን የተለየ ነበር!

ግን እውነቱን ለመናገር ይህ ሁሉ ትርጉምም ቁም ነገርም አልነበረውም። የኛ የዜና መከታተል ከቤት እመቤት የድራማ ትርዒት መከታተል ከወጣቱ የስፖርት ግጥምያ መከታተል ምንም አይለይም። ሁላችንም ሚና የማንጫወትበት ዋጋ የማንከፍልበት በአድ የሆኑ ነገሮችን ነው እንደራሳችን አድርገን የምንከታተለው። ግን የዜና ፕሮግራሞችን በመመልከት ትምሕርታዊ ቁም ነገር እያደረግን ነው ብለን እራሳችንን እናታልል ነበር!

ዜና መከታተል ግን ከማንኛውም መዝናንያ ትርዒትን ከማየት አይለይም፤ እንደዛው የአዕምሮ ማደንዘዥያ የኑሮ ማምለጭያ ነው። የዜና ትርዒቶች ከተራ ወሬ ሃሜት አሉባልታ ምንም አይለይም ከግብዝነቱ በቀር። ዜና እውነት አስተማሪና ቁም ነገር ነኝ ይላል! ግን ከተከታታይ ድራማዎች ምንም አይለይም። ጭራሽ ይብሳል፤ አብዛኞች የድራማ ትርዒት ትከታታዮች ቁም ነገር ነው ብለው እራሳቸውን አያታልሉም!

ዛሬ ቴለቪዥንም አላይም ዜናም አልከታተልም። በኢንተርኔት አረስቶችን አያለሁ ግን ከተለመዱት የዜና ድረ ገልጾች አይደለም። እርግጥ ነው አንዳንዴ ጽሁፉ አይቼ ይስበኛል እስቲ ጠልቄ ላንብብ እላለሁ ግን እራሴን አቆማለሁ።

ሆኖም ከኢንቴርነት ነው «ዜና መከታተል ያጃጅላል» የሚለውን ጽሁፍ ያገኘሁት። አንብቡት። አልፎ ተርፎ የዜን ፕሮግራሞች አትከታተሉ። በተለይ ሲኤንኤንን (CNN) መቼም አትመልከቱ። ካላችሁበት ቦታ በቴለቪዥን ላይ ካያችሁትም ሮጣችሁ ሽሹ! እራሳችሁን ከአዕምሮአዊ «ቅኝ ግዛት» አድኑ። ቴለቪዥን የምታዩበትን ትርፍ ጊዜአችሁን ከጎረቤታችሁ ጋር በመጫወት አውሉት። እናንተንም እርሱንም እጅግ ይበልጥ ይጠቅማችኋልና።

Thursday, 1 February 2018

ትህትና

አባ ቲኾን በጻፉት መጸሃፍ "Everyday Saints" አባ ቲኾን አንድ ታላቅና ጀግና መኖክሲት፤ በሶቪዬት መንግስት ደጋግመው የታሰሩ የሆኑ፤ ስለ ገዳም ኑሮ ሲጠይቋቸው እኚህ መኖክሲት እንደዚህ አልዋቸው፤ «ዋናውና መጀመርያው ነገር ይህ ነው፤ ማንንም ላይ አትፍረድ»

አለመፍረድ ማለት አለመኮነን ነው። ይህ መፍረድ ድርጊትን ወይም አቋምን ጥሩ ነው ወይ መትፎ ነው ማለት አይደለም። እንደዚህ አይነት ፍርድ ተገቢም አስፈላጊም ነው። አትፍረዱ ማለት አትኮንኑ፤ ሰውን ከድርጊቱ ጋር አታቆራኙ። ሰውየው እራሱ መጥፎ ነው፤ ሃጥያተኛ ነው፤ እኔ ከሱ እሻላለሁ፤ እሱ ወደ ገሃንም ይገባል አይነቱ ነው አትበሉ አታስቡ የምንባለው። ስለዚህ ለክርስቲያን በድርጊት መፍረድ ተገቢ ነው ግን በሰው ማንነት መፍረድ ትክክል አይደለም።

በሰው መፍረድ ኢክርስቲያናዊ የሆነው አንዱ ምክነያት መፍረድ ወደ ተዕቢት ስለሚመራ ነው። ተዕቢት ደግሞ የመጀመርያውና ዋናው እግዚአብሔርን ያጣንበት ምክንያት ነው። አዳምና ሄዋን በትዕቢታቸው ምክንያት መልአክት ለመሆን አስበው ነው እጸ በለሱን የበሉትና። ስለዝህ እንደ ክርስቲያን ከትእቢት ርቀን ወደ ተቃራኒው ትህትና ነው መጠጋት ያለብን።

አዎን ትህትና አንድ ክርስቲያን ከሚፈልገው ዋና ጥሩ ባህርይ ነው። «ትህትናና ፍርሃ እግዚአብሔር ከሁሉ መልክአ ምግባር በላይ ናቸው» ትብሏል። ትህትና የሰው ልጅን ዋና ተልኮ፤ ማለት ወደ እግዚአብሔር መቅረብ፤ ለማሟላት ግድ ነው። እራሱን እንዲገመግም፤ ከፈተናና ሴጣን እንዲርቅ፤ ሌሎችን ላይ ከመጠቆም እራሱን ላይ መጠቆም። እነዚህ በሙሉ ትህትና ይጠይቃሉ።

እንደዚህ ሆኖ ማንም ሰው፤ በተለይ መሪ፤ ትህትናን ሲያንጸባርቅ ደስ ይለኛል። እራሱን ወይም ወገኑን የማያሞገስ፤ እራሱን አጥፊና ሃላፊ የሚያደርግ፤ እራሱን ጥልቆ የሚገመግም፤ ሌሎችን በፍርድ ሳይሆን በመቆርቆር አይን የሚያይ ሰው ደስ ይለኛል። ይህ ባህሪዎች ለራሱም ለዙርያው ላሉትም እጅግ ይበጃል።

እኔ አቶ ለማ መገርሳን አላውቋቸውም ግን ያዳማጥኳቸው ንግግሮቻቸው በትህትና የተሞሉ በመሆናቸው ተደስጭያለው። በዚህ ረድፍ ለሁላችንም ታላቅ ምሳሌ መሆናቸው ነው ከሁሉም በላይ ያስደሰተኝ።

ከአቶ ለማ ሌሎችን በሰሞኑ አይቻለሁ። ብአዴን በደብረ ብርሃን የጠራው የምሁራን ስብሰባ ላይ አንድ ወጣት ምህሩን በጥህትና እጅግ እጅግ አስደሰተኝ። እኛ ምሁራን ባንኖር ገበሬው (ብዙሃኑ) በሰላም አብሮ ይኖር ነበርና እኛ ነን ችግሩ። ለችግሩ መፍትሄ እናገኝለታለን ከማለት መጀመርያ እራሳችንን እንፈትሽ ብሎ ታላቅና አስደናቂ ንግግር አቀረበ። እንደዚህ አይነቱ የምላስ ሳይሆን የመንፈስ ጀግና ነው ሁላችንም የሚያስፈልገን።

ሁላችንም በሌላ ላይ ከመጠቆም፤ ችግርሮቻችንን ብሌላ ከማሳበበ፤ መፍትሄም ከሌሎች ነው የሚመጣው ብለን ከምናሰብ፤ እራሳችንን ወድቅ (disempower) ከማድረግ፤ ውስጣችንን መርምረን ሌሎች ላይ ሳንፈርድ ብንራመድ ለሁላችንም መልካም እንሆን ነበር።

እግዚአብሔር ትህትና ይስጠን። ከትዕቢት ፈተና ያርቀን። የእርስበርስ ሰላም እንድሽ ይርዳን።