Friday, 8 June 2018

ሃይማኖታዊዋ ትግራይ እንዴት በፀረ ሃይማኖት ፓርቲ ትመራለች?

የትግዳይ ህዝብ ረዥም ታሪክ እንዳለው ወግ እና ትውፊቱን እንደሚወድ እንደሚአከብር ይታወቃል። ለምሳሌ ሃይማኖቶቻቸውን የሚአስቀድሙ እንደሚአጠብቁ ይነገራል ይታያል። በክብረ በአልም በዘውትር ጊዜም አክሱምን የጎበኘ ክርስቲያን ይህንን ሊመሰክር ይችላል። የህዝቡ አምልኮት ልዩ እና ጠንካራ መሆኑ ይታያል።

ታድያ እንደዚህ አይነቱ ህዝብ እንዴትቢሆን ነው በ ፀረ ሃይማኖት የሆነ የፖለቲካ ኃይል የሚገዛው እንዴት ይህን ኃይል ለዓመታት ከሌሎች ለይቶ ይደግፋል የሚለው ጥያቄ እንዴት ነው የማይጠየቀው። ፀረ ሃይማኖት ስል ከህወሓት አባላት መካከላማኞች የሉም ማለቴ ሳይሆን ግን የፓርቲው ርዕዮት ዓለም ፀረ ሃይማኖት መሆኑ ግልጽ ነው። አጀማመሩም እንደዚሁ ነው ዛሬም እንደዚህ ነው። አንድቀላል ምሳሌ ስለ ጎሰኝነት ያላቸው አመለካከት ቀትታ ከማርክሲዝም የመጣ ነው። የ «ጨቋኝ ተጨቋኝ» አመለካከታቸውም እንደዚሁም። እነዚህ «ከ ሃይማኖት ነፃ» የሆኑ አመለካከቶች ሳይሆኑ ፀረሃይማኖት ፀረ ትውፊት ናቸው።

እርግጥ ሃይማኖታዊ ትውፊት አክባሪ የሆነ ህብረተሰብ እንዴት በፀረ ሃይማኖት ወይም ሃይማ ኦት የለሽ ገዥ መደብ ወይም ልሂቃን ይመራል የሚለው ጥያቄ ትግራይን ብቻ ሳይሆን መላ ኢትዮጵያን ይመለከታል። ከኦርቶዶክስ ክርስቲያን አንፃር መልሱ ቀላል ነው፤ የህዝቡ የኛ ሐጢአት ነው ምክንያቱ። በጾቪዬት እስር ቤት የተሰቃዩት አለክሻንደር ሶልዠኒትሲን ከእስር ቤት ሆነው የጻፉትን እንደገና ልጥቀስ
ከእስርቤታችን አልጋ የሆነው የበሰበሰው ገለባ ላይ ጋደም ብዬ ነው ለመጀመርያ ከውስጤ የበጎ መንፈስ የተሰማኝ። ቀስ በቀስ መረዳት የጀመርኩት ይህ ነው፤ ጥሩና ክፉን የሚለየው መስመር በሀገሮች፤ መደቦች፤ የፖለቲካ ፓርቲዎችም መካከል አይደለም የሚያልፈው፤ ይህ መስመር የሚያልፈው በያንዳንዱ የሰው ልብ መኻል ነው። መስመሩእድሜአችን በሙሉ ከውስጣችን ወደፊት ወደኋላ ይላል። በክፉ የተሞሉ ልቦችም ቢያንስ ቅንጣት ያህል ጥሩነት ይኖራል፤ ከሁሉም ጥሩ ከሚባለውም ልብ ከአንድ ጥጓ ትንሽ ክፉነት ይኖራል።
በየቦታው እየዞሩ ያሉ ክፉ ስራ የሚሰሩ ክፉ ሰዎች ቢኖሩና እነሱን ከኛ መለየትና ማጥፋት ብቻ ቢሆን ኖሮ እንዴት ቀላል ነበር? ግን ጥሩና ክፉን የሚለየው መስመር ከያንዳንዱ የሰው ልጅ ልብ መካከል ነው የሚያልፈውና ማን አለ ከራሱ ልብ ቁራጭ ቆርጦ ለማጥፋት ፈቃደኛ ይሆነ?
እያንዳንዶቻችን ልብ ውስጥ ያለው ክፋት ተጠራቅሞ ነው በመሪዎቻችን ላይ የሚታየው።

ሆኖም አሁን የህወሓት ስልጣን በሚገባው እየመነመነ ስለሆነ የትቭራይ ህዝብ ስለማንነታቸው ስለ ሃይማኖት እና ትውፊታቸው ስለ ፀረ ሃይማኖት መሪዎቻቸው እራሳቸውን ለመመርመር ጥሩ ጊዜ ይመስለኛል። የትግራይ ህዝብ በመጀመርያ ኮሙዩ ኢስት ነው ወይንም ሃይማኖተኛ። ልጎቹ ሃይማኖት የለሽ ገንዘብ እና ስልጣን አምላኪዎች ሆነው እንዲያድጉ ነው የሚፈልጉት? መሪዎቻቸው እየወደቈየተነሱምቢሆን ሃይማኖታዊ ቢሆኗይሻልም ወይ። ይህ ነው ወይም ካርል ማርክስ ወዘተ ነው የ ትግራይ ትውፊት? እነዚህን ጥያቄዎችን ለመጠየቅ ትክክለኛው ጊዜ ይመስለኛል።

እኔ በትክክሉ ይር ትግራይ ሰው ባልሆንም እንደ ኢትዮጵያዊነቴ ይበልጥ እንደ ኦርቶዶክስ ክርስቲያን መሆኔ ይህ ጉዳይ የ ኤርትራም ተመሳሳይ በማርክሲስት ሻብያ መገዛቱ ጉዳይ እጅግ ያሳዝነኛል። እነዚህ ቦታዎች ለክርስትናችን ቁልፍ ምናልባትም ምንጭ ቦታዎች ናቸው። እንዴት ሐጢአተኞች ብንሆን ነው ወደ ፀረ ሃይማኖታዊ አገዛዝ የሸጥናቸው። እግዚአብሔር ይቅር ይበለን።

Monday, 4 June 2018

የዘመናዊነት ዕቅድ (The Modern Project)

ይህ ከቀሲስ/መምህር ስቲፈን (እስቲፋኖስ) ፍሪማን ጽሁፍ (https://blogs.ancientfaith.com/glory2godforallthings/2014/01/10/the-modern-project/) በሰፊው የተረጎምኩት ነው። ቀሲስ ስቲፈን አሜሪካዊ (ምስራቃዊ ወይም ቃልቄዶናዊ) ኦርቶዶክስ ቄስ ናቸው። ከፕሮቴስታንትነት ወደ ኦርቶዶክስ እምነት «ከተመለሱት» በርካታ አሜሪካዊ ካህናት መካከል ናቸው። አሜሪካዊ በመሆናቸው ብቻ ሳይሆን በቀለም ትምሕርት እና በሃይማኖት ታሪካቸው ምክንያት ስለ በዘመናችን የነገሰው ዘመናዊነት ፍልስፍና በደምብ ያውቃሉ ለክርስትና ዋና ጠላት መሆኑንም ይገነዘባሉ። ሆኖም የዘመናዊነት ፍልስፍና የነገሰ ስለሆነ ሳናውቀው ሁላችንም በተወሰነ ደገጃ እንደተቀበልነው ያውቃሉ። ሰለዚህም ነው ቀሲስ ስቲፈን በዚህ ጉዳይ ዙርያ ብዙ የሚጽፉት። ጽሁፋቸው ለሁላችንም ገላጭ እና አስተማሪ ነው ብዬ አምናለው። ብሎጋቸውን ብታነቡ እጅግ ጠቃሚ ይሆናችኋል ብዬ አምናለው።

ሁለተኛ ዲግሪዬን በ«ቴኦሎጂ» በምማርበት ወቅት (1970 ዎቹ) «የዘመናዊነት ዕቅድ» ('the project of modernity') የውይይት ርዕስ የነበረበት ጊዜ ነበር። ይህ የዘመናዊነት ዕቅድ «ዘመናዊውን» ዓለም ('the modern world') ለመገንባት የሚሰሩትን ማህበራዊ፤ ፍልስፍናዊ፤ ፖለቲካዊ እና ሃይማኖታዊ ስራዎችን ያካትታል። በ17ኛ ክፍለ ዘመን የመነጨው «የብርሃን መብራት» ('the Enlightenment') ፍልስፍና አዲስ የአስተሳሰብ አይነቶች ወደ ምዕራባዊው ዓለም (ከዛ ቀጥሎ ወደ መላው ዓለም) አመጣ። ለምሳሌ ለ«ሀገር» የምንለው ፅንሰ ሃሳብ አዲስ ትርጉም እና አወቃቀር ፈጠረ። የክርስትና ሃይማኖትን በአዲስ መልክ ፈጠረ (ለምሳሌ ፕሮቴስታንትነት)። ከሁሉም በላይ ግን የሰው ልጅ ማንነትን ሌላ ትርጉም ሰጠው።

እኛ የዚህ ዘመን ሰዎች የዚህ ፍልስፍና ወራሾች ነን። የዘመናዊነት እና የዘመናዊነት ዕቅድ ልጆች ነን። ዛሬ ማንም ትምህርት የሌለውም ሰው «የዘመናዊነት ዕቅድ» ያመጣውን አስተሳሰቦችን ሳያውቀውም ቢሆን አድሮበታል አምኖበታልም። በትምህርት ቤትም በሚዲያም በሌሎች መንገዶች አስተሳሰቡን ወርሰነዋል። እኛ «የዘመናዊነት ዕቅዱ» ውጤቶቹ ሆነናል።

ዘመናዊነት ዕቅዱ የሰው ልጅን ማንነት ሲደነግግ እንደዚህ ይላል፤ « የሰው ልጅ በራሱ ብቻ የሚተዳደር ነፍስ ነው፤ ውሳኔዎቹ እና ስራው ብቻ ነው ማንነቱን የሚወስን»። ይህ ማለት፤

1. በራሱ ብቻ የሚተዳደር ነፍስ፤ የሰው ልጅ የማንነቱ መሰረት በማወቅ እና ማሰብ ችሎታው የተወሰነ ነው። «የማሰብ እና ማወቅ ችሎታዬ ብቻ ነው የሰው ልጅ የሚአደርገኝ»። ከዚህ ቀጥሎ በፈቃዴ ከሌሎች ጋር መጋራት እችላለሁ ግን ማንነቴ በራሴ ብቻ ነው የሚወስነው። ከሌሎች ጋር ያለኝን ግንኙነትም እኔ ብቻ ነው የምወስነው። ይህ ነው በዘመናዊው ዓለም የምናየው የ«ግለኝነት» አኗኗር መሰረታዊ ሃሳብ።

2. ውሳኔዎቻችን እና ስራዎቻችን ማንነታችንን እና የህይወት ጉዞዋችንን ይወስናሉ፤ በዚህ ዓለም ያለኝ የማንነት ምደባ የራሴ አመራረጥ፤ ውሳኔዎች እና ያሳለፍኩት ልምዶች ናቸው የሚወስኑት። ውሳኔዎቼ ማንነቴን ይወስናሉ እና መሆን የምፈልገውን መሆን እንድችል ብቸኛ ሚና ይጫወታሉ። የኔ ምርጫ እና ውሳኔዎች ናቸው የህይወቴን ትርጉም እና ማን መሆን እንደምፈልግ የሚወስኑት።

እነዚህን ፅንሰ ሃሳቦች ካሰላሰልናቸው የዘመናችን ታሪክን ወሳኝ ነገር «ነፃነት» ለምን እንደሆነ በቀላሉ እንረዳለን። (ይህ «ነፃነት» የሚባለው የመወሰን እና የመምረጥ «መብት» ነው እንጂ እውነተኛው ነፃነት አይደለም።) የሰው ልጅ ማንነት ትርጉም ከላይ የተጻፈው ከሆነ ይህ «ነፃነት» የግድ ይሆናል። ይህን ነፃነት የሚገድብ ሁሉ የሰው ልጅ ህልውና እና ፍላጎት ጠላት ይሆናል። እንደ ፈለግኩኝ መምረጥ መወሰን ስችል ነው ፍላጎቴን ማምዋላት የምችል ሰው መሆን የምችለው።

ከላይ እንደጠቀስኩት ባሁኑ ዘመን እነዚህ አይነት አስተሳሰቦች ሳናውቀው ሰርቀው አዕምሮአችን ውስጥ ገብተዋል። ዓለም ዙርያ ታውቀዋል። እንደ «ነፃነት» እና «ምርጫ» አይነቶቹ ቃላቶት ምን ማለት እንደሆኑ ብዙሃኑ ተውሕዶታል። እነዚህን ቃላቶችን ስንጠቀም ሁሉም ሰው ትርጉማቸውን «ያውቃል»።

አንዳንድ የክርስቲያን ቡድኖች በተለይም የፕሮቴስታንት ንቅናቄ ይህን አስተሳሰብ አቀናብረው አንጸራጭተውታል። እነዚህ የክርስቲያን ቡድኖች ከአሜሪካ እና አውሮፓ ተነስተው የ«ዘመናዊ» ክርስትና ዓለም ዙርያ አስፋፍተዋል። በጥናታዊ ክርስትና ያልነበሩ አስተያየቶች እና ጥያቂዎችን አስፋፍተው የተለመዱ እንዲሆኑ አደረጉ። ለምሳሌ የህፃንነት ጥምቀት ጥያቄ፤ ዛሬ ሰው ለምን በህፃንነቱ ክርስትና ይነሳል የሚለው ጥያቄ ይጠየቃል። ልበ በሉ ለመጀመርያዎቹ ፕሮቴስታንቶች ይህ ጥያቄ አልነበረም ግን የተከሉት ዘር ወደዚህ አመራ። ጥያቄ የሆነው ምክነያት የህጻንነት ጥምቀት «ነፃነትን» ይሽራል ተብሎ ነው! «ህፃኑ እንዴት አለ «ምርጫው» ይጠመቃል። ለመጠመቅ ላለመጠመቅ ነፃነቱ ሊኖረው አይገባምን?» ይባላል! በዘመናዊነቱ ዕቅድ ምርጫን ወይም የራስ ውሳኔን የሚገድብ ነገር አደገኛ ነው ተብሎ ይሰየማል። በየ «ኤቫንጀሊካል» ፖሮቴስታንት ቤተ ክርስቲያን ክርስቲያን መሆን የ«ነፃ ምርጫ» ጉዳይ ነው ይባላል። «የውሳኔው ስዓት» ሰዎች ክርስቶርስን ጠቀብያለሁ የሚሉበት ጊዜ በዘመናችን ተለምዷል።

ቤተ ክርስቲያን ስለ ገብረ ግብ የምታስተምረውም በዘመናዊነት ዕቅዱ ምክንያት በጥርጣሬ ላይ ወድቋል። ዘመናዊ ሰዎች እራሳቸውን «ካቶሊክ»፤ «ኦርቶዶክስ»፤ «ጴንጤቆስጣል»፤ «ፕሬስቢቴሪያን» ወዘተ ብሎ ቢሰይምም ቤተ ክርስቲያናቸው ስለ ግብረ ገብ ወይም ስነ መግባር ኑሮዋቸው መወሰን የለባትም ብለው ያምናሉ። እራሳቸውን «ካቶሊክ» ብለው ቢሰይሙም በካቶሊክ እምነት አይገዙም። ለምሳሌ አብዛኞች አሜሪካዊ ካቶሊኮች ቤተ ክርስቲያናቸው በተለይ ስለ ቤተሰብ እና ጋብቻ የምታስተምረውን ሌሎችም ትምህርቶቿንም ይክዳሉ! ከቤተ ክርስቲያናቸው እምነቶች የሚፈልጉትን ይመርጣሉ የግል ምርጫዬ ነው የነፃነት ጉዳይ ነው ብለው ያምናሉ። ግን ይህ «የግል ሃይማኖታቸውን» በራሳቸው «ነፃነት» እና ምርጫ «ካቶሊክ» ብለው ይሰይማሉ። በዚህ አስተሳሰብ «ካቶሊክ»፤ «ኦርቶዶክስ»፤ «ሉቴራን» ወዘተ ሰው የሚመርጠው ማንነት ነው እንጂ ማንነትን እና ህይወትን የሚወስን ጉባኤ አይደለም።

የዘመናዊነት ዕቅዱ የጥንታዊ ክርስትና ጠላት ነው።

በጥንታዊ አመለካከት የሰው ልጅ ለራሱ ብቸኛ ወሳኝ አይደለም። በዚህ ዓለም የምንገኘው ከራሳችን ሌላ በሆነው በእግዚአብሔር ፈቃድ ነው። ህይወታችን የእግዚአብሔር ስጦታ ነው። የህይወታችን አላማው፤ ትርጉሙ እና አቅጣጫው በእግዚአብሔር የተሰጠ ነው። የሰው ልጅ የሚያደርገን እና ዋጋ የሚሰጠን በእግዚአብሔር ምሳሌ መፈጠራችን ነው እንጂ ውሳኔዎቻችን ወይም የመወሰን አቅም ስላለን አይደለም። የሁላችንም ታናሾች አቅም የሌላቸው፤ ችሎታ የሌላቸው፤ ከአልጋ ተኝተው መንቀሳቀስ የማይችሉት፤ ወዘተ በኢግዚአብሔር ምሳሌ በመፈጠራቸው ክብር እና ዋጋ አላቸው።

ማንነታችን በህይወት ምርጫዎቻችን እና ውሳኔዎቻችን ብቻ አይደለም የሚወሰነው። ህይወታችን እና ማንነታችን ከእግዚአብሔር ያገኘነው ስጦታ ነው። እሰረታዊ ማንነታችን በተወሰነ ደረጃ የተመደበ ነው። ይህ ማንነት በክርስትና ህይወት የሚገለጽ እና የሚለወት ነው እንጂ አንድ ሰው በግሉ የሚፈጥረው አይደለም። ምርጫዎቻችን እና ውሳኔዎቻችን ሚና ይጫወታሉ ግን ከእግዚአብሔር ውሳኔ ስር ነው ሚናቸው። ዞሮ ዞሮ የእግዚአብሔር ፍጥረቶች ነን ስለዚህ ውሳኔዎቻችን ትርጉም ያላቸው ከሱ ጋር ባለን ግንኝነት ነው።

በዘመናዊነት ዕቅዱ እና በጥንታዊው አመለካከት ያለው ጦርነት በደምብ የሚታየው በተለይም በምዕራቡ ዓለም በስነ ህይወት (biology) እና የሰው ግንኝነት ዙርያ። ጥንታዊ የክርስትና አመለካከት ስነ ህይወታችን፤ ማለትም ሰውነትና አካላችን ወዘተ፤ የተሰጠን ነው። እንደ አባት፤ እናት፤ ወንድም፤ እህት ወዘተ ያለን ከሰው ጋር ያለን ግንኙነቶችም የተሰጡን ናቸው። ጾታ ምርጫ አይደለም። ቤተሰብም የደም ተፈጥሮ ነው እንጂ በምርጫ አይደለም። በባለና ሚስት መካከል ወይም ሌሎች ወሰባዊ ግንኙነቶች የተሰጠ አላማ አላቸው እንጂ የግል ፍላጎት ማምዋያ አይደሉም። ግን የዘመናዊነት ዕቅዱ «ነፃነትን» እና «ምርጫን» እንዲሰፍኑ ማድረግ ነው የሚፈልገው። የሰው ተፈጥሮ እውነት ነው ግን ወሳኝ አይደለም ይላል (ለዚህም ነው ዛሬ አንዳንዶች ጾታቸውን የሚመርጡት)። ቤተሰብ የምርጫ ጉዳይ ነው የምንፈልገውን ግንኙነቶችን እንመርጣለን። የደም ትሥሥር የተሰጠ መሆኑ እና በደም ትሥሥር ምክንያት ሃላፊነቶች መኖራቸው በምዕራባዊ ሀገራት መንግስታት እና ፍርድ ቤቶች እየተካደ ነው። ለዚህም ነው በእግዚአብሔር ፈቃድ የተጸነሰው ከ«ነፃነት» ጋር መወዳደር ያልቻለው እና ጽንስን ማስወረድ የሰፈነው።

ዛሬ «እውነት» የሚባለው ነገር አሻሚ ሆኗል። የኔ እውነት ካንተ እውነት ይለያል ግን ሁለቱም እውነቶች ናቸው ይባላል። እውነትም የምርጫ ጉዳይ ሆኗል። አንድ የሆነ እውነት የለም ይባላል። በዚህ ዘመናዊ ዓለም እውነት አንድ ነው ማለት እንደ ጭቆና ነው የሚቆጠረው። የጥንታዊ ክርስትና አስተያየት ከነ ህግ እና እምነቱ የማይመች እና መጥፋት ያለበት ሆኖ ነው የሚታየው። ዘመናዊው ዕቅድ «ለምን እግዚአብሔርንም በራሳችን ምርጫ በራሳችን ምናብ አንፈጥረውም አንወስነውም» ይለናል።

መጨረሻው

ከመጀመርያ ጀምሮ ለ400 ዓመታት በላይ የዘመናዊው ዕቅድ የጥንታዊ ክርስትናን ተዋግቶ ከሰው ልጅ ከህዝብ ማስወገድ ነው አላማው። የዘመናዊነት ጥያቄ «እግዚአብሔር እንዴት ነው የፈጠረን» ሳይሆን «ዓለምን ምን እንዲመስል ነው የምንፈልገው?» ነው። የዓለም ሁኔታ የሰው ምርጫ ጉዳይ ነው ብሎ ነው የሚያምነው። ስለዚህ ነው የዘመናዊ ዕቅዱ ልጅ የሆነው የፕሮቴስታንት ስነ መለኮት (ቴኦሎጂ) የክርስትናን ትውፊት እና ወግን ከመመርመር እና ማጥናት ይልቅ ወንጌልን በራሱ ምናብ መተርጎም የፈለገው።

ማርቲን ሉተር «በመጻሐፍት ብቻ» ('Sola Scriptura') የሚባለው የፕሮቴስታንት አቋምን ሲፈጥር ማንም ሰው መጸሀፍ ቅዱስን አንብቦ አለ እርዳታ አለ ቤተ ክርስቲያን አለ ሃዋርያት በትክክሉ ይተረጉመዋል ለማለት ነው። ማርቲን ሉተር የሮሜ ጳጳስን ወይም የሮሜ ቤተ ክርስቲያን ችግሮችን በመቃወም ስበብ ክርስትናን በራሱ ውሳኔ እና ምርጫ መቅረስ ፈለገ። በዝህ መልክ ይህ «በመጸሐፍት ብቻ» የሚባለው አስተያየት በመጀመርያ ቤተ ክርስቲያንን እና ትውፊቷን ለመለየት የተጠቀሙበት መሳርያ ነበር። ግን ባልታሰበበት (ግን ሊታሰብበት) መልክ ይህ አስተሳሰብ ሰዎች መጸሀፍ ቅዱስን በግላቸው እንተርጉም እያሉ ከአንድ ከሉተር ከሁለት የሉተር ተፎካካሪ ዝዊንግሊ ወደ 30 ሺ አተረጓገም (ዛሬ ዓለም ዙርያ ያሉት የፕሮቴስታንት ቡድኖች ቁጥር) ደርሷል።

ግን «የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም» እና ዛሬም የጥንታዊ ክርስትና አለች የዘመናዊነቱን ዕቅድን የስጋው መውግያ ናት። የዘመኑ ሚዲያ ቫቲካንን አትኩረው ያያሉ ገና ለገና መሰረቷን ሸርሽራ ትጨርሳለች እጇን ሙሉ በሙሉ ለዘመናዊነቱን ዕቅድ ትሰጣለች ብለው። በሩስያ ከሞት የተነሳችው ኦርቶዶክስ እምነት ደግሞ ከፖለቲካዊ «አምባገነን» ጋር የተያያዘ እና «ኋላ ቀር» ብለው ይሰይሙታል! ጦርነት ነው!

ዛሬ የጥንታዊ ክርስትና መንገድ ከባድ ነው። አታላዩ መንገድ ዝም ብሎ ጸረ የዘመናዊው አብዮት መሆን ነው። ከዘመናዊነት ዕቅዱ እኩል እንደ አማራጭ መወዳደር። ግን ክርስትና እንዳዚህ ካረገች እጇን ለዘመናዊው ዕቅድ ሰጠች ማለት ነው። ሌላ «ምርጫ» ሆነች ማለት ነው። ግን ጥንታዊ ክርስትና የምርቻዎቻን ውጤቶች አይደለንም ህይወቶቻችን በእግዚአብሔር ጸጋ እና ስጦታ ነው የሚወሰነው ሁሉም ነገር ከእግዚአብሔር አኳያ ነው የምንመለከተው ነው። የቤተ ክርስቲያን ተውፊት የለ የተሰጠ ነገር ነው እንጂ ምርጫ አይደለም። ስለዚህ እራሱን እንደ አንድ አማራጭ አያቀርብም ሊያቀርብም አይችልም።

የጥንትዊ ክርስትና መንፈስ ስለ በራስ መምርጥ ሳይሆን እራስን ባዶ ማድረግ። ማለት የራስን ፍላጎት ትቶ የእግዚአብሔርን ፍላጎት ማወቅ እና ማክበር። እጅን ለእግዚአብሔር ሙሉ በሙሉ መስጠት። ጥንታዊ ክርስትና ህይወት የተሰጠ እንደሆነ ይረዳል። የተፈጥሮ የደም ትሥሥር፤ ቤተ ሰብ እና ዝምድና ተጭባጭ ናቸው እና ህይወታችን ላይ ተገቢ ሚና ይጫወታሉ ሃላፊነት ይሰጡናል። ዓለም እንደዚህ ትሁን እንደዛ ትሁን ብለን ማለም ከለት ለለት ከባድ የሆነ የክርስትና ኑሮአችን እንድንርቅ እንድንሰንፍ ፈተና ነው። የዓለም ድሃ ይረዳ እያልኩኝ እየተፈላሰፍኩኝ ድሃ ባለንጀራዬን ዞር ብዬ አላየውም! ግን የዘመናዊነት ዕቅድ እንደዚህ ነው የሚያስበው። ዓለምን አሻሽላለው ይላል። ከ«ነፃነት» በደምብ ማትረፍ የሚችሉትን ባለ ሃብቶች እና በትምሐርት ጎበዞች በደምብ አትርፈዋል። ግን ይህ የዘመናዊነት ዕቅድ ፉከራ ባዶ ነው ህይወታችንን በራሳችን መወሰን ስለማንችል። እራሳችንን ከእውነታችን በላይ ታላቅ አርገን ብናስብም መጨረሻ ላይ ሞት ምርጫችንን አያከብርም! ምናልባትም የዛሬው ታላቅ አሽሙር የዘመናዊነት ዕቅዱ የ«መሞት መብት»ን ማራመዱ ነው አለመሞት ምርጫ እንደሆነ!

Wednesday, 23 May 2018

የቤተ ክርስቲያንናችን ዕርቅ ጉዳይ፤ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት

ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ስለ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንናችን የዕርቅ ሂደት ከዚህ ጽፏል።

http://www.danielkibret.com/2018/05/blog-post_18.html

ብዙ የምጨምርበት የለም። የሩኢሲያው ቅዱስ ሴራፊም እንደ መከሩን «የሰላምን መንፈስ ተቀበሉና ዙርያችሁ ያሉ ሺዎች ይድናሉ»። የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ተቀብልን በኛ እንዲሰራ ከፈቀድን፤ ማለት ከጸለይን፤ ካማተብን፤ ይቅር ካልን፤ አንደበታችን ጥሩ ከሆነ፤ ኢነዚህን ሁሉ «ትናንሽ ነገሮችን ካደረግን ሌሎችን እንቀይራለን። ስለዚህ የኛ የምዕመናን ድርሻ ከመፍረድ እና ማማት እራሳችንን ቆጥበን እነዚህን ነገሮችን ማድረግ ነው ማበረታታትም ነው። ኢግዚአብሔር ሌላውን ይችላል።

http://asfawdarguemeshal.blogspot.ca/2016/11/2009.html

Thursday, 17 May 2018

የ«አማራ ብሄርተኝነት» ትውፊታዊ ነውን?

የ«አማራ ብሄርተኝነት» ትውፊታዊ ነው ወይስ እንደ ሌሎች የጎሳ ብሄርተኞቻችን (ኤርትራ፤ ትግራይ፤ ኦሮሞ፤ ወዘተ) በፈረንጅ በምዕራባዊ በ«ተራማጅ» በማርክሲስት ፍልስፍና የተመሰረተ ነው?

እርግጥ ብዙ አይነት የአማራ ብሄርተኝነቶች አሉ፤ ለፖለቲካ ስልት ወይንም «ታክቲክ» ብቻ የሆነ አለ፤ በስመ አማራ ላለፉት 27/40 ዓመታት ለተበደሉት ፍትሕ መጠየቅያ የሆነ አለ፤ ዛሬ አማሮች ላይ የሚደርስባቸውን በደል ለመታገል የሆነ አለ፤ በሀገር ደረጃ በፖለቲካ ድርድር ለአማራ ህዝብ የሚቆም አለ፤ በሃሰት የታማው የአማራ ህዝብን ታሪክ እውነቱ እንዲታወቅ የሚንቀሳቀስ አለ፤ የአማራ ህዝብ ክብርና ማንነትን ለመመለስ የሚታገለው አለ፤ ወዘተ። ዛሬ እነዚህ ሁሉ አይነት እንቅስቃሴዎች በስመ አማራ ብሄርተኝነት ይጠራሉ።

ዞሮ ዞሮ ዋናው ነጥብ ይህ የፖለቲካና መሃበራዊ ንቅናቄ እራሱን የ«አማራ ብሄርተኝነት» ብሎ መሰየሙ ነው። አላማው ምንም ቢሆን በዚህ «አማራ ብሄርተኝነት» የሚለው ስም መጠራት ይፈልጋል። በዚህ ስም መጠራቱ ምን ይነግረናል? በተለይ በትውፊትና በተቃራኒው ምዕራባዊ ተራማጅነት ያለው ግንኙነቱ ምንድነው?

ደስ የሚለው ነገር የሁሉም አይነት የአማራ ብሄርተኝነት ምልክቶች ትውፊታዊ ናቸው። ለምሳሌ ዓፄ ቴዎድሮስ አንዱ ዋና የአማራ ብሄርተኝነት ንቅናቄ ምልክት ናቸው። የአማራ ታሪክን በትክክሉ ማስተዋወቅና መናገር ሌላው የአማራ ብሄርተኝነት አላማና ምልክት ነው። ግን ዓፄ ቴዎድሮስ እራሳቸውን ወይንም ሀገራቸውን ወይንም አገዛዛቸውን የአማራ ወይንም «አማራ ብሄርተኛ» ብለው ይሰይሙ ይሆን? የአማራ ታሪክ የምንለው በታሪክ ሰሪዎቹ እና በዘጋቢዎች ዘንድ የአማራ ታሪክ ይባል ነበር? የአማራ ብሄርተኝነትን ያንጸባርቅ ነበር?

ለነዚህ ሁለቱም ጥያቄዎች መልሱ «አይደለም» እንደሆነ ነው የማውቀው። ዓፄ ቴዎድሮስ እንደ ሁሉም ንጉሶቻችን በስመ ኢትዮጵያዊነት ነበር እራሳቸውን የሚመለከቱት። ታሪካችም እንዲሁ ኢትዮጵያዊነት ላይ ነው የሚያቶክረው አማራነትን አይደለም። ይህ ማለት «አማራ» የሚባል ህዝብ የለም አልነበረም ማለት አይደለም! መኖሩ በታሪክ በተለያየ ቦታ መመዝገቡ ይታወቃል። ግን እስከማውቀው ማንም በስመ አማራ አልተንቅሳቀስም። ትውፊታችንና ታሪካችን እንደዚህ ከሆነ እንዴት እራሱን «አማራ ብሄርተኝነት» ብሎ የሰየመ ንቅናቄ ትውፊታዊ ነው ማለት ይቻላል?

በሁለተኛ (ወይንም አንደኛ!) ደረጃ ጠቅላላ የጎሳ ብሄርተኝነት የሚባለው ነገር የምዕራባዊ የፖለቲካ ፍልፍና እንደሆነ ይታወሳል። በትውፊታዊ ፖለቲካ «ሀገር» ነው ያለው፤ «ጎሳ» የለም። ይህ አባባሌ ብዙ ነገሮች ስለሚያከማች ሁሉንም በዚህ ጽሁፍ አልጠቅስም ግን በጠቅላላ የ«ጎሳ ብሄርተኝነት» የዘመናዊ የምዕራባዊ ጽንሰ ሐሳብ ነው።

የምፈራው ነገር ይህ አዲሱ የአማራ ብሄርተኝነት ልክ እንደ በፊቶቹ የኤርትራ፤ የትግራይ፤ የኦሮሞ፤ ወዘተ ብሄርተኝነቶች በብሶት እና በበአድ ምዕራባዊ ርዕዮተ ዓለም የተመሰረተ ኢተውፊታዊ ንቅናቄ ይሆናል ብሄ ነው። የኤርትራ እና የትግራይ ብሄርተኝነት በመሰረቱ ጸረ ትውፊት ናቸው። በቀላሉ ምሳሌ ለህዝባቸው መሰረት የሆነው ሃይማኖትና ባህልን የሚጠላ ርዕዮተ ዓለም ነው እነዚህ ብሄርተኝነቶች የተመሰረቱት። የኦሮሞ ብሄርተኝነት እንደዚህም ቢሆን ቢያንስ ወደ ኦሮሞ ትውፊት ለመመልከትና እንደ ገዳ አይነቱን ተውፊት ማክበር ሞክሯል። ሆኖም መሰረቱ የማርሲስት የጨቋኝ ተጨቋኝ የጎሳ ብሄርተኝነት አስተሳሰብ ነው። የአማራ ብሄርተኝነትም እንደዚህ እንዳይሆን መጠንቀቅ ይኖርበታል። ግን እራሱን «አማራ» ብሎ ከሰየመ እዚህ ወጥመድ ውስጥ ቀድሞ ገብቷል ማለት ይመስለኛል።

ጎበዝ፤ ጠንካራ፤ ሀገር ወዳድ ምሁራን በተለይ ወጣቶች የአማራ ብሄርተኝነት ያቀፉ አሉ። ምክንያቱ ለሁላችንም ሊገባን ይገባል፤ ለብሶት መልስ ነው። የአስራት ወልደየስ ፖለቲካ የብሶት ሳይሆን እራሳቸው እንዳሉት የግዴታ ነበር። የዛሬው ግን የ27/40 ዓመታት ያመጣው ብሶት ነው። ብሶቱ በህወሓት ላይ ብቻ ሳይሆን በሁሉም፤ በድሮ ምሁራን፤ ልሂቃን፤ ተቃዋሚ፤ ወዘተ ነው። እኔ እንደሚመስለኝ የተማሪው ንቅናቄ ወደ እንደ ማርክሲዝም አይነቱ ምዕራባዊ ፍልስፍና እና ርዕዮተ ዓለም በብሶት ምክንያት እንደገባው የዛሬው ትውልድ በብሶቶች ምክንያት እንደ ቀድሞው ተማሪ ንቅናቄ ወደ ኢ-ትውፊታዊ (ምን አልባት ጸረ ኢትዮጵያዊ) የማይሆን አስተሳሰብ እየገባ ነው። ስለ ተውፊቱ ስላልተማረ በምዕራባዊ የቀለም ትምሕርት የሚሰግድ ህብረተሰብ ውስጥ ስላደገ ሳያውቀው ብዙ ኢ-ትውፊታዊ አስተሳሰቦች አድረውበታል።

ስለዚህ ጉዳዩን ወደ ኋላ ወደ መሰረታችን ተመልሰን አመለካከታችንን በሙሉ ከ«ሀ» ብንገመግም ጥሩ ይመስለኛል። ከዛ በኋላ ነው የአማራ ብሄርተኝነት ትውፊታዊ ነው ወይ የሚለውን ጥያቄ በትክክሉ ልንመልሰው የምንችል የሚመስለኝ።


Friday, 20 April 2018

ህወሓትን የሚያመልኩ «አማሮች»

ታማኝ በየነ በቅርቡ ባቀረበው «የቁልቁለት ዘመን» የሚባለው ትረካ የተለያዩ የብአዴንና ሌሎች ህወሓት ያልሆኑ የኢህአዴግ መሪዎች ለህወሓትና ለትግራይ ህዝብ ልክ የሌለሽ ሙገሳ ስያደርጉ አየን። ከሙገሳው ይሁን ግን አልፎ ተርፎ እነዚህ ሰዎች ሌላውን በተለይ የአማራ ህብረተሰብን ሲተቹ ሲሰድቡ ይታያል። እንደዚህ አይነት አመለካከት ለ27 ዓመታት ያየነው የሰማነው የኖርነው ቢሆንም እንዲዝህ አይነቱን ክስተት ደግሞ አይቶ መመርመሩ አስፈላጊ ይመስለኛል። ከነዚህ ሰዎች ባሕሪና አስተያየት የምንማረው ነገሮች ለፍትሕ እና ነፃነት ትግላችን ይጠቅማናልና።

ከትረካው ላይ እነ ካሳ ተክለብርሃን፤ አዲሱ ለገሰ፤ ዓለምነህ መኮነን፤ በረከት ስመዖን፤ ተፈራ ዋልዋ፤ ኃይለማርያም ደሳለኝ፤ ታምራት ላይኔ፤ ወዘተ በዚህ አይነት አስተያየት ሲናገሩ ይታያል። ንግግራቸውም አነጋገራቸውም ስሜታዊ ነው። ለህወሓት ድርጅት እና ፍልስፍና ያላቸው ስሜት እና ተገዥነት በደምብ ይታይባቸዋል። እነዚህ አይነት ሰዎች ቁጥራቸው ትንሽ መሆኑ ቢታወቅም ህብረተሰባችንን ለመጉዳት ትልቅ ሚና ተጫውተዋል ይጫወታሉም። እንደዚህ አይነት ሰዎች ወይም እንደዚህ አይነት አስተሳሰብ እንዴት ሊመጣ ይችላል የሚለውን ጥያቄ ካሰላሰልን እና መመለስ ከቻልን  ላሁንም ለወደፊቱም እንደዚህ አይነት ሰዎች እንዳይፈጠሩ ለማድረግ ይረዳናል። ብዚህ መንገድ ትግላችን ይረዳናል።

ዛሬ የነዚህ አይነት ሰዎች እና አስተሳሰብ አመጣትን በዚህ መንገድ እንየው… ለማቅለል ያህል
የንጉሳዊ መንግስቶቻችን የአገዛዝ መርህ በመደብ የተወሰነ ነው እንበል። እርግጥ እንደ አውሮፓ «ፍዩዳሊዝም» አልነበርም ከአንድ መደብ ወደ ሌላ ምሻገገር ይቻላል ግን ዞሮ ዞሮ ንጉሱ መሳፍንቱ ያሉበት የገዥ መደብ አለ ሌሎቹ ደግሞ ተገዥ መደም ውስጥ ናቸው። በዚህ ሥርዓት ሁሉም የራሱ ተልዕኮ አለው ውድድርና ግጭቶች በቀጥታ ከስልጣን እና መሬት ወይም ንብረት የተያያዙ ናቸው።

«ዘመናዊ» መንግስቶቻችን ደርግና ኢህአዴግ ግን በጨቋኝ እና ተጨቋኝ ርዕዮተ ዓለም የተመሰረተ መርህ ነው የሚመሩት። ሁልጊዜ ጨቋኝ ተጨቋኝ፤ በዳይ ተበዳይ፤ ተራማጅ አድሃሪ ወይን ኋላ ቀር፤ አብዮተኛ ትምክተኛ፤ ሰፊ ጠባብ፤ ወዘተ መኖር አለበት። በአንድ በኩል በጥላቻ የተመሰረተ ርዕዮተ ዓለምና ፍልስፍና ነው ማለት ይቻላል።

በዚህ አይነቱ ርዕዮተ ዓለም የሚመራ መንግስት ሁለት አይነት ሰዎችን ይገኛሉ። አንዱ አይነት «ቢሮክራት» ብለን እንሰይመው። እነዚህ ሰዎች በተለያየ ምክንያቶች ለርዕዮተ ዓለሙን «እውነት አማኞች» ሆነዋል። እውነት ነው ብለው አምነውበታል። ምሳሌ ልስጣችሁ። በ1966 አንድ አዲስ አበባ የተወለደ ባለ መጀመርያ ዲግሪ ወጣት ለስራ ወደ ክፍለ ሀገር ይላካል። የሚያየው ድህነት እና ረሃብ እጅግ አሳዝኖት ለ«እኩልነት» መታገል ይጀምራል። ደርግ ስልጣን ሲይዝ ዳኛ ሆኖ ይሾማል «አድሃሪዎችን» ያስቀጣል ንብረታቸውን ያስወስዳል። ለአድሃሪዎቹ ጥላቻ የለውም ብዙም አይተቻቸውም አይሰድባቸውም። ግን ርዕዮተ ዓለሙን በደምን ስላመነበት ጥያቄ ሳይጠይቅ እራሱን ሳይመረምር የፖለቲካ ተልዕኮውን ይፈጽማል። ይህ አይነቱን «ቢሮክራት» እንበለው።

ሌላው አይነቱን «ብሶተኛ» ብለን እንበለው። እንደገና በምሳሌ ልግለጸው። የልጁ አስተዳደግ ምቹ አልነበረም። ትንሽ ሆኖ መንገድ ላይምን ትምሕርትቤትም ከሌሎች ልጆች በላይ ጥቃትና ስድም ይደርስበታል። እያደገ ሲሄድ ቤተሰቡ ከሰፈሩ የተገለሉ መሆናቸውን መረዳት ይጀምራል። የተገለሉበትን ምክንያት በትትክል ማወቅ አልቻለም ግን የተለያዩ ፍንጮችን ሲያቀናብር ድሮ አባቱ ባደረጉት ድርጊት ምክንያት መሆኑን ይረዳል። ሆኖም ልጁ እንደተሰደበ እንደተገለለ ያድጋል። ኢህአፓ አባላት ሲመለምል ጓደኝነት እና ማህበርነት ፍለጋ ልጁ ይሳተፋል። ጫካ ገብቶ በህውሓቶች ይማረካል። ጥሩ ወገናቸውን ያሳዩታል ሃላፊነት እና የቤተሰባዊ ስሜት ያሳዩታል። ኖሮት የማያውቀው ጓደኞች እና ዘመዶች ይሆኑለታል በዚህ ምክንያት ይወዳቸዋል። አብሮ ታግሎ አዲስ አበባ ይገባል። የህወሓት ስኬታማነት ይበልጥ እንዲወዳቸው እንዲወድሳቸው ያደርጋል። ፍልስፍናቸውም እውነት መሆኑን ያረጋግጥለታል። ትግሬ ባይሆንም ቀንደኛ የህወሓት ተቀናቃኝ ይሆናል። ሀወሓትን የማይወዱትን እንደ ጠላት ያያቸዋል። በተለይም የተወለደበት እና ያደገበት ህብረተሰብ ላይ ያለው ጥላቻ ይብሳል። አሁን ካለው ወርቃማ ሁብረተሰብ ጋር ሲያወዳድራቸው …

ስለዚህ «ቢሮክራት» እና «ብሶተኛ»። እርግጠኛ ነኝ ሁላችንም እንደዚህ አይነት ሰዎች እናውቃለን። (እራሳችንም እንደዚህ እንሆን ይሆናል።) ግን ምናልባት ይህ ሰው ክፉ ነው ወይም የተሳሳተ ነው ብለን ላዩን ወይም ሰሙን ብቻ አይተን ትተነዋል። ምንድነው እንደዚህ ያደረገው ብለን ሳንመረምር አልፈነዋል። ግን ለፍርድ ባንቸኩል እና ሰውየውን ተቆርቁረን ብንመለከተው ህይወቱ ለመን ወደዚህ እንዳመራ ለማየት እንችላለን።

ምን ዋጋ አለው እንደዚህ አይነቶችን ሰዎች ማስወገድ ነው ትሉኝ ይሆናል። ግን እንደዚህ ቀላል ቢሆን ኖሮ ድሮ አስወግደናቸው ሰላም አግኝተን ነበር! ያልቻልንበት ምክንያት ህብረተሰባችን እንዲዝህ አይነት ሰዎችን በርካታ አድርጎ ስለሚወልድ ነው። «ቢሮክራቱ» የሚፈጠረው 1) በህብረተሰባችን የእኩልነት፤ ስብዕና፤ ፍትሕ እጦት ስላለ 2) ትምሕርታችን ባህል እና ትውፊትን ንቆ የ«ዘመናዊ» ትምሕርት ላይ ስለሚያተኩር ተማሪዎቻችን መሰረታቸውን ማንነታቸውን ትተው ወደ የማያቁት ጸንፈኛ እና በአድ የሆነ ፍልስፍና ይገባሉ። ስለዚህ ህብረተሰባችን ያልፈታውን ችግር አይተን ችግሩን በራሳችን ትውፊት ከመፍታት በማይሆነው ጸንፈኛ እና በአዳዊ መንገድ መፍታት እንሞክራለን።

ምሳሌ ልስጣችሁ… በኃይለ ሥላሴ መንግስት የነበረው ዋና ቅራኔ የመሬት ጉዳይ ነው። ባላባቶች ሌሎችም በተለያየ አግባብ ያልሆነ መንገድ መሬት አግኝተው ወይም ወርሰው ጭሰኛውን ያሰቃያሉ። የተውፊታችን ምሶሶ የሆኑት ሃይማኖቶቻችን መስረቅ፤ መዝረፍ፤ መጭቆን፤ ወዘተ ልክ አይደለም ይላሉ። ሀብታም ድሃን መርዳት ግድ ነው ይላሉ። ይህን ተከትሎ የመሬት ሽግሽግ እንዲደረግ በርካታ ሰዎች እየሞከሩ ነበር። ቢያንስ ጪሰኞች የመሬቶቻቸው ባለቤት እንዲሆኑ ባላባቶች ሌላውን መሬቶቻቸውን ይዘው እንዲጠብቁ። ግን ይህን ትውፊታዊ አካሄድ ማድረግ ባለመቻላችን ጉዳዩን በማርክሲስት አብዮታዊ መንገድ እንፍታው ለሚሉት መንገድ ከፈትን። ከዚህ ጽሁፍ «ቢሮክራት» የምላቸው ከዚህ ጎራ ናቸው።

ይህ አይነቱ ክስተት እንዳይከሰት ህብረተሰብም ግለሰብም ማድረግ ያለብን በተቻለ ቁጥር ቢያንስ በግል ኑሮዋችን ሰላም እና ፍትሕ እንዲኖር የተጎዱትን ድኾችን መርዳት ነው። ከህብረተሰባችን መሰረታዊ ክፍፍሎችና ችግሮች እንዳይኖሩ ማድረግ ነው። በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ልጆቻችን ባህል እና ትውፊታቸውን ተምረው እንዲያድጉ በበአድ አስተሳሰብ እንዳይዋዥቁ ማድረግ ነው።

ወደ «ብሶተኛው» ስንመጣ ደግሞ… ከ«ቢሮክራቱ» ይብሳል ጉዳቱም ኃይለኛ ነው። ቢሮክራቱ በመረጃ ሀሳቡን ሊቀይር ይችላል ግን ብሶተኛው በጥላቻ ምክንያት እውነትን ማየት አይፈልግም ጭለማ ውስጥ ነው። ስለዚህ እንደ ማህበረሰብም እንደ ግለሰብም እንደዚህ አይነት ሰዎች እንዳይፈጠሩ ከተፈጠሩም ከማህበረሰቡ እንደ «ሽፍታ» ከሚፈነግሉ አቅርብን መያዝ ነው። «ንቀት» የሚባለውን ነገር በማጥፋት ነው።

ብሶተኛ እንዳይኖር ማህበረሰብ ውስጥ ክፍፍል እንዳይኖር ማድረግ አለብን። እስቲ የኃይለ ሥላሴ መንግስት ሲወርድ የሰማነውን «ሌባ፤ ሌባ» የሚለውን መፈክር እናስታውስ። ማን ነው በስሜት እና ንዴት እንደዚህ የጮኸው። ይንቁኛል ብሎ የሚያምን። በመደቤ በማንነቴ ወደ ታች አድርገው ያዩኛል ብሎ የሚያምን። ወዘተ።

የታማኝን ትረካ ሳይ ይሄ ነው በአዕምሮኤ የታየኝ። አንዳንድ «ቢሮክራቶች» ግን አብዛኛው «ብሶተኛ»። ያሳዝናሉ። የራስን ህዝብ የራሽን ማንነት መጥላት እና መናቅ ከባድ ነገር ነው። ለብሶተናውም ከባድ ነው ለማህበረሰቡም ከባድ ነው። እግዚአብሔር ብሶተኛ የማንወልድ ማህበረሰብ ያድርግን። ልጆቻችንን በአግባቡ በባህልና ተውፊታቸው እንድናሳድግ ይርዳን። ብሶት ያላቸውንም ብስታቸውን አይተን፤ ገብቶን፤ ሳንፈርድባቸው ከማህበረሰቡ ሳይሸፍቱ እንድንረዳቸው ይርዳን።

Monday, 16 April 2018

ለራሳችን ክብር የሌለን አልቃሾችና ለማኞች ነንን?

አንድ አመት በፊት ስለ ኢህአዴግ ማልቀስ አቁመን ወደ ተግባር እንግባ የሚል ጽሁፍ ጽፌ ነበር። ይቅርታ አድርጉልኝና ያንን መልዕክት በጠንከር ያለ ቋንቋ ልድገመው።

ላለፉት 27 ዓመታት እኛ «ተቃዋሚዎች» «የኢትዮጵያ ወዳጆች» «የኢትዮጵያ ብሄርተኞች» «ፍትህና ዴሞክራሲ ፈላጊዎች» ስለ ኢህአዴግ ወይንም ስለ ህወሓት እንደ ህፃኖች ስናለቅስ ስናማርር ለፈረንጆች አቤቱታ ስናቀርብ ቆይተናል። ውርደት አይደለምን? አናፍርም እንዴ? በአንድ ጎን ህወሓት የሀገሪቷን 6% ነው የሚወክለው እንላለን። ህዝቡ አይፈልጋቸውም እንላለን። ብሌላ ጎን ደግሞ በጠመንጃቸው፤ ማሰቃያቸው፤ ይሉኝታቢስ እነታቸው፤ ጉብዝናቸው፤ ብልጠታቸው፤ የውጭ ድጋፋቸው ወዘተ ምክንያት ይገዙናል እንላለን። አይገርምም 6% የሆነው ይህን ሁል መቻሉ 90% የሆነው እንደ ጅል መመልከቱ?

እስቲ አንዴና ለመጨረሻ እንወስን፤ ህወሓት 6% ወይንም ከነ አደርባዮቻቸው 10% በቻ ድጋፍ ነው ያላቸው? መልሳቸን «አይደለም» ከዛ በላይ በርከት ያለ ድጋፍ አላቸው ከሆነ ኢህአዴግ ብዙ ደጋፊ አለው ማለት ነው። ስለዚህ ኢህአዴግ የጥቂቶች መንግስት ነው ዴሞክራሲ የለም ወዘተ ማለት አንችልም። ግን በዚ አብዛኞቻችን የምንስማማ አይመስለኝም። በተለይ ሌት ከቀን ስለ ህወሓት ለምናለቅሰው በዚህ አንስማማም።

ስለዚ ለጥያቄው መልሳችን «አዎን ኢህአዴግ የትንሽ ሰው ድጋፍ ምናልባትም የትግሬ ብቻ ድጋፍ ነው አለው» ነው የሚሆነው። እንደዚህ ከሆነ ግን ለ27 ዓመታት በጥቂት ሰዎች ነው የምንገዛው ወደ ማለት ያስኬደናል! 10%ው 90%ውን ለ27 ዓመታት ገዝቷል! እንዴት ነው 10%ው 90%ውን የሚገዛው ካልን ደግሞ መልሱ አንድ ብቻ ነው። እጅግ አናሳ (minority) የሆነ ቡድን ብዙሃንን (majority) መግዛት የሚችለው በአናሳው ጥንካሬ ሳይሆን በብዙሃኑ ፈቃደኝነት ነው። ልድገመው፤ በብዙሃኑ ፈቃደኝነት ነው። ስለ 40%ው 60%ውን መግዛት አይደለም የምናወራው። ስለ 30%ው 70%ውን መግዛት አይደለም የምናወራው። 10%ው 90%ውን ገዝቷል። ያውም በመደብ በርዕዮት ዓለም ሳይሆን በጎሳ። የጎሳ አገዛዝ ብዙሃኑን ይበልጥ ሊያስነሳው ይገባ ነበር። አለመነሳቱ እንደ ፈቃድ ይቆጠር።

ስለዚህ ህወሓት ኢትዮጵያን ገዝታለች ካልን የማን ጥፋት ነው፤ የ10% የሆኑት «ገዥዎች» ወይንም 90% የሆኑት «ተገዦች»? ምን ጥያቄ አለው፤ ሃላፊነቱም መፍትሄውም ሙሉ በሙሉ የ90% የሆነው ብዙሃኑ ነው። ግን እኛ «ተቃዋሚዎች» ሙሉ በሙሉ አቅማችንን፤ ግዜያችንን፤ ወሬአችንንና ገንዘባችንን በአሳፋሪ መልኩ ስለ10% የሆኑት ስናለቅስ ነው የምናጠፋው። የችግሩ ምንጭና የመፍትሄው ምንጭ የሆነው ብዙሃን የሆንነው «ተቃዋሚ ጎራ» ላይ በሚገባው ከመስራት ፋንታ ችግሩ ባልሆነው ለመፍትሄ ዝግጁ ባልሆነው ላይ «እንሰራለን»። ያሳዝናል፤ ያሳፍራል፤ ለምን ለ27 ዓመታት ለውጥ እንዳልመጣ በትክክሉ ያስረዳል።

እሺ አሁን እውነታው ከተገለጸልን እንዴት ነው ወደ ፊት መራመድ ያለብን የሚለውን እንዳስስ። የመጀመርያው የችግር መፍትሄ ችግር እንዳለ ማወቅና ማመን ነው። ህወሓት ስልጣን የያዘው አልፎ ተርፎ ህወሓት/ሻእብያ ኢትዮጵያን ከደርግ በኋላ የተቆጣጠሩት በኛ ጥፋት ነው። የሌላ የማንም ጥፋት አይደለም። በመጀመርያ ደረጃ እንደ ኮሙኒዝም አይነቱ የማይሆን የምዕራብ ፍልስፍና አስተማርናቸው። ከዛ ቀጥሎ እኛ አንዴ አድሃሪ፤ ኢህአፓ፤ ምኤሶን፤ ኢዲዩ፤ ደርግ ወዘተ ስንባባል ስንገዳደል ነው እነዚህ በመሃል ገብተው ባዶ የሆነውን የምንግስትን ጎራ የተቆጣጠሩት። ከዛም በኋላ ህወሓት ሀገራችንን አጥበቃ የተቆጣጠረው እኛ «ተቃዋሚዎች» ከነ ፓርቲዎቻችን፤ ድርጅቶቻችን፤ ጋዜጦቻችን፤ ሚዲያዎቻችን ተባብረን መንቀሳቀስ ስላልቻልን ነው።

የህወሓት ጉብዝና፤ ብልጠት፤ «ወርቃማነት» አይደለም የግዛት ዘመናቸውን ለ27 ዓመታት እንዲቀጥል ያደረገው። አባቶቻችን ትውፊታችን በራሳችን እንድንተማመን በሚገባው እንድንኮራ ነው ያሳደጉን። እንደ አንድ ኩሩ ኢትዮጵያዊ 10% ድጋፍ ያለው ህወሓት በጉብዝና ሌሎቻችንን ያሽከረክራል ማለት በፍፁም አልችልም። አልችልም ብቻ ሳይሆን እውነትም አይደለም።

በተዘዋዋሪ ሰዎቻችን የህወሓትን አገዛዝ «አፓርታይድ» (apartheid) ሲሉ እጅግ አፍራለው። የደቡብ አፍሪካ ነጮች በ ትምሕርት፤ እውቀት፤ የአገዛዝ ስልት ወዘተ ከጥቁሮቹ እጅግ የተለዩ ነበሩ። በደቡብ አፍሪካ ነጮችና ጥቁሮች ያለው አይነት ልዩነት ነው በህወሓት ደጋፊዎችና በሌሎቻን ያለው ብሎ የሚያምን አለ? አለ? ይቅርጣ አድሩጉልኝ ግን እንደዚህ የሚያምን በኢትዮጵያዊነቱ የማያምን የማይኮራ የበታችነት ስሜት ያለው ነው። ተሳስቻለሁ?

ወደ ዋናው ነጥብ ልመለስና ምን ያህል ያለንበት ሁኔታ እራሳችን የፈጠርነው እንደሆነ ለማየት እስቲ በመንግስት አስተዳደራችን ማን ማን እንዳለ እንመልከት። በየ መንግስት መስርያቤት ከቁልፍ ቦታዎች በቀር በጣም አብዛኛው የስራ ቦታ በትግሬ ያልሆኑ ነው የተቆጣጠረው። አስቡት 6% ሆነው በየቦታ መሆን አይችሉም። በርካታ ትግሬዎች ደግሞ መንግስት ከመስራት ንግድ ዓለሙን ይፈልጉታል። ስለዚህ መንግስታችን በአብዛኛው በሌሎቻችን ነው የሚስተዳደረው። ጦር ሰራዊቱም ከመሪዎቹ በቀር በኦሮሞ፤ አማራና ደቡብ ነው የተሞላው። አዛዡ ትግሬ ቢሆንም መሳርያው ከሌላው እጅ ነው! ይህ ሆኖ በምን ተአምር ነው በህወሓት ደጋፊዎች ወይም «ትግሬዎች» ነው የተገዛነው የሚባለው?!

ይህን ሁሉ የምለው እኛ 90% የሆንነው ብዙሃኑ ነው ኢህአዴግ መንግስት ሆነው ለ27 ዓመታት እንዲቆዩ ያደረግነው። እኛ «ተቃዋሚዎች» የራሳችንን ጎራ ማስተካከል ስላልቻልን ነው። እንኳን መተባበር ጭራሽ በደምብን መነጋገር ስላልቻልን ነው። የፖለቲካ ብስለት ስለሌለን ነው። እንደ ልሂቃን ባለፉት 50 ዓመታት እርስ በርስ ተገዳድለን ሀገሪቷን አቢዮት በአቢዮት አድርገን ፈራርሰን ገና ስላዳንን ነው።

ለዚህ አባባሌ መልስ ሊኖራችሁ ይሆናል። የኢህአዴግ ጭቆና ነው «ተቃዋሚ» ጎራውን ያደከመው ትሉ ይሆናል። እረ። ኢህአዴግ ነው ዲያስፖራው ድርስ መጥቶ ተቃዋሚው እርስ በርስ እንዲጣላ ያደረገው?! ተአምርተኞች ናቸው! በነፃነትና ምንም እግዳ በሌለባቸው ሀገሮች ተቃዋሚው ላለፉት 27 ዓመት በሚገባን ደረጃ መደራጀት አልቻልንም ማለት ይቻላል። ተለይም ተቃዋሚው የ90% ህብረተሰቡ ድጋፍ አለው ካልን የተቃዋሚው ውጤት ከዜሮ በታች ነው ማለት ማጋነን አይደለም። ዛሬ ከ27 ዓመት በኋላ የተቃዋሚው ሁኔታ ጭራሽ ብሶበት ነው የሚገኘው። ምናልባት ከ ኢሳት፤ ግንቦት 7፤ አሁን ደግሞ ቄሮ በቀር ትንሽም ሚና መጫወት የሚችል ስብስብ ወይንም ድርጅት የለም። ቄሮ ተሽሎ ቢገኝም የነዚህም ድርጅቶች አቅም እጅግ ትንሽ ነው። አልፎ ተርፎ ስለ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የውስጥ መረጃ ያላችሁ የኢህአዴግ ሚን ሳይሆን የተቃዋሚዎች ሚና ነው በእርስ በርስ አለመስማማታቸው በርካታውንአስተዋጾ ያደረገው።

እና ይህ የተቃሚው ጎራ በተለይ የተቃዋሚ ልሂቃኑ ድክመት ነው ኢህአዴግን ለ27 ዓመት በስልጣን ያዋለው ማለት ይቻላል። እንደዚህ ከሆነ ለውጥ የምንፈልገው ገንዘባችንን፤ ንግግራችንን፤ ጊዜያችንን፤ ጠቅላላ አቅማችንን በህወሓት ላይ በማልቀስ ነው ማዋል ያለብን ወይንም የራሳችንን ጎራ በማስተካከልና በማጠንከር ነው? ጥያቄ የለውም፤ ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ጀምሮ ስለኢህአዴግ በማልቀስ ያጠፋነውን ግማሽ ጊዜ እኛ ላይ በመስራት አውለን ቢሆን ኖሮ እስካሁን ጠንክረን ለውጥ አምጥተን ነበር።

እሺ፤ አቅማችንን በመገንባት እና እራሳችንን በማጠንከር ላይ ማጥፋት አለብን ስል ምን ማለት ነው። መደራጀት አለብን። አንዳንዴ እኛ ኢትዮጵያዊያን ተቃዎሚዎች ምን እያስበን እንደሆነ ግራ ይገባኛል። በሌሎች በአምባገነን መንግስት የሚመሩ ሀገሮች «ተቃዋሚ» የሚባለው ጎራ ድርጅት ወይንም ድርጅቶች፤ ገንዘብ፤ አቅም፤ ሚዲያ ወዘተ አለው። በዓመት በሚሊዮኖች የሚቆጠር በጀት ያላቸው ማለት ነው። እኛ ግን ከዚህ አንጻር ምንም የለንም። ስለተከፋፈልን ብቻ አይደልም። «አንድ ጎራ ነን አንድ አቋም ዓለን» የምንለውም አልተደራጀንም። እርስ በርስ እንፋጃለን። መነጋገርም ያቅተናል። ይህን ለማስተካከል ወይይት ያስፈልጋል። አንድ ሁለት ስብሰባ ሳይሆን ለወራት ለዓመታት የሚዘልቁ ተከታታይና ውጤታማ ውይይቶች። እንደዚህ ከባድ ስራ ነው የመደራጀት ሂደት። የግለሰብም የቡድንም አቅም መገንበት (capacity building) ያስፈልገናል። በተለይ በታላቅ እንቅፋት የሆነን ቅራኔ መፍታት (conflict resolution) ድክመታችን ላይ ብዙ መስራት አለብን። የፖለቲካ ስልታችንን ማዳበር አለብን። ብዙ ስራ ነው። ብዙ ብቻ ሳይሆን ለለውጥ ቅድመ ሁኔታ የሆነ ስራ ነው።

አይ ይህን ከባድ ስራ ከምንሰራ ስለ ህወሓት ማልቀስ ይሻለናል። ስለ ህወሓት ክፉነት በቂ ከዘፈንን ህዝቡ ተነሳስቶ መንግስትን ይገለብጣል ትሉ ይሆናል። የዚህ አይነት አመለካከት ምን ለበለው? በመጀመርያ ለ27 ዓመታት ያልሰራ አስተሳሰብ ነው። መቼም አንድ ነገር ደጋግመህ አድርገሀው ካልሰራ መቀጠሉ ሞኝነት ነው። ሁለተኛ፤ የኢትዮጵያ ህዝብ የህወሓትን ክፋት በቂ አያውቀውም ማለታችን ነው?! እንደዚህ ካልን ደግሞ ህዝቡ ወይ ደደብ ነው ወይንም የህወሓት ከፋት እስከዚህም ነው ማለት ነው! ግን እንደዚህ የምናስብ አይመስለኝም። ህዝባችን ስለ ሀውሓት አገዛዝ ችግር ብበቂ ሁኔታ ይገበዋል ብቻ ሳይሆን ይኖረዋል። የሚያውቀውን ከምንደግምለት መፍትሄ ሀሳቦች ብንሰጠው ይመረጣል።

እዚህ ላይ ለመናዘዝ ያህል እኔም እንደዚሁ ስለኢህአዴግ የማማርር አልቃሽ እንደነበርኩኝ ልንገራችሁ። ከቅንጅት ምርጫ በፊት በየ ውጭ ሀገር መንግስታትና መሪዎች ቢሮ እየዞሩ «ወደ ምርጫችን ታዛቢ ላኩ» ከዛ «መንግስታችንን የሚቃወም መግለጫ ስጡ» ከዛ «መአቀብ አድርጉ» ከሚሉት አንዱ ነበርኩኝ። ግን የቅንጅት መፈራረስ እራሴን ጥያቄዎች እንድጠይቅ አደረገኝ። ችግራችን ኢህአዴግና የውጭ መንግስታት ሳይሆኑ እኛ ተቃዋሚዎች እንደሆንን ገባኝ። ኢህአዴግ በስልጣን ላይ የቆየው በብልጠቱም በውጭ መንግስታት ድጋፍም ሳይሆን በመጀመርያ ደረጃ በኛ በተቃዋሚዎች ድክመት ነው የሚለውን ድምዳሜ ላይ ደረስኩኝ።

የውጭ ሀገር መንግስታትም ኤንጂኦችም ግለሰቦችም ስለ ኢትዮጵያ ሁኔታ ላለመጠየቅ ላለማነጋገር ወሰንኩኝ። እራሳችንን የማንችል እንደ በታቾች እንደሚያዩን ተገነዘብኩኝ እነሱ ጋር መሄድ እንደ ውርደት መሆኑ ተሰማኝ። በተለያዩ ምክንያቶች የነዚህ ፍልጋት ከኢትዮጵያውያን ፍላጎት የሚጻረር እንደሆነ ተረዳሁኝ። እነዚህ ሁሉም ለጥቅም ይህን ወይንም ለርእዮተ ዓለም ኢትዮጵያ እነሱ እንደሚፈልጉት እንድትሆን ነው የሚፈልጉት። እራሳችንን እንዳንችል ነው የሚፈልጉት። በአዲሱ ቅኝ ግዛት እንዲቆጣጠሩን ነው የሚፈልጉት እራሳቸውን እንደ ኝጹሃን አድርገው ቢያቀርቡም። እነሱን በኢትዮጵያ ጎዳይ ውስጥ ማስገባት ማንነትን መሸጥና እዳ መፍጠር ነው። ለኢትዮጵያ ትክክለኛው መፍትሄ ከራሷ ህዝብ ነው የሚመጣው የሚለውን ድምዳሜ ላይ ደረስኩኝ ዞር ብዬ የውጭ ሀገር ሰው ስለ ኢትዮጵያ አላናግርም አልኩኝ።

ስለዚህ ስለህወሓት ማልቀስ ስለውጭ ሀገራትን መለመን አውቀዋለሁ እና ከንቱ ነው ብዬ ነው ያማምነው። ደግሞ ከላይ እንደጠቀስኩት የ27 ዓመት ልምዳችን እንዳማይሰራ አሳይቶናል! ከዚህ በላይ መረጃ አያስፈልገንም።

የዚህ ጽሁፍ አርስት «ክብር» የሚለውን ቃል ይጠቅሳል። ስለእውነት ያቀፈ ክብር ነው የማወራው እንጂ ስለ በባዶ ቤት መኮፈስ አይደለም። በባህላችን ክብር ትልቅ ነገር ነው። አንዱ የክብር ማሳያ እራስን ከሌሎች እኩል አድርጎ ማየትና የበታችነት ስሜት አለመኖር ነው። እኛ «ተቃዋሚዎች» 90% ህዝባችንን «ወክለን» ስለ 10% የሆነውን ህወሓት ማልቀስ ሀወሓቶች ከኛ የሚበልጡ ፍጡሮች ናቸው ማለት ነው። ለራሳችን ክብር ካለን እንደዚህ ማለት የለብንም። ውርደት ነው። በሁለተኛ ደረጃ የሀገራችንን ችግር እንዲፈቱልን የውጭ ሀገር ሰዎችን መለመንም እንደ ውርደት ማየት ይቻላል። አዎን እንደ ስልት ብቻ ልናየው እንችላለን ግን ለወደፊት አደገኛ ሊሆን ይችላል። የኛ በተለይ የምሁራኖቻችን ጭንቅላት ለ60 ዓመት በምዕራብ ዓለም ፍልስፍና እየተገዛ ነውና ካልተጠነቀቅን ሳናውቀው የአዲሱ የቅኝ ተገዢዎች (የአእምሮ ቅኝ ግዛት) ልንሆን እንችላለን። ስለዚህ ክብራችንን ጠብቀን የችግራችን ዋና ምክንያትን ማለት እራሳችንን እንዋጋ እናስተካክል

በራስን ማክበር ዙርያ ሌላ ነገር ልጠቅስ እወዳለሁ። ህወሓት፤ ሻእብያ፤ ኢህአዴግ ሁሉም እኛ «ኢትዮጵያዊ ነን» የምንለው የወለድናቸው ድርጅቶች ናቸው ማለት እውነትም ነው ክብራችንን የሚጠብቅ አባባል ነው። ከ«ውጭ» መጥተው ወረሩን ከሆነ እራሳችንን እንደ የውጭ ኃይል ተሻናፊ እንቆጥራለን። ግን በኛ ድክመት ከኛ ነው የመነጩት ማለት ችግሩን ይኛ አደረግነው ማለት ነው መፍሄውንም የኛ ሆነ ማለት ነው። ይህ የሚያጎለብት (empower) አስተሳሰብ ነው ወደ መፍትሄ የሚያደርሰን አስተሳሰብ ነው።

ጽሁፉ ረዘመ! ለማጠቃለል ህወሓት እኛ በስተታችን የፈጠርነው ልጅ ነው። ህወሓት በስልጣን የቆየው የሚቆየውም በኛ ፈቃድና ድክመት ነው እንጂ በራሱ የተለየ ብልጠትና «ጉብዝና» አይደለም። የኛ ድክመት ለ50 ዓመታት ልሂቃኖቻችን እርስ በርስ በመፋጀት እራሳቸውን ስላጠፉ ነው። በዚህ ድክመታችን አትኩረን ከሰራን እና እራሳችንን ካሸነፍን ለሀገራችን የሚበጅ የፖለቲካ ለውጥ በቀላሉ ይመጣል።