Showing posts with label የአማራ ብሄርተኝነት. Show all posts
Showing posts with label የአማራ ብሄርተኝነት. Show all posts

Friday, 31 August 2018

የሰርቢያ ትምሕርት ለአማራ ብሄርተኝነት

የሰርቢያ እና የአማራ ታሪክ ብዙ ልዩነቶች አሉት። ግን አንድ ሁለት ተመሳሳይ ነገሮች አሉ፤

1. ልክ እንደ ኢትዮጵያ ዙርያ አማራው እንደተበታተነው ሰርቢያኖች ዩጎስላቪያ ዙርያ ከሌሎች ጎሳዎች በጣም በይበልት ተበታትነው ይኖራሉ። በርካታ አማራ በየ ክልሉ ይኖራል። ከኦሮሞ ክልል ውጭ የሚኖር የኦሮሞ ህዝብ ከዚህ አንጻር እጅግ አነስተኛ ነው።

2. ከዮጎስላቭ መሪ ቲቶ ሞት በኋላ የዩጎስላቪያ የተለያዩ ጎሳዎች ከሰርቦች በቀር ጎሰኝነታቸው እያየለ ሲሄድ ከሀገሪቷ እንገንጠል ማለት ሲጀምሩ ሰርቦቹ እንደ መልስ «ጠንካራ» ጸንፍ የያዘ በእሾኽ በእሶኽ የሚያምን መሪ ሚሎሴቪች ወደ ስልጣን አመጡ። የሚሎሴቪች ምሳሌ የአማራ ብሄርተኝነት ነው።

እዚህ ላይ አንድ ነጥብ… ስሎቦዳን ሚሎሴቪች «አክራሪ» ሰርብ ቢሆንም በምዕራባዊያን የተከሰሰበት ወንጀሎች ሃሰት ናቸው ማለት ይቻላል። የጎሳ ወንድሞቹን ሰርቦቹን ባሉበት እካካከልላቸዋለው ብሎ ነበር የሚዋጋው ልክ እንደ ሌሎቹ ጎሳዎች ክሮአቶች፤ ቦስኒያኖች፤ ኮሶቮች እንደ ሚዋጉት። ስለዚህ ያአማራ ብሄርተኞች እንደ ሚሎሴቪች ናቸው ማለት ወንጀለኞች ናቸው ማለት አይደለመ።

ሆኖም ሚሎሴቪች እና ደጋፊዎቹ ታላቅ የፖለቲካ ስህተት ነው የፈጸሙት። ሰርቢያኖቹ ሶስት ነገሮች አዩ፤

1. ስሎቬኒያኖቹ፤ ክሮአቶቹ፤ ቦዝኒያኖቹ እና ኮሶቮቹ ሁሉ መገንጠል እንደሚፈልጉ
2. እነዚህ በሙሉ ሰርቢያ ውስጥ ብዙ ነዋሪ የላቸውም ግን ሰርቢያኖች በነዚህ «ክልሎች» ብዙ ናቸው። መገንጠል ከመጣ ስሎቬኒያ፤ ክሮኤሺያ፤ ቦዝኒያ እና ኮሶቮ የሚኖሩ ሰርቦች ናቸው ዋና ሰለቦች ሀገር የለሽ የሚሆኑት። ሰርቢያ ውስጥ ብዙ ስሎቪኖች፤ ክሮአቶች፤ ቦስኒያኖች፤ ኮሶቮዎች ስለሌሉ እነሱ ግድ አልነበራቸውም መገነጣጠልን ይፈልጉታል።
3. የምዕራብ ዓለም በሙሉ ዩጎስላቪያ እንዲበታተን እና ሰርቦቹ እንዲንበረከኩ (ሩስያን ለመጉዳት እና የአውሮፓ ህብረትን ለማጠንከር) ነው የሚፈልገው።

የሰርቢያ ልሂቃን ይህን አይተው በዜዴ የሀገራቸውን ጥቅም አስከብሮ ከመስራት ፋንታ ለምሳሌ ስሎቪኒያን እና ክሮኤሺያን በስምምነት ለቆ አቁምን በቦዝኒያ እና ኮሶቮ ላይ ከማዋል ፋንታ ሁሉንም እንዋጋ አሉ። ሰርቢያ እንዳለ ምዕራብ አለሙን ሲዋጋ ማን እንዳሸነፈ እናውቃለን። አሁን በክሮኤሺያ የሚኖሩት ሰርቦች፤ በቦዝኒያ የሚኖሩት ሰርቦች እና በኮሶቮ የሚኖሩት ሰርቦች የዚህ ያልበሰላ ፖለቲካ አካሄድ ዋና ሰለቦች ሆነው ቀርተዋል። ሰርቢያም እጅግ ተጎሳቁላለች ሞራልዋ ሞቷል።

የአማራ ብሄርተኝነት እሾኽ በ እሾኽ አመለካከትም እንዲሁ ይሆናል ብዬ እሰጋለሁ። በነ ኦሮሚያ፤ ቤኒሻንጉል፤ ደቡብ፤ ሶማሌ ወዘተ ክልሎች የጎሳ ብሄርተኝነት ጠንከር ያለ ነው። የነዚህ ክልል «ጎሳዎች» ከክልላቸው ወጭ በብዛት አይኖሩም። አሉ ግን ብዛታቸው ውስን ነው። አማራው ግን በሚሊዮን የሚቆጠር ከክልል ውጭ አለ።

አማራው ጠንክሮ በአማራነቱ ቢደራጅ እና ከሌሎች የጎሳ ድርጅቶች (ወኪሎች) ሲደራደር እነሱ ለሚያደርጉት እሾኽ በ እሾኽ (tit for tat) ልመልስ ከሆነ ውጤቱ ምን ይሆን። አማራው ምንም ጠንካራ ቢሆን ከግዴለሽነት ጋር መዋጋት አይችልም። ኦሮሚያ አማራው ዜጋ አይደለም ቢል የአማራው መልስ በአማራ ክልል ያሉትን ኦሮሞዎችን እንደዛው ማደረግ ነው። ግን ኦሮሞ ብሄርተኛው ግድ የለውም እንደዚህን ለመሰዋት ዝግዱ ነው።

አያችሁ ሁኔታው ሚዛናዊ አይደለም። Asymmetrical ነው። አማራ በየቦታው አለ ሌላው ግን ክልል ውስጥ ነው። ይህ ማለት ሁለቱ ወገኖች የሚጠቀሙበት የትግል ዘዴ መለያየት አለበት። የአኖሌ ሃውልት ገንብተሃል እና የጣይቱ ሃውልት ልገንባ (አዎ አኖሌ ታሪኩ ሃሰት ነው አውቃለው) ማለት የተሳሳተ ብድር መላሽ ፖለቲካ ነው።

አማራው ግን በኢትዮጵያዊነት ከተደራጀ በዛ ጥላ ስር በርካታ አማራ ያልሆኑም ይይዛል። እነዚህ ሰዎች ኦሮሚያ ውስጥ ውግያ ሳይፈጥሩ ግን በዘዴ ታላቅ የፖለቲካ ኃይል መያዝ ይችላሉ። ይህን ኃይል ተተቅሞ የጎሳ ብሄርተኝነትን የሚቀንሱ ፖሊሲዎችን ለማራመድ ድጋፍ አስፈላጊ ድጋፍ ይሰጣሉ። እነዚህ ፖሊሲዎች ለዓመታት ከሰሩ በኋላ የጎሳ ብሄርተኝነት ይቀንሳል። ከዛ በኋላ የጣይቱ ሃውልት ይሰራ ቢባል ማንም አያስቸግርም። ዘዴው እንዲህ ነው።

የሰርቦች እጣ ፋንታ እንዳይደርስብን። ስሜታዊ ፖለቲካ በጀግንነት እና ፍልፍና ሸፍነን አናራምድ። ከልባችን አለ bias ጉዳዩን በክፍት የሆነ አዕምሮ እናስብበት።

Tuesday, 28 August 2018

ከአማራ እና ከአማራ ውጭ የተወለዱ አማሮች…

ካአማራ ክልል ውጭ የተወለድን አማራዎች እና አማራ ክልል የተወለዱ አማራዎች ትንሽ የትውውቅ ጉድለት ያለን ይመስለኛል። በተለይም የአዲሱ የኢህአዴግ ዘመን ትውልድ በዚህ ዙርያ የመረጃ እጦት አለው። በዚህ ጽሁፍ ይህንን የመረጃ እጦት ለማስተካከል እና መተዋወቅን ለማምጣት ነው የምሞክረው።

እኔ ከ«ነፍጠኛ» ቤተሰብ ነው የተወለድኩት። አያቶቼ፤ ቅድመ አያቶቼ፤ ቅድመ ቅድመ አያቶቼ የትወለዱት ከምዕራብ ሃረርጌ «ጨርጨር» ከሚባለው አካባቢ ነው። አያቶቼ ከጎጃም፤ ከአማራ ሳይንት፤ ከወሎ እና ከመራቤቴ ነበር «ነፍጠኛ» ሆነው ወደ ሃረር የመጡት።

«ነፍጠኛ» ምን ማለት ነው? ወታደሮች ከነቤተሰቦቻቸው፤ መሬት የሚፈልግ ብዙሃን ገበሬ፤ አዲስ መሬት የሚፈልግ ባላባት/ባለሃብት፤ ለአስተዳደር ስራ የተገመገመ ግለሰቦች፤ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚፈልጉ ካህነት ወዘተ። እነዚህ በሙሉ አጼ ምኒልክ አካባቢውን ከተቆጣጠሩት አብረው ወይንም በኋላ የገቡ ናቸው። የመጡበት ደግሞ ከተለያየ ቦታ ነው ግን አብዛኛው የአማርኛ ተናጋሪዎች ነበሩ።

ነፍጠኛው አንዳንዱ በደሞዝ እና ንግድ ይተዳደር ነበር። ብዙዎቹ (እንደ የኔ ቤተሰብ) ለመተዳደርያ ተብሎ መንግስት መሬት ሰጣቸው። ከፊሉ መሬት ባዶ ሰው ያልሰፈረበት የማይጠቀምበት ነበር። ሌላው ደግሞ ሰዎች (ገበሬዎች) የሚኖሩበት ነበር። የኔ ቤተሰብ መሬቶች ሁለቱም አይነት ነበራቸው የመሬታቸው ስፋት ደግሞ እጅግ ትልቅ ነበር። መሬታቸው የተነጠቀባቸው ነባር ገበሬዎቹ በአብዛኛው ጭሰኛ ወይንም ገባር ሆኑ። አልፎ ተርፎ በምዕራብ ሃረርጌ በርካታው የመንግስት እና አስተዳደር ስራ የተሰጠው ለነባሩ ሳይሆን ለነፍጠኛች ነበር። ሁሉም ሳይሆን አብዛኛው እንዲህ ነበር።

ስለዚህ የነባሩ ህብረተሰብ ቁጭቱ ባጭሩ ሁለት ነበር፤ በገዛ መሬቱ ጭሰኛ መሆኑ እና በ«ወራሪ» መስተዳደሩ። በወራሪ መስተዳደር ኢትዮጵያ ውስጥ የተለመደ ነበር በየ ጊዜው መግዛት መገዛት ስለነበር ኦሮሞም ምዕራብ ሃረርጌ የገባው በወረራ ስለነበር (ግን ከመቶ አመታት በፊት)። ሆኖም ብዙ ጊዜ ወራሪው ከነበሩ ጋር ከጊዜ በኋላ ይወሃዳል። ግን በኔ አያቶች ዘመን የሃይማኖት ልዩነት ስለነበር በቂ ጊዜም ስላልቆጠረ በምዕራብ ሃረርጌ በነፍጠኛው እና ነባሩ ብዙ ውህደት አልተካሄድም።

ይህ እንደሆነ በኔ እይታ እኛ እንደ ነፍጠኞች እና የነፍጠኞች ልጆች ሁለት ነገሮች ማድረግ ነበረብን። አንዱ ከገበሬዎች የተነጠቀውን መሬት መመለስ ከቻለ ከነ ካሳ ሲሆን ሁለተኛው ስረዓቱ በሚፈቅደው ደረጃ የነባሩ ቋንቋ እና ባህል በትምሕርት እና አስተዳደር ደረጀ እንዲንጸባረቅ ማድረግ።

ሁለቱንም ማድረግ ስላቃተን ደርግ መጥቶ የሁላችንንም መሬት ወሰደ ጭሰኛውንም ባላባቱንም የመንግስት ጭሰኛ አደረገ! የቋንቋ እና ባህል «እኩልነትንም» ማስፋፋት ሞከረ። የነፍጠኛ ዘመን አበቃ። በደርግ ዘመን የነፍጠኛውም ልጆች የነባሩም ልጆች በመንግስት አይን እኩል ሆኑ። በነገራችን ላይ በርካታ የነፍጠኛ ልጆች በተማሪ ንቅናቄው ተሳትፈው ለደርግ መምጣት ታላቅ አስተዋጾ አድርገዋል።

ኢህአዴግ ስልጣን ሲይዝ እና የጎሳ አስተዳደር እና ጎሰኝነትን ሲሰብክ ከነ «ጨቋኝ አማራ» የሚለው ትርክት እኛ የነፍጠኛ ልጆች በከባድ ተጠቃን። የቅርብ ዘሞደቼ በአማራነታቸው ብቻ ከመረሸን ለጥቂት ነው የተረፉት። ታሪኩንም ለመናገር ከብዷቸው ብዙ አይናገሩትም ነበር።

በጠቅላላ አማራው እና ሊላው እንደ «መጤ» እና «ክርስቲያን» የሚሰየመው ጉዳት የደረሰበት አካላዊ ብቻ አይደለም። ከሞላ ጎደል በሀገሩ ሁለእኛ ዜጋ ሆነ። በመንግስት ደረጃ በተለያየ መንገድ በቢሮክራሲውም በፍትህም (በፍርድ ቤት) ይጨቆናል። በማህበራዊ ኑሮ ደረጃም በየጊዜው ዛቻ እና ማስፈራርያ ያጋጥመዋል። ሙስሊም ካሎንክ መሬትህን ልቀህ ውጣ ይባላል። በየጊዜው ዘረፋ እና ግድያ ይፈጸማል። በየ ጊዜው ነገሮች ሲብሱ ፌደራል ፖሊስ ውየን ጦር ስራዊት ገብተው ወንጀለኞቹን ይረሽኗቸዋል። ግን በሌላው ጎን መንግስት ጎሰኝነትን በመስበክ ጸንፈኛ ጎሰኛ እና ሙስሊሞችን ያበረታታል። «መጤዎቹ» በጨርጨር ለ120 ዓመት በላይ የኖሩ የዛሬ ኑሮዋቸው በቢለዋ ስል ላይ ነው። በጣም ብዙዎቹ ገና 20 ዓመት በፊት ይህ ሀገራቹህ አይደለም ተብለናል ብለው ወደ አዲስ አበባ ወጥተዋል። ቀሪዎቹ በከፊል ፍርሃት ነው የሚኖሩት።

ይህ ነው ባጭሩ የአንድ ነፍጠኛ ልጅ ቤተሰብ እና ሀገር ታሪክ። እኔ አሁን ጨርጨር አልኖርም። ተመልሰህ ትኖራለህ ወይ ብባል አይመስለኝም። በአድነት ይሰማኛል እንዲሰምኝ ይደረጋል። የቋንቋ ጉዳይ አይደለም። ኦሮምኛን መቻል ግድ ነው ባይሆንም አምንበታለው። ግን አማራ በመሆኔ በመንግስት ደረጃም በ27 ዓመት የጎሰኝነት ስብከት ምክንያት በማህበረሰብ ደረጃም እንደ ሁለተኛ ዜጋ እንዳ በአድ ነው የምታየው።

ግን የደብረ ማርቆስ አማራ ይህን ስሜት አያውቀውም። በደርግ ወይንም ኢህአዴግ ወይንም በሌላ ምክንያት ከደብረ ማርቆስ ተሰድዶ አሁን ልመለስ ቢል ሀገር አለው! በአድነት እንዲሰማው የሚያደርግ የለም። መንግስትም ህዝብም ይቀበለዋል። ሀገሬን ልርዳ ቢል ልጃችን እንኳን ደህና ተመለስክ ነው የሚባለው። ሄዶ ቢኖር እንደ ማንኛውም ዜጋ በእኩልነት ይኖራል። «መጤ» አይባልም።

የደብረ ማርቆስ አማራው በኢህአዴግ ዘመን እንደ ማንም በፖለቲካ ተጨቁኛለሁ ሊል ይችላል። በአማራነቴም ተጨቁኛለሁ ማለት ይችላል። ግን ማንም ደብረ ማርቆስ ሀገርህ አይደለም ውጣ ያለው የለም። አብዛኞቹ የጨቆኑት ደግሞ «የራሱ» ሰዎች በገንዘብ ወይንም ርዕዮተ ዓለም የተገዙ ነበሩ። ህወሓት ደብረ ማርቆስ መጥቶ በቀጥታ አልገዛም፤ በወኪል (proxy) ነው ያደረገው። ከሞላ ጎደል አማራው ስለ ህወሓት ብሎ አማራውን እንዲጨቁን ነው የተደረገው። ከሃዲዎች ብዙ ነበሩ። ይህ በደብረ ማርቆስ ልጅ በአማራነቱ እንዲያፍር ሳያረገው አይቀርም። በትንሹ ህወሓት ተገዛሁኝ ብሎ ተገቢ ህፍረት ይሰማዋል። የራሴ ወንድሞች ካዱኝ ብሎ ያስባል። በራሱ መተማመን እና በራሱ በማንነቱ መኩራት እየከበደው ሄዷል።

አያችሁ የሁለቱ ታሪክ ልዩነቶች። ብዙ ነው። ሁለቱም በአማራነታቸው ቢጨቆኑም ታሪካቸው ይለያያል። የጨርጨሩ አማራ የችግሩን አመጣት ይረዳል። ቅድመ አያቶቼ ባደረጉት ነው ብሎ ይገበዋል። አሁን የሚደረገው ተገቢ ባይሆንም አመጣጡ ይገበዋል። ግን የደብረ ማርቆስ ልጁ አይገባውም። ቤተሰቡ ነፍጠኛ ሆኖ አያውቅም ነፍጠኝነት ምን እንደሆንም ላያውቅ ይችላል። የገበሬ፤ ወዛደር ወይንም ነጋዴ ልጅ ነው ማንንም አስገብሮ አያውቅም። ግን አማራ ነፍጠኛ ትምክህተኛ ነው ተብሎ ተጭቆኔ። እድል አጋጥሞት ከመንደሩ ወጥቶ ከፍተኛ ትምሕርት ከገባ የሚጠሉት ኦሮሞ እና ትግሬ ብሄርተኞች ያጋጥሙታል። ዘሮቼ ምን አድርገው ነው ይላል? ታሪኩን ያውቅ ይሆናል ግን በቀጥታ የሱ ታሪክ ስላልሆነ በተወሰነ ደረጃ ለጉዳዩ ባይተዋር ነው።

አሁን የደብረ ማርቆሱ ልጅ በአማራነትህ ተጨቁነሃል በአማራነትህ ተነሳ ሲባል አዎን አለምክንያት ተጨቁኛለሁ ብሎ ሊነሳ ይችላል። ግን የሃረጉ አማራ ምክንያቱን ይበልጥ በግል ደረጃ ያውቀዋል። የጭቆናው ምክንያት ተገቢ አይደለም ሃረር ለኔም እኩል ሀገሬ ነው ቢልም የችግሩ የታሪክ አመጣጡን ያውቀዋል። በዚህ ምክንያት ምናልባትም ስለ መፍትሄው ሲያስብ ሰከን እና ለዘብ ያለ አመለካከት ይኖረዋል። አልፎ ተርፎ ስተት ከተፈጠረ የሚጠብቀው ጉዳት እጅግ ከባድ እንደሆነ ስለሚያውቅ ከወደ ጽንፈኝነት መንቀዥቀዥ ይቆጥበዋል። የደብረ ማርቆሱ ልጅ ግን ከፖለቲቃ ቀውስ በቀር ምንም አይደርስበትም። አይታረድም። ሀገር አለው። የማንነት ኩራቱን ነው መመለስ የሚፈልገው።

ይህ ወደ መጨረሻ የሳፍኩት በሙሉ ግምቴ ነው። እንስቲ እናስብበት እንወያይበት። ይህ የኔ አመለካከት ብቻ ነው። ግን በአማራ ውጭ እና አማራ ውስጥ የተወለዱ አማሮች መከከል የታሪክ እና የልምድ ልዩነቶች በደምብ እንዳሉ ማወቅ አስፈላጊ ነው። መግባባት እና መናበብ እና መተባበር እንድንችል ስለዚህ መወያየት ግድ ይመስለኛል።




Friday, 17 August 2018

የአማራ ኩራት የት ሄደ?

ለመጀመርያ ጊዜ በአማራ ስም ፋንታ በኢትዮጵያ ስም ብትደራጁ አይሻልም ወይ ብዬ የአማራ ብሄርተኞችን ስጠይቅ ያገኘሁት መልሶች (ስድቦቹን ትተን) አስገራሚ ነበር። ምናልባት 80% ስለ አማራ ላይ ባለፉት 27/40 ዓመት የደረሰበት በደል እና ጭቆና ነው። የአማራ ህዝብ ጥቅም ይበልጥ የሚከበረው በአማራነት በመደራጀት ነው ወይንም በኢትዮጵያዊነት በሚለው ዙርያ ከመወያየት ፋንታ ስለ አማራ መጨቆን የጭቆና ቆጠራ ውስጥ ገባን። ይህን ስል አማራው አልተጨቆነም ማለቴ አይደለም ከሌሎች ይልቅ በመንግስት ብቻ ሳይሆን በግለ ሰብ እና በቡድን በአማራነቱ ተጭቁኗል «መጤም» እየተባለ በትውልድ ሀገሩ ባይተዋር ሆኗል። ይህ ሁሉም የሚያቀው ነው። ግን ይህ በፍፁም የአማራ ማንነት መግለጫ መሆን የለበትም። ላስረዳ…

እንደገባኝ ይህ የ27 ዓመት ጭቆና የዛሬው የአማራ ማንነት መሰረት ሆኗል። እስቲ ስለ አማራ እና አማራነት ንገረኝ ሲባል የዘመኑ አማራ ላለፉት አመታት «እጅግ የተጨቆነ፤ የተበድለ፤ የተፈናቀለ፤ የተዋረደ፤ ባሁሉ የተሰደበ፤ ማንነቱ የተገፈፈ» ወዘተ ነው የሚለው። የድሮ አማራ ይህንን ቢሰማ እጅግ ግራ ነበር የሚገባው። ማን ነው አማራ ምንድነው አማራነት ብለህ የድሮ አማራን ብትጠይቀው 3000 ዓመት ታሪክ ያለው፤ ሃይማኖት ያለው፤ ስልጣኔ ያለው፤ የአፍሪካ ቁንጮ፤ የሰው ልጅ ቁንጮ፤ ፍርሃ እግዚአብሔር ወዘተ ነው የሚለው! ልዩነቱን አያችሁ። አማራ በወጉ መሰረት እራሱን የሚሰይመው ማንነቱን የሚገልጸው በአዎንታዊ መንገድ ነው። ዛሬ ግን እድሜ ለረዥም ዓመት ጫና እና የጎሳ ብሄርተኝነት እና የማርክሲዝም ፕሮፓጋንዳ አማራው ማንነቱን ስቷል።

የዛሬ አማራ የበታችነትን ስሜት (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/07/blog-post_30.html) መቀበል ብቻ ሳይሆን የማንነቱ መሰረት ያደረገው ይመስላል። የሰለባ አመለካከት (victim complex)፤ የበታችነት ስሜት (inferiority complex) አጥቅቶናል። እንደ ጥቁር አሜሪካኖች ወይንም ሌሎች በጭቆና ምክንያት ማንነታቸውን ሙሉ በሙሉ ለ«ጭቁን ነው ማንነቴ» የሚለው አስተሳሰብ እራሳችንን ሰጥተናል።

በራሳችን መተማመን እና መኩራት ቀርቷል። ጣልያን ለአምስት ዓመት ኢትዮጵያ ውስጥ ቆይቶ ተጭቁነናል ተገዝተናል ብለን አናውቅም። የድሮ አማራ ምንም ያህል ቢጭቆን እራሱን «ተጨቋኝ ነኝ» ብሎ አይሰይምም። ጦርነት ላይ ነኝ ነው የሚለው። እንደ አያቶቼ አሸንፋለው ነው የሚለው። እንጂ እጁን ለበታችነት ስሜት አይሰጥም ምን እንደሆነም አያቅም። ለዚህ ነው እስከ ዛሬ ጣልያን ገዝቶናል አንልም። ውግያ ላይ ነበርን ነው የምንለው። ይህ ነበር የድሮ እና ትክክለኛ ተውፊተኛ የአማራ ስለራሱ ማንነት አስተሳሰብ።

ዛሬ ግን ይህ ባለመሆኑ ብዙ አማራ በተለይ ወጣቱ «ጭቁን ብሄረሰብ» ነኝ የሚለው አስተሳሰብ አምኖበት ውጦታል (internalize) ተዋህዶታል። ስለዚህ ይመስለኛል የ«አማራ ብሄርተኝነት» ድሮ ታይቶ የማይተወቀው ዛሬ እንደዚህ መነሳት የጀመረው። በጎሳ ብሄርተኝነት የማናምነው ወንድሞች እና እህቶች ይህ የአማራ ብሄርተኝነት ፖለቲካ ለአማራ ህዝብ ያዋጣል ወይ በሚለው እንነጋገር ስንል ብዙ ጊዜ ስሜታዊ መልስ እና ስድብ ነው የሚጠብቀን። ምክንያቱ የአማራ ብሄርተኛውን ማንነት ጥያቄ ውስጥ ስላደረግን ነው። ማንነቱ «ጭቁን አማራ» ሆኗል። አንድ ሰው ይህ ነው ማንኔቴ ብሎ ከሰየመ አልፎ ተርፎ ቁስል ያለው ከሆነ በዚህ ዙራይ መወያየት አይችልም። ውይይቱ በሃሳብ ሳይሆን በማንነት ስለሆነ በዚህ መደራደር የለም። ስሜት እና ቁጣ ብቻ ነው።

ይህ ክስተት እነ ሻዕቢያ፤ ህወሓት፤ እና ኦነግ ሲመሰረቱ አይተነዋል። ወደነዚህ የሚያዘንብሎ ሰዎችን ድሮ ስናናገር አንዴ እንዲሁም እንዴት ማንነቴን በጥያቄ መልክ ታቀርበዋለሁ ብለው ይናደዱ ነበር። በማንነት ድርድር የለም ይሉ ነበር። መገንጠል አይበጅም ኢትዮጵያዊ ናችሁ ወዘተ አይነት ነበር በፍፁም መስማት ብቻ ሳይሆን ስለዚህ መነጋገርም አይፈልጉም። አንዴ ማንነት ከተቀየረ በአጭር ጊዜ ምንም ማድረግ አይቻልም።

ስለዚህ አሁን ጥንቃቄ ያስፈልጋል። ብዙ በተለይ ልጅ የሆኑ አማራ እህት እና ወንድሞቻችን ባለፈው 27 ዓመት የጎሰኝነት፤ ፀረ አማራ፤ ማርክሲዝም ፕሮፓጋንዳ ቶሞልተው የአማራ ማንነታቸው ተቀይሯል። «ጭቁን» ነኝ ብለው አምነዋል። ለዚህ ጭቆና መልሱ ወደ «አማራነት» ከ«ኢትዮጵያዊነት» ማስቀደም ነው ብለው አምነዋል። ይህን በሰላም መተቸት ማንነትን መተቸት ሆኗል።

ጉዳዩ እንደዚህ ባይሆን እና የበታችንነት እና የ«ጭቁን» አስተሳሰብ ባይህኖር መርሰረታዊ ጥያቄውን በአማራ ስም ነው ወይም በኢትዮጵያ ስም ነው መደራጀት የሚበጀን መወያየት እንችል ነበር። አሁን ግን ለብዙዋች ውይይት አቻልም ስሜት ይነካልና ማንነትን ይነካልና።

አንድ ማረግ የምንችለው የአማራ ባህል እና ወግ በትክክሉ ማስተማር ነው። የአማራ 3000 ዓመት ታሪክ በራሱ መኩራት እና መተማመን ነው። ፍርሃት የለውም። እንደ ጠ/ሚ አብይ (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/08/blog-post_10.html) ማንም አይነት ሰውን አቅፎ ይዞ እግዚአብሔር ልጅ መሆኑን አምኖ ወደ ትክክለኛ መንገድ ማምጣት ነው ባህላችን።  ወደዛ ለመመለስ እንጥራ። መሰረታዊ ማንነቱን ያጣ ህብረተሰብ ይወድቃል።

Tuesday, 31 July 2018

ከኢትዮጵያ ብሄርተኞች (አንድነት ኃይሎች) የእርስ በርስ መጠፋፋት ታሪክ እንማር!

ኢትዮጵያዊነትን የምናራምድ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ባለፉት 60 ዓመታት በተደጋጋሚ እርስ በርስ መጣላት ሀገራችንን አደጋ ላይ መጣላችን ይታወቃል (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/07/blog-post_15.html)። መቼም በዚህ እፍረታችን ምክንያት የሀገራችንን ችግሮች በሌሎች (ጎሳ ብሄርተኞች፤ የውጭ ኃይሎች ወዘተ) ማሳበብ ሱስ ቢሆብንም እውነቱ የኛ ጥፋት መሆኑን መቀበል ግዴታችን ነው። ለሀገራችን ችግሮች ዘላቂ መፍትሄ የኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች አንድነት እና ታላቅ ተሳትፎ አስፈላጊ መሆኑ የታወቀ ነው።

ከዚህ ጽሁፍ ትምሕርት እንዲሆነን እና ወደ ፊት ስህተቶቻችንን እንዳንደግም ዘንድ ወደ ኋላ ሄጄ እኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች እርስ በርስ የተፋጀንበት ታሪኮችን ማስታወስ እወዳለሁ። ዛሬ በሀገራችን ፖለቲካ ታላቁ ጉዳይ የጎሳ ብሄርተኝነት ስለሆነ እኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ከታሪካችን ተምረን ለሚመጣው የፖለቲካ ሂደት በደምብ መዘጋጀት አለብን። አሁን ያለንን የታሪክ እድል መጠቀም ግድ ነው። እግዚአብሔር ከዚ በኋላ ሌላ እድል ላይሰጠን ይችላልና።

እንሆ ላለፉት 60 ዓመታት የኢትዮጵያ ብሄርተኞች እርስ በርስ መጣላት ታሪክ ዝርዝር፤

1. የነ መንግስቱ ነዋይ እና ግርማሜ ነዋይ የመንግስት ግልበጣ ሙከራ (1953)፤ አስፈላጊ ለውጦችን ለማምጣት ባለው መዋቀር ውስጥ በትእግስት ከመስራት ፋንታ ግርማሜ በውጭ ሀገር በተማረው «ማርክሲዝም» ፍልስፍና ተመስርቶ ወደ «ስር ነቀል ለውጥ» ወይንም አብዮት አመራ። ይህ የተከሰተው ኃይለ ሥላሴ ወደ ሀገራቸው ከተመለሱ ገና 18 ዓመት ካላፈ በኋላ ነው። ኢትዮጵያ ገና አቅም የሌላት ደሃ ሀገር ነበረች። ግርማሜ እና ደጋፊዎቹ ኃይለ ሥላሴ ወደ ውጭ ሀገር እንዲማሩ ከላኳቸው ተማሪዎች ነበሩ። ይህ ነበር የመጀመርያው ጊዜ የኃይለ ሥላሴ የፈረንጅ ትምሕርት ፖሊሲ በራሳቸው ላይ ጥቃት ያመጣባቸው። የኃይለ ሥላሴ መንግስት ከዚህ ተምሮ አስፈላጊ ለውጦችን ከማድረግ ፋንታ ስልጣንን ይበልት ሰበሰባ ለሰላማዊ የፖለቲካ መፍትሄ ከፍተቶችን ዘጋ።

2. የተማሪዎች ንቅናቄ፤ ከነመንግስቱ ነዋይ ግልበጣ ሙከራ በኋላም የኃይለ ሥላሴ መንግስት ተማሪዎችን ለትምሕርት ወደ ውጭ ሀገር መላክ አላቆመም። የኢትዮጵያን ባህል እና ትውፊት ከማስተማር ፋንታ የምዕራባዊ ፍልስፍና እና ሶሺያል ሳየንስ እንዲማሩ አደረገ። እነዚህ ተማሪዎች ኢ-ኢትዮጵያዊ አስተሳሰቦች ይዘው ወደ ኢትዮጵያ መንግስት እና ሌሎች መስርያቤቶች ገቡ። የቀለም ትምሕርት አለአግባብ በመደነቁ ምክንያት «የተማረ ይግደለኝ» የሚለው አባባል ተፈጠረ (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2016/12/blog-post_7.html)። ይህ እሳት እየተለኮሰም መንግስት በትምሕርትም ደረጃ በፍትህ በተለይም በመሬት ፍትህ ዘርፍ ምንም አላደረገም። የኃይለ ሥላሴ መንግስት የኢትዮጵያ ለረዥም ዓመታት መርዝ የሚሆናት ትውልድ እና ባህል ፈጠረ። የ«ጨቋኝ ተጨቋኝ» አስተሳሰብ እንዲሰፍን አደረገ። የመደብ እና የጎሳ ጦርነት እንዲጀምር አደረገ። ዛሬ የዚህን "legacy" ነው የወረስነው።

3. የደርግ አብዮት፤ በኃይለ ሥላሴ መንግስት ተሃድሶ የሚፈልጉ በርካቶች ነበሩ ግን እድሉ ሳይደርሳቸው የተማሪዎች ንቅናቄ የሚፈልገው ስር ነቀል አብዮት መጣ እና ሀገሪቷን አፈነዳ። በርካታ ልሂቃን ተገደሉ ተሰደዱ። ለኢትዮጵያ ብቻ ስያሆን ለማንም ሀገር የማይሆን የፖለቲካ ፍልስፍና ሰፈነ። መሰረታዊ ነገር እንደ «መሬት ለአራሹ» ወደ «መሬት ለመንግስቱ» ሆኖ ቀረ። ኢትዮጵያ በደምብ ቁልቁል መውረድ ጀመረች። የደርግ በኃይል የተመሰረተ ጨቋኝ አገዛዝ ለጎሳ ብሄርተኞች በንዚን ሆናቸው እና በደምብ መንቀሳቀስ ጀመሩ። ድሮ በቀላሉ በትናንሽ ሰላማዊ ለውጦች መስተካከል የሚችሉት የጎሳ ጉዳዮች ወደ ጦር ሜዳ ገቡ።

4. የኢዲዩ መፈራረስ፤ ማርክሲስት ያልሆኑት የደርግ ተቃዋሚዎች በኢዲዩ ድርጅት ስር ለመታገል ወደ ሱዳን ገቡ። ከሞላ ጎደል አንድ አቋም እና አንድ አመጣጥ ኖሯቸውም እርስ በርስ መስማማት ባለመቻላቸው ከትንሽ ጊዜ በኋላ ተበታተኑ። ይህ በአንድ አቋም ያላቸው ኢትዮጵያ ብሄርተኞች መካከል እርስ በርስ መጣላት ታሪክ እስካሁን እየተደጋገመ ነው።

5. የኢህአፓ፤ መኢሶን፤ ደርግ ግጭት፤ እንዴ ማንኛውም የማርክሲስት አብዮት አብዮተኞ የፍልስፍና፤ የጥቅም እና የስልጣን ልዩነቶቻቸውን በተብ መንጃ ነው እነ ኢህአፓ፤ መኢሶን፤ ደርግ እና ሌሎች የተወጡት። የእነዚህ ድርጅቶች አብዛኛው አባላት በ«አንድ ኢትዮጵያ» የሚያምኑ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ነበሩ። እነ ኢህአፓ በመገንጠል እናምናለን ቢሉም ብዙ ኤርትራ እና ትግራይ ብሄርተኞች ቢኖሯቸውም አብዛኞቻቸው ኢትዮጵያ ብሄርተኞች ነበሩ። መኢሶንም የኦሮሞ ብሄርተኞች ቢኖሩትም አብዛኛው በአንድነት ያሚያምን ነበር። ደርግም እንዲሁም የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ስፍራ ነበር። ሆኖም የነዚህ ድርጅቶች መፋጃጀት ለጎሳ ብሄርተኞች ታላቅ ድል ሆነ። የኢትዮጵያ ብሄርተኛው እርስ በርስ ሲተላለቅ የጎሳ ብሄርተኛ እየቀረ ሄደ ካስፈለገ ወደ ሻዕብያ፤ ህወሓት እና ኦነግ ገባ። ቀይ ሽብሩ ካበቃ በኋላ የተቆሳሰለች ኢትዮጵያ ናት የቀረችው። በጎሳ ብሄርተኞች ለመገዛት ዝግዱ የሆነች ደካማ ኢትዮጵያ ናት የቀረችው። ደርግ ከስልጣን ሲወርድ የኢትዮጵያ ብሄርተኛ ልሂቃን ራሱን አጥፍቶ ርዝራዡ ብቻ ነው የቅረው። ብዙሃኑም የፖለቲካ ልቡ ተስብሮ እየተንገዳገደ ነበር። የኢትዮጵያ የወደፊት የጎሰኝነት ዘመን ተወሰነላት።

6. የመላው አማራ እና መላው ኢትዮጵያ ፓርቲዎች ግጭት፤ ደርግ ኤኮኖሚውን ገድሎ፤ ህዝቡን አጥፍቶ፤ የሶቪየት ህብረት ሲፈርስ ገንዘብ አጥቶ እነ ሻዕብያ እና ህወሓትን ወደ መንግስት አስገባ። የኢትዮጵያ ብሄርተኛው ጎራ እራሱን አትፍቶ ሜዳውን ሙሉ በሙሉ ለጎሳ ብሄርተኞቹ ተወ። እነሱም ደንግጠውም ቢሆን ያልጠበቁትም ቢሆን ሜዳውን ለመቆጣጠር ቶሎ ስራ ጀመሩ። የኢትዮጵያ ብሄርተኛ ጎራው ከድንጋጤው በኋላ ልደራጅ ሲል የለመደው አብሮ መስራት አለመቻል እርስ በርስ መጣላት በሽታው እንደገና ተነሳበት። «መላው ኢትዮጵያ» ይህን ወይንም «መላው አማራ» ይሁን አውራ ፓርቲአችን በሚለው ጥያቄ የኛ «ወታደሮች» በ«ጠላት ሜዳ» ላይ እርስ በርስ መጣላት ጀመሩ! ላለመስማማት መስማማት እና በጋራ ጥቅም አብሮ መስራት ፋንታ አንዳችን ብቻ ነው የሚቀረው ብለው እርስ በርስ ተፋጁ እና ሁለቱንም ድርጅቶች («መላው ኢትዮጵያም» «መላው አማራም») አደከሙ። የጎሳ ብሄርተኞች ከዳር ሆነው በሳቅ ሞቱ። ግን አሁንም እኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ጥፋታችንን ከማመን እነ ከመፍታት ፋንታ የጎሳ ብሄርተኞች ጥፋት ነው እነሱ ናቸው ያከፋፈሉን ብለን እንደ ህጻናት አሳበብን። እንሆ ችግራችንን ስላላመንን አልፈታነውም። አልፎ ተርፎ ይህን ስህተትን ወደፊት ለመድገም እራሳችንን አዘጋደን!

7. የቅንጅት ግጭት፤ ወደ ምርጫ 97 ስንገባ ጠ/ሚ መለስ ዘናዊ በተለያዩ ምክንያቶች ነጻ ምርጫ እናሸንፋለን ዓለም ያከብረናል ብለው ነጻ ምርጫ አወጁ። ድንቅ ውሳኔ ነበር አሁንም ይደንቃል። ግን በዛን ግዜ የኢትዮጵያ ብሄርተኛ ጎራው በራሱ ካመጣው ቁስሎቹ ገና አልዳነም ነበር። ጠንካራ ድርጅት ከሀገር ውስጥም ውጭም አልነበረም። የእርስ በርስ ጥሉ እንዳለ ነበር። በዚህም ምክንያት ነው የኢትዮጵያ ብሄርተኛው ወደ አንድ ስምምነት (ቅንጅት) የገባው በመጨራሻው ደቂቃ ከምርጫው ሶስት ወር በፊት! ግን አርፍዶ ቢዘጋጅም እንደምንም አድርጎ የኢትዮጵያ ብሄርተኛው ጎራ በምርጫው ተሳትፎ በሚደንቅ ሁኔታ አሸነፈ። ካሸነፈ ብኋላ የምናውቀው ፈተናዎች አጋጠሙት። እነዚህን ፈተናዎች በደምብ አድርጎ ወደቀ። በሰው የተፈጥሮ ባህሪ ጓዶች አብረው ሲታሰሩ ፍቅራቸው እና ትብብራቸው ይጨምራል። የቅንጅት መሪዎች ሲታሰሩ ጭራሽ እርስ በርስ ተጣሉ!ድርጅቱም ምን ያህል ባዶ እንደነበረ ታየ። ከላይ የተወሰኑ መሪዎች በ100 የሚቆጠሩ ነበሩ ከዛ በታች ግን መዋቅር የሚባል ነገር አልነበረም። መዋቅር ስል በይፋ ብቻ ሳይሆን በልብም አልነበረም። ስለዚህ መንግስት ቅንጅትን ሲያጠቃ በምርጫው 70% እንዳሸነፈ ድርጅት ጥቃቱን ጠንክሮ ከመቋቋም ይልቅ እንደ ምንም ድጋፍ የሌለው ድርጅት ቀለጠ። ቅንጅት አሸዋ ላይ የተገነባ ቤት መሆኑን አየን። ግን ለዚህ ሽንፈት ምክንያት እንደነበረ እንገንዘብ። የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ልሂቃን ከዛ በፊት ለ30 ዓመታት እርስ በርስ መፋጀት ታሪክ ምክንያት በጣም ሳስቶ ነበር። ለዚህም ነው ቅንጅት በተንሽ ግፊት የፈራረሰው። መሪዎቹ "cream of the crop" ሳይሆኑ ካለፈው 30 ዓመት የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ጎራ እርስ በርስ መጨራረስ የተራረፉ ነበሩ። ታሪካችን ምን ያህል እንደ ጎዳን አየን።

8. ዛሬ፤ አሁንም የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ጎራ እጅግ ደካማ ነው። አሁንም ሀገር ውስጥም ውጭም ብዙሀኑን በሚገባው የሚወክል ድርጅት የለውም። ግን ብዙሃኑ አለ ልሂቃን እየታገለ እንደሆነ የሚያሳየው እንደ ጠ/ሚ አብይ አህመድ አይነቱን ሰዎች ከዚህ ብዙሃን መውለዳቸው ነው።  እንጂ ከ27 ዓመት የጎሳ ብሄርተኝነት በኋላ ኢትዮጵያ እውነትም የብሄር ብሄረሰቦች እስር ቤት ብትሆን እና በርካታ የሀገር ብሄርተኛ ባይኖራት እንደ አብይ አይነቱ አይፈጠርም ነበር እንቋን ወደ ስልጣን መግባት። ግን ይህ ብዙሃን ልሂቃን ያስፈልገዋል። እነ ጠ/ሚ አብይ በርካታ እገዛ ያስፈልጋቸዋል። ቢያንስ እንቅፋት አያስፈልጋቸውም!

አንድ እንቅፋት ሊሆን የሚችለው አዲሱ የ«አማራ ብሄርተኝነት» (https://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/06/blog-post_14.html) ነው። የአማራ ብሄርተኝነት በኢትዮጵያዊነት አምናለው ይላል ግን  የኢትዮጵያ ብሄርተኛውን ጎራ የመከፋፈል እና የማድከም አዝማምያ አለው። የአስተያየት ልዩነት መልካም ነው በአንድ አንድ ነገር ሳይስማሙ አብሮ መስራት ይቻላል። ግን አሁን የሚታየው የአብሮ መስራት አዝማምያ ሳይሆን የጥሎ ማለፍ መንፈስ ነው። የአማራ ብሄርተኛው ጎራ አንዱ መፈከሩ የኢትዮጵያ ብሄርተኝነት ድርጅቶች ዋጋ የላቸውም ነው። ከኢትዮጵያ ብሄርተኛ ድርጅቶች ጋር አብሮ ከመስራት ያጣጥልዋቸዋል። ያው የነ ሻዕብያ፤ ህወሓት፤ ኦነግ ፎቶኮፕይ ማለት ነው። የህዝብን ብሶት በጎሳ ቤንዚን ለኩሶ የፖለቲካ ኃይል ማግኘት ነው። ልክ ህወሓት በመጀመርያ ነባር የጥግራይ ልሂቃንን እንዳጠፋ አንድ አንድ የአማራ ብሄርተኞች የኢትዮጵያ ብሄርተኝነት ድርጅቶችን ማጥፋት ይፈልጋሉ። እንደነ ኢህአፓ/መኢሶን/ደርግ የማርክሲስት ዜሮ ድምር ፖለቲካ ማለት ነው።

ይህ የሚመስልኝ ታሪክን መድገም ነው። የኢትዮጵያ ብሄርተኞች እንደገና እርስ በርስ ሲፋጁ የጎሳ ብሄርተኖች ስልጣን ይቆጣጠራሉ የኢትዮጵያ ብሄርተኛ ብዙሃን እንደገና መሪ አልባ ሆኖ ይጠቃል። ከታሪካችን ብንማር ይበጀናል። በዛሬው የፖለቲካ ለውጥ እግዚአብሔር የማይገባንን እድል ሰጥቶናል። እኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኛ ልሂቃን ምንም የሚጠቅም ነገር ሳናደርግ ከኢህአዴግ መሃል የለማ ቡድን ተነስቶ ለአንድነት መንፈስ ቆሟል። ታላቁ «ኢትዮጵያዊ» ዶናልድ ለቪን ደጋግመው እንዳሉት በርካታ እድሎቻችንን አበላሽተናል (https://scholarworks.wmich.edu/ijad/vol1/iss1/3/)። ይህን እድል ደግሞ ካበላሽን ታሪክ ለዘለዓለም ይወቅሰናል።

Monday, 30 July 2018

የብሶት ፖለቲካ

የብሶት (grievance) ፖለቲካ በተማሪዎች ንቅናቄ ዘመን ከ«ጨቛኝ እና ተጨቛኝ» ፖለቲካ አብሮ ወደ ሀገራችን ገብቶ እንሆ ወደ 60 ዓመት ቆይቷል (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/02/blog-post_16.html)። ምንድነው የብሶት ፖለቲካ? ባጭሩ በብሶት፤ ንዴት፤ ቂም፤ ጭቆና፤ በደል ዙርያ የተመሰረተ ፖለቲካ ነው። በአሉታ (negativity) የተመሰረተ ፖለቲካ ነው። በሰለባ ወይንም ተጨቛኝ አስተያየት (victim mentality) የተመሰረተ ነው።

የብሶት ፖለቲካ መፈክሮች እንዲህ ናቸው፤

1. ተበድያለሁ ተጨቁኛለሁ (ማንንም በድዬ አላውቅም)
2. በዳዮቼ ሊክሱኝ ይገባል (እኔ ማንንም ልክስ አይገባም)
3. ዛሬ ላለሁበት ሁኔታ እና ችግር ሙሉ ጥፋተና ሃላፊነት የበዳዮቼ ነው (ዛሬ ላለሁበት ሁኔታ እና ችግር እኔ ምንም ሃላፊነት የለብኝም)
4. የበደሌኝን ማጥፋት ቢቻል ለሁላችንም ይበጀን ነበር
5. መበደሌን ያላመነ እንደ በዳይ ይቆጠር ሊወገዝ ሊጨቆን ይገባዋል

የብሶት ፖለቲካ ምንጭ ምንድነው? በመጀመርያ ደረጃ ምንጩ እውነተኛ ብሶት ነው። የሰው ልጅ በተለያየ ምክንያት ብሶት አለው፤ ይህን መካድ አይቻልም። ለምሳሌ ጭሰኛው መሬቱ ከሱ ወይንም ከአባቱ ወይንም ከአያቱ ተወስዶበት መሬቱን ለወሰደው እንዲገብር ተደርጎ ብሶት ይኖረዋል። ተጨቁኛለሁ ቢል ይገበዋል። የቤት ሰራተኛዋ አለአጋባብ ስራ ሲቆለልባት እንደ ባርያ ስትነዳ ቤተ ክርስቲያንም ለመሄድ ሳይፈቀድላት ሲቆይ ብሶት እየተጠራቀምባት ይሄዳል። ኦሮምኛ ተናጋሪው በቋንቋ ሲቀለድበት እንደ ዝቅተኛ ሰው ሲታይ ብሶት ይይዘዋል።

ግን በኢትዮጵያ የነበረው ያለው ብሶት እንደዚህ አይነቱ ብቻ አይደለም። ሁሉም ሰው በተለያዩ መልኩ ብሶት አለበት። በጎረቤት መካከል ግጭት፤ ቅራኔ እና ብሶት አለ። በአለካ እና ሰራተኛ፤ በአዛዥ እና ታዛዥ፤ በባልደረባዎች መካከል፤ በቤተሰብ መካከል (ምናልባትም ይህ ከሁሉም ይበልጣል) ወዘተ። በሰው ልጅ መካከል ግጭት እስካለ ድረስ ብሶት አለ። ግጭት ደግሞ በተለየዩ መልኩ አይቀርም።

ስለዚህ ጥያቄው ይህን የማይቀረውም ብሶት እንዴት ነው የምናክመው ነው። በርግጠኝነት ይህን ብሶት ወደ ፖለቲካ ምድር ማምጣት ብዙ ጊዜ አደገኛ ነው ፍትሃዊም ላይሆን ይችላል። የኃይለ ሥላሴ ተማሪዎች የተመረዙበት የማርክሲስት ኮምዩኒዝም ፖለቲካ ይህን ነው በመጀመርያ ደረጃ ያደረገው። ዓለምን ወደ «ጨቋኝ እና ተጨቋኝ» ከፋፍሎ ብሶትህን ተወጣ የሚል ፖለቲካ ነው። በዳይህን አጥፋው በማለት ነው። ታላቁ የደቡብ አፍሪካ መሪ ኔልሰን ማንዴላ እንዳሉት "dialectical materialism" (የብሶት ወይንም ጨቋኝ ተጨቋኝ ፖለቲካ መሰረት) ለነፃነት ታጋይ እንደ ፈንጅ ነው»። ይህ ማለት ኃይለኛ መሳርያ ነው ችግሩን የሚፈታ ብቻ ሳይሆን ዙርያውን በሙሉ ድምጥማጡን የሚያጠፋ። የፈንጅ ወርዋሪውይንም፤ ጠቅላላ ህብረተሰቡንም፤ ሌሎች ሀገራትም ሊያጠፋ የሚችል መሳርያ ነው! መቆጣጠር የማይቻል መሳርያ ነው። ያለንን ብሶት ወደ ፖለቲካ አምጥተን በጨቛኝ ተጨቛኝ የብሶት ፖለቲካ እናስተናግደው ከሆነ ሁላችንም ፉንጂ አፈነዳን ማለት ነው። ይህን ነው በሀገራችን ባለፉት 40 ዓመታት ያየነው። ሀገራችንን አፈንድደናል።

በሀገራችን ይህ የብሶት ፖለቲካዊ አሰተሳሰብ በመደብ፤ በጎሳ፤ በሃይማኖት ወዘተ ታይቷል። ዛሬም በሚያሳዝን ሁኔታ እየታየ ነው። አሳዛኝ ነው የምልበት ምክንያት ሁለት ነው፤ 1) ውሸት ነው፤ የሰው ልጅ እራሱን በዋናነት «ተበዳይ» ብሎ ከገለጸ ማንነቱን አጥቷል ማለት ነው። የሰው ልጅ ሊበደል ይችላል ገን «ተበዳይ» ማንነቱ ሊሆን አይገባም። 2) ይህ አስተሳሰብ ቅራኔን፤ ግጭት፤ ማፈናቀል፤ ግድያ ወዘተ ያሰፍናል ሀገርን ያፈርሳል እና ታላቅ እልቂት ያመጣል። እንዴት?

በመጀመርያ የብሶት ፖለቲካ ሁሉንም አቅመቢስ እና ተበዳይ ያደርጋል (victim)። ሁሉም ተበድያለሁ ይላል ማንም በደልኹኝ አይልም። ሁሉም ካሳ ይገባኛል ይላል ማንም የሚክስ አይኖርም። ሁሉም መቀየም ይገባኛል ይላል ማንም ይቅርታ አይልም። ሁሉም እራሱን አቅመ ቢስ (disempowered) አድርጎ ይቆጥራል ማንም እራሱን እንደ ጎለበተ (empowered) ሰው አይቆጥርም። ይህ ማለት ሁሉም ፈላጊ ሆኖ ሰጭ ወይም አቅራቢ የለም። ይህ አስተሳሰብ ግጭትን ያሰፍናል። ተበድያለሁ ሲል አዎን ብሎ ይቅርታ የሚለው ሲያጣ፤ ካሳ ይገባኛል ሲል የሚክሰው ሳይኖር፤ ሰለባ ነኝ ሲል ፍትህ ሳያገኝ፤ አቅም የለኝም ሲል የሚያጎለብተው ሳይኖር፤ ይህ መሬት የኔ ነው ሲል ሌላውም የኔ ነው ሲል ወዘተ የብሶት እሽቅድድም እና ግጭት ይሰፍናል።

ላለፉት 27 ዓመት ከኢትዮጵያ የሰፈነው የጎሳ አስተዳደር ይህን ክስተት በደምብ ያንጸባረቃል። ሁሉም ብሄሮች ተበድያለሁ አሉ። ለምሳሌ ኦሮሞ ብሄርተኛው ለ150 ዓመት ተበድያለሁ አሁን ቢሻሻልም ገና ዴሞክራሲ ያስፈልገናል፤ ካሳ ያስፈልገናል፤ ታሪክ መስተካከል አለበት፤ አዲስ አበባ የኛ ናት ወዘተ ይላል። ትግሬ ብሄርተኛውም እስካሁን በኢትዮጵያ የብሄሮች እስር ቤት ታስረን ነበር አሁን ነው ነፃ የወጣነው ግን አሁንም በነፍጠኛ እና ጠባብ እንጠቃለን ይላል። በደርግ እና ኃይለ ሥላሴ ዘመን የደረሰብን በደል ምክንያት ካሳ ያስፈልገናል ይላሉ። አዲሱ አማራ ብሄርተኛውም በአቅሙ ተበድያለሁ ለ27 ምናልባትም ለ40 ዓመት የተለያዩ ብሄሮች ሰለቦች ሆነናል ይላል። የሀገራችን ችግር በሙሉ በኛ ይሳበባል ያላል። ዘራችን እየጠፋ ነው "genocide" በኛ በተለየ መጠን ተፈጽሟል ይላል። ሌሎች ብሄር ብሄረሰቦች ነፍጠኛ እያሉ በየ ቦታው ያሳድዱናል ያፈናቅሉናል። ካሳ ይገባናል ይላሉ አማራ ብሄርተኛው።

ግልጽ ነው፤ ሁሉም ተበዳይ በመሆኑ እርስ በርስ ያጋጫል። ለስልጣን፤ ለጥቅም፤ ለመሬት ወዘተ በብሄር ደረጃ ይወዳደራል፤ ይጣላል፤ ይዋጋል፤ ይገዳደላል። የፖለቲካ ውድድሩ በጎሳ እና በብሶት ብቻ የተመሰረተ ነው። እንደዚህ አይነቱ ውድድር ደግሞ ከርዕዮት ዓለም ውድድር ይልቅ ቶሎ ወደ ግጭት እና ጦር ያመራል። እነዚህ ግጭቶች ደግሞ ሀገሪቷን ወደ መፈረካከስ ይወስዳሉ። መረጃውን ላለፉት ቢያንስ 27 ዓመት አይተነዋል። ልደገመው፤ የምለው «ቴኦሪ» አይደለም የብዙ ዓመት ማስረጃ አለን።

መፍትሄው ምንድነው ታድያ? አንዳንድ የጎሳ ብሄርተኞች ይቅርታ ብንጠየቅ፤ ታሪክ ቢስተካከልልን፤ መሬት ቢመለስልን ሁሉም ያበቃል ይላሉ! ግን እንደማይበቃ እናውቃለን፤ የሰው ልጅ አንዴ የሰለባ አስተያየት (victim mentality) ከሰፈነበት ከራሱ ውጭ የሚመጣ ነገር መቼም ከዚህ እስር አስተሳሰብ አይፈታውም። ከውስጡ ከልቡ ብቻ ነው ከሰለባ ወደ አቅም እና ሃላፊነት ያለው ሰው መቀየር የሚችለው። ምንም ይቅርታ እና ካሳ ይህንን ለውጥ ሊያመጣ አይችልም። የልብ ለውጥ ነው የሚያስፈልገው።

ይህንን የልብ ለውጥ እንዴት ይመጣል? ምሳሌ 1። የተበደኩኝ ጭሰኛ ከሆንኩኝ በዳዬን ማጥፋት አይደለም ማሰብ ያለብኝ። መበደሌንም ማቆም አይደለም ማሰብ ያለብኝ። ግቤ መሆን ያለበት ፍትሃዊ የሆነ ኑሮ እና ሁኔታ መፍጠር ነው። ግቤ አሉታዊ ሳይሆን ገምቢ መሆን አለበት። እንዲህ ቢሆን ኖር 40 ዓመት በፊት የጭሰኛ ችግር በ«መሬት ለመንግስት» (አሉታዊ - negative) ሳይሆን በ«መሬት ለአራሹ» (ገምቢ - positive) ይፈታ ነበር። ግን በብሶት ፖለቲካ አሉታዊ አስተሳሰብ ለእውነት የሆኑ ችግሮች የውሸት መፍትሄ ያቀርባል።

ምሳሌ 2። በጎሳ ወይንም ቋንቋ ደረጃ እኔ በቋንቋዬ እና ባህሌ መሰረት ነው መኖር የምፈልገው ከሆነ ያንን ነው ግብ ማድረግ። ሌላውን ጨቋኝ ብሎ መሰየም እና ለማጥፋት መነሳት የብሶት ፖለቲካ አካሄድ ነው። የኦሮሞ ብሄርተኛ ኦሮሚያ ለኦሮሞ የሚለው መፈከር አሉታዊ አካሄድ ነው። ኦሮሚያ ለኦሮሞ ማለት ሌላውን ማስወጣት ወይንም ሁለተኛ ዜጋ ማድረግ ስለሆነ። ሌላውን መጉዳት ስለሆነ። ግን ኦሮምኛ ሀገር ዙርያ ይነገር የሀገር ቋንቋ ይሁን ኦሮሞነታችን ሁሉም ውስጥ ይግባ ማለት ገምቢ የሆነ አመለካከት ነው። የብሶት ሳይሆን የገምቢ ፖለቲካ ነው። ይህ አስተሳሰብ ደግሞ ግጭት ሳይሆን ትብብር የሚጋብዝ ነው።

ስለዚህ ያሉንን በሙሉ ማሀበረሰባዊም ግለሰባዊም ብሶቶች በብሶት ፖለቲካ ሳይሆን በ«ገምቢ ፖለቲካ» ማካሄድ ነው ያለብን። (ጠ/ሚ አብይ «መደመር» ሲሉ ይህን ማለታቸው ይመስለኛል)። የብሶት ፖለቲካ የግጭት እና ህምም ምንጭ በመሆኑ ምክንያት ማስወገድ አለብን። ይህ ማስወገድ የሚጀምረው ከላይም ጠ/ሚ አብይ እንደሚያረጉት ከታችም እኛ ብዙሃን ማደረግ እንዳለብን። ከሁሉም ትምሕርት ደረጃ ይህ የብሶት እና የጨቋኝ ተጨቋኝ አስተሳሰብን አጥፍቶ ወደ ግምቢ አስተሳሰብ መቀየር አለበት። ከአሉታዊ ወደ ገሚቢ መሄድ አለብን። ይህን መልእክት ከሃይማኖት ተቋማትም መንሰራጨት አለበት። የህዝባችን አስተሳሰብ መቀየር አለበት። ወደ ገምቢ ፖለቲካ መምጣት አለብን።

Thursday, 14 June 2018

አማራ ብሄራዊ ንቅናቄ

ስለ አማራ ፖለቲካዊ ንቅናቄ ለኢትዮጵያ ህልውና ያለው አስፈላጊነት (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2016/09/blog-post_23.html) ሁለት ዓመት በፊት ጽፌ ነበር። ያኔ አንዳንዶች  ከዚህ ንቅናቄ ተነስተው በአማራ ስም የተሰየመ የፖለቲካ ድርጅት ያቁቁማሉ ብዬ አልጠበቅሁም። ግን እንሆ «የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ» (አብን) ተወልዷል!

ዛሬ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ሁኔታ በፍጥነት እየተቀያየረ ነው። በየቀኑ ያልተጠበቁ ለውጦች እየተካሄዱ ነው። የሀገር ግንባታ ወቅት ነው (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/02/blog-post_20.html)። የጥያቄ፤ ውይይት፤ ምርምር፤ ድርድር እና ስምምነት ምመስረት ወቅት ነው። ይህን እድል ለማግኘታችን ተመስገን ማለት ያለብን ይመስለኛል፤ ማንናችንም ሁለት ዓመት በፊት ይህንን የተነበየ የለም። በዚህ የውይይት መንፈስ ነው ስለ «አማራ ብሄራዊ ንቅናቄ» ይህን  ጽሁፍ የማቀርበው።

የአማር ብሄራዊ ንቅናቄ አቋሙን፤ ፖሊሲዎቹን እና መመርያዎቹን አርቅቆ ባይጨርስም ሁለት ዋና ግቦቹን አሳውቋል። እነዚህ፤

1. የአማራ ህዝብን ከደረሰበት ያለው ግፍ እና ወንጀል ከነ መፈናቀል፤ መገደል፤ የተለያዩ ጥቃቶች፤ ታሪኩ እና ክብሩ በሃሰት መተቸቱ ወዘተ መከላከል እና ማዳን።

2. የጎሳ አስተዳደርን ማጥፋት። የህወሓትን ጎሰኛ ህገ መንግስትን ብዚህ መልኩ መቀየር፤ መሰረቱ «ብሄር ብሄረሰቦች ህዝቦች» ሳይሆን «ዜጋ» እንዲሆን፤ «ብሄር» ወይንም «ጎሳ» በህገ መንግስት ደረጃ እውቅና እንዳይኖረው (ቋንቋ ሊኖረው ይችላል)፤ ክልሎች የዜጎች እንዲሆኑ፤ ወዘተ።

ጥሩ ግቦች ናቸው። ብዙዎቻችን የምንስማማባቸው ይመስለኛል።

ግቦቹን እንደተቀበልን ወደ ዋናው ጥያቄ እንምጣ፤ እነዚህን ግቦች ለማሳካት በስመ «አማራ ብሄር» መደራጀት ነው የሚሻለው ወይንም በስመ «ኢትዮጵያ» በ«ህብረ ብሄራዊ» መልክ መደራጀት ነው የሚሻለው? እነዚህን ግቦች ለመምታት በህብረ ብሄራዊ መልክ መደራጀቱ ከበጀ ያ መንገድ ይሻላል ማለት ነው። አለበለዛ የ«አብን» መንገድ ነው የሚያስፈልገው ማለት ነው።

በ«አማራነት» ወይንም በ«ኢትዮጵያዊነት» የመደራጀት ጥቅም እና ጉዳት

በስመ «አማራ» መደራጀት ዋና ጥቅሙ የብሄራዊ ወይንም ጎሳዊ ስሜትን ሃይል እና አቅም ለመገንባት መጠቀም ነው። በስመ አማራ ከተደራጀን በ«ኢትዮጵያዊነት» ከምንደራጅ ይልቅ ህዝቡ በአማራነት ስሜት ይበልጥ ይሳተፋል ነው።  በታሪካችን ዛሬም ያሉት ሌሎቹ የጎሳ ድርጅቶች ይህ አንዱ ለመፈጠራቸው የሚሰጡት ምክንያት ነው። ሰውዉን በ«ኢትዮጵያዊነት» ይልቅ በ«ጎሳዊነት» መቀስቀስ ይቀላል ነው።

በስመ አማራነት መደራጀት ሁለተኛ ጥቅም የአማራ ህዝብ «አጄንዳ» ላይ ማተኮር ነው። ህብረ ብሄራዊ ድርጅት የሁሉንም ጉዳዮች ማስተናገድ አለበት። በዚህ መካከል የአማራው ጉዳይ አንዱ ይሆናል። ለምሳሌ በአማራ መፈናቀል ስራ መስራት ከተፈለገ የሁሉንም ትብብር ይጠይቃል። በአማራ ላይ የተለጠፈውን ሃሰተኛ ታሪክ ማስተካከል ከሆነም የሁሉን ትብብር ይጠይቃል። ወዘተ። ግን የአማራ ብቻ ድርጅት እነዚህን ስራዎች አትኩሮ መስራት ይችላል።

የህብረ ብሄር አደረጀት ዋና ጥቅም ኃይል እና አቅም (capacity) ነው። በማንኛውም ጉዳይ ላይ የአማራ ብቻ ሳይሆን የሌሎችም አቅም ማሳተፍ ይችላል። ለምሳሌ አማራ ከቤኒሻንጉል ሲፈናቀሉ አማራዎች ብቻ ሳይሆኑ ሌሎችም የዚህ ህብረ ብሄር ድርጅት አባሎች አቅማቸውን ሰምስበው ጉዳዩ ላይ ይሰራሉ። ባጭሩ ትልቅ ድርጅት በመሆኑ ትልቅ አቅም ይኖረዋል።

ሌላው ጥቅሙ በአንድ ብሄር የተወሰነ ባለመሆኑ በርካታ አቋማቸው ያልሰከነ ሰዎችን የመሰብሰብ አቅም ነው። እንደሚታወቀው ከጎሳኝነት እና አንድነት ፖለቲካ የሚዋዥቁ በርካታ ኢትዮጵያዊያን አሉ። እነዚህ ጸንፈኛ ጎሰኛ ያልሆኑት በውይይት እና መግባባት ወደ አንድነት አቋም ሊመጡ ይችላሉ እና የህብረ ብሄር ፓርቲ አባል ሊሆኑ ይችላሉ። የህብረ ብሄር ድርጅት ይህንን ማድረግ ይችላል ግን መቼም የአማራ ድርጅት አይችልም።

ሶስተኛው ልጠቅስ የምወደው በህብረ ብሄራዊ መልክ መደራጀቱ ጥቅም ይህ ነው፤ በመአላው ኢትዮጵያ በተለይም በአማራ ህዝብ መካከል በኢትዮጵያዊነት መደራጀት የተለመደ ነው። በኢትዮጵያዊነት መደራጀት ረዥም እና የሰከነ ታሪክ አለው። ይህ አይነት አደረጃጀት ክርክር የለውም ተቃውሞ የለውም (ከጎሰኞች በቀር)። በታሪካችን የተለመደ ነው። ትክክል ቢሆንም ባይሆንም በስመ አማራ መደራጀት ግን ሁልጊዜ አከራካሪ ነው ግጭት እና ጥል ያመጣል። አቅምን ይጎዳል ሰውን ይከፋፍላል። ይህን ታሪክ ከዚህ በፊት አይተነዋል ዛሬም እያየነው ነው።

ግቦቻችንን ለመምታት የትኛው መንገድ ይሻላል

የመጀመርያ የ«አብን» ግብ አማራን ባለበት ቦታ ማዳን እና ለመብቱ መከራከር እና መታገል ነው። እንደ ቅንጅት አይነቱ በስመ «ኢትዮጵያ» የተመሰረተ የህብረ ብሄራዊ ድርጅት ይበልጥ ያአማራ መብትን ማስከበር ይችላል ብዬ ገምታለሁ። በመጀመርያ ደረጃ ይህ ድርጅት ከአማራነት የሰፋ ስለሆን ከላይ እንደጠቀስኩት በርካታ አማራ ያልሆኑ የሌላ ብሄር ሰዎች፤ ቅኝት (ከአንድ በላይ ጎሳ) የሆኑ ሰዎች፤ ጎሰኝነትን የማይወዱ ግን አማራ ወይንም አማራ ብቻ ያልሆኑ ሰዎች ወዘተ ያሳትፋል። ይህ በርካታ አቅም በአማራ የሚደርሰውን ግፍ ላማስቆም ታላቅ ሚና ይጫወታል። ለምሳሌ ከኦሮሚያ ክልል አማሮች ከተፈናቀሉ አማሮች ብቻ ሳይሆኑ ኦሮሞዎችም በአንድ በህብረ ብሄራዊ ድርጅት ስም ይህን ወንጀል ይታገሉታል። ኦሮሞ ከሶማሌ ክልል ሲፈናቀል እንዲሁም። ይህ አካሄድ አንድነትን ይጎለብታል።

ግን እንደ «አብን» የሆነ የአማራ ድርጅት አማሮችን ብቻ በጉዳዩ ማሳተፍ ስለሚችል አቅሙ ውስን ይሆናል። በስመ አማራ እራሱን የገለለ (exclusive) ስለሆነ ወይንም ለሁሉም ክፍት ስላልሆነ  የሌሎች ትብብር ለማግኘት ይከብደዋል። እራሳችሁ ተወጡት ይባላል። እኛ እና እነሱ አይነት ስሜትን ያጎለብታል።

አይ የአማራ ድርጅት ከሊሎች ብሄራዊ ድርጅቶች ለምሳሌ ከኦሮሞ ብሄራዊ ድርጅቶች ጋር አብሮ መስራት ከሆነ ለምን መጀመርያዉኑ በሰፊ በጎሳ ሳይሆን በዜግነት የተመሰረተ ጥላ አይሰራም! ይህ አስተሳሰብ አንዱ የጎሳ አስተዳደር ርዕዮት ዓለም ምሶሶ ነው አይደለምን? ጎሰኞቹ የሚሉት የኢትዮጵያ ፖለቲካ በጠቅላላ ጥሩ ሁኔታ ላይ የሚደርሰው ሁሉም በጎሳ ከተደራጀ ነው። እና ግን እምንለው ሰፊው (ህብረ ብሄራዊ ድርጅት) ጥላ የጎሰኝነት ስሜትን ያበርዳል ትብብርን ያመቻል ግን ሁለት የብሄራዊ ድርጅቶች ሲደራደሩ የጎሳ ስሜት እና አደገኛ የግሳ ውድድር ስለሚቀድም አዋጪ እና ዘላቂ ትብብር ለመፍጠር ከባድ ይሆናል።

በዚህ ምክነያቶች የአማራ ህዝብን ከጥቃት ለማዳን ህብረ ብሄራዊው መንገዱ ይሻላል።

እስቲ የሁለተኛውን ግብ እንመልከት፤ ጎሳዊ አስተዳደርን አፍርሶ ዜጋዊ አስተዳደርን እንዲሰፍን ማድረግ። ይህ ጉዳይ ብዙ ተሳታፊዎች በሚገኙበት ፖለቲካዊ ድርድር ላይ ነው የሚፈታው።  እንደ «አብን» አይነቱ የአማራ ድርጅት ለዚህ ድርድር ምን ሚና ይጫወታል። የአማራ ህዝብን በበርካታ ደረጃ ወክሏል እንበል። አብን ከዚህ ድርድር ማለት የሚችለው የአማራ ህዝብን ወክዬ ህገ መንግስታችን ከጎሰኝነት ወደ ዜጋዊነት እንዲቀየር እጠይቃለሁ ነው። ሌሎች ደግሞ የኦሮሞ ህዝብን ወክዬ ወይንም የቲግራይን ህዝብ ወክዬ ወዘተ ይህንን አንፈልግም ይላሉ። ከዚህ ድርድር የሚሳተፈው የህብረ ብሄር ድርጅቶች ደግሞ እንደግፋለን ይላሉ። ስለዚህ አንዱ «ሴናሪዮ» የአማራው እና የህብረ ብሄር ድርጅቶች ባንድ ወገን ሆነው ህገ መንግስቱ ይቀየር ይላሉ ሌሎቹ የጎሳ ድርጅቶች አይቀየር ይላሉ።

እዚህ ላይ የማን ድምጽ ያሸንፋል (ማስተዋል ያለብን እንደዚህ አይነት የሀገር ግንበታ ድርድር ላይ 50%+1 አይነት ሳይሆን ቢያንስ 70% በላይ ያስፈልጋል ለዘላቂ ስምምነት)። ህገ መንግስቱ አይቀየር የሚሉት ያሸንፋሉ። ለምን?

በአንድ ወገን ያሉት የአማራ እና የህብረ ብሄር ድርጅቶች ድምራቸው ደካማ ነው የሚሆነው። ለምን ብትሉ የአማራ ድርጅት በመፈጠሩ የተነሳው ክርክር እና ጥል የዚህ ወገንን አቅም (capacity) በታላቅ ደረጃ ይመነምናል። ይህንን በመላው አማራ እና መላው ኢትዮጵያ ክርክር ጊዜ አይተነዋል። አሁንም ለተወሰነ ዓመት በአማራ ብሄርተኝነት የሚያራምዱ እና በግንቦት 7 መካከል አይተነዋል። የታወቀ ነገር ነው ጉዳዩ ከፋፋይ ነው ቂም እና ቁስል ትቶ ነው የሚሄደው። ሁለቱ ድርጅቶች ሁለት ከሚሆኑ አንድ ቢሆኑ እጅግ ይበልጥ ተንካራ ይሆናሉ። ግን ለብቻ ሆነው አንድ አቋም ቢኖራቸውም ህገ መንግስቱን ለማስቀየር በቂ አቅም አይኖራቸውም። ህገ መንግስቱን ለመቀየር ግብ አይመታም ማለት ነው።

በተቃራኒው አማራው እንዳለ በህብረ ብሄር ድርጅቱ ስር ቢገባ ይህ ጎጂ ህዝብ ከፖለቲካእና ከመሳተፍ የሚያርቅ ክርክር ይቀራል። ለዚህ ውጤት ማስራጃ እንደ ናሙና ምርጫ 97ን መመልከት ይቻላል። እውነት ነው ረዝም ዓመት በፊት ነበር ሁኔታዎችም ተቀይረዋል ግን ያለን ናሙና ይህ ነው። ህብረ ብሄራዊ ቅንጅት ምርጫውን ጠረገው። ከአማራ ክልል ውጭ በርካታ ድጋፍ አግኝቶ አሸነፈ። ይህ የሚያሳየው አማራው በህብረ ብሄራዊ መልክ ሲጠቃለል የህብረ ብሄራዊ ድርጅቱ አቅም ግዙፍ እንደሚሆን ነው። በቀላል ቋንቋ የአማራ ድርጅት ሲደመር የህብረ ብሄራዊ ድርጅት አቅሙ "2" ነው ካልን አንድ ላይ በአንድ ህብረ ብሄራዊ ድርጅት ስር ቢሆኑ የዚህ ትልቅ ድርጅት አቅም "3" ነው የሚሆነው። እና ይህ ግዚፍ ድርጅት በህገ መንግስት ድርድር ላይ ታላቅ ሚና መጫወት ይችላል ግቡን በቁጥር ሃይል ሊአስፈጽም ይችላል።

በአጭሩ ለሁለቱም ከዚህ ጽሁፍ የገለጽኳቸው የ«አብን» ግቦች አንድ የሆነ የሌሎች ብሄር ሰዎች የሚያጠቃልል በህብረ ብሄር በኢትዮጵያዊነት የተመሰረተ ድርጅት ይበልት ይመረጣል። ይህ ድርጅት በግዙፍነቱ እና ሁሉን አቀፍ በመሆኑ ምክንያት የአማራ መብትን ለማስከበርም ህገ መንግስቱን ለመቀየርም አቅሙ ይኖረዋል።

በተጨማሪ አንድ ነጥብ ላነሳ እወዳለሁ። ከላይ እንደጠቀስኩት አንዱ በአማራነት መደራጀት ጥቅሙ በጎሰኝነት ስሜት ምክነያት ተጨማሪ የአማራ ህዝብ ደጋፍ እና ተሳትፎ ለማግኘት ነው። በ«ኢትዮጵያዊነት» ከምንደራጀት በ«አማራነት» መደራጀት ከአማራ ህዝብ ይበልጥ ተሳትፎ እንደሚያመጣ እና የሚፈጠረውን ድርጅት ይበልጥ የሚያጠነክር ከሆነ የአማራ ህዝብ ለጎሳው ያለው ስሜት ለሀገሩ ካለው ስሜት ይበልጣል ማለት ነው! ወይንም በበቂ ቅስቀሳ እና ፕሮፓጋንዳ የአማራ ህዝብ ከኢትዮጵያዊነት ወደ ጎሰኝነት ስሜት እንዲያድል ማድረግ ይቻላል ማለት ነው። የአማራ ህዝብ እውነታ እንደዚህ ነው? አይመስለኝም። ምናልባት የተወሰነውን ይሳተፋል ሌላው በሚመጣው ጭቅጭቅ ምክነያት ወይንም በጎሳ አደረጃጀት ባለማመን ምክነያት ይቀራል አይሳተፍም።

ግን የህዝቡ ጎሰኝነት ስሜቱ አይሎ ጠንክሮ «አብን» ይጠነክራል እንበል። ይህ ድርጅት በስመ አማራ ተደራጅቶ በአማሮች ድጋፍ አግኝቶ ጠንክሮ እንዴት ነው ህገ መንግስቱ እንዲቀየር መታገል የሚችለው? የጎሳ አስተዳደር ጠፋ ማለት አብን ይጠፋል ነው። ድርጅት እራሱን አያጠፋም። ያቋቋሙት ሰዎች የህገ መንግስቱ መቀየርን ቢፈልጉም እንዴት አንድ ፓሪቲ ህልውናውን አውቆ ያጠፋል? ድርጅቱ አንዴ ከተቋቋመ እና መዋቅር ከሆነ በኋላ እራሱን ለማዘጋት ዝግጁ አይሆንም። በሌላ ቋንቋ አብን እንደዚህ ይላል፤ «የጎሳ ችግር የጎሳ አስተዳደር ነው እንድፈጠር ያደረገኝ፤ የጎሳ አስተዳደር ከጠፋ እኔም እጠፋለሁ፤ ስለዚህ ህገ መንግስቱ እንዳለ ይቀጥል!»

ለዚህ ነው እንደ አብን አይነቱ የጎሳ ወይንም የብሄር ድርጅት ማቋቋም እና የጎሳ አስተዳደር ይቅር ማለት ተቃራኒ ጉዳዮች የሚመስሉት። አብን የተቁቁመው ጎሰኝነት ስላለ ይህ ጎሰኝነት አማራን ስላጠቃ ነው። የአብን «ቤንዚን» ወይንም ኃይል ለጎሳው የተቆረቆረ አማራ ነው። አብን ከህብረ ብሄራዊ ድርጅት ይሻላል የተባለው ይህ የአማራ ተቆርቋሪ በህብረ ብሄራዊ መንገድ ከሚታገል በስመ አማራ ቢታገል ይሻለዋል ተሳትፎውን ይጨምራል ተባሎ ነው። ስለዚህ ጎሰኝነቱ በአማራውም አድሯል ማለት ነው። እንዴት አብን ይህ በንዚኑ ይቅር ይላል። አይለም። የጎሳ አስተዳደሩ ቢቀጥል ነው የሚጠቀመው። ይህ ነው «ፓራዶክሱ»።

Thursday, 17 May 2018

የ«አማራ ብሄርተኝነት» ትውፊታዊ ነውን?

የ«አማራ ብሄርተኝነት» ትውፊታዊ ነው ወይስ እንደ ሌሎች የጎሳ ብሄርተኞቻችን (ኤርትራ፤ ትግራይ፤ ኦሮሞ፤ ወዘተ) በፈረንጅ በምዕራባዊ በ«ተራማጅ» በማርክሲስት ፍልስፍና የተመሰረተ ነው?

እርግጥ ብዙ አይነት የአማራ ብሄርተኝነቶች አሉ፤ ለፖለቲካ ስልት ወይንም «ታክቲክ» ብቻ የሆነ አለ፤ በስመ አማራ ላለፉት 27/40 ዓመታት ለተበደሉት ፍትሕ መጠየቅያ የሆነ አለ፤ ዛሬ አማሮች ላይ የሚደርስባቸውን በደል ለመታገል የሆነ አለ፤ በሀገር ደረጃ በፖለቲካ ድርድር ለአማራ ህዝብ የሚቆም አለ፤ በሃሰት የታማው የአማራ ህዝብን ታሪክ እውነቱ እንዲታወቅ የሚንቀሳቀስ አለ፤ የአማራ ህዝብ ክብርና ማንነትን ለመመለስ የሚታገለው አለ፤ ወዘተ። ዛሬ እነዚህ ሁሉ አይነት እንቅስቃሴዎች በስመ አማራ ብሄርተኝነት ይጠራሉ።

ዞሮ ዞሮ ዋናው ነጥብ ይህ የፖለቲካና መሃበራዊ ንቅናቄ እራሱን የ«አማራ ብሄርተኝነት» ብሎ መሰየሙ ነው። አላማው ምንም ቢሆን በዚህ «አማራ ብሄርተኝነት» የሚለው ስም መጠራት ይፈልጋል። በዚህ ስም መጠራቱ ምን ይነግረናል? በተለይ በትውፊትና በተቃራኒው ምዕራባዊ ተራማጅነት ያለው ግንኙነቱ ምንድነው?

ደስ የሚለው ነገር የሁሉም አይነት የአማራ ብሄርተኝነት ምልክቶች ትውፊታዊ ናቸው። ለምሳሌ ዓፄ ቴዎድሮስ አንዱ ዋና የአማራ ብሄርተኝነት ንቅናቄ ምልክት ናቸው። የአማራ ታሪክን በትክክሉ ማስተዋወቅና መናገር ሌላው የአማራ ብሄርተኝነት አላማና ምልክት ነው። ግን ዓፄ ቴዎድሮስ እራሳቸውን ወይንም ሀገራቸውን ወይንም አገዛዛቸውን የአማራ ወይንም «አማራ ብሄርተኛ» ብለው ይሰይሙ ይሆን? የአማራ ታሪክ የምንለው በታሪክ ሰሪዎቹ እና በዘጋቢዎች ዘንድ የአማራ ታሪክ ይባል ነበር? የአማራ ብሄርተኝነትን ያንጸባርቅ ነበር?

ለነዚህ ሁለቱም ጥያቄዎች መልሱ «አይደለም» እንደሆነ ነው የማውቀው። ዓፄ ቴዎድሮስ እንደ ሁሉም ንጉሶቻችን በስመ ኢትዮጵያዊነት ነበር እራሳቸውን የሚመለከቱት። ታሪካችም እንዲሁ ኢትዮጵያዊነት ላይ ነው የሚያቶክረው አማራነትን አይደለም። ይህ ማለት «አማራ» የሚባል ህዝብ የለም አልነበረም ማለት አይደለም! መኖሩ በታሪክ በተለያየ ቦታ መመዝገቡ ይታወቃል። ግን እስከማውቀው ማንም በስመ አማራ አልተንቅሳቀስም። ትውፊታችንና ታሪካችን እንደዚህ ከሆነ እንዴት እራሱን «አማራ ብሄርተኝነት» ብሎ የሰየመ ንቅናቄ ትውፊታዊ ነው ማለት ይቻላል?

በሁለተኛ (ወይንም አንደኛ!) ደረጃ ጠቅላላ የጎሳ ብሄርተኝነት የሚባለው ነገር የምዕራባዊ የፖለቲካ ፍልፍና እንደሆነ ይታወሳል። በትውፊታዊ ፖለቲካ «ሀገር» ነው ያለው፤ «ጎሳ» የለም። ይህ አባባሌ ብዙ ነገሮች ስለሚያከማች ሁሉንም በዚህ ጽሁፍ አልጠቅስም ግን በጠቅላላ የ«ጎሳ ብሄርተኝነት» የዘመናዊ የምዕራባዊ ጽንሰ ሐሳብ ነው።

የምፈራው ነገር ይህ አዲሱ የአማራ ብሄርተኝነት ልክ እንደ በፊቶቹ የኤርትራ፤ የትግራይ፤ የኦሮሞ፤ ወዘተ ብሄርተኝነቶች በብሶት እና በበአድ ምዕራባዊ ርዕዮተ ዓለም የተመሰረተ ኢተውፊታዊ ንቅናቄ ይሆናል ብሄ ነው። የኤርትራ እና የትግራይ ብሄርተኝነት በመሰረቱ ጸረ ትውፊት ናቸው። በቀላሉ ምሳሌ ለህዝባቸው መሰረት የሆነው ሃይማኖትና ባህልን የሚጠላ ርዕዮተ ዓለም ነው እነዚህ ብሄርተኝነቶች የተመሰረቱት። የኦሮሞ ብሄርተኝነት እንደዚህም ቢሆን ቢያንስ ወደ ኦሮሞ ትውፊት ለመመልከትና እንደ ገዳ አይነቱን ተውፊት ማክበር ሞክሯል። ሆኖም መሰረቱ የማርሲስት የጨቋኝ ተጨቋኝ የጎሳ ብሄርተኝነት አስተሳሰብ ነው። የአማራ ብሄርተኝነትም እንደዚህ እንዳይሆን መጠንቀቅ ይኖርበታል። ግን እራሱን «አማራ» ብሎ ከሰየመ እዚህ ወጥመድ ውስጥ ቀድሞ ገብቷል ማለት ይመስለኛል።

ጎበዝ፤ ጠንካራ፤ ሀገር ወዳድ ምሁራን በተለይ ወጣቶች የአማራ ብሄርተኝነት ያቀፉ አሉ። ምክንያቱ ለሁላችንም ሊገባን ይገባል፤ ለብሶት መልስ ነው። የአስራት ወልደየስ ፖለቲካ የብሶት ሳይሆን እራሳቸው እንዳሉት የግዴታ ነበር። የዛሬው ግን የ27/40 ዓመታት ያመጣው ብሶት ነው። ብሶቱ በህወሓት ላይ ብቻ ሳይሆን በሁሉም፤ በድሮ ምሁራን፤ ልሂቃን፤ ተቃዋሚ፤ ወዘተ ነው። እኔ እንደሚመስለኝ የተማሪው ንቅናቄ ወደ እንደ ማርክሲዝም አይነቱ ምዕራባዊ ፍልስፍና እና ርዕዮተ ዓለም በብሶት ምክንያት እንደገባው የዛሬው ትውልድ በብሶቶች ምክንያት እንደ ቀድሞው ተማሪ ንቅናቄ ወደ ኢ-ትውፊታዊ (ምን አልባት ጸረ ኢትዮጵያዊ) የማይሆን አስተሳሰብ እየገባ ነው። ስለ ተውፊቱ ስላልተማረ በምዕራባዊ የቀለም ትምሕርት የሚሰግድ ህብረተሰብ ውስጥ ስላደገ ሳያውቀው ብዙ ኢ-ትውፊታዊ አስተሳሰቦች አድረውበታል።

ስለዚህ ጉዳዩን ወደ ኋላ ወደ መሰረታችን ተመልሰን አመለካከታችንን በሙሉ ከ«ሀ» ብንገመግም ጥሩ ይመስለኛል። ከዛ በኋላ ነው የአማራ ብሄርተኝነት ትውፊታዊ ነው ወይ የሚለውን ጥያቄ በትክክሉ ልንመልሰው የምንችል የሚመስለኝ።