Showing posts with label መፍረድ. Show all posts
Showing posts with label መፍረድ. Show all posts

Monday, 10 September 2018

ቤተ ክርስቲያን በፍጥነት መፅዳት አለባት

ቅዱስ ዮሃንስ አፈወርቅ ፓትሪአርክ በሆኑበት ዘመን 11 ፓፓሳትን አባረዋል ይባላል። ቅዱስ ጳውሎስ በመልክቶቹ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ንፅሁ የሆኑ፤ ጥሩ ምሳሌ የሆኑ እና ህዝቡን የማያሳስቱ መሆን አለባቸው ብሎ በተደጋጋሚ ጽፏል። በርካታ መልክቶቹ ውስጥ ስለቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያለን ችግር እና እንዴት መጽዳት እንዳለበት ጽፏል። በዛሬው ዘመን ይህንን የቅዱስ ጳውሎስ ምክሮችን እና የቅዱስ ዮሃንስ አፈወርቅን ምሳሌ ብንከተል ወይንም ቢያንስ ብናስብበት ጥሩ ይመስለኛል።

በቤተ ክርስቲያናችን አመራር ማለትም ጳጳሳት፤ ካህናት እና አስተዳደር በርካታ የእምነት እና ግብረ ገብ ችግሮች እንዳሉ ይታወቃል። እነዚህ ችግሮች በተለየዩ መንገዶች ባለፉት ዓመታት መጥተዋል በዝተዋል። ይህ ችግር ለቤተ ክርስቲያናችን ታላቅ ጉዳት እያመጣ እንደሆነ ይታወቃል።

ስለ የቤተ ክርስቲያን አመራር ችግሮች ስንወያይ ታላቅ ጥንቃቄ ያስፈልጋል፤

1. ግብዝነትን እና ትዕቢትን መራቅ አለብን፤ እንደ አንድ ምዕመን አመራር ላይ ጣቴን ሳተኩር የራሴን ኃጢአቴን እረሳለሁ። ለዚህ ነው ምዕመናን መሪዎችን እና የቤተ ክርስቲያን ፖለቲካን አትመልከቱ ብሎ የሚመከረው በክርስትና ህይወት።

2. መፍረድ የለብንም። አመራሮች ላይ ችግር ስናይ ሰው በመሆናችን አንዱን ታላቅ ኃጢአት «መፍረድ» ለማድረግ እንፈተናለን። «ድርጊቱ ላይ እንፍረድ ሰውዉ ላይ ግን መፍረድ የለብንም» የሚለውን ትምሕርት ብናውቅም እንረሰዋለን። መርሳት የልብንም። አመራር ሲሳሳት ብናይ በመጀመርያ ለዛ ሰው መጸለይ ነው ያለብን እና እግዚአብሔርን ሁላችንን ከኃጢአት እንዲያርቀን መለመን ነው ያለብን።

ይህን ካልኩኝ በኋላ ግን ቦትዬ ባይሆንም ለህሊናዬ አደገኛ ቢሆንም በዚህ ጉዳይ ሃሳቤን መነገሬ ጥሩ ይመስለኛል። ቅዱስ ጳውሎስ በመልክቱ እንደዚህ አይነት ጉዳዮች የ«እረኝነት» (pastoral) ጉዳዮች እንደሆኑ ገልጿል። ለምሳሌ ተደጋጋሚ ህዝብ የሚያውቀው ኃጢአቶች የሚፈጽም ካህን ወይንም ጳጳስ ካለ አለቆቻቸው ምን እናድርግ ሲሉ እንደ ዘመናዊ ፍርድ ቤት ህግን ከሞላ ጎደል በጭፍን መልኩ አያሰፍኑም። ምን ቢደረግ ነው ካህኑ የሚድነው? ምን ቢደረግ ነው ህዝቡ የሚድነው? ነገሮች ሚዛን ላይ ተደርገው መታየት አለባቸው እንጂ ጥቁር እና ነጭ አይደሉም። አራት መስፈርቶች፤ ክስተቱ፤ ሁኔታው፤ ሰዎቹ እና ዘመኑ መታየት አለበት።

በኔ እየታ በአሁኑ ዘመን ትሉቁ ጎልቶ የሚታየው መስፈርት «ዘመን» ነው። ምዕመናን በመሪዎች ስህተት በጣም ሊወዛበቡ የሚችሉበት ዘመን ነው። ዛሬ አይኑ ብዙ ነው። ወሬው እና ጫጫታው ብዙ ነው። አንድ ችግር ያለው ጳጳስ ወይንም ካህን ቶሎ ከስራ ካልተወገደ በርካታ ምዕመን በፍጥነት መሰናከል (በእምነት ማጣትም በመፍረድም) የሚችልበት ዘመን ነው። የፍጥነት ዘመን ነው። አንድ ችግር ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሲገባ በሽታው በፍጥነት ነው የሚስፋፋው እና መሰረት የሚጥለው።

ይህን በሲኖዶስ ችግራችን በደምብ አይተነዋል። አሁን በቤተ ክርስቲያን አመራሮቻችን የጉቦ፤ ሙስና እና ሌሎች የግብረ ገብ እጦት በምዕመናን ያመጣው ችግርን አይተነዋል። ከኛ ቤተ ክርስቲያን ውጭም በካቶሊች ቤተ ክርስቲያን ችልተኝነት እና መታገስ ባለፉት 30-40 ዓመት ያመጡት ችግሮችን አይተናል።

ስለዚህ አሁን እረኞቻችን ሚዛኑን ከትዕግስት ይልቅ ወደ ፍትነት እና ችኮላ ማድላት ያለባቸው ይመስለኛል። እንደ ዮሃንስ አፈወርቅ ጎልቶ የሚታይ ችግር ሲፈጸም ቶሎ ብሎ ህዝቡ ሳይሰናከል እርምጃ መውሰድ። በሽታው መሰረት ለመጣል እና መስፋፋት እድሉ ሳይኖረው ወድያው ማከም። ይህ በዛሬው ዘመን ለኃጢአት አድራጊውም እጅግ ይጠቅመዋል። በፍጥነት ወደ ኃጢአት ኑሮ ውስጥ ከሚገባ ቶሎ ወደ ንስሃ እንዲገባ ይረደዋል። ይህ የፍጥነት ዘመኑ በቀላሉ እንዳይቆጣጠረው ይረደዋል።

ስለዚህ የቤተ ክርስቲያን አመራሮች እባካችሁን የቤተ ክርስቲያን ጽዳት ዘመቻችንን አፋጥኑ። ችላ አንበል። ታጋሽ አንሁን። በማንም አንፍረድ በስራው ብቻ። ግን ህዝቡን ከፈተና እንጠብቅ። ግልጽና ግዙፍ ኃጢአትን የሚፈጽሙት ጳጳሳት እና ካህናትን ቶሎ ከሃላፊነት ይወገዱ እና ወደ ክርስትናዊ ህክምናቸው ይግቡ። የአሁኑ ዘመን ይህን መንገድ የሚያስገድድ ይመስለኛል።

Thursday, 13 October 2016

ኦርቶዶክስ ክርስትናና ፖለቲካ

2009/2/3 .. (2016/10/13)

«እግዚአብሔር በሁልም ስፍራ አለ በሁሉም ነገርም ይገኛል» (God is everywhere present and in all things) አንድ የኦርቶዶክስ ሃይማኖት መሰረታዊ እምነት ነው። ይህ አባባል እግዚአብሔር የፈተራት ዓለም በሁለት በ«አለማዊ» እና በ«ሃይማኖታዊ» ስፍሮች እንዳልተከፈለች ይገልጻል። ወደ ቤተሰባችን፤ ስራችን፤ ንግዳችን፤ ዘፈናችን፤ መዝኒያናችን፤ ስፖርታችን፤ ትምህርትቤታችን፤ እርሻችን፤ ፖለቲካችንም ስንሄድ እግዚአብሔርንና እምነታችንን ትትን መሄድ አይቻላም! እግዚአብሔር በነዚ ስፍሮች ሁሉ አለና። ግድብ የለውም። ስለዚህ ፖለቲካና ክርስትና የተለያዩና የማይገናኙ ናቸው ማለት አይቻልም።

ስለዚህ ክርስትያኖች በፖለቲካ ልንሳተፍ እንችላለን። የማህበራዊ ኑሮ ፖለቲካን ስለሚይካትት ብንፈልግም ባንፈልጉም በተወሰነ ደረጃ ቢሆንም ፖለቲካ ውስጥ ተሳትፈናል። ሁለት ምሳሌዎች ልስጣችሁ፤ ቀረጥ መክፈል ማለት ገንዘብ ለመንግስት መስጠት ነው። የዚህን ገንዘብን አጥቃቀም የሚወስኑት ፖለቲከኞች ናቸው። በገንዘባችን ለሚያደርጉት ግን ተጠሪ ነን ግንዘባችን ነውና። በቀበሌ ወይም በማንኛውም የምንግስት መሥሪያቤት ስንገለገል ፖለቲከኞች የዘረጉትን የአስተዳድራዊ ዘዴ መቀበል ማለት ነው። ብለት ኑሮአችን ፖለቲካ አይጠፋም። ፖለቲካ አንዱ የህይወታችን ዘርፍ ነው።

ታድያ የአንድ ክርስትያን ፖለቲካዊ ኑሮ እንዴት መሆን አለበት? ይህን ለመመለስ በመጀመርያ አንዳንድ መሰረታዊ የሆኑ የክርስትና እምነቶች እንመልከት። ከላይ እግዚአብሔር ከሁሉም አለ የሚለውን አባባል ጠቅሽያለሁ። ቀጥሎ «በዐይነህ ውስጥ ያለውን ግንድ ሳትመለከት፤ በወንድምህ ዐይን ያለውን ጉድፍ ለምን ታያለህ» የሚለውን እስቲ እንመልከት። ባለንጀራችሁን እንደራሳችሁ ውደዱ ይበልጥ ደግሞ እኔ እንደምወዳችሁ ያህል ውደዱት ብሎ ክርስቶስ አዞናል። ይህን አባባልንም እንመልከት።

ሌላ አባባል፤ ቅዱስ ባስሊዮስ እንደዚህ አሉ፤ « የባለንጀራህ ሀጥያት ብቻ ከሆነ የሚታይህ ያንን ብቻ ከማየት ይልቅ በፊትም አሁንም የሚያደርገውን ጥሩ ነገሮች እንዳሉ ተገንዘብ። መፍረድን ትተህ ይህን ለማድረግ ስትሞክር ጭራሽ እርሱ ካንተ የተሻለ እንደሆነ ትረዳለህ።» ይህ አባባል ሁለት መሰረታዊ እምነቶታችንን ይገልጻል፤ እግዚአብሔር የፈጠረው ሁሉም ሰው ትንሽም ቢሆን ጥሩነት ስላለው በሌላ ሰው መፍረድ ተገቢ አይደለም።

ክርስቶስ «እኔ በልቤ የዋህና ትሑት ነኝ» ብሎ እኛም እንደሱ እንድንሆን አዞናል። ትሕትና የቀደመውና ዋናው ሀጥያታችን «ትዕቢት» ተቃራኒና መድሀኒት ስለሆነ የሃይማኖት አባቶች የምያተኩሩበት መልካ መግባር ነው። አባ ይስሐቅ ዘሶሪያ እንዲህ ብለዋል፤ «ጨው ለምግብ እንደሚሆን ትህትና ለሁሉ መልካ መግባር ይሆናል።»

የክርስትያን ፖለቲካ ኑሮ ከላይ በጠቀስኳቸው አባባሎች የሚያስተምሩን መልካ መግባሮች ነው መካተትና መመራት አለበት፤ 1) እግዚአብሔር ከሁሉም አለ፤ 2) የሌላውን ሀጥያት ከማየት ፋንታ የራሳችንን ሀጥያት አይተን ንስሃ እንጋባ እናርማቸውም፤ 3) ባለንጀራችንን ክርስቶስ እንደሚወደን እንውደድ፤ 4) በሰው አንፍረድ፤ ትሑት እንሁን ከትዕቢትና ትምክህት እንራቅ።

በዛሬው የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሁኔታ አንድ ክርስትያን እነዚህን እምነቶች ተከትሎ ምን ሊያደርግ ይገባዋል? አትፍረዱ፤ ትሑት ሁኑ፤ የራሳችሁን ሀጥያት ተመልከቱ፤ አብዛኞቻችን በፖለቲካ ዙርያ የሌላው ሰው፤ ወገን፤ ጎሳ፤ ፓርቲ ጥፋት ብቻ ነው የሚታየን። የኢህአዴግ፤ የህወሓት፤ የኦነግ፤ የሻእቢያ፤ የኢዴፓ፤ የደርግ፤ የኢሀፓ፤ የኃይለ ስላሴ፤ የዘንድሮ ተቃዋሚ፤ የዲያስፖራ፤ ወዘተ። አንድ ክርስትያን እራሱን ሳይመረምር የራሱን ጥፋቶች ተረድቶ ንስሀ ሳይገባ የማንንም፤ የኢህአዴግንም፤ ጥፋትና ስህተትን ላይ ማተኮር የለበትም።

ግን ምን የፖለቲካ ሀጥያት አለብኝ ብለን የምንጠይቅ ብዙ ነን። ከበርካታ ሰዎች ከገደለው ካሰቃየው ኢህአዴግ፤ ደርግ፤ ወዘተ ምኔ ሊወዳደር ይችላል። እስቲ ይህን ጥያቄ በምሳሌዎች ለመመለስ ልሞክር።

ጎረቤቴ ለ«ኢንቬስተር» ተብሎ መሬቱን ሲነጠቅ ረዳሁትን? ትንሽም ነገር አደረግኩለት?የምፍረአቸውን የሰፈሬን ዱሪዬዎችን ለመርዳትና ጥሩ መስመር ለማስያዝ ያረግኩት ነገር አለ? ወይም የራሳቸው ጉዳይ ብዬ ዞር ብዬም አላያቸውም። ችግር እስኪያመጡ። በፖለቲካ ዙሪያ «ኦሮሞ» ሲባል በልቤ ፍርሃትና ጥርጣሬ አይሰፍንም? ነው በንጹ ልቦና ጉዳዩን እመለከታለሁ? «እነሱ ከሚገዙን ወያኔ ይግዛን» ብዬ አስቤ አላቅምን? ግን አንድ ቀንም «ከነሱ» ጋር ቁጭ ብዬ ተወያይቼ አላቅም። ከጎረቤቶቼ ጋር ድሮ ተጣልቼ አሁንም አልተቀየምኳቸውም? በዚህ ጥላቻ ምክነያት እንኳን ለፖለቲካ ለውጥ ለምንም ነገር ከነሱ ጋር መተባበር አልችልም አይደ? ከባልደረባዬ ምሁር በትንሽ አስተሳሰብ ልዩነት ምክነያት ጠላቶች አልሆንም? እንኳን አብረን ለመስራት መተያየትም አንፈልግም አይደለምን? ስራተኞቼን እንደ ሰው ቆጥሬ አላውቅም እሁድ ቤተክርስትያን ለመሄድም እድል አልሰጣቸውም! ዘላለማዊ ቂም አልፈጠርኩባቸውም? ኢህአዴግ ይህንን ቂም ተጠቅሞ እነዚህን ሰራተኞቼን እኔን ለመግዳት ወይም የኔን አቋም ለማዳከም መጠቀም አይችልምን? የማይገባኝ ጥቅም ለማግኘት ጉቦ ሰጥችሄ አላውቅምን? ከስራ ቦታዬ በኔ ሃሳቦች የማይስማሙትን አልኮንንም? ሰራተኞች ሲሳሳቱ ችግራቸውን ከመረዳት ፋንታ አልፈርድባቸውም? ልጄ ውትድርና ገብቶ የማያምንበትን ክፉ ድርጊቶች እንዲያደርግ ይታዘዛል ያደርጋል። ልጄ ነው የሚጦረኝ እና እንደዚህ አይነቱን ጉዳይ ለሱ በማንሳት ላበሳጨው አልፈልግም እላለሁ። ታድያ እንደ የኢግዚአብሔር ልጅ ሃላፊነቴን አልካድኩምን?

እራሳችንን በደምብ ከመረመርን እነዚህ አይነቶቹ ሀጥያቶች እንዴት ከኛ ወደ ህብረተሰቡ፤ ከህብረተሰብ ወደ መንግስታችን እንደሚተላለፍ እንደሚያንጸባርቅ ልንገነዘብ እንችላለን። ክርስትያኖች የሁላችንም ኃጢአት የተገናኘው እንደሆነ እናምናለን። ለሌሎችንም ኃጢአት ሃላፊነት እንዳለብን እናምናለን። አባቶች ይህን ተጠንቅቀው ነው የሚያስተምሩን። ከላይ እንደምሳሌ የጠቀስኳቸው ኃጢአቶች እንዴት አሁን ካለው የምንግስት ስረዓት ባህሪ ጋር እንደሚገናኙ ግልጽ እንደሆነ ተስፋ አለኝ።

ክርስትያን በመሆኔ መጠን ለነዚህ ኃጢአቶች ንስሃ ገብቼ እየወደኩኝ እየተነሳሁኝ እያስተካከልኩኝ መኖር ነው የሚጥበቅብኝ። የፖለቲካ ኑሮዬም እንደዚህ ነው መሆን ያለበት። የምደግፈው የፖለቲካ አቋም፤ አመለካከት፤ ፓርቲ፤ ርዕዮተ ዓለም፤ ወዘተ ከክርስትያንነቴ ስር ነው መሆን ያለባቸው። እንደ ክርስትያን እስከኖርኩኝ ድረስ ፖለቲካው እራሱን ያስተካክላል።

ሆኖም ማንም ሰው አጥፊና ክፉ ነበር የሚያደርግ መንግስት ወይም ተቋምን መታገል የለበትም ማለት አይቻልም። እያንዳንዱ የራሱን ልብ ያውቃልና ልታገል ቢል በሱ ልፈርድ አልችልም፤ ግን ትግሉ ውጤታማ እንዲሆን በመጀመርያ የራሱን ልብና ገበና መፈተሽ አለበት። ሳይፈትሽ ሌላውን ለማስወገድ ብቻ ከታገለ ትግሉን አያሸንፍም። ወይም ይባስ ያሸንፍና ከታገለው የባሰ ሆኖ ይገኛል። ይህን እውነታ ሃይማኖታችን ያስተምረናል። እውነታም ስለሆነ በታሪክ በትደጋጋሚ ሲከሰት አይተናል! ስለዚህ በመጀመርያ ክርስትያን እንሁን፤ ሙሉ ክርስትያን እንሁን። ከሆንን ሌላው እራሱን ያስተካክላል።