Showing posts with label Ethiopian Orthodox Church. Show all posts
Showing posts with label Ethiopian Orthodox Church. Show all posts

Friday, 18 December 2020

የቤተ ክርስቲያን ሚና በፖለቲካ - ጥቂት ሃሳቦች

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን እና ምእመናን በሀገራችን ፖለቲካ ምን አይነት ሚና መጫወት አለብን የሚለው ጥያቄ ሰፊና ውስብስብ ነው። ከዚህ ጽሁፍ በዚህ ጉዳይ ላይ አንዳንድ መሰረታዊ የሚመስሉኝን ሃሳቦችን ማቅረብ እወዳለሁ።

1. በእምነታችን እግዚአብሔር ከሁሉም ቦታ በሁሉም ጊዜ በሁሉም ዘመን ይገኛል። እግዚአብሔር የሌለበት ስፍራ የለም። ይህ ማለት ዓለምን በተለምዶ «ዓለማዊ» እና «መንፈሳዊ» ብሎ መለየት አይቻልም። እግዚአብሔር በቤተሰባችን፤ በመስሪያቤታችን፤ በንግዶቻችን፤ በትምሕርትቤቶቻችን፤ በእስርቤቶቻችን፤ በፖለቲካችን፤ በሁሉም ቦታ አለ። ስለዚህ ለእምነታችን off limits የሆነ ቦታ የለም። ሊኖርም አይችልም። ግን ጥያቄው እንዴት ነው እምነታችንን የምናንጸባርቀው ነው! እውነት እምነታችንን እናንጸባርቃለን ወይንም ኑፋቄ፤ ሰላም እናንጸባርቃለን ወይንም አመጽ፤ ደግነት እናንጸባርቃለን ወይንም ክፋት?

2. ክርስቶስ ፍቅርና ሰላም ነውና የክርስትና በፖለቲካ ላይ ያለው አመለካከት ፍቅርና ሰላም መሆን አለበት። መፈለግ ያለብን ሰላምን የሚያሰፍን እና ፍኩ ነገር የማያስደርገን (do no harm) ፖለቲካ ነው። ሁሉ አካሄዳችን በነዚህ ሁለት መርህዎች ስር መሆን አለበት። ሁሉ አቋሞቻችን በነዚህ መርህዎች መፈተሽ አለባቸው። ይህን ወይንም ያንን ፖሊሲ ወይም ፖለቲካዊ ተግባር ይጽደቅ ወይንም ይፈጸም ስንል ይህ ፖሊሲ ወይንም ተግባር ሰላም ያመጣል ወይ እና ክፉ እንዳናደርግ ይከለክለናል ወይ ብለን መጠየቅ አለብን። 

3. በሃይማኖታችን አንድ እውነት አለ፤ ይህ እውነት የኦርቶዶክሳዊ እምነታችን ነው። በዚህ በሃይማኖታችን መደራደር አይቻልም። ግን ከሃይማኖት ውች ሁሉ ነገር አሻሚ ነው። የፖለቲካ አቋም፤ ፖሊሲ፤ አተገባበር ሁሉ ትክክል ሊሆን፤ ሊሳሳት፤ መስተካከል ሊኖረው ይችላል። ፍፁም እውነት የሆነ ፖለቲካ የለም። ፖለቲካ እንደ ማንኛውም ስራ ግብአሩን እና ውጤቱን መርምሮ ገምቶ የሚሰራ ነው። ስተት ሊኖር ይችላል፤ ስተት ይኖራል። ግምቶችም ግቦችም የተሳሳቱ ሊሆኑ ይችላሉ። ስለዚህ ክርስቲያኖች የፖለቲካ አቋምን እንደ ጣኦት እንዳንቆጥር በጣም መጠንቀቅ አለብን። «ሶሽያሊዝም»፤ «ዴሞክራሲ»፤ «ሚክስድ ኤኮኖምይ»፤ «ነጻ ገበያ»፤ «ንጹህ ኤነርጂ» ወዘተ ሁሉም ሊጠቅሙ ላይጠቅሙ ይችላሉ። ከእሴቶቻችን ጋር አወራርድን የሚሆነውን ወስደን የማይሆነውን ትተን መራመድ ነው። እንደ ሁኔታው፤ ጊዜው፤ እና ችግሩ አቋምና ተግባራችንን ማስተካከል። የተለየ አቋም ያለውን አለመውቀስ ልንሳሳትንችላለንና። ፖለቲካ ጣኦት አይደለም!

4. ትህትና (humility) አንዱ የሃይማኖታችን ዋና እሴት ነው። «የተሰበርውንና የተዋረደውን ልብ እግዚአብሔር አይንቅም።» የሃይማኖት አባቶቻችን ከድርሳናቶቻቸው ትህትና ላይ በጣም ያተኩራሉ። ክርስቲያን በማንኛውም ስፍራ ትህትናውን መጠበቅ አለበት በፖለቲካ ስፍራውም እንዲሁ። የፖለቲካ አቋም ስንወስድ ተሳስተን ይሆናል ብለን ማሰብ አለብን። ከላይ እንዳልኩት ፖለቲካ ጣኦት አይደለምና አቋሞቻችንን እንደ ፍፁም አርገን መውሰድ አንችልም። ትህትና የግድ ነው። የትህትና ተቃራኒ እብሪት ክፉ ነው።

5. ንስሐ ከእግዚአብሔር የምንገናኝበት አንዱ ዋና መንገድ ነው። አለ ንስሐ ክስቲያናዊ ኑሮ የለም። እንደምንሳሳት ማመን አለብን። ስንሳሳት ማወቅና ማመን አለብን። ከዛ ንስሐ መግባት አለብን። በፖለቲካው ዓለምም እንዲሁ። ክርስቲያኖች በአቋምም በአፈጻጻምም ልንሳሳት እንችላለን። ይህን መካድ ታላቅ ስህተት ነው ኦርቶዶክሳዊ አይደለም። የንስሐ ፖለቲካ ፍቱን ነው። እኛ ኦርቶዶክሳዊ ኢትዮጵያኖች ትህትና እና ንስሐ በምሳሌ እያሳየን ፖለቲካችንን የሰላምና ፍቅር ማድረግ እንችል ይሆናል።

6. «አንቻቻልም!» መቻቻል አሉታዊ ነው፤ የማንወደውን ግን አማራጭ የሌለንን ነገር ነው የምንችለው። እግዚአብሔር ተቻቻሉ ሳይሆን ተዋደዱ ነው ያለው። ስለዚህ ኦርቶዶክስ ክርስቲያን ሁሉንም ሰው ይወዳል ወይንም መውደድ አለበት። ሁሉንም ሃሳብ አይወድም፤ ሁሉንም ድርጊት አይወድም፤ ግን ሁሉንም ሰው ይወዳል። እንደ ክርስቲያኖች ይህንን የእግዚአብሔርን ፍቅር ማንጸባረቅ አለብን። 

7. ምሳሌ መሆን የክርስቲያን ዋና ተግባር ነው። ሰውን ማስተማር የምንችለው በስብከት ሳይሆን በምሳሌ ነው፤ ይህ መሰረታዊ ትህምሕርታችን ነው። «የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ አግኝና ዙርያህ ያሉ በሺዎች የሚቆጠሩ ይድናሉ» የሩሲያው ቅዱስ ሴራፊም እንዳስተማረን።

Thursday, 7 February 2019

በህዝብ ቆጠራው ላይ የኦርቶዶክስ አማኝ ቁጥር ከታሰበው በታች ቢሆን ምን እንል ይሆን?

በሚመጣው የህዝብ ቆጠራ ላይ የኦርቶዶክስ አማኝ ቁጥር ከታሰበው ወይንም ከሚፈለገው በታች ቢሆን እንደ ኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች ምን እንል ይሆን? ይህን መረጃ / ሰነድ ስናገኝ ምንድነው ማድረግ ያለብን?

በመጀመርያ ደረጃ ንስሃ ነው መግባት ያለብን። የኦርቶዶክስ አማኝ ቁጥር ከመነመነ ዋናው ጥፋት የኛ የኦርቶዶክስ ምዕመናን ስለሆነ። እምነታችን፤ ክርስቶስም፤ የሃይማኖት አባቶችም አስረግጠው ይነግሩናል፤ እኛ ጥሩ ክርስቲያኖች ከሆንን እንደ ብርሃን ሌሎችን ወደ ብርሃን፤ ወደ ቃሉ፤ ወደ ክርስቶስ እናመጣለን። በአንጻሩ ጥሩ ክርስቲያኖች ካልሆንን፤ ጭለማዎች ከሆንን፤ ሌሎችን ወደ ክርስትና እንዳይመጡ እናደርጋለን። አልፎ ተርፎ ከኛም ያሉትን እንዲወጡ እናደርጋለን።

ይህን እውነት በአጭሩ ለመግለጽ የሩሲያዊው ቅዱስ ሴራፊም (ሱራፌል) ዘ-ሳሮቭ  እንዲህ ብለዋል፤

«መንፈስ ቅዱስ እንዲያድርባችሁ ከፈቀዳችሁ ዙርያችሁ ያሉ በሺዎች የሚቆጠሩ ይድናሉ።»

በዚህ ጉዳይ ላይ ለተጨማሪ ማብራርያ ይህን የታወቁት የቆጵሮስ (ሊማሱ ከተማ) ጳጳስ አታናሲዮስ ቃለ ምልልስ ያንብቡ፤ http://orthochristian.com/79957.html። «ክርስቶስን የማያውቁ ሰዎች መኖራቸው የኛ (የክርስቲያኖች) ጥፋት ነው» ይላሉ። ይህ መሰረታዊ እምነታችን ነው።

በመንፈሳዊ ህግ ኃጢአት የቦታ እና የጊዜ ግድብ የለውም። የሁላችንም ኃጢአት ሁላችንንም በተለያየ መንገድ ይነካል። ለምሳሌ፤ እንዴ ወንድሜን ከበደክሉኝ ችግሩ ከኔ እና እሱ መካከል ሆኖ አይቀርም። ይተላለፋል። ወንድሜ ተበሳጭቶ ሌሎችን ይበድላል። ቤት ሲሄድ ቤተሰቡ አክሩፎ ያገኙታል። እኔ ስለበደልኩት ህይወቱን በሙሉ ቁስሉን ተሸክሞ በቁስሉ ምክንያት አስተሳሰቡም ድርጊቶቹም ሊሳባ ይችላል። ቂም ሊይዝ ይችላል። ሰውን በጥርጣሬ ሊያይ ይችላል። በዚህ መንገድ የኔ ኃጢአት እንደ ተላላፊ በሽታ ይንሰራጫል።

ክርስቲያኖች በመንፈሳዊ ህግ ኃጢአት ከቦታ ቦታ ብቻ ሳይሆን ዘመናትን ይሸጋገራል ብለን እናምናለን። ይህ ማለት ኃጢአት ለትውልድ ይተላለፋል። ይህ የሃይማኖታችን መሰረታዊ እምነት ነው። የአዳም ኃጢአትን መውረሳችን ይህን ይገልጻል። ለአዳም ኃጢአት ሃላፊነት ባይኖረንም ውጤቱን ወርሰናል። እኛም ኃጢአት በመስራታችን እንዲሁም አስተላልፈንዋል። ለምሳሌ ከወላጆቼ የወረስኩት ችግርን ተሸክሜ ለልጆቼ በትወሰነ ደረጃ አስተላልፋለሁ። ችግሩ በሃሳብ ብቻ ሳይሆን በደምም (በዲኤኔአችን) ይተላለፋል።

በመንፈሳዊ ህግ ኃጢአት በሀገር ደረጃም ይታወቃል። የእስራኤል ህዝብ ለሀገራዊ ኃጢአታቸው የታዋቁ ናቸው በራሳቸው በኦሪት ታሪክም በወንጌልም ይህ ታሪካቸው ተዘርዝሯል። ሌሎች በርካታ ህዝቦች እንደ ህዝብ ወይንም ሀገር ለኃጢአቶቻቸው ዋጋ ከፍለዋል። ዛሬም እንዲሁ ነው (https://blogs.ancientfaith.com/glory2godforallthings/2015/06/27/dostoevsky-and-the-sins-of-the-nation/)።

ስለዚህ እንደ ግለሰብም እንደሀገርም ኃጢአቶቻችን በቦታ እና ጊዜ ይተላለፋል። ለዚህ ኃጢአቶቻችንን አምነን ንስሃ መግባት አለብን። ይህ መሰረታዊ የክርስትና እምነት ነው። እንኳን በኢትዮጵያ በዓለም ዙርያ ችግር ሲከሰት ወደ ራሳችን ተመልክትን «ምን አድርጌ ወይህም ምን ባለማድረጌ ነው ይህ የሆነው» ብለን እራሳችንን መጠየቅ አለብን።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ መእመን ቁጥር ከቀነሰ ወይንም ካልጨመረ እሄኑኑ ጥያቄ እራሳችንን መጠየቅ ነው ያለብን። አማራጭ የለንም። እውነቱ ይህ ነው። ለዚህ ችግር ሌሎችን ጥፋተኛ ማድረግ ኢ-ክርቲያናዊ አካሄድ ነው። እንደ ኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች «ጴንጤዎቹ»፤ «ሙስሊሞቹ»፤ ወይንም «ሴኩላሪስቶቹ» ናቸው ምእመኖቻችንን የወሰዱብን ማለት አንችልም። ወደራሳችን ብቻ ነው መመልከት ያለብን። እኛ ብርሃን ከሆንን ምንም አይሳነንም፤ ዓለም በሙሉ ወደ ክርስቶስ ይመጣ ነበር። እዚህ ላይ ነው ማተኮር ያለብን። ይመስለኛል።

Monday, 10 September 2018

ቤተ ክርስቲያን በፍጥነት መፅዳት አለባት

ቅዱስ ዮሃንስ አፈወርቅ ፓትሪአርክ በሆኑበት ዘመን 11 ፓፓሳትን አባረዋል ይባላል። ቅዱስ ጳውሎስ በመልክቶቹ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ንፅሁ የሆኑ፤ ጥሩ ምሳሌ የሆኑ እና ህዝቡን የማያሳስቱ መሆን አለባቸው ብሎ በተደጋጋሚ ጽፏል። በርካታ መልክቶቹ ውስጥ ስለቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያለን ችግር እና እንዴት መጽዳት እንዳለበት ጽፏል። በዛሬው ዘመን ይህንን የቅዱስ ጳውሎስ ምክሮችን እና የቅዱስ ዮሃንስ አፈወርቅን ምሳሌ ብንከተል ወይንም ቢያንስ ብናስብበት ጥሩ ይመስለኛል።

በቤተ ክርስቲያናችን አመራር ማለትም ጳጳሳት፤ ካህናት እና አስተዳደር በርካታ የእምነት እና ግብረ ገብ ችግሮች እንዳሉ ይታወቃል። እነዚህ ችግሮች በተለየዩ መንገዶች ባለፉት ዓመታት መጥተዋል በዝተዋል። ይህ ችግር ለቤተ ክርስቲያናችን ታላቅ ጉዳት እያመጣ እንደሆነ ይታወቃል።

ስለ የቤተ ክርስቲያን አመራር ችግሮች ስንወያይ ታላቅ ጥንቃቄ ያስፈልጋል፤

1. ግብዝነትን እና ትዕቢትን መራቅ አለብን፤ እንደ አንድ ምዕመን አመራር ላይ ጣቴን ሳተኩር የራሴን ኃጢአቴን እረሳለሁ። ለዚህ ነው ምዕመናን መሪዎችን እና የቤተ ክርስቲያን ፖለቲካን አትመልከቱ ብሎ የሚመከረው በክርስትና ህይወት።

2. መፍረድ የለብንም። አመራሮች ላይ ችግር ስናይ ሰው በመሆናችን አንዱን ታላቅ ኃጢአት «መፍረድ» ለማድረግ እንፈተናለን። «ድርጊቱ ላይ እንፍረድ ሰውዉ ላይ ግን መፍረድ የለብንም» የሚለውን ትምሕርት ብናውቅም እንረሰዋለን። መርሳት የልብንም። አመራር ሲሳሳት ብናይ በመጀመርያ ለዛ ሰው መጸለይ ነው ያለብን እና እግዚአብሔርን ሁላችንን ከኃጢአት እንዲያርቀን መለመን ነው ያለብን።

ይህን ካልኩኝ በኋላ ግን ቦትዬ ባይሆንም ለህሊናዬ አደገኛ ቢሆንም በዚህ ጉዳይ ሃሳቤን መነገሬ ጥሩ ይመስለኛል። ቅዱስ ጳውሎስ በመልክቱ እንደዚህ አይነት ጉዳዮች የ«እረኝነት» (pastoral) ጉዳዮች እንደሆኑ ገልጿል። ለምሳሌ ተደጋጋሚ ህዝብ የሚያውቀው ኃጢአቶች የሚፈጽም ካህን ወይንም ጳጳስ ካለ አለቆቻቸው ምን እናድርግ ሲሉ እንደ ዘመናዊ ፍርድ ቤት ህግን ከሞላ ጎደል በጭፍን መልኩ አያሰፍኑም። ምን ቢደረግ ነው ካህኑ የሚድነው? ምን ቢደረግ ነው ህዝቡ የሚድነው? ነገሮች ሚዛን ላይ ተደርገው መታየት አለባቸው እንጂ ጥቁር እና ነጭ አይደሉም። አራት መስፈርቶች፤ ክስተቱ፤ ሁኔታው፤ ሰዎቹ እና ዘመኑ መታየት አለበት።

በኔ እየታ በአሁኑ ዘመን ትሉቁ ጎልቶ የሚታየው መስፈርት «ዘመን» ነው። ምዕመናን በመሪዎች ስህተት በጣም ሊወዛበቡ የሚችሉበት ዘመን ነው። ዛሬ አይኑ ብዙ ነው። ወሬው እና ጫጫታው ብዙ ነው። አንድ ችግር ያለው ጳጳስ ወይንም ካህን ቶሎ ከስራ ካልተወገደ በርካታ ምዕመን በፍጥነት መሰናከል (በእምነት ማጣትም በመፍረድም) የሚችልበት ዘመን ነው። የፍጥነት ዘመን ነው። አንድ ችግር ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሲገባ በሽታው በፍጥነት ነው የሚስፋፋው እና መሰረት የሚጥለው።

ይህን በሲኖዶስ ችግራችን በደምብ አይተነዋል። አሁን በቤተ ክርስቲያን አመራሮቻችን የጉቦ፤ ሙስና እና ሌሎች የግብረ ገብ እጦት በምዕመናን ያመጣው ችግርን አይተነዋል። ከኛ ቤተ ክርስቲያን ውጭም በካቶሊች ቤተ ክርስቲያን ችልተኝነት እና መታገስ ባለፉት 30-40 ዓመት ያመጡት ችግሮችን አይተናል።

ስለዚህ አሁን እረኞቻችን ሚዛኑን ከትዕግስት ይልቅ ወደ ፍትነት እና ችኮላ ማድላት ያለባቸው ይመስለኛል። እንደ ዮሃንስ አፈወርቅ ጎልቶ የሚታይ ችግር ሲፈጸም ቶሎ ብሎ ህዝቡ ሳይሰናከል እርምጃ መውሰድ። በሽታው መሰረት ለመጣል እና መስፋፋት እድሉ ሳይኖረው ወድያው ማከም። ይህ በዛሬው ዘመን ለኃጢአት አድራጊውም እጅግ ይጠቅመዋል። በፍጥነት ወደ ኃጢአት ኑሮ ውስጥ ከሚገባ ቶሎ ወደ ንስሃ እንዲገባ ይረደዋል። ይህ የፍጥነት ዘመኑ በቀላሉ እንዳይቆጣጠረው ይረደዋል።

ስለዚህ የቤተ ክርስቲያን አመራሮች እባካችሁን የቤተ ክርስቲያን ጽዳት ዘመቻችንን አፋጥኑ። ችላ አንበል። ታጋሽ አንሁን። በማንም አንፍረድ በስራው ብቻ። ግን ህዝቡን ከፈተና እንጠብቅ። ግልጽና ግዙፍ ኃጢአትን የሚፈጽሙት ጳጳሳት እና ካህናትን ቶሎ ከሃላፊነት ይወገዱ እና ወደ ክርስትናዊ ህክምናቸው ይግቡ። የአሁኑ ዘመን ይህን መንገድ የሚያስገድድ ይመስለኛል።

Friday, 16 February 2018

ጨቋኝና ተጨቋኝ

እንደተረዳሁት ባለፈው ባወጣው መግለጫ ኦህዴድ የኢትዮጵያ መሰረታዊ የጭቆና ታሪክ የ«መደብ ጭቆና» ነበር እንጂ የ«ብሄር ጭቆና» አልነበረም ብሏል። ለዚህ አቋማቸው ኦህዴድን አደንቃለው አመሰግናለውም። ከረዥም ዓመታት የተሳሳተ እምነታቸው መቀየር ከባድ ነውና ጥንካሬና ህሊና ይጠይቃል። ዛሬ በሃገራችን ያለውን ከፍተኛና ኢ-ጤናማ የጎሳ ውጥረትንም ተገንዝበው የተሳሳተ ርእዮተ ዓለማቸውን ገምግመው ሃሳባቸውን ቀይረው ይህንን በይፋ ማውጣታቸው ትልቅ ነገር ነው። ደግሞ ከሌሎች አጋር ፓርቲዎቻቸው ቀድመው ይህን ማድረጋቸውም ሊደነቅላቸው ይገባል። እነ ለማ መገርሳ ለኢትዮጵያዊነት ታላቅ አስተዋጾ እያደረጉ ነው።

ሆኖም ይህ ዜና በሃገራችን መሰረታዊ የሆነ አሳዛኝ አስተሳሰብ አሁንም እንዳለ ይገልጻል? «ጨቋኝ» እና «ተጨቋኝ» እራሱ የተሳሳተ ቋንቋ ነው። ጽንሰ ሃሳብ የመጣው ከውሸትና ኢባህላዊ የሆነ የምእራባዊ የኮምዩኒስት አስተሳሰብ የመነጨ ነው። እስቲ አንድ እርምጃ ወደ ኋላ ተመልሰን ለምንድነው የሰው ታሪክ በ«ጨቋኝና ተጨቋኝ» የሚለው አስተሳሰብ መወሰን ያለበት? እንደዚህ አይነቱ አስተሳሰብ በሃሳብም ደረጃ በተግባርም ግጭት፤ ቅሬታ፤ ቂም፤ ጦርነት፤ ግድያ፤ አብዮት ወዘተ የሚያስገድድ ነው። አንድነት፤ ፍቅር፤ ይቅርታ፤ ትህትና፤ መስማማት ወዘተ የሚቃረን አስተሳሰብ ነው።

አልፎ ተርፎ ማን ግለሰብም ህብረተሰብም ፍፁም ንፁሃን ፍፁም ጥፋተኛ የሆነ የለም። እያንዳዳችን ጨቁነናል ተጭቁነናል፤ በድለናል ተበድለናል፤ ወደናል ተወደናል፤ ተስማምተናል ተጣልተናል፤ ተሳስተናል ስታታችንን አምነን ይቅርታ ጠይቀናል፤ ቂም ይዘናል ይቅርታን ተቀብለናል። በዚህ ዓለም እኔ ነኝ ንጹ ተጨቋኝ የሚል የራሱን ጥፋት ስለማይመለከት ወደ ከባድ ጥፋጡስት ይገባል ሰፊ በደልም ይፈጽማል።

በዚህ ጉዳይ ታላቅ የሩሲያ ደራሲ አለክሳንደር ሶልዠኒትሲን ያሉትን በደምብ ሊገባን ይገባል፤
ከእስርቤታችን አልጋ የሆነው የበሰበሰው ገለባ ላይ ጋደም ብዬ ነው ለመጀመርያ ከውስጤ የበጎ መንፈስ የተሰማኝ። ቀስ በቀስ መረዳት የጀመርኩት ይህ ነው፤ ጥሩና ክፉን የሚለየው መስመር በሀገሮች፤ መደቦች፤ የፖለቲካ ፓርቲዎችም መካከል አይደለም የሚያልፈው፤ ይህ መስመር የሚያልፈው በያንዳንዱ የሰው ልብ መኻል ነው። መስመሩ እድሜአችን በሙሉ ከውስጣችን ወደፊት ወደኋላ ይላል። በክፉ የተሞሉ ልቦችም ቢያንስ ቅንጣት ያህል ጥሩነት ይኖራል፤ ከሁሉም ጥሩ ከሚባለውም ልብ ከአንድ ጥጓ ትንሽ ክፉነት ይኖራል።
በየቦታው እየዞሩ ያሉ ክፉ ስራ የሚሰሩ ክፉ ሰዎች ቢኖሩና እነሱን ከኛ መለየትና ማጥፋት ብቻ ቢሆን ኖሮ እንዴት ቀላል ነበር? ግን ጥሩና ክፉን የሚለየው መስመር ከያንዳንዱ የሰው ልጅ ልብ መካከል ነው የሚያልፈውና ማን አለ ከራሱ ልብ ቁራጭ ቆርጦ ለማጥፋት ፈቃደኛ ይሆነ?
ሶልዘኒትሲን ኮምዩኒስት የነበሩ ወታደር የነበሩ ስታሊን ለዓመታት በሞት እስር ቤት (ጉላግ) ያሰራቸው ከሩሲያ ወደ ኦርቶዶክስ ሃይማኖታቸው የተመለሱ የሩሲያ ጀግና ነበሩ። ተጨቋኝ ነኝ ማለት የሚገባቸው ነበሩ። ለሃገረቸው ጦርነት ተዋግተው በማግስቱ የታሰሩ ናቸው። አለምንም ጥርጥር ተጨቋኝ ነኝ ማለት የሚገባቸው ነበር። ግን እስር ቤት የሌሎችን ሳይሆን የራሳቸውን ኃጢያት እንዲገለጽላቸው አደረገ! የሰው ልጅ እውነተኛ ባሕርይ እንዲረዱ አደረገ። የሰው ልጅ ችግርም እንዴት መቅረፍ እንደሚቻል ገባቸው። በጦርነት፤ በማስወገድ፤ በማባረር፤ በመወገን ሳይሆን በንስሃ፤ በመስማማት፤ በመከባበር፤ በመቻቻል ነው።

ይህ ሩሲያዊ ሶልዠኒትሲን የዘመኑን «ጭቋኝና ተጨቋኝ» አስተሳሰብን ትተው የእውነትን ባህላዊ የኢትዮጵያዊ አስተሳሰብ ነው የገለጹት። ሩሲያዊው ኦርቶዶክስ ባህላችንን ያስታውሱን። ለምንናውም የኢትዮጵያ ባህል፤ ማንኛውም ሃይማኖት፤ ይህ የ«ጨቋኝና ተጨቋኝ» ርእዮተ ዓለም በአድ ነው። በአድ ነው። ሚስኪኖቹ የጃንሆይ ተመሪዎች ወደ ሃገራችን ከምእራብ ሃገራት ያመጡት መርዝ ነው። መርዙን እናውጣው። ወደ እራሳችን እንመለስ።

Thursday, 15 February 2018

ቤተ ክርስቲያን መቅደም አለባት!

ከትላንት ወድያ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ዙርያ ያልጠበቅናቸው መልካም አሳቢዎች እንደ ለማ መገርሳና አቢይ አህመድ ብቅ ማለት ጀመሩ። ትላንትና መንግስት ለረዥም ዓመታት የሚለመነውን ነገር አደረገ፤ ያለጥፋት የታሰሩትንና የተሰቃዩትን በርካታ እስረኞችን ፈታ። ዛሬ ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስቴራችን ኃይለማርያም ደሳለኝ በፈቃደኝነታቸው ስልጣናቸውን ከቀቁ። መልካ ለውጦች ይታያሉ፤ እግዚአብሔር መጨረሻውን ያሳምርልን።

ግን ከፖለቲካው ቤተ ክርስቲያናችን መቅደም አልነበረበትም? (ይህን ስል እኔም እንደ አንድ ምእመናን እራሴን እየወቀስኩኝ ነው።) የኛ ለማ መገርሳዎች፤ በትህትና አለመፍረድ፤ በፍቅርና በምሳሌ፤ የሚናገሩት የት አሉ? እርግጥ አሉ፤ ግን በሌሎቻችን ተከበው ድምጻቸው በአግባቡ አይሰማም። እስረኞችንን መቼ ነው የምንፈታው? በርካታ እስረኞች አሉን፤ ፍቅር፤ ሃላፊነት፤ እርቅ፤ ትህትና፤ ሰላም። እነዚህንንሁሉ አስረን ቁጭ ብለናል። መቼ ነው የምንፈታቸው? ደግሞ መቼ ነው ሃላፊነት ወስደን እራሳችንን ህዝብ ፊት ዝቅ የምናደርገው። እንዲህ የሚያደርጉ አሉ ግን በኔ አይነቱ ተከበው አይታዩም። እንቅፋትም ሆነናቸዋል።

ቤተ ክርስቲያናችን እንደ አቡነ ጴጥሮስ መምራት መጀመር አለባት። በፖለቲካው መመራት ወይም መቀደም እፍረት ነው። አሁን ከቤተ ክርስቲያን እርቅ በፊት በሃገራችን ፖለቲካ እርቅ ቢመጣ ታላቅ እፍረት አይደለም? ከዛ በሗላ መጀመሪያውኑ ፖለቲካ ነው ያስቸገረን ብለን ልናሳብብ ነው? እነ ቅዱስ ጴጥሮስ በሮሜ ፖለቲካ እየተሰውዉ ደፍሮ ያላሉትን ልንል ነው?! ይህ ቢሆን እጅግ አሳሳዛኝ ነው።

ስለዚህ እንምራ! በሃገር ውስጥና በውጭ ያሉት ስይኖዶስ መካከል ፈጥነን እርቅ እናምጣ። ለኢትዮጵያ ህዝብ ምሳሌ እንሁን። ፈተናው ብዙ ነው። ገና እየበዛ ይሄዳል። ግን እግዚአብሔር ሁልጊዜ በሁሉም ቦታ ከኛ ጋር ነው። ይህን ካመንን ለፍቅር እንድፈር፤ አንፍራ!

Tuesday, 8 November 2016

የሲኖዶሱ ጉዳይ በ2009

2009/2/29 .. (2016/11/8)

(pdf)

እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያናችን ሁለት የተወጋገዙ ሲኖዶሶች አላት፤ በኢትዮጵያ ያለው ሲኖዶስና ስደተኛው ሲኖዶስ። ይህ ሁኔታ የተፈጠረው ኢህአዴግ ስልጣን ሲይዝ የቤተ ክርስቲያናችን ፓትሪያርክ አቡነ መርቆርዮስ በመሰደዳቸው ነው። ስለ መሰደዳቸው ሁኔታ በዛን ጊዜ ጠቅላይ ሚኒስቴር የነበሩት አቶ ታምራት ላይኔ ከመንበር እንዲወርዱ ያዘዝኩት እኔ ነኝ ብለው እንደመሰከሩ ይታወሳል። ምንም ቢሆን በአቡነ መርቆርዮስ መሰደድና በአቡነ ጳውሎስ መሾም መካከል ጳጳሳቱ የመንግስት ጫና አድሮባቸው እንደነበረ ግልጽ ነው። ሆኖም መንግስት በቤተ ክርስቲያን ላይ ጫና ሲያደርግ ይህ የመጀመርያ ጊዜ አልነበረም። በደርግ ጊዜም እንዲሁ ነበር፤ በኃይለ ሥላሴም፤ ከዛም በፊትም በነግስታቱ ዘመን የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ጳጳሳቶችዋ ይህ ፈተና ሁልጊዜ ዪደርስባቸው ነበር። ሆኖም የዛሬው ክፍፍል ምንጭ ይሄው የመንግስት ጫና በሲኖዶሱ ላይ በመሆኑ ነው።

ታድያ መፍትሄው ምንድነው? እንደሚታወሰው በሲኖዶሶቹ መካከል እርቅ ለማምጣት በተለያየ ጊዜ ግለሰቦችም፤ ሽማግሌዎችም፤ እንዲሁም የቤተ ክርስቲያን ሃላፊዎች ሞክረዋል። አንዳንዱም ሙከራ ጥሩና ያልተጠበቀ የማቀራረብ ውጤቶችን አሳይተዋል። ግን እስካሁን ጉዳዩ አልተቋጨም።

በዚህ ጽሁፍ የጉዳዩን ጠቅላላ ይዞታ አልተችም፤ ጉዳዩና የእርቅ ስራው እጅግ ከባድና ውስብስብ ናቸውና። በዚህ ጽሁፍ ከጉዳዩ አንዱን ንብርብር ለመላጥ ነው የምሞክረው፤ ይህ ደግሞ ሲኖዶስ ሊሰደድ ይችላል ወይ የሚለው ጥያቄ ነው።

ይህን ጉዳይ ለዘብ ባለ መንገድ ከታየ ስምምነት ላይ እንደሚደረስና ችግሩም መፍትሄ አንደሚያገኝ እርግጠኛ ነኝ። ነገር ግን አክራሪ አስተያየቶች ናቸው የሰፈኑት። እነዚህ «ሲኖዶስ ሊሰደድ አይችልም» እና «መንግስት ሲኖዶስ ላይ ጫና ካደረገ ፓትሪያርኩ ግድ መሰደድ አለባቸው ስለዚህ ሲኖዶሱ ውጭ ይሆናል ማለት ነው» የሚሉት ናቸው።

በመጀመሪያ በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በማንም የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ቀኖና ሲኖዶስ መንቀሳቀስ አይችልም የሚል ህግ የለም፤ ሊኖርም አይችልም። ጣልያን ኢትዮጵያን ወርራ ከአንድ በስተቀር ጳጳሳቱን በሙሉ ረሽና ቢሆን እኚህ አንድ የቀሩት ጳጳስ ተሰደው ቤተ ክርስቲያኑን ካሉበት ቢመሩ ህገ ወጥ ነው? በፍጹም። ግን ዋናው ጥያቄ ህገ ወጥ ነው ወይ ሳይሆን ክርስቲያናዊ አይደለም ወይ? ቤተ ክርስቲያን በዚህ መንገድ እራስዋን ማዳንና በጎቿን መጠበቅ አለባት። አንዳንድ ሁኔታ መሰደድን ያስገድዳልም ይመክራልም።

እነዚህ ሁኔታዎች ምን እንደሆኑ አስቀድሞ አይታወቅም፤ ጊዜው ሲደርስ ሁኔታው ተጠንቶ ነው መወሰን የሚቻለው። ለዚህም ነው ከላይ ስለ ሲኖዶስ መሰደድ ቤተ ክርስቲያናዊ ህግ ሊኖር አይችልም ያልኩት። እንደ ሁኔታው፣ እንደ አደገኛነቱና እንደ አስፈላጊነቱ ውሳኔው ይለያያል።

ለዚህ እውነታ ጥሩ ምሳሌው የሩሲያ ኦርቶዶክስ ሲኖዶስ በ1910 በሩሲያ ኮምዩኒስት አብዮት ምክንያት መሰደዱ ነው። የሶቪዬት ኮምዩኒስት መንግስት በቤተ ክርስቲያንዋ ላይ ያደረሰው ጥቃት እጅግ ከባድ በመሆኑ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ካህናትና አማኞች በህሊናም ቢሆን ለማሰብ ያስቸግራል። በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ያህል ካህናት ናቸው በተለያየ መንገድ የተገደሉት። ሌሎቹ በሞት እስር ቤቶች ታሰሩና አብዛኞቻቸው ሞቱ።

በዚህ ሁኔታ በ1913 የሩሲያ ኦርቶዶክስ ፓትሪያርክ ቅዱስ ቲኾን ቤተ ክርስቲያንዋ ታላቅ ችግር ላይ መሆንዋንና የሶቪዬት መንግስት ካህናት እየገደሉ የራሱን ካድሬዎች ካህን አድርጎ ወደ ቤተ ክርስቲያን እያስገባ እንደሆነ ተገንዝበው በውጭ ያሉት የተሰደዱት ጳጳሳት እራሳቸውን እንዲያስተዳደሩ አዘዙ። ያሉበትን ሁኔታም ለመገምገምና ይህ ውሳኔ ላይ ለመድረስ ሶስት አመት ፈጀባቸው። ሲኖዶሱ፣ ማለትም ጳጳሳቱ በመንግስት ቁጥጥር ስር እንደሆኑ ሲያውቁ ነው ፓትሪያርኩ ውጭ ላሉት ጳጳሳት ካሁን ወዲያ በኛ መተማመን አትችሉምና እራችሁን ቻሉ ያሏዋቸው።

ሆኖም የውጩ ፓትሪያርክ ወዲያው አልተሾመም። ፓትሪያርክ ቲኾን ከተሰዉ (አሁን ቅዱስ ቲኾን ናቸው) በኋላና የሩሲያ (ሞስኮብ) ሀገረ ስብከት ከመጠን በላይ የካድሬ ግዛት ሲሆን የውጭ ሲኖዶሱ ፓትሪያርክ ሾመ። ከዛ ቀጥሎ እስከ 1999 የሩሲያ የውጭ ሲኖዶስ (ROCOR) እና የሞስኮብ ሲኖዶስ ተለያይተው እንዲሁም ሲወጋገዙ ቆዩ።

1999 ሁለቱ ሲኖዶሶች ተታረቁ። የውጭ ሲኖዶሱ ከማን ጋር ነው የትታረቀው፤ የሩሲያው ሲኖዶስ በካድሬ የሞላ አልነበረምን ብላችሁ እያሰባችሁ ይሆናል። በሚገርም ሁኔታ ካድሬ ያልሆኑ ታላላቅ አባቶችና መነኮሳት አንገታቸውን ደፍተው ከፖለቲካ ራሳቸውን አርቀው እየሰሩ እየተፈቱ እየተደበቁ የሶቪዬት ኮምዩኒስት ዘመንን ያሳለፉ ነበሩ። አንዳንዶቹ ጭራሽ ራሳቸውን እንደ ካድሬ አስመስለው ሌሎች ወንድሞቻቸው ካህናትን ክጥቃት የመጠበቅ ስራ ይዘው ነበር። አሁንም በሀገራችን ኢትዮጵያ ከጳጳሳቱና ሀገረ ስብከቱ የካድሬ መንፈስ፤ የካድሬ ብቻ ሳይሆን ሲብስ የተራ ሙስናና ሐጥያት መንፈስ፤ ቢኖርም ከዛ መካከል እጅግ ብፁ የሆኑ አገልጋዮች እንዳሉ እናውቃለን። ካድሬ የሚባሉት ውስጥም እንደሁላችንም ከራሳቸው ጋር እየተሟገቱ ንስሀ እየገቡ እየወደ እየተነሱ የሚኖሩ አሉ። በሩሲያም ሲኖዶስ እንዲሁ ስለነበር ነው እርቅ ላይ ሊደርሱ የቻሉት

በተዘዋዋሪ በዚህ በሩሲያ ታሪክ ሌላ አስደናቂ ሁኔታ ተፈጥሮ ነበር። በሁለተኛ የአለም ጦርነት ጀርመኖቹ ለተወሰነ ጊዜ ምእራብ የሶቪዬት ህብረትን ተቆጣጥረው የሩሲያ ኦርቶዶክስ ሀገረ ስብከት የተዘጉትን በሺህ የሚቆጠሩ ቤተ ክርስቲያኖችን እንደገና እንዲከፍት ፈቀዱ። ከግድያ የተረፉት እውነተኛ የሆኑት ካህናት ይህን ነፃነት ተጠቅመን ህዝቡን እናገልግል ወይስ የሀገራችን ወራሪ የሰጠንን ነፃነት ለክርስቶስም ቢሆን ልንጠቀምበት አይገባም በሚለው ጥያቄ ልባቸው ተከፋፍሎ ነበር። ምእመናኑ ሃይማኖቱ እጅግ ጠምቷቸው ስለነበር በርካታ ካህናት ወደ ቤተ ክርስቲያኖቻቸው ተመልሰው አገለገሉ። ጦርነቱ ሲይበቃም የሶቬት መንግስት እንደዚህ አይነት ካህናትን እንደጠበቁት እስር ቤት ላካቸው ወይም ረሸናቸው። (ስለዚህ ታሪክ «ካህኑ» የሚባለውን የሩሲያ ፊልም እንድታዩ እጋብዛችኋለው፤ እጅግ አስተማሪ ነው።)

የሩሲያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የመሰደድ ታሪክ የሚያሳየን የሲኖዶስ መሰደድ ጉዳይ እንደ በርካታ የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ጉዳዮች «ጥቁርና ነጭ» አይደለም። እንዲህ ቢሆን ይሰደዳል እንዲህ ቢሆን አይሰደድም የሚል አስቀድሞ ሁሉንም ሁኔታ የሚያካትት ህግ የለም። እንደ ሁኔታው ነው ውሳኔ የሚወሰነው።

ታድያ በኢትዮጵያ በ1983 የነበረው ሁኔታ አቡነ መርቆርዮስ የሲኖዶስ መንበራቸውን ይዘው እንዲሰደዱ ያስገድዳቸው ነበር? ይህ ጥያቄ እውነት ወይ ውሸት የለውም፤ እንደ እያንዳንዱ ሰው አመለካከት ነው። አዎን መንግስት በጳጳሳቱ ላይ ጫና እያደረገ ነው ግን ያን ያህል ስላልሆነ መሰደድ አያስገድድም፤ ጳጳሳቱ ጫናውን ሊቋቋሙ ይገባል ማለት ይቻላል። ወይም ጫናው የቤተ ክርስቲያኑን መሰረት አናግቶታልና በነፃነት ምእመናኑን ለማገልገል ሲኖዶሱ ከሀገር ውጭ መሆን ነበረበት ማለት ይቻላል። ሁለቱም አስተያየቶች ያስኬዳሉ።

ከዚህ መማር የምንችለው ታላቅ ትምህርት ሁሉም ነገር እንደ ሃይማኖት ዶግማ ወይም ቀኖና ማየት የለብንም። በነዚህ ታሪኮች አንድ እውነት ብቻ ነው ያለው። ስለሆነም እነዚህን የመሰሉ ችግሮችን እንደ ዶግማ እና ቀኖና እንደ አስፈላጊነቱ የማይሻሻሉ አድርገን ማየት የለብንም። ከሃይማኖታችን መሰረተ ትምህርትና ስርዓት በቀር ሌላውን ጉዳይ በሙሉ በትህትና ነው ማየት ያለብን። አቋሞቻችንንም በትህትና መያዝና ሃሳቦቻችንን መቀየር መቻል አለብን። ጥሩ ክርስቲያን አንድ አምላክ እግዚአብሔርን እንጂ ሃሳቡን፣ የሚከተለውን ርዕዮት አለም፤ ወይንም አቋሙን አያመልክም።

በመጨረሻ አንደ ልጠቅስ የምፈልገው ነገር አለ፤ ሁለቱ ሲኖዶሶቹ ቢታረቁ ለሀገራዊ እርቅ ሰላምና የመንፈሳዊ ደስታና መረጋጋት ታላቅ ድል ይሆናል። በዛሬ ኢትዮጵያ ህዝቡ ያጣው መሪ ነው የሚባለው እውነት ነው። ልጄ ሲያድግ እንደ ከሌ ቢሆንልኝ የሚባል መሪ በየትኛውም በመንግስትም በሃይማኖትም በመሃበራዊም ዘርፍ የለም። ከግዥ መደቡ ጥሩ ምሳሌ የሚባልና የሚደነቅ የለም፤ ጭሽ ህዝቡ ሙስናና ተመሳሳይ መትፎ ስነ መግባር ውስጥ ሲገባ መሪዎቻችንም ያረጉታል ለምን እኛም አናደርገውም እያለ ነው። ስለዚህ እንደ ሲኖዶስ እርቅ አይነቱ ዜና ከቤተ ክርስቲያን መሪዎች ቢመጣ ለህዝባችን ታላቅ ምሳሌና ለሀገራዊ እርቅ ታላቅ ድል ነው የሚሆነው። ይህ እርቅን ለማምጣት ደግሞ በሃይማኖታዊም በፖለቲካውም አቅጣጫ ቢታይ ከባድ ያልሆነ ጥቅሙ ከጉዳቱ እጅግ ከፍ ያለ ነግር ነው። ከሌሎች ጉዳዮች ይልቅ ብዙም ከባድ አይደለም። እግዚአብሔር ይህንን እርቅ ለማድረስ ልቦናውን ይስጠን።