Friday, 13 April 2018

ብቸኝነት

ወደ 10-15 ዓመታት ይሆነዋል የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ስለ የለት ኑሮዋቸው ስለ ማህበራዊ ኑሮዋቸው መለወጥ መገንዘብና ማዘን ከጀመሩ። «ሰዉ እንደ ድሮ አይደለም» ይላሉ። «ጊዜ የለም። ወላጆቼን ዘመዶቼን በወር አንዴም አላገኛቸውም።» «ጥዋት በ12 ሰዓት ወጥቼ ማታ በሁለት ነው ቤት የምገባው። ልጆቼን ከቅዳሜና እሁድ በቀር አላገኛቸውም።» «ጎረቤቶቼን አላውቃቸውም። ዛሬ ማንም ለጎረቤት ጋር አይተዋወቅም። ችግር ቢያጋጥመን ማን እንደሚደርስልን አናውቅም።» «ለእድር ማህበር ቤተ ክርስትያን ጊዜ የለንም። ማህበራዊ ኑሮ የለንም።» «እንደ ድሮ እህል ወዘተ ማዘጋጀት አልችልም የምገዛው ደግሞ ጥራቱ አይታመነም ከየት እንደሚመጣም አላውቅም።» «ዛሬ ሰዉ አይታመንም ለገንዘብ ብሎ ሰው ይሸጣል ራስ ወዳድ ነው።» ወዘተ። ሁላችሁም እነዚህን አባባሎችን ሰምተናቸዋል።

አዲስ አበበ ባለፉት ቅርብ ዓመታት በህዝብ የመብዛትና በኤኮኖሚው ፈጣን እድገት ምክንያት የ«ብልጽግና» ("development") የ«ዘመናዊነት» ("modernity") ችግሮችን ይታዩባታል። አንዱ ችግር በ«ያደገው» ወይም በ«የለጸገው» ዓለም ለረዥም ዓመታት የሚታየው የህብረተሰባዊ ችግር ነው። ብዙዎች ይህን ችግር የማኅበራዊ ኑሮን ማጣት ይሉታል። ግን ጠልቀን ካየነው በሌላ ቃል ልናጠቃልለው እንችላለን፤ «ብቸኝነት» (loneliness)። ይህ ለሰው ልጅ ኢተፈጥሮ የሆነው ብቸኝነት ኢትዮጵያንም ዓለምንም ለማጥፋት ከባድ ስራ እየሰራ ነው።

የበለጸገና ዘመናዊ ህብረተሰቦችና ሀገሮች የብቸኛ ርዕዮት ዓለም (individualism) የሰፈነባቸው ናቸው። ልክ የአዲስ አበባ ሰዎች እንደሚሉት እነዚህ ሀገር ሰው አይተዋወቅም ጊዜ የለውም ማህበራዊ ኑሮ የለውም ጓደኝነት የለም የሚደግፈውም የሚገድበውም ማህበረሰብ የለውም። እራሱ ይወስናል ለራሱ ይኖራል በራሱ ይተማመናል በሚዲያ ጫና በማስተዋወቂያ ካልሆነ ከማህበረሰቡ ምንም ሀሳብ ድጋፍ አያገኝም። እግዚአብሔርም የለውም ወይም እራሱ የፈጠረው የሰየመው በራሱ የሚወሰን አምላክ ነው ያለው።

በአዲስ አበባም አሁን ይህ ቀስ ብሎ እየገባ ነው። ልጅ ተወልዱ በሕፃንነቱ ወደ ሕፃናት ማቆያ ይላካል። እናትም አባትም መስራት አለባቸው ከዋጋ ግሽበት ጋር ለመወዳደር። ምናልባትም ለትንሽ ቤት ለማጠራቀም። ልጁ ጥዋትና ልተኛ ሲል ነው ወላጆቹን የሚያገኘው፤ ያውም ካገኛቸው። ቤተሰቡ ከዘመድም ከማንም ጋር አይገናኝም ጊዜ የለምና። ወደ አያቶቹ ለመሄድ የአንድ ሰዓት መንገድ ነው በታክሲ። የአክስቱ ቤት የሁለት ሰዓት መንገድ ነው። የጎረቤት ልጆችን በደምብ አያቃቸውም ከቅዳሜ እሁድ በቀር ከቤት አይወጣምና። ልጁ ከወላጅና እህት ወንድም በቀር ከሌሎች ተገሎ ነው የሚያድገው።

ልጁ ጎበዝ ተማሪ ነው ሁለተኛ ትምሕርት ቤት ጨርሶ ከአዲስ አበባ ሩቅ የሆነ ዩኒቨርሲቲ ይሄዳል። ትምሕርቱን አጠናቆ አሁንም ከአዲስ አበባ ሩቅ የሆነ ከተማ ለስራ ይበደባል። ከተወሰነ ዓመታት በኋላ እንደምንም አድርጎ ወደ አዲስ አበባ ተመልሶ ጥሩ የኪራይ ዋጋ በማግኘቱ ከወላጆቹ ሩቅ ቦታ ቤት ይከራያል።

ትዳር ይመሰርታል ልጅ ይወልዳል ልጁ አያቶቹን በሁለት ሶስት ወር አንዴ ነው የሚያገናቸው። እነዚህ አያቶች አሁን እያረጁ ነው የሚጦራቸው ያስፈልጋቸዋል። ልጆቻቸው ሁሉ ከነሱ ርቀው ነው የሚኖሩት። ጊዜም የላቸውም። ሰራተኛ ጠባቂም አይገኝም። እንደ ምዕራቡ ዓለም የአዛውንት ማረፍያ (ወይም «መጣያ») የለም። ምን ይደረግ! እነዚህ አያት የሆኑ አዛውንቶች የመጨረሻ እድሜአቸውን ከልጆቻቸው የልጅ ልጆቻቸውና ዘመዶቻቸው ተለይተው ሊኖሩ ነው። ይህ ነው የዘመኑ የብቸኝነት ኑሮ።

እግዚአብሔር ሲፈጥረን በቤተሰብ እንድንኖር ነው። ሚስት እንደ ቤተ ክርስትያን ባል እንደ ክርስቶስ አንድ ሆነው ልጆች ይወልዳሉ። የዚህ ቤተሰብ አንዱ ተልዕኮ መማርያ ማስተማርያ ነው። የእግዚአብሔርን ፍቅር እንድንማር እግዚአብሔር ለኛ ያለውን ፍፁም ፍቅርን እንድንማር ትዳርና ልጆች ሰጠን። ባለቤታችንን ልጆቻችንን በመውደድ ለነሱ መሥዋዕት በማድረግ ስለ እግዚአብሔር ፍቅር ትንሽ ልንረዳ እንችላለን። ከዛ አልፎ እንደሱ አይነት ፍቅር እንዲኖረን መሞከር እንችላለን እንደሱ መሆን መሞከር እንችላለን።

እንዲሁም እግዚአብሔር ሲፈጥረን ከህብረተሰብ ማህል አድርጎ ነው። ግለሰብ ብቻ ወይንም አባት እናት ልጆች ብቻ አድርጎ አልፈጠረንም። አንዱ የቤተ ክርስትያን ተልዕኮ ይህ ነው፤ ህብረት እንዲሆነን ነው። ይህ ህብረተሰብንም እንደ አባት እናት ልጆች የእግዚአብሔር ፍቅር መማርያ ይሆነናል። ስለዚህም ነው ከጥንት ጀምሮ ክርስትያኖች በደብር ዙርያ እንደ አንድ ህብረተሰብ የምንኖረው። ይህ አኗኗር ከአባቶቻችን የወረስነው ነው። በተዘዋዋሪ የገዳምም አኗኗር እንደዚሁ ነው።

ስለዚህ ቤተሰባዊና ማህበራዊ ኑሮ እግዚአብሔር የሰጠን አኗኗር ነው። አኗኗራችን በዚህ መልክ ካልሆነና የብቸኝነት ኑሮ ከያዝን ኢተፈጥሮ ነውና እንጎዳልን። እንጓደላለን። እንታመማለን። እናጣለን።

ግን «ብልጽግና» እና «ዘመናዊነት» ይህን ኢተፈጥሮአዊ የሆነውን የብቸኝነትን ኑሮ ነው የሚያመጡት የሚያራምዱት። ታድያ እንዴት አድርገን ነው ይህን መከላከልና መቀየር የምንችለው? ወደ መፍትሄ ከመሄድ መጀመርያ ችግሩን በትክክል መረዳት አለብን። ለዚህ ገና ነን። ለምን ቢባል ብልጽግና ዘመናዊነት ከ«ካፒታሊዝም» ጋር አብሮ ከብቸኝነት የሚመጡርን የጠቀስኩትን ጉዳትና ህምምን የሚያስታግስ ዕፅ ይሰጡናል። ገንዘብ ምቾት መዝናኛ ጨዋታ። ቤት ትልቅ ቤት መኪና ትልቅ መኪና ቴሌቪዥን ፊልም ዘፈን ስፖርት/ቴያትር  ዝነኞች አሉባልታ ወሬ ከፍልስፍና እስከ ሙዚቃ እስከ መዝናኛ የተለያዩ ጣዖቶች። እነዚህ ዕፆች የኢተፈጥሮ አኗኗራችንን ብቸኝነታችንን የማደንዘዝ ስራ ብቻ አይደለም የሚያደርጉት በመጀመርያ አኗኗራችን ኢተፈጥሮ እንደሆነ እንዳንረዳ ነው የሚያደርጉን። እንዳመመን እንዳናውቅ እያመመን ምክንያቱን እንዳናውቅ ነው የሚያረጉን።

ስለዚህ እስቲ ሁላችንም አኗኗራችንን እንድንመለከት እጋብዛለሁ። ባል ሚስት ልጆች ቢኖሩንም ብቸኞች አይደለንምን? የሚጦርን አይኖርምን? ልፋታችን ከንቱ አይሆንምን? እስቲ እራሳችንን እንጠይቅ።


Wednesday, 11 April 2018

የኢትዮጵያ ፖለቲካ እውነቶች (እንደሚመስለኝ)

እስቲ በነዚህ እውነታ የሚመስሉኝን ነጥቦች ዙርያ እነወያይ፤

1. ድሮ የነበረን የልሂቃን (elite) እራሱን አጠፋ። በኃይለ ሥላሴ መንግስት የነበረው ልሂቃን በአብዮት ምክንያት ተባረረ ተገደለ ተበታተነ። የኃይለ ሥላሴ ልጆች  የሆኑት አብዮቱን የመሩት አዲስ ልሂቃን በአብዮቱ ዘመን እርስ በርስ ተፋጅተው ተላለቁ። የተረፈው የደርግ ልሂቃን በደካማ ርዕዮት ዓለም እና አስተዳደር በተጨማሪ በዓለም ፖለቲካ ክስተቶች ምክንያት ፈራረሰ። ሻእብያ ህወሓትና ኦነግ ኢትዮጵያን ሲቆጣጠሯት የበፊቱ የልሂቃን በተለይ በሀገር ብሄርተኝነት (የጎሳ ብሄርተኝነት ተቃራኒ) የሚያምነው የልሂቃን ቡድን ጠፍቶ ነበር። ኢትዮጵያ የቀራት አቅም (capacity) ያለው ልሂቃን ጎሰኛ ወይም የጎሳ ብሄርተኛ ጎራው ብቻ ነበር። እስካሁን የሀገር ብሄርተኛ ልሂቃኑ ከነበረው ጉዳት በቂ አላገገመም።

2. የዚህ የልሂቃን ቡድን መፍረስ ያለፉት 27 ዓመት የኢትዮጵያ ፖለቲካ ሁኔታ ላይ ከምናስበው በላይ ከባድ አስተዋጾ አድርጓል። በበፊቱ ልሂቃን ቡድን መፍረስ ምክንያት ነው ለ27 አመት የ«ተቃዋሚ» ጎራው ደካማ ሆኖ የቀረው። ተቃዋሚዎች ነፃነት ባለበት በውጭ ሀገርም መደራጀት ያልቻሉበት ምክንያት ልሂቃኑ ስለፈረሰ በቂ የልምድ የሰው ኃይል የመደራጀት ልምድ የታሪቅ ምሶሶ እና የተመሳሰሉት የልሂቃን ውጤቶች ስለሌለው ነው። በዚህ ምክንያት ነው ቢያንስ 70% እስከ 90% ከብዙሃኑ ድጋፍ ማግኘት የሚገባው ተቃዋሚ ለ27 ዓመት ብዙ ማድረግ ያልቻለው። ለተቃዋሚ ድክመት ሌላው የሚሰጠው ምክንያት የኢህአዴግ ጫና ከዚህ አንጻር እንደ ዋና ምክንያት ሊቆጠር አይችልም።

3. በሀገር ውስጥም በሀገር ውችም ያለው የተቃዋሚ ድክመት ምክንያት  የፖለቲካ ለውጥ ከተቃዋሚ ፓርቲና ቡድኖች ሳይሆን ከብዙሃኑና ከኢህአዴግ ውስጥ ነው እየመጣ ያለው። (ተቃዋሚዎች ምንም ሚና አልተጫወቱም ለማለት ሳይሆን ከሚገባው አነስተኛ ሚና ነው የተጫወቱት አቅማቸው ውስን ስለሆነ።) እንደሚታየው የቅርብ ዓመታቱ የህዝብ ተቃውሞ የልሂቃን ማበረታጭያና ድጋፍ በጣም ያንሰዋል። ይህ የልሂቃን ወይም የመሪ እጥረት እጅግ አሳሳቢ ነው።

4. «አዲሱ ትውልድ መሪዎችን አልፎ ትቶ ሄዷል» ሲባል እውነት አይመስለኝም ነበር። ግን የዛሬው ትውልድ «ፖለቲካ ኮሬንቲ ነው» የሚባለውን አልፏል አባባሉንም ጭራሽ አያውቀውም። ኢህአዴግ ለ27 ዓመት ሳይቀየር የገዛበት አንዱ ምክንያት የበፊቱ ትውልድ ባለፉት አብዮቶች ተማሮ ተቃጥሎ በፖለቲካ ነክ ጉዳዮች በሚገባው መጠን ስላልተሳተፈ ነው። አሁን ግን ያ ዘመን አልፎ አዲሱ ተውልድ ለመሳተፍ ፍርሃት የለውም። አንዴ በእጽ በኳስ በገንዘብ ወዘተ ቢደነዝዝም ፖለቲካ ውስጥ እየተሳተፈ ነው። ነገር ግን አባት አያት አስተማሪ መሪ ታሪክ ትውፊት ይጎለዋል የበፊቱ ትውልድና ልሂቃን ስላላወረሰው።

5. ከውጭ ሀገር ሆኖ የፖለቲካ ወይም ማህበረሰባዊ ንቅናቄ ቡድን ድርጅት ፓርቲ አቋቁሞ መተጋል እስካሁን ውጤታማ አልሆነም ማለት ይቻላል። ወይንም አነስተኛ ውጤት ነው ያፈራው። ሰዎች እየሞከሩ አይደለም ማለት አይደለም። ከድሮ ጀምሮ እስካሁን እንደነ ኢሳት አይነት ትልቅ ሙከራዎችና ስኬቶች አሉ። ግን ከላይ እንደጠቀስኩት ኢህአዴግ የ10% ደጋፍ ድርጅት ነው ካልን እነዚህ ስኬቶች ከሚገባው እጅግ አነስተኛ ናቸው። ስለዚህ ይህ የውጭ ድርግታዊ ትግል አስፈላጊ ነው ቢባልም ዋናው ውጤታማው ትግል አይደለም።

6. ሀገር ውስጥ ያለ የይፋ ተቃውሞ በግለሰብ በቡድን በድርጅት በፓርቲም ይሁን ለ27 ዓመት በሁለት ምክንያቶች ደካማ ሆኖ ተገኝቷል። ከላይ እንደጠቀስኩት ዋናው ምክንያት የልሂቃን እጥረት ተቃዋሚዎች የመተባበር የአብሮ መስራት የቅራኔ መፍታት የመደራጀት ስልቶች እንዳይኖረን አድርጓል። ልድገመው፤ ይህ ነው ዋናው የተቃዋሚ ድክመት ምክንያት። የኢህአዴግ ጫና ሁለተኛ ደረጃ ምክንያት ነው። ሆኖም በተለይ ላለፉት 10 ዓመት ኢህአዴግ ተቃዋሚን (እንደ ቻይና) ጨርሶ ለማጥፋት ሲወስን ተቃዋሚዎች በጣም ተጎድተዋል። ዛሬ ግን ድርጅቶች ቢጎዱም በህዝብ ደረጃ ተቃውሞ ምን ያህል አዋጪ እንደሆነ ይታያል የዛሬውንም ለውጥ ያመጣው ይህ የብዙሃኑ ተቃውሞ ነው። ስለዚህ ብዙሃኑ በዚው ከቀጠለ የፖለቲካ ለውጡ እየተንከባለለ እንዲቀጥል ያደርጋል። ይህ ተቃውሞ ስኬታማ ሆኗል አሁንም ስኬታማ ይሆናል። ግን እንደገና ልበለው እየጨመረ ሲሄድ መሪ ያስፈልገዋል።

7. ያለፉት አራት ዓመታት የብዙሃኑ ተቃውሞ በዋነኝነት ስለ «የጎሳ አድሎ»  ነው። ህዝቡ በ«ትግሬ አድሎ» (በተጨማሪ በ«አደርባይ አድሎ») ተማረናል እያለ ነው ሰልፍ የሚወጣው። እርግጥ የፖለቲካ እስረኞች ይፈቱ ነፃነት ይኑር መሬታችን አይነጠቅ ወዘተ የሚሉ መፈክሮች ይሰማሉ ግን የህዝብ ጥያቄ ቢደረግ አድሎ በዋነኝነት እንደሚጠቀስ የታወቀ ነው። ይህ አስተሳሰብ ደግሞ ከድኻ እስከ ሀብታም ከወዝ አደር እስከ ነጋዴ ይሰማል።(በአንድ በኩል ከፍቅር ሰላምና ፍትሕ ይልቅ ትኩረቱ የትግሬ አድሎ ላይ መሆኑ ያሳዝናል ግን እውነቱ ይህ ነው።)

8. ከሌሎች ጉዳዮች ይልቅ የትግሬ አድሎ ህዝቡን ያማረረው ምክንያት የጎሳ አስተዳደር ያመጣው ወይም ያበራታታው የጎሰኝነት ስሜት ነው። በኃይለ ሥላሴ ወይም በደርግ ዘመን በመደብ በዝምድና በትውውቅ በፓርቲ አድሎ ነበር። ግን በዛን ጊዜ የህዝብ ተቃውሞ በመሬት ፍትሕ ነፃነት ተመስርቶ ነበር። ትኩረቱ አድሎ ላይ አልነበረም። ለምን ብትሉ በሰው ልጅ ተፈጥሮ የጎሳ አድሎ ከመደብ ወይም ከፓርቲ አድሎ ይበልጥ ያማርራል። በዚህ ምክናይት ነው ለረዥም ዓመታት እንደተጠበቀው ህወሓትን ስልጣን ላይ ያቆየው የጎሳ አስተዳደር አሁን ከስልጣን የሚያባርረው ወይም ለውጥን የሚያመጣ የሆነው። ይህንም በማወቅ ነው ኢህአዴግ ላለፉት አምስት ዓመት እራሱን ከጎሰኝነት ወደ «ኢትዮጵያዊነት» ማሸጋገር የሚሞክረው።

9. ከላይ እንደጠቀስኩት ዛሬ የምናየው የፖለቲካ ለውጦች ሁለት ዋና ምንጮች አላቸው፤ 1) የብዙሃኑ ተቃውሞ እና 2) ከኢህአዴግ ውስጥ የመጣ ለውጥ። ሁለቱም ወሳኝ ናቸው። እስካሁን በኢህአዴግ ውስጥ የሚመጣው ለውጥ በነ ለማ መገርሳ የሚመራው «የለማ ቡድን» ነው የሚካሄደው እንበል። የለማ ቡድን በኢህአዴግን ሰርጎ ገብቶ ከውስጥ ሆኖ ድርጅቱን የመቆጣጠርና የመቀየር ስራ ነው የያዘው። ቡድኑ ተቅላይ ሚኒስቴር ዶክተር አቢይን እስከማሾም ያበቃው ከኦህዴድ ብአዴን ድህዴን ምናልባትም ከህውሓት ደጋፊዎች ተሳታፊዎች ስላሉት ነው። ይህ ቡድን በርካታ የፖለቲካ ልምድ አቅምና እውቀት አለው ተፈትኗልም። ለዚህ ነው ከ«ተቃዋሚው» ጎራ ሲነጻጸር የለማ ቡደን ለለውጥ የሚጫወተው ሚና የሚበልጠው። ተቃዋሚው ከላይ በጠቀስኳቸው የታሪካዊ ምክንያቶች ደካማ ስለሆነ። የለማ ቡድን ለውጥ ማምጣት ከሚፈልጉት የልሂቃን ቡድኖች ብቸኛ አቅም ያለው ነው።  የቡድኑ ስራ ለሀገራችን በዋና አስፈላጊነት መያዝ አለበት።

10. ኢትዮጵያ የሚኖር ለፖለቲካ ለውት መታገል እፈልጋለሁ የሚል ተቀናቃኝ ልሂቅ ምሁር ወይንም ማንም ሰው አንድ ትልቅ ሚና መጫወት የሚችለው አንዱን የኢህአዴግ ፓርቲ ውስጥ በመግባት ነው። የለማ ቡድን ኢህአዴግን ለመቆጣጠር በርካታ የሰው ኃይል ያስፈልገዋል። ኦህዴድ ብአዴን ደህዴን ውስጥ ያሉትን የዚህ ሥርዓት ደጋፊዎች አክራሪዎችን በሰው ቁጥር ኃይል መብለጥ ማሸነፍ አለባቸው። እስካሁን የደረሱበት ደረጃ የደረሱት ቀስ በቀስ የነሱን ደጋፊዎችና ተሳታፊዎች ቁጥር እየጨመሩ እና ሌሎችን እያሳመኑ እየለወጡ ነው። አሁንም የለማ ቡደን ወደ ፊት ለመራመድ ከነሱ ሀሳብ የሚጋራ ስራ መስራት የሚችል የሰው ኃይል ያስፈልገዋል። የሰው ቁጥር ብቻ ሳይሆን ሀሳብ መስጠት ስራ ማስፈጸም በጠቅላላ አቅም የሚገነባ የሰው ኃይል ያስፈልገዋቸዋል። በዚህ መንገድ ነው የለማ ቡድን ኢህአዴግንም አልፎ ተርፎ ጦር ሥራዊቱንም ደህንነቱንም መቆጣጠር የሚችለው።

11. ለውጥ የሚመጣው በብዙሃኑ ተቃውሞና በለማ ቡድን የሚባለው የኢህአዴግ ተሃድሶዎች ነው ብለናል። የብዙሃኑ እንቅስቃሴ ከደከመ በህወሓት የሚገዙት የኢህአዴግ አክራሪዎች ከለማ ቡድን ያይላሉ። የለማ ቡድን ከደከማና የብዙሃኑ ትግል ከቀጠለ ወደ መሪ አልባ አብዮት እንሄዳለን። ሁለቱም የማንፈልጋቸው ውጤቶች ናቸው። ስለዚህ የብዙሃኑም ትግል የለማ ቡድንም መጠንከር አለባቸው ግን መናበብ መቀናበርም አለባቸው። ልድገመው፤ መናበብ መቀናበርም አለባቸው።

12. የኢትዮጵያ ልሂቃን ምሁራን ላለፉት 50 ዓመታት በትክክሉ ያልተደረገውን የፖለቲካ ውይይት ዛሬውኑ ጀምሮ ማድረግ አለባቸው። ላለፉት 50 ዓመታት ጊዜአችንን ወይ ኃይለ ሥላሴን ወይ ደርግን ወይ ኢህአዴግን ስንወነጅል እንጂ ሃሳቦች ስንገነባ አይደለም ያጠፋነው። የተቃዋሚው ድክመት ምክንያት አንዱ ይህ ነው። አሁንም እነዚህን ውይይቶች ማድረግ ግድ ነው። አሁን የፖለቲካ ውድድር ጊዜ ሳይሆን የሀገር መገንባት ጊዜ ነው። ሊዚህ ስራ ደግሞ ጣት መጠቆም መተቸት መጯጯህ ሳይሆን መወያየት መግባባት መተማመን መስማማት ነው የሚያስፈልገው። ለዚህ ውይይት ሀገር ውስጥም ውጭም ያለነው ትልቅ ሚና መጫወት እንችላለን።

13. የዛሬው የኢትዮጵያ ጦር ስራዊት በአብዛኛው ኦሮሞ አማራ እና ደቡብ ነው። የትግሬ ወታደር ቁጥር አናሳ ነው እየመነመነም ነው። መሪዎቹ ባብዛኛው የህወሓት ደጋፊዎች እንደሆኑ እናውቃለን ግን ጠመንጃው በሌላው እጅ ነው። በዚህ ምክንያት ጦር ስራዊቱ ለተወሰነ ጊዜ በላይ ሀገሩን በአስጨኳይ ጊዜ አዋጁ ተመስርቶ ሊያፍን አይችልም። ጦር ስራዊቱ ህዝቡን የሚጨቁንበት ጊዜና መጠን በጨመረ ቁጥር ውጥረቱ በጨመረ ቁጥር እርስ በርሱ ልዩነቶች እየበዙ ይሄዳሉ የጎሳ ክልልፍ ያድርበታል። የስራዊቱ መሪዎች ይህንን ያውቁጣል በትንሽ ጊዜ ሀገሪቷን ጠቆጣጥረን ወደ ጊቢዎቻችን መመለስ እንችላለን ብለው ነው ተስፋ የሚያደርጉት። ግን የዝቡ ተቃውሞ እንዳለፉት አራት ዓመት ከቀጠለ ጦር ስራዊቱ ግድ ወደ ኋላ መመለስ ይኖርበታል። ስለዚህ የጦር ስራዊቱ በመሪነት በህወሓት ደጋፊዎች መቆጣጠሩ አሁን ብዙ ትርጉም የለውም።

14. የማንም ሀገር ደህንነት ጎራ የኢትዮጵያም ተጨምሮ አስቸጋሪ ነው። ደህንነት በባህሪው ስነ መግባር ቢስ የሆነ በህብረተሰቡ ብሶት የላቸውን ሰዎች ወደሱ ይጋብዛል ይቀጥራል። የሁላችንም ኃጢአት ክምችት በደህንነት ድርጅቶች ይታያል። ግን ደህንነት አለ ፖለቲካ ጎራው እጅግ ደካማ ነው። አሁን የፖለቲካው ጎራ በነ ለማ ቡድን እየተቀየረ ነው። የህዝብ ትግልና የለማ ቡድን ስራ በዚሁ ከቀጠለ ጦር ሰራዊቱም ወደ ባራኩ ይመለሳል። ሁለቱ ጎራ ዎችን ከተቆጣጠርን ደህንነት አቅም የለውም እሱም ግድ ይለወጣል።

Friday, 6 April 2018

የህዝብ ብዛት

የኢትዮጵያ ህዝብ ቁጥር በዝቷል በተለያዩ መንገዶች የህዝብ ቁጥር እድገትን መቀነስ አለብን ሲባል እጅግ አዝናለሁ። በተለይ የኛ ምሁራን ልሂቃን እንደዚህ ሲሉ ስለ ሀገራችን ህልውና እሰጋለሁ። ሀገራችን ብዙ የፖለቲካ የኤኮኖሚ የመሐበረሰብ ችግሮች አሉትና ከነዚህ ሁሉ የሰው ቁትር መብዛት «ችግር» ከተባለም ትንሹ ነው። የሰው ቁጥር አለ አግባብ ጨምሯል ከተባለም ምክንያቱ የእርግዝና መከላከያ እጦት ሳይሆን ሌሎች የኤኮኖሚና የፖለቲካ ችግሮች ናቸው።

እስቲ አንዳንድ እውነታዎች እንመልከት፤

1. በገጠር ሴቶች በአማካይ ስድስት ልጆች ይወልዳሉ። በአዲስ አበባ በአማካይ ሁለት ልጆች ይወልዳሉ። ላለፉት 43 ዓመት የመንግስታችን የመሬት ፖሊሲ ህዝባችን ከገጥር እንዳይወጣ አድርጓል። ምክንያቱም አንድ ገበሬ ገጠርን ትቶ ወደ ከተማ መምጣት ከፈለገ መሬቱን መሸጥ ስለማይችል ከሞላ ጎደል ባዶ እጁን ወደ ከተመ መምጣት ስለሚሆንበት አያደርገውም። በዚህ ምክንያት 43 ዓመት በፊት የህዝባችን 85% የገጠር ነዋሪ ነበር አሁንም ወደ 80% የገጠር ነዋሪ ነው። የመሬት ፖሊሲው ባይኖር ይህ ቁጥር ዛሬ ምናልባት 60% ይሆን ነበር። እንደዚህ ቢሆን ኖር 80% ፋንታ 60% ነበር ስድስ ልግ የሚወልድው 20% ፋንታ 40% ሁለት ልግ ይወልዳል። በዚህ ምክንያት የጠቅላላ የህዝብ ቁጥር እድገት ይቀንስ ነበር።

2. ሀብት ምቾት ድሎት ከትመት (urbanization) በጠቅላላ ብልጽግና (development) በጨመረ ቁጥር የቤተሰብ መጠን ይቀንሳል። ይህ ንድፈ ሐሳብ (theory) ሳይሆን ያለፈው የ100 አመት የዓለም ታሪክ የመሰከረው እውነታ ነው። በሀገርም በህብረተሰብም ደረጃ ይህ እውነታ ይታያል። ሀብታም ሀገሮች ብዙ አይወልዱም ከነሱም የሚወልዱት ካልበለጸጉ ሀገሮች የመጡ መጤዎች ናቸው። ማንኛውም ሀገር አማካይ ሀብቱ በጨመረ ቁጥር የቤተሰብ መጠኑ ይቀንሳል። ስለዚህ በኢትዮጵያም «ብልጽግና» በጨመረ ቁጥር የሚወለደው ቁጥር ይቀንሳል። ስለዚህ አሁን እንቀንሰው ብሎ መርሯሯጥ አያስፈልግም።

3. የህዝብ ብዛት ሀብት ነው። የምዕራብ ሀገሮች ፍልሰትን (immigration) የሚጋብዙት ምክንያት የሰው እጥረት ስላላቸው ኤኮኖሚያቸው እየተጎዳ ስለሆነ ነው። የአዲስ አበባ ኤኮኖሚ የሚንርበት አንዱ ምክንያት ከገጠር ወደ ከተማ ያለው ፍልሰት ነው። የሰው ኃይልና የሸማች (consumer) ቁጥር በመጨመረ ቁጥር የኤኮኖሚ እንቅሳሴ ይጨምራል። በውጭ ግንኙነት አንጻርም ብዙ ህዝብ ያለው ሀገር በዓለም ላይ ያለው ኃይልና ሚና ይጨምራል። የኢትዮጵያ የዝብን ቁጥር በአባይ ግድብ ላይ ያለው ሚና ትንሽ አይደለም። ስለዚህ የህዝብ ብዛት እንደ እንቅፋት ብቻ መታየት የለበተም።

4. ኢትዮጵያ ገና ብዙ የህዝብ ቁጥር ማስተናገድ የምትችል ሀገር ናት። ካላት ለም መሬትና ሌሎች የተፈጥሮ ምንጮች አንጻር ምናልባት እስከ 200 ሚሊዮን ትችላለች። ጃፓን የኢትዮጵያ አራት እጥፍ ሰው በካሬ ኪሎሜትር አላት። ስለዚህ ኢትዮጵያ ትጨናነቃለች ብለን ልንሰጋ አይገባም።

ከዚህ አልፎ ተርፎ እንደ ኦርቶዶክስ ክርትያን የህዝብ ቁጥርን «መቆጣጠር» የሚባለው ነገር ያሳስበኛል። በተለይ የወሊድ መቆጣጠርን ማስፋፋት ያሳስበኛል። እንደዚህ አይነት ጉዳይ ውስጥ መግባት ትዕቢትን ነው የሚጋበዘው። እራሳችንን እንደ አምላክ እንድናይ ይፈትነናል። ከእግዚአብሔር የሰጠንን የተፈጥሮ ተልእኮ እንድንወጣ ይፈትነናል። ለዚህም ነው የሃይማኖት አባቶቻችን በሙሉ የቃወሙታ። ይህን መጠቀም ከሰው ተልእኮና ማንነት ይጋጫል ማጣት ነው ይላሉ። እርግጥ ካህናት በእረኝነት ሚናቸው በአንዳንድ አጋጣሚዎች የሃይማኖት ልጆቻቸውን እንዲጠቀሙ ሊፈቅዱ ይችላሉ ግን በጠቅላላ ከተቻለ አይመከርም። የስጋ ግንኙነትና መውለድ በተፈጥሮ የተገናኙ ናቸው ማለያየት ለሰው ልጅ ጎጂ ነውና።

ይህን እያወቅን የህዝብ ቁጥር እድገት እንዲቀንስ ተግባራዊ ስራዎች እናካሄድ ማለት ይከብደኛል። በተለይ በወሊድ መቆጣጠርያን በመጠቀም እንቀንስ ማለት ይከብደኛል። ለተጠቃሚው መንፈስ ጎጂ ነው ብዬ የማምነው ነገርን ማስፋፋት ህሊናዬ አይፈቅድልኝም። ሰዎች በገዛ ፍቃዳቸው ቢጠቀሙ ልፈርድባቸው አይገባም አልችልም «መብታቸው» ነው። ግን እንደ መንግስት መርህ ይህን ማስተዋወቅና ማስፋፋት ጎጂ ነው ብዬ ነው የማምነው። የቤተሰብ መጠንን ይቀንሳል ግን የመንፈሳዊ ጉዳቱ በምዕራቡ ዓለም የምናየው ኢትዮጵያ ውስጥ ማየት አልፈልግም። አዎ ዛሬ በሀገራችን በደምብ ተስፋፍቷል ግን መንግስት ከዚህ ጉዳይ እራሱን ቢያወጣ እወዳለሁ።

አልፎ ተርፎ ከላይ እንደጠቀስኩት በኔ እምነት የህዝብ ቁጥራችን አሳሳቢ ጉዳይም አይደለም። ክትመት ብልጽግና በጨመሩ ቁጥር የህዝብ ቁጥር እድገት ይቀንሳል። ቻይና ለ40 አመት ህዝቧ እንዳይወልዱ አድርጋ አሁን የህዝብ ቁጥራችን አንሶ አሳስቦናል ትላለች! እንማር!

ሀገራችን ገና «አልሞላችም»። ስለዚህ ትኩረታችንን ወደ ሌሎች የኤኮኖሚ የፖለቲካ የመሐበረሰብ ጉዳዮች ይሁን። እነዚህን ጉዳዮች በማሸነፍ የህዝብ ብዛት ጉዳያችንም በራሱ ይስተካከላል።

Thursday, 5 April 2018

የአሜሪካ መንግስት ከኢትዮጵያ መንግስት ይሻላል?

ባለፉት 18 ዓመታት በተለያዩ የአሜሪካ ጦርነቶች ምክንያት ወደ አንድ ሚሊዮን አካባቢ ሰዎች ሞተዋል። በርካታ ሀገሮች ተበጥብጠዋል መንግስታት ተገልብጠዋል ህብረተሰብ ተጎሳቅሏል። ሆኖም በርካታ ኢትዮጵያዊያን በተለይ ምሁራን ልሂቃን ሀገራችን «እንደ አሜሪካ በሆነች» እንላለን።

ይህ አባባላችን ምን ማለት እንደሆነ እንመርምር። በምርመራችን ሂደት ግረ መንገድ ስለ ራሳችን ስለ አቋማችን ማንነታችን አንዳንድ ቁም ነገሮች እንማራለን። ይህ ትምሕርት ለሰላምና ፍትሕ ያለንን ትግል አስፈላጊ ነው ያጠነክረዋልም።

እስቲ ስለ አንድ መጠነኛ የመርካቶ ነጋዴ የሆነ ኢትዮጵያዊ እናስብ። እድሜ ለህዝብ ብዛት ለኤኮኖሚ እድገት ንግዱም ገቢውም እያደገ ነው። ከመንግስትም ከሌላም ወገን እንቅፋቶች ቢያጋጥሙትም እንደ ጓዶቹ ብልህ ነውና ለንግዱ ለንብረቱ ብዙ ስጋት የለውም። ሆኖም አጋጣሚው ሲፈቅድ የተወሰነ ገንዘቡን ወደ ውጭ ሀገር ያወጣል። ኑሮው የተመቸ ቢሆንም ሀገሪቷ የሰላም የፍትሕ የፖለቲካ ችግሮች እንዳሏት ያቃል ያምናል። ግን ቱክረቱ የለት ኑሮው ላይ ነው። እንደማንኛውም ሰው ለኑሮ ይሯሯጣል ጥዋት እስከ ማታ ይሰራል። የሥርዓቱ ተበዳዮች የታሰሩትን የተገደሉትን መሬታቸውን የተቀማባቸውን አንዳንዴ ቢረዳም ብዙ ሊያያቸው አይፈልግም። እንዳሉ ቢያውቅም «ምን ይደረግ በተቻለ ቁጥር ከፖለቲካ መራቅ ነው» ብሎ ይኖራል።

እስቲ አንድ በአሜሪካ ያለ ኢትዮጵያዊ ስደተኛን እንመልከት። አሜሪካ መጥቶ ታግሎ በትምሕርቱ ገፍቶ ጥሩ ገቢና መአረግ ያለው ስራ ከያዘ ቆይቷል። የአሜሪካ «መካከለኛ መደብ» አባል ሆኗል። ባለቤቱም ትሰራለች ቤት መኪኖችም አላቸው ልጆቻቸው ይማራሉ በቅርብ ከፍተኛ ትምሕርትቤት ይገባሉ። ኑሮ ተመችቷቸዋል። አሜሪካ ተመችቷቸዋል። አዎ አንዳንዴ ስለ ዘረኝነት ስለወንጀል ይማረራሉ ግን እነዚህ ነገሮች ሕይወታቸውን አልነኩም። እንደ ፈረንጆች «አሜሪካ ታላቅ ሀገር ናት» ይላሉ። ስለ የኢራቅ ጦርነት ሰለቦች ወይም ሌሎች የአሜሪካ መንግስት ተጎጂዎች ብዙ አያስቡም፤ ምን አገባቸው። የለት ኑሮ በቂ ነው።

ግን ይህ «ኢትዮ-አሜሪካዊ» ኢትዮጵያ የሚኖረውን ነጋዴ ይተቸዋል። «እንዴት ዙርያህ ሰው እየተጭቆነ እየተገደለ እየተበደለ ዝም ዝም ብለህ ትኖራለህ» ይላል! እራሱ ግን  ለአሜሪካ መንግስት የሚሰጠው ቀረጥ ሀገሮችን ለመውረር ህዝብን ለመግደል ሲውል ዝም ይላል። እንቋን አሜሪካን መተቸት «አሜሪካ ጥሩ ሀገር ናት» ይላል። አልፎ ተርፎ «ኢትዮጵያ እንደ አሜሪካ ትሁን» ይላል!

ከዚህ ምንድነው መማር የምንችለው? በመጀመርያ የሰው ልጅ «ሲመቸው» ሲደላው ያለውን ችግር የሀገርም የግለሰብም የባለንጀራውም ችግር አይመለከትም። ለሰው ልጅ ድሎቱ ያሳውረዋል። ይህ እውነታ በፖለቲካ ደረጃ ሲንጸባረቅ ዓለም ዙርያ ይታያል። የቻይና መንግስት ኤኮኖሚውን በማፋጠን ህዝቡን ዝም አሰኛለሁ በሚል መርህ (policy) ነው ላለፉት 35 ዓመታት የሰራው። በኢትዮጵያም ይህ የፖለቲካ መርህ በ«ልማታዊ አስተዳደር» ስም ይራመዳል። ግን በጎሳ ፖለቲካ ሥርዓቱ ምክንያት ህዝቡን ዝም አላሰኘም። ከላይ እንደጠቀስኩት በአሜሪካም ድሎት ህዝቡን የመንግስት ግፎችን እንዳይመለከት ያደርጋል። ስለዚህ ለኢትዮጵያ ሰላምና ፍትሕ የምንፊልገው ይህን የሰው ባህሪ እና በፖለቲካ ያለውን ሚና አውቀን ነው መርህዎቻችን ስልቶቻችን መወቀር ያለብን።

ሁለተኛው ትምሕርት፤ የኢህአዴግ መንግስት ከሌሎች ያዓለም መንግስታት ተለይቶ «ሴጣን» አለመሆኑ ነው። አዎን መጥፎ መንግስት ነው ለ27 ዓመታት የፈጸመው ግፎች ተመዝግቧል። ሆኖም የኢህአዴግ ማንነትና አሰራር ውስብስብ ነው በቀላሉ «ሴጣን» ነው ማለት እውነቱን አለመገንዘብ ነው። ለዚህም ነው እንደ የ«ለማ ቡደን» አይነቱ ከኢህአዴግ ውስጥ ገብቶ ሰርቶ የደረሰበት ደረጃ የደረሰው። በጭፍን «ሴጣናዊ» መንግስት ቢሆን እንደዚህ አይነት ስራ ሊሰራበት አይችልም ነበር። ግን እንደማንኛውም መንግስት ስልጣን ዋናው አላማ ቢሆንም ለስልጣኑ ለፖለቲካ ህልውናው ያሉት ምርህዎች የሚያካሄደው ስራዎች ለሰላምና ፍትሕ ታጋዮች ከፍተት ፈጥሯል ይፈጥራልም። እነዚህን ክፍተቶች እንዳሉ ተገንዝበን መጠቀም አለብን።

ሶስተኛ ትምሕርት፤ ሀገራችን እንደ ማንም ሀገር «ትሁን» አንበል። አንድ፤ ማንም ፍፁም የለም። ከአሜሪካ እስከ ጀርመን እስከ ኮሪያ ሁሉም የራሳቸው ታሪክ የራሳቸው ችግሮች አሏቸው። ከሌሎች ሀገሮች ጠቃሚ ሃሳቦች መጠቀም አለብን ግን እነዚህ ሃሳቦችን ከኛ መሰረታዊ ማንነት ስር አድርገን ነው መጠቀም ያለብን። አለበለዛ እንደ ከላይ የጠቀስኩት ኢትዮ-አሜሪካዊ የገንዛቤ ድክመቶች ይኖርብናል።

በመጨረሻ መማር የሚገባን በፖለቲካ አስተያየት ትህትናና ለሰው መቆርቆር (empathy) ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆኑ ነው። ከላይ የጠቀስኳቸው ምሳሌዎችን ለመጠቀም… እራሳችንን በሰዎቹ በኩል አድርገን ማሰብ አለብን። ኢትዮጵያ ያለው ነጋደ ሀገር ውስጥ በመሆኑ ምንድነው የሚያጋጥመው የሚያስበው የሚያደርገው። ማናልባት ዙርያውን ያለውን ህዝብ በተለያየ መንገድ እየጠቀመ ይሆናል። ኢትዮ-አሜሪካዊው ደግሞ እንደ ማንም አሜሪካዊ ስለ ሀገሩ ችግር በደምብ አይገነዘብም። የሰው ልጅ ተፈጥሮ ነው ልንፈርድበት አይገባም። ወዘተ። አይመስልም እንጂ ትህትና ዋና የፖለቲካ መሳርያ ነው ሁላችንም ተገንዝበነው ትሁት መሆን መሞከር ይገባናል።

ስለዚህ ፖለቲካ ውስብስብ ነው። በተራ ግንዛቤ ብቻ የምናይ ከሆነ አሜሪካ ገነት ኢትዮጵያ ሲኦል ኢህአዴግ ሴጣን ይመስለናል። ግን እውነቱ እንደዚህ ቀላል አይደለም። ትክክለኛ ሀሳብና ተግባር እንዲኖረን ይህን መገንዘብ አለብን።

Wednesday, 4 April 2018

ዜና (ወሬ) ያጃጅላል ባርያ ያደርጋል!

በ2017/11 የተጻፈን ትርጓሜ

አባቴ ኢትዮጵያዊ ምሁር ነበር ማለት ይቻላል። ቤታችን እንደሌሎች የኢትዮጵያዊ ምሁራን ቤቶች የፖለቲካ የፍልስፍና ውይይት ስፍራ ነበር። እኔና አባቴ ብቻችን ሆነንም ከጓደኞች ከእንግዶች ጋርም ምሳ እራት ዝግጅት ሲኖርም «ሁለት ወይም ሶስት» ሆነን በተገኘን ቁጥር ፖለቲካ አብሮን ነበር!

የፖለቲካ ዜናም በቴሌቪዥን እንከታተል ነበር። ከጥቂት ኮሜዲዎች ወይንም የካውቦይ ፊልሞች በቀር ዜና ብቻ ነበር የምንከታተለው። ዋናው ዜና ነበር። ወደ ሰሜን አሜሪካ ስንፈልስ ደግሞ ዜና እስከሚበቃን ማየት ቻልን! የፖለቲካ ትንታኔ ፕሮግራሞችም በሽ ነበሩ።

ዜናን በመከታተላችን እራሳችንን የተማርን ሊቆች ብለን እንቆጥር ነበር። እንደሌሎች ሰዎች የማይረቡ ትርዒቶች አናይ! የሰለጠንን ምሁራን ቁም ነገረኞች ነበርን! ጎረቤቶቻችን ሜክሲኮም እንኳን የት እንደሆነ የማያውቁ ሲሆን እኛ አብዛኞቹ የዓለም ዋና ከተሞችን እናውቃለን። የአሜሪካ የፕሬዚደንት ምርጫ ክርክሮችንም እንከታተላለን። ያውም ምርጫው ገና በእጪ ደረጃም ሆኖ! ስልጣኔአችን የተለየ ነበር!

ግን እውነቱን ለመናገር ይህ ሁሉ ትርጉምም ቁም ነገርም አልነበረውም። የኛ የዜና መከታተል ከቤት እመቤት የድራማ ትርዒት መከታተል ከወጣቱ የስፖርት ግጥምያ መከታተል ምንም አይለይም። ሁላችንም ሚና የማንጫወትበት ዋጋ የማንከፍልበት በአድ የሆኑ ነገሮችን ነው እንደራሳችን አድርገን የምንከታተለው። ግን የዜና ፕሮግራሞችን በመመልከት ትምሕርታዊ ቁም ነገር እያደረግን ነው ብለን እራሳችንን እናታልል ነበር!

ዜና መከታተል ግን ከማንኛውም መዝናንያ ትርዒትን ከማየት አይለይም፤ እንደዛው የአዕምሮ ማደንዘዥያ የኑሮ ማምለጭያ ነው። የዜና ትርዒቶች ከተራ ወሬ ሃሜት አሉባልታ ምንም አይለይም ከግብዝነቱ በቀር። ዜና እውነት አስተማሪና ቁም ነገር ነኝ ይላል! ግን ከተከታታይ ድራማዎች ምንም አይለይም። ጭራሽ ይብሳል፤ አብዛኞች የድራማ ትርዒት ትከታታዮች ቁም ነገር ነው ብለው እራሳቸውን አያታልሉም!

ዛሬ ቴለቪዥንም አላይም ዜናም አልከታተልም። በኢንተርኔት አረስቶችን አያለሁ ግን ከተለመዱት የዜና ድረ ገልጾች አይደለም። እርግጥ ነው አንዳንዴ ጽሁፉ አይቼ ይስበኛል እስቲ ጠልቄ ላንብብ እላለሁ ግን እራሴን አቆማለሁ።

ሆኖም ከኢንቴርነት ነው «ዜና መከታተል ያጃጅላል» የሚለውን ጽሁፍ ያገኘሁት። አንብቡት። አልፎ ተርፎ የዜን ፕሮግራሞች አትከታተሉ። በተለይ ሲኤንኤንን (CNN) መቼም አትመልከቱ። ካላችሁበት ቦታ በቴለቪዥን ላይ ካያችሁትም ሮጣችሁ ሽሹ! እራሳችሁን ከአዕምሮአዊ «ቅኝ ግዛት» አድኑ። ቴለቪዥን የምታዩበትን ትርፍ ጊዜአችሁን ከጎረቤታችሁ ጋር በመጫወት አውሉት። እናንተንም እርሱንም እጅግ ይበልጥ ይጠቅማችኋልና።

Tuesday, 3 April 2018

ሃይማኖታዊ መቻቻል

በዚህ ዘመን የቃላቶች ትርጉም ተተንቅቀን ነጣጥለን ማየት አለብን።

እስቲ በመጀመርያ «መቻቻል» ምን ማለት እንደሆነ እንመርምር። ሰው የሚወድውን ነገር «ቻለው» ይባላል? አይባልም! የማይወደውን ግን በተለያዩ ምክንያቶች ስለነገሩ ምንም ማድረግ የማይችለውን ወይም ማድረግ የማይፈልገውን ነገር ነው «ቻለው» የሚባለው።

ለምሳሌ… ሙስሊም ጎረቤቴ በየጊዜው ድምጽ የበዛው የጸሎት ዝግጅት ያካሄዳል ከበቱ። ጩኸቱን አልወደውም ግን ለሰላም ብዬ ዝም እላለሁ። ይህ የመቻቻል አንድ ምሳሌ ነው።

እዚ ጋር አንድ ነገርን ልብ እንበል። ጎረቤቴን ዝም ያልኩት ስለምወደው ወይም ጥሩ ልሁንለት ብዬ አይደለም። «ነግ በኔን» አስቤ ነው። ለራሴ ጥቅም ብዬ ነው። እኔም ዝግጅቶችህን ተው ብዬ አላስቸግረውም እሱም እኔ እንደዚሁ አይነት ፕሮግራም ባዘጋጅ ዝም ይለኛል። አልፎ ተርፎ ጸብ ስለሌለን ግንኙነታችን ሰላማዊ ስለሆነ ወደ ፊት በተለያዩ የሚጠቁሙን ጉዳዮች መተባበር መረዳዳት ቀላል ሊሆን ይችላል።

ስለዚህ «መቻቻል» የአብሮ መኖር ስልት ነው። የጥሩነት ወይም በጎ መግባር ውጤት አይደለም የመዋደድ የፍቅርም ውጤት አይደለም።

መቻቻል እንዲህ ከሆነ ለኛ ኦርቶዶክስ ክርስትያኖች ምን ማለት ነው? መቻቻል አለብን ወይ? የሌላ ሃይማኖት ተከታዮችን «መቻል» አለብን ወይ? «የሃይማኖት መቻቻልን» መተግበር አለብን ወይ? በፍፁም! በመጀመርያ እንደ ክርስትናችን «መውደድ» ነው ያለብን። አምላካችን እንዳለን እሱ እንደሚወደን ያህል ባለንጀራችንን መውደድ አለብን። የኛ የክርስትያኖች ተዕልኮ «ፍቅር» ነው እንጂ «መቻቻል» አይደለም! ማንም ሰው ከልምድና ምቾት አንጻር መቻቻል ይችላል፤ ግን ክርስትያኖች መውደድ ነው ያለብን።

ወደ ቅድሙ ምሳሌአችን ከተመለሰን የሙስሊም ጎረቤቴን ስለ ጸሎት ዝግጅቶቹ የማላስቸግረው ምክንያት «መቻቻል» ሳይሆን «ፍቅር» ነው መሆን ያለበት። ስለ ዝግጅቱ ካላማረርኩኝ አለማማረሬ ከፍቅር የመነጨ መሆን አለበት እንጂ ለራሴ ጥቅም ብዬ መሆን የለበትም። እሱም ይሉኝታ ኖሮት ዝም ይለንኛል ብዬ ከሱ ጠብቄ ሳይሆን ምንም ሳልጠብቅ ምሆን አለበት። ስለዚህ ክርስትያኖች መቻቻልን መተግበር አለባቸው ማለት ትርጉም የለውም። ከመቻቻል በላይ ሰማይ ጠቀሱን ፍቅር መተግበር ነው ያለን።

እንግዲህ አንዳንዶቻችሁ «አምላካችሁ ውደዱ ቢላችሁም አትሰሙትም» ትሉኝ ይሆናል። «እናንተ ኦርቶዶክስ ክርስትያኖች ድሮም አሁንም ፍቅርን አታውቁም።» አልክድም፤ እውነት ነው፤ እኔ ኦርቶዶክስ ክርስትያን ብሆንም ኃጢአተኛ ነኝ ፍቅር ይጎለኛል። ፍቅር የሆነውን ተልዕኮኤን ሁል ጊዜ እየሳትኩኝ ነው የምኖረው። ይህ ኃጢአተኝነቴ ግን የሚስተካከለው ወይንም በትክክሉ ቋንቋ የሚታከመው መቻቻልን መተግበር በመሞከር አይደለም። ፍቅርን በመተግበር ነው። ካልቻልኩኝ ከወደቅኩኝ ተመልሼ መሞከር መነሳት ነው። ይህ ነው የክርስትና ኑሮ። እንጂ መውደድ አልችልም ብዬ ተስፋ ቆርቼ እስቲ መቻቻልን ልሞርክ ማለት ውድቅ ሀሳብ ነው።

ስለዚህ ፕሮቴስታንት ወንድሜ፤ ሙስሊም እህቴ፤ ሴኩላሪስት ወንድሜ፤ ካስቀየምኩህ ካስቸገርኩህ ከጎዳሁህ እኔን ኃጢአተኛውን ይቅር በለኝ። መሻሻል እሞክራለሁ። ልችልህ ሳይሆን በእግዚአብሔር እርዳታ ልወድህ እሞክራለሁ።