Saturday 14 November 2020

ድላችን ጦር ሜዳ ላይ እንዳይቀር

ህወሓት በጦር ሜዳ መሸነፉ የሚቀር አይመስለኝም። ጊዜ ይፈጅ ይሆናል፤ በርካታ ጉዳት ይደርስ ይሆናል፤ ግን የኢትዮጵያ መንግስት ህወሓትን ይቆጣጠረዋል። ትልቁ ጥያቄ ግን «ከዝያስ?» ነው። የፌደራል መንግስት ብቻውን በትግራይ ክልልም በመላው ኢትዮጵያም ሰላም ሊያሰፍን ይችላል ወይ?

የሚችል አይመስለኝም። የጠ/ሚ ዓቢይ አህመድ መንግስት ላለፉት ሁለት ዓመታት ከባድ የፖለቲካ ስራ ሰርቷል። መንግስቱ ብዙ ነገር ቢሳካለትም የቀሩት ችግሮች ብዙና ከባድ ናቸው። ሽብር፤ የዘር ጭቆና፤ ማፈናቀልና ግድያ ቀጥሏል። መንግስት እነዚህን ችግሮች እስካሁን ሊፈታ አልቻለም። (አንዳንዶች መንግስት እንኳን ሊፈታው የችግሩ አካል ነው ይባላል ግን ለኔ ይህ ስሜታዊነት ነው።)

መንግስት እነዚህን ችግሮች ለምን መፍታት አልቻልም ለሚለው ጥያቄ መልሴ ብቻውን ሊፈታው ከአቅሙ በላይ ነው ነው። መንግስት ችግሮቹን ለመፍታት የህዝብ ጠንካራ ስሜታዊ ሳይሆን ተግባራዊ ትብብር ያስፈልገዋል ግን ይህን እስካሁን በበቂ ደረጃ አላገኝም። 

የህዝብ ተሳትፎ አስፈላጊነትን ለመረዳት ያህል እስቲ የህወሓትን ትግል እንመልከት። የህወሓት አመራር፤ አባላት፤ የአባል አክስትና አጎት፤ አያት፤ ልጅ፤ ወዘተ ናቸው ለህወሓት የሚታገሉት!! ለዚህም ነው ስምንት ሚሊዮን ህዝብ ወክላለው የሚል ድርጅት ሀገር ሙሉን የገዛው እና ዛሬ የሀገር መንግስት ሊሞግት የቻለው። ሁላችንም የናውቀው ግን ለመናገር የሚያሳፍረን ነገር ነው። ሀውሓት ከጫካ እስከ መንግስት እስከ መቀለ ስደት በሄደበት ጉዞ ታላቅ የተቀናበረ የምሁራን፤ የሊሂቃን፤ የነጋዴና የህዝብ ድጋፍ ኖሮት ነው።

የጠ/ሚ ዓቢይ መንግስት ግን እንደዚህ አይነት የተቀነባበረ የተግባር ድጋፍ በበቂ ደረጃ የለውም። ላለፉት 50 ዓመታት ጣቅላላ የ«አንድነት» ፖለቲካ ጎራው እንደ ህወሓት ወይንም ሻቢያ ትልቅ የፖለቲካ «ማሺን» ኖሮት አያውቅም። ለዚህ ነው ህወሓት በቁጥር ትንሽ ሆኖ የአንድነት ጎራውን ለሰላሳ ዓመት በቀላሉ የተቆጣጠረው።

የአንድነት ፖለቲካ ጎራው ከዚህ ግድ መማር አለበት። የሀገር ህልውና ጉዳይ ነው፤ ካሁን ወድያ በመንግስት ብቻ መመካት አይቻልም። እንደ ህወሓት እና ሻቢያ በሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የተሟላ የፖለቲካ ማሺን ያስፈልገዋል። ሁላችንም ከነ አክስት አጎቶቻችን በተናጠል ሳይሆን በተቀነባበረ መልኩ ተሳትፈን አብረን መስራት አለብን። በዚህ መንገድ ለአንድነትና ለሰላም ፖለቲካ ከታገልን ስኬታማ እንሆናልን። እንኳን ትናንሽ ተቀናቃኞች እንደ ህወሓት የዓለም ግዙፍ ሀገራትንም መቋቋም እንችላለን። አለበለዛ ለመንግስት ብቻ ትተነው የራሳችን ተሳትፎ በተናጥል የወሬ ድጋፍ መስጠት ከሆነ እድላችን አነስተኛ ነው የሚሆነው።

No comments:

Post a Comment

ለሀሳብዎ አመሰግናለሁ!