Showing posts with label ዘመናዊነት. Show all posts
Showing posts with label ዘመናዊነት. Show all posts

Monday, 4 June 2018

የዘመናዊነት ዕቅድ (The Modern Project)

ይህ ከቀሲስ/መምህር ስቲፈን (እስቲፋኖስ) ፍሪማን ጽሁፍ (https://blogs.ancientfaith.com/glory2godforallthings/2014/01/10/the-modern-project/) በሰፊው የተረጎምኩት ነው። ቀሲስ ስቲፈን አሜሪካዊ (ምስራቃዊ ወይም ቃልቄዶናዊ) ኦርቶዶክስ ቄስ ናቸው። ከፕሮቴስታንትነት ወደ ኦርቶዶክስ እምነት «ከተመለሱት» በርካታ አሜሪካዊ ካህናት መካከል ናቸው። አሜሪካዊ በመሆናቸው ብቻ ሳይሆን በቀለም ትምሕርት እና በሃይማኖት ታሪካቸው ምክንያት ስለ በዘመናችን የነገሰው ዘመናዊነት ፍልስፍና በደምብ ያውቃሉ ለክርስትና ዋና ጠላት መሆኑንም ይገነዘባሉ። ሆኖም የዘመናዊነት ፍልስፍና የነገሰ ስለሆነ ሳናውቀው ሁላችንም በተወሰነ ደገጃ እንደተቀበልነው ያውቃሉ። ሰለዚህም ነው ቀሲስ ስቲፈን በዚህ ጉዳይ ዙርያ ብዙ የሚጽፉት። ጽሁፋቸው ለሁላችንም ገላጭ እና አስተማሪ ነው ብዬ አምናለው። ብሎጋቸውን ብታነቡ እጅግ ጠቃሚ ይሆናችኋል ብዬ አምናለው።

ሁለተኛ ዲግሪዬን በ«ቴኦሎጂ» በምማርበት ወቅት (1970 ዎቹ) «የዘመናዊነት ዕቅድ» ('the project of modernity') የውይይት ርዕስ የነበረበት ጊዜ ነበር። ይህ የዘመናዊነት ዕቅድ «ዘመናዊውን» ዓለም ('the modern world') ለመገንባት የሚሰሩትን ማህበራዊ፤ ፍልስፍናዊ፤ ፖለቲካዊ እና ሃይማኖታዊ ስራዎችን ያካትታል። በ17ኛ ክፍለ ዘመን የመነጨው «የብርሃን መብራት» ('the Enlightenment') ፍልስፍና አዲስ የአስተሳሰብ አይነቶች ወደ ምዕራባዊው ዓለም (ከዛ ቀጥሎ ወደ መላው ዓለም) አመጣ። ለምሳሌ ለ«ሀገር» የምንለው ፅንሰ ሃሳብ አዲስ ትርጉም እና አወቃቀር ፈጠረ። የክርስትና ሃይማኖትን በአዲስ መልክ ፈጠረ (ለምሳሌ ፕሮቴስታንትነት)። ከሁሉም በላይ ግን የሰው ልጅ ማንነትን ሌላ ትርጉም ሰጠው።

እኛ የዚህ ዘመን ሰዎች የዚህ ፍልስፍና ወራሾች ነን። የዘመናዊነት እና የዘመናዊነት ዕቅድ ልጆች ነን። ዛሬ ማንም ትምህርት የሌለውም ሰው «የዘመናዊነት ዕቅድ» ያመጣውን አስተሳሰቦችን ሳያውቀውም ቢሆን አድሮበታል አምኖበታልም። በትምህርት ቤትም በሚዲያም በሌሎች መንገዶች አስተሳሰቡን ወርሰነዋል። እኛ «የዘመናዊነት ዕቅዱ» ውጤቶቹ ሆነናል።

ዘመናዊነት ዕቅዱ የሰው ልጅን ማንነት ሲደነግግ እንደዚህ ይላል፤ « የሰው ልጅ በራሱ ብቻ የሚተዳደር ነፍስ ነው፤ ውሳኔዎቹ እና ስራው ብቻ ነው ማንነቱን የሚወስን»። ይህ ማለት፤

1. በራሱ ብቻ የሚተዳደር ነፍስ፤ የሰው ልጅ የማንነቱ መሰረት በማወቅ እና ማሰብ ችሎታው የተወሰነ ነው። «የማሰብ እና ማወቅ ችሎታዬ ብቻ ነው የሰው ልጅ የሚአደርገኝ»። ከዚህ ቀጥሎ በፈቃዴ ከሌሎች ጋር መጋራት እችላለሁ ግን ማንነቴ በራሴ ብቻ ነው የሚወስነው። ከሌሎች ጋር ያለኝን ግንኙነትም እኔ ብቻ ነው የምወስነው። ይህ ነው በዘመናዊው ዓለም የምናየው የ«ግለኝነት» አኗኗር መሰረታዊ ሃሳብ።

2. ውሳኔዎቻችን እና ስራዎቻችን ማንነታችንን እና የህይወት ጉዞዋችንን ይወስናሉ፤ በዚህ ዓለም ያለኝ የማንነት ምደባ የራሴ አመራረጥ፤ ውሳኔዎች እና ያሳለፍኩት ልምዶች ናቸው የሚወስኑት። ውሳኔዎቼ ማንነቴን ይወስናሉ እና መሆን የምፈልገውን መሆን እንድችል ብቸኛ ሚና ይጫወታሉ። የኔ ምርጫ እና ውሳኔዎች ናቸው የህይወቴን ትርጉም እና ማን መሆን እንደምፈልግ የሚወስኑት።

እነዚህን ፅንሰ ሃሳቦች ካሰላሰልናቸው የዘመናችን ታሪክን ወሳኝ ነገር «ነፃነት» ለምን እንደሆነ በቀላሉ እንረዳለን። (ይህ «ነፃነት» የሚባለው የመወሰን እና የመምረጥ «መብት» ነው እንጂ እውነተኛው ነፃነት አይደለም።) የሰው ልጅ ማንነት ትርጉም ከላይ የተጻፈው ከሆነ ይህ «ነፃነት» የግድ ይሆናል። ይህን ነፃነት የሚገድብ ሁሉ የሰው ልጅ ህልውና እና ፍላጎት ጠላት ይሆናል። እንደ ፈለግኩኝ መምረጥ መወሰን ስችል ነው ፍላጎቴን ማምዋላት የምችል ሰው መሆን የምችለው።

ከላይ እንደጠቀስኩት ባሁኑ ዘመን እነዚህ አይነት አስተሳሰቦች ሳናውቀው ሰርቀው አዕምሮአችን ውስጥ ገብተዋል። ዓለም ዙርያ ታውቀዋል። እንደ «ነፃነት» እና «ምርጫ» አይነቶቹ ቃላቶት ምን ማለት እንደሆኑ ብዙሃኑ ተውሕዶታል። እነዚህን ቃላቶችን ስንጠቀም ሁሉም ሰው ትርጉማቸውን «ያውቃል»።

አንዳንድ የክርስቲያን ቡድኖች በተለይም የፕሮቴስታንት ንቅናቄ ይህን አስተሳሰብ አቀናብረው አንጸራጭተውታል። እነዚህ የክርስቲያን ቡድኖች ከአሜሪካ እና አውሮፓ ተነስተው የ«ዘመናዊ» ክርስትና ዓለም ዙርያ አስፋፍተዋል። በጥናታዊ ክርስትና ያልነበሩ አስተያየቶች እና ጥያቂዎችን አስፋፍተው የተለመዱ እንዲሆኑ አደረጉ። ለምሳሌ የህፃንነት ጥምቀት ጥያቄ፤ ዛሬ ሰው ለምን በህፃንነቱ ክርስትና ይነሳል የሚለው ጥያቄ ይጠየቃል። ልበ በሉ ለመጀመርያዎቹ ፕሮቴስታንቶች ይህ ጥያቄ አልነበረም ግን የተከሉት ዘር ወደዚህ አመራ። ጥያቄ የሆነው ምክነያት የህጻንነት ጥምቀት «ነፃነትን» ይሽራል ተብሎ ነው! «ህፃኑ እንዴት አለ «ምርጫው» ይጠመቃል። ለመጠመቅ ላለመጠመቅ ነፃነቱ ሊኖረው አይገባምን?» ይባላል! በዘመናዊነቱ ዕቅድ ምርጫን ወይም የራስ ውሳኔን የሚገድብ ነገር አደገኛ ነው ተብሎ ይሰየማል። በየ «ኤቫንጀሊካል» ፖሮቴስታንት ቤተ ክርስቲያን ክርስቲያን መሆን የ«ነፃ ምርጫ» ጉዳይ ነው ይባላል። «የውሳኔው ስዓት» ሰዎች ክርስቶርስን ጠቀብያለሁ የሚሉበት ጊዜ በዘመናችን ተለምዷል።

ቤተ ክርስቲያን ስለ ገብረ ግብ የምታስተምረውም በዘመናዊነት ዕቅዱ ምክንያት በጥርጣሬ ላይ ወድቋል። ዘመናዊ ሰዎች እራሳቸውን «ካቶሊክ»፤ «ኦርቶዶክስ»፤ «ጴንጤቆስጣል»፤ «ፕሬስቢቴሪያን» ወዘተ ብሎ ቢሰይምም ቤተ ክርስቲያናቸው ስለ ግብረ ገብ ወይም ስነ መግባር ኑሮዋቸው መወሰን የለባትም ብለው ያምናሉ። እራሳቸውን «ካቶሊክ» ብለው ቢሰይሙም በካቶሊክ እምነት አይገዙም። ለምሳሌ አብዛኞች አሜሪካዊ ካቶሊኮች ቤተ ክርስቲያናቸው በተለይ ስለ ቤተሰብ እና ጋብቻ የምታስተምረውን ሌሎችም ትምህርቶቿንም ይክዳሉ! ከቤተ ክርስቲያናቸው እምነቶች የሚፈልጉትን ይመርጣሉ የግል ምርጫዬ ነው የነፃነት ጉዳይ ነው ብለው ያምናሉ። ግን ይህ «የግል ሃይማኖታቸውን» በራሳቸው «ነፃነት» እና ምርጫ «ካቶሊክ» ብለው ይሰይማሉ። በዚህ አስተሳሰብ «ካቶሊክ»፤ «ኦርቶዶክስ»፤ «ሉቴራን» ወዘተ ሰው የሚመርጠው ማንነት ነው እንጂ ማንነትን እና ህይወትን የሚወስን ጉባኤ አይደለም።

የዘመናዊነት ዕቅዱ የጥንታዊ ክርስትና ጠላት ነው።

በጥንታዊ አመለካከት የሰው ልጅ ለራሱ ብቸኛ ወሳኝ አይደለም። በዚህ ዓለም የምንገኘው ከራሳችን ሌላ በሆነው በእግዚአብሔር ፈቃድ ነው። ህይወታችን የእግዚአብሔር ስጦታ ነው። የህይወታችን አላማው፤ ትርጉሙ እና አቅጣጫው በእግዚአብሔር የተሰጠ ነው። የሰው ልጅ የሚያደርገን እና ዋጋ የሚሰጠን በእግዚአብሔር ምሳሌ መፈጠራችን ነው እንጂ ውሳኔዎቻችን ወይም የመወሰን አቅም ስላለን አይደለም። የሁላችንም ታናሾች አቅም የሌላቸው፤ ችሎታ የሌላቸው፤ ከአልጋ ተኝተው መንቀሳቀስ የማይችሉት፤ ወዘተ በኢግዚአብሔር ምሳሌ በመፈጠራቸው ክብር እና ዋጋ አላቸው።

ማንነታችን በህይወት ምርጫዎቻችን እና ውሳኔዎቻችን ብቻ አይደለም የሚወሰነው። ህይወታችን እና ማንነታችን ከእግዚአብሔር ያገኘነው ስጦታ ነው። እሰረታዊ ማንነታችን በተወሰነ ደረጃ የተመደበ ነው። ይህ ማንነት በክርስትና ህይወት የሚገለጽ እና የሚለወት ነው እንጂ አንድ ሰው በግሉ የሚፈጥረው አይደለም። ምርጫዎቻችን እና ውሳኔዎቻችን ሚና ይጫወታሉ ግን ከእግዚአብሔር ውሳኔ ስር ነው ሚናቸው። ዞሮ ዞሮ የእግዚአብሔር ፍጥረቶች ነን ስለዚህ ውሳኔዎቻችን ትርጉም ያላቸው ከሱ ጋር ባለን ግንኝነት ነው።

በዘመናዊነት ዕቅዱ እና በጥንታዊው አመለካከት ያለው ጦርነት በደምብ የሚታየው በተለይም በምዕራቡ ዓለም በስነ ህይወት (biology) እና የሰው ግንኝነት ዙርያ። ጥንታዊ የክርስትና አመለካከት ስነ ህይወታችን፤ ማለትም ሰውነትና አካላችን ወዘተ፤ የተሰጠን ነው። እንደ አባት፤ እናት፤ ወንድም፤ እህት ወዘተ ያለን ከሰው ጋር ያለን ግንኙነቶችም የተሰጡን ናቸው። ጾታ ምርጫ አይደለም። ቤተሰብም የደም ተፈጥሮ ነው እንጂ በምርጫ አይደለም። በባለና ሚስት መካከል ወይም ሌሎች ወሰባዊ ግንኙነቶች የተሰጠ አላማ አላቸው እንጂ የግል ፍላጎት ማምዋያ አይደሉም። ግን የዘመናዊነት ዕቅዱ «ነፃነትን» እና «ምርጫን» እንዲሰፍኑ ማድረግ ነው የሚፈልገው። የሰው ተፈጥሮ እውነት ነው ግን ወሳኝ አይደለም ይላል (ለዚህም ነው ዛሬ አንዳንዶች ጾታቸውን የሚመርጡት)። ቤተሰብ የምርጫ ጉዳይ ነው የምንፈልገውን ግንኙነቶችን እንመርጣለን። የደም ትሥሥር የተሰጠ መሆኑ እና በደም ትሥሥር ምክንያት ሃላፊነቶች መኖራቸው በምዕራባዊ ሀገራት መንግስታት እና ፍርድ ቤቶች እየተካደ ነው። ለዚህም ነው በእግዚአብሔር ፈቃድ የተጸነሰው ከ«ነፃነት» ጋር መወዳደር ያልቻለው እና ጽንስን ማስወረድ የሰፈነው።

ዛሬ «እውነት» የሚባለው ነገር አሻሚ ሆኗል። የኔ እውነት ካንተ እውነት ይለያል ግን ሁለቱም እውነቶች ናቸው ይባላል። እውነትም የምርጫ ጉዳይ ሆኗል። አንድ የሆነ እውነት የለም ይባላል። በዚህ ዘመናዊ ዓለም እውነት አንድ ነው ማለት እንደ ጭቆና ነው የሚቆጠረው። የጥንታዊ ክርስትና አስተያየት ከነ ህግ እና እምነቱ የማይመች እና መጥፋት ያለበት ሆኖ ነው የሚታየው። ዘመናዊው ዕቅድ «ለምን እግዚአብሔርንም በራሳችን ምርጫ በራሳችን ምናብ አንፈጥረውም አንወስነውም» ይለናል።

መጨረሻው

ከመጀመርያ ጀምሮ ለ400 ዓመታት በላይ የዘመናዊው ዕቅድ የጥንታዊ ክርስትናን ተዋግቶ ከሰው ልጅ ከህዝብ ማስወገድ ነው አላማው። የዘመናዊነት ጥያቄ «እግዚአብሔር እንዴት ነው የፈጠረን» ሳይሆን «ዓለምን ምን እንዲመስል ነው የምንፈልገው?» ነው። የዓለም ሁኔታ የሰው ምርጫ ጉዳይ ነው ብሎ ነው የሚያምነው። ስለዚህ ነው የዘመናዊ ዕቅዱ ልጅ የሆነው የፕሮቴስታንት ስነ መለኮት (ቴኦሎጂ) የክርስትናን ትውፊት እና ወግን ከመመርመር እና ማጥናት ይልቅ ወንጌልን በራሱ ምናብ መተርጎም የፈለገው።

ማርቲን ሉተር «በመጻሐፍት ብቻ» ('Sola Scriptura') የሚባለው የፕሮቴስታንት አቋምን ሲፈጥር ማንም ሰው መጸሀፍ ቅዱስን አንብቦ አለ እርዳታ አለ ቤተ ክርስቲያን አለ ሃዋርያት በትክክሉ ይተረጉመዋል ለማለት ነው። ማርቲን ሉተር የሮሜ ጳጳስን ወይም የሮሜ ቤተ ክርስቲያን ችግሮችን በመቃወም ስበብ ክርስትናን በራሱ ውሳኔ እና ምርጫ መቅረስ ፈለገ። በዝህ መልክ ይህ «በመጸሐፍት ብቻ» የሚባለው አስተያየት በመጀመርያ ቤተ ክርስቲያንን እና ትውፊቷን ለመለየት የተጠቀሙበት መሳርያ ነበር። ግን ባልታሰበበት (ግን ሊታሰብበት) መልክ ይህ አስተሳሰብ ሰዎች መጸሀፍ ቅዱስን በግላቸው እንተርጉም እያሉ ከአንድ ከሉተር ከሁለት የሉተር ተፎካካሪ ዝዊንግሊ ወደ 30 ሺ አተረጓገም (ዛሬ ዓለም ዙርያ ያሉት የፕሮቴስታንት ቡድኖች ቁጥር) ደርሷል።

ግን «የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም» እና ዛሬም የጥንታዊ ክርስትና አለች የዘመናዊነቱን ዕቅድን የስጋው መውግያ ናት። የዘመኑ ሚዲያ ቫቲካንን አትኩረው ያያሉ ገና ለገና መሰረቷን ሸርሽራ ትጨርሳለች እጇን ሙሉ በሙሉ ለዘመናዊነቱን ዕቅድ ትሰጣለች ብለው። በሩስያ ከሞት የተነሳችው ኦርቶዶክስ እምነት ደግሞ ከፖለቲካዊ «አምባገነን» ጋር የተያያዘ እና «ኋላ ቀር» ብለው ይሰይሙታል! ጦርነት ነው!

ዛሬ የጥንታዊ ክርስትና መንገድ ከባድ ነው። አታላዩ መንገድ ዝም ብሎ ጸረ የዘመናዊው አብዮት መሆን ነው። ከዘመናዊነት ዕቅዱ እኩል እንደ አማራጭ መወዳደር። ግን ክርስትና እንዳዚህ ካረገች እጇን ለዘመናዊው ዕቅድ ሰጠች ማለት ነው። ሌላ «ምርጫ» ሆነች ማለት ነው። ግን ጥንታዊ ክርስትና የምርቻዎቻን ውጤቶች አይደለንም ህይወቶቻችን በእግዚአብሔር ጸጋ እና ስጦታ ነው የሚወሰነው ሁሉም ነገር ከእግዚአብሔር አኳያ ነው የምንመለከተው ነው። የቤተ ክርስቲያን ተውፊት የለ የተሰጠ ነገር ነው እንጂ ምርጫ አይደለም። ስለዚህ እራሱን እንደ አንድ አማራጭ አያቀርብም ሊያቀርብም አይችልም።

የጥንትዊ ክርስትና መንፈስ ስለ በራስ መምርጥ ሳይሆን እራስን ባዶ ማድረግ። ማለት የራስን ፍላጎት ትቶ የእግዚአብሔርን ፍላጎት ማወቅ እና ማክበር። እጅን ለእግዚአብሔር ሙሉ በሙሉ መስጠት። ጥንታዊ ክርስትና ህይወት የተሰጠ እንደሆነ ይረዳል። የተፈጥሮ የደም ትሥሥር፤ ቤተ ሰብ እና ዝምድና ተጭባጭ ናቸው እና ህይወታችን ላይ ተገቢ ሚና ይጫወታሉ ሃላፊነት ይሰጡናል። ዓለም እንደዚህ ትሁን እንደዛ ትሁን ብለን ማለም ከለት ለለት ከባድ የሆነ የክርስትና ኑሮአችን እንድንርቅ እንድንሰንፍ ፈተና ነው። የዓለም ድሃ ይረዳ እያልኩኝ እየተፈላሰፍኩኝ ድሃ ባለንጀራዬን ዞር ብዬ አላየውም! ግን የዘመናዊነት ዕቅድ እንደዚህ ነው የሚያስበው። ዓለምን አሻሽላለው ይላል። ከ«ነፃነት» በደምብ ማትረፍ የሚችሉትን ባለ ሃብቶች እና በትምሐርት ጎበዞች በደምብ አትርፈዋል። ግን ይህ የዘመናዊነት ዕቅድ ፉከራ ባዶ ነው ህይወታችንን በራሳችን መወሰን ስለማንችል። እራሳችንን ከእውነታችን በላይ ታላቅ አርገን ብናስብም መጨረሻ ላይ ሞት ምርጫችንን አያከብርም! ምናልባትም የዛሬው ታላቅ አሽሙር የዘመናዊነት ዕቅዱ የ«መሞት መብት»ን ማራመዱ ነው አለመሞት ምርጫ እንደሆነ!

Friday, 6 April 2018

የህዝብ ብዛት

የኢትዮጵያ ህዝብ ቁጥር በዝቷል በተለያዩ መንገዶች የህዝብ ቁጥር እድገትን መቀነስ አለብን ሲባል እጅግ አዝናለሁ። በተለይ የኛ ምሁራን ልሂቃን እንደዚህ ሲሉ ስለ ሀገራችን ህልውና እሰጋለሁ። ሀገራችን ብዙ የፖለቲካ የኤኮኖሚ የመሐበረሰብ ችግሮች አሉትና ከነዚህ ሁሉ የሰው ቁትር መብዛት «ችግር» ከተባለም ትንሹ ነው። የሰው ቁጥር አለ አግባብ ጨምሯል ከተባለም ምክንያቱ የእርግዝና መከላከያ እጦት ሳይሆን ሌሎች የኤኮኖሚና የፖለቲካ ችግሮች ናቸው።

እስቲ አንዳንድ እውነታዎች እንመልከት፤

1. በገጠር ሴቶች በአማካይ ስድስት ልጆች ይወልዳሉ። በአዲስ አበባ በአማካይ ሁለት ልጆች ይወልዳሉ። ላለፉት 43 ዓመት የመንግስታችን የመሬት ፖሊሲ ህዝባችን ከገጥር እንዳይወጣ አድርጓል። ምክንያቱም አንድ ገበሬ ገጠርን ትቶ ወደ ከተማ መምጣት ከፈለገ መሬቱን መሸጥ ስለማይችል ከሞላ ጎደል ባዶ እጁን ወደ ከተመ መምጣት ስለሚሆንበት አያደርገውም። በዚህ ምክንያት 43 ዓመት በፊት የህዝባችን 85% የገጠር ነዋሪ ነበር አሁንም ወደ 80% የገጠር ነዋሪ ነው። የመሬት ፖሊሲው ባይኖር ይህ ቁጥር ዛሬ ምናልባት 60% ይሆን ነበር። እንደዚህ ቢሆን ኖር 80% ፋንታ 60% ነበር ስድስ ልግ የሚወልድው 20% ፋንታ 40% ሁለት ልግ ይወልዳል። በዚህ ምክንያት የጠቅላላ የህዝብ ቁጥር እድገት ይቀንስ ነበር።

2. ሀብት ምቾት ድሎት ከትመት (urbanization) በጠቅላላ ብልጽግና (development) በጨመረ ቁጥር የቤተሰብ መጠን ይቀንሳል። ይህ ንድፈ ሐሳብ (theory) ሳይሆን ያለፈው የ100 አመት የዓለም ታሪክ የመሰከረው እውነታ ነው። በሀገርም በህብረተሰብም ደረጃ ይህ እውነታ ይታያል። ሀብታም ሀገሮች ብዙ አይወልዱም ከነሱም የሚወልዱት ካልበለጸጉ ሀገሮች የመጡ መጤዎች ናቸው። ማንኛውም ሀገር አማካይ ሀብቱ በጨመረ ቁጥር የቤተሰብ መጠኑ ይቀንሳል። ስለዚህ በኢትዮጵያም «ብልጽግና» በጨመረ ቁጥር የሚወለደው ቁጥር ይቀንሳል። ስለዚህ አሁን እንቀንሰው ብሎ መርሯሯጥ አያስፈልግም።

3. የህዝብ ብዛት ሀብት ነው። የምዕራብ ሀገሮች ፍልሰትን (immigration) የሚጋብዙት ምክንያት የሰው እጥረት ስላላቸው ኤኮኖሚያቸው እየተጎዳ ስለሆነ ነው። የአዲስ አበባ ኤኮኖሚ የሚንርበት አንዱ ምክንያት ከገጠር ወደ ከተማ ያለው ፍልሰት ነው። የሰው ኃይልና የሸማች (consumer) ቁጥር በመጨመረ ቁጥር የኤኮኖሚ እንቅሳሴ ይጨምራል። በውጭ ግንኙነት አንጻርም ብዙ ህዝብ ያለው ሀገር በዓለም ላይ ያለው ኃይልና ሚና ይጨምራል። የኢትዮጵያ የዝብን ቁጥር በአባይ ግድብ ላይ ያለው ሚና ትንሽ አይደለም። ስለዚህ የህዝብ ብዛት እንደ እንቅፋት ብቻ መታየት የለበተም።

4. ኢትዮጵያ ገና ብዙ የህዝብ ቁጥር ማስተናገድ የምትችል ሀገር ናት። ካላት ለም መሬትና ሌሎች የተፈጥሮ ምንጮች አንጻር ምናልባት እስከ 200 ሚሊዮን ትችላለች። ጃፓን የኢትዮጵያ አራት እጥፍ ሰው በካሬ ኪሎሜትር አላት። ስለዚህ ኢትዮጵያ ትጨናነቃለች ብለን ልንሰጋ አይገባም።

ከዚህ አልፎ ተርፎ እንደ ኦርቶዶክስ ክርትያን የህዝብ ቁጥርን «መቆጣጠር» የሚባለው ነገር ያሳስበኛል። በተለይ የወሊድ መቆጣጠርን ማስፋፋት ያሳስበኛል። እንደዚህ አይነት ጉዳይ ውስጥ መግባት ትዕቢትን ነው የሚጋበዘው። እራሳችንን እንደ አምላክ እንድናይ ይፈትነናል። ከእግዚአብሔር የሰጠንን የተፈጥሮ ተልእኮ እንድንወጣ ይፈትነናል። ለዚህም ነው የሃይማኖት አባቶቻችን በሙሉ የቃወሙታ። ይህን መጠቀም ከሰው ተልእኮና ማንነት ይጋጫል ማጣት ነው ይላሉ። እርግጥ ካህናት በእረኝነት ሚናቸው በአንዳንድ አጋጣሚዎች የሃይማኖት ልጆቻቸውን እንዲጠቀሙ ሊፈቅዱ ይችላሉ ግን በጠቅላላ ከተቻለ አይመከርም። የስጋ ግንኙነትና መውለድ በተፈጥሮ የተገናኙ ናቸው ማለያየት ለሰው ልጅ ጎጂ ነውና።

ይህን እያወቅን የህዝብ ቁጥር እድገት እንዲቀንስ ተግባራዊ ስራዎች እናካሄድ ማለት ይከብደኛል። በተለይ በወሊድ መቆጣጠርያን በመጠቀም እንቀንስ ማለት ይከብደኛል። ለተጠቃሚው መንፈስ ጎጂ ነው ብዬ የማምነው ነገርን ማስፋፋት ህሊናዬ አይፈቅድልኝም። ሰዎች በገዛ ፍቃዳቸው ቢጠቀሙ ልፈርድባቸው አይገባም አልችልም «መብታቸው» ነው። ግን እንደ መንግስት መርህ ይህን ማስተዋወቅና ማስፋፋት ጎጂ ነው ብዬ ነው የማምነው። የቤተሰብ መጠንን ይቀንሳል ግን የመንፈሳዊ ጉዳቱ በምዕራቡ ዓለም የምናየው ኢትዮጵያ ውስጥ ማየት አልፈልግም። አዎ ዛሬ በሀገራችን በደምብ ተስፋፍቷል ግን መንግስት ከዚህ ጉዳይ እራሱን ቢያወጣ እወዳለሁ።

አልፎ ተርፎ ከላይ እንደጠቀስኩት በኔ እምነት የህዝብ ቁጥራችን አሳሳቢ ጉዳይም አይደለም። ክትመት ብልጽግና በጨመሩ ቁጥር የህዝብ ቁጥር እድገት ይቀንሳል። ቻይና ለ40 አመት ህዝቧ እንዳይወልዱ አድርጋ አሁን የህዝብ ቁጥራችን አንሶ አሳስቦናል ትላለች! እንማር!

ሀገራችን ገና «አልሞላችም»። ስለዚህ ትኩረታችንን ወደ ሌሎች የኤኮኖሚ የፖለቲካ የመሐበረሰብ ጉዳዮች ይሁን። እነዚህን ጉዳዮች በማሸነፍ የህዝብ ብዛት ጉዳያችንም በራሱ ይስተካከላል።

Tuesday, 3 April 2018

ሃይማኖታዊ መቻቻል

በዚህ ዘመን የቃላቶች ትርጉም ተተንቅቀን ነጣጥለን ማየት አለብን።

እስቲ በመጀመርያ «መቻቻል» ምን ማለት እንደሆነ እንመርምር። ሰው የሚወድውን ነገር «ቻለው» ይባላል? አይባልም! የማይወደውን ግን በተለያዩ ምክንያቶች ስለነገሩ ምንም ማድረግ የማይችለውን ወይም ማድረግ የማይፈልገውን ነገር ነው «ቻለው» የሚባለው።

ለምሳሌ… ሙስሊም ጎረቤቴ በየጊዜው ድምጽ የበዛው የጸሎት ዝግጅት ያካሄዳል ከበቱ። ጩኸቱን አልወደውም ግን ለሰላም ብዬ ዝም እላለሁ። ይህ የመቻቻል አንድ ምሳሌ ነው።

እዚ ጋር አንድ ነገርን ልብ እንበል። ጎረቤቴን ዝም ያልኩት ስለምወደው ወይም ጥሩ ልሁንለት ብዬ አይደለም። «ነግ በኔን» አስቤ ነው። ለራሴ ጥቅም ብዬ ነው። እኔም ዝግጅቶችህን ተው ብዬ አላስቸግረውም እሱም እኔ እንደዚሁ አይነት ፕሮግራም ባዘጋጅ ዝም ይለኛል። አልፎ ተርፎ ጸብ ስለሌለን ግንኙነታችን ሰላማዊ ስለሆነ ወደ ፊት በተለያዩ የሚጠቁሙን ጉዳዮች መተባበር መረዳዳት ቀላል ሊሆን ይችላል።

ስለዚህ «መቻቻል» የአብሮ መኖር ስልት ነው። የጥሩነት ወይም በጎ መግባር ውጤት አይደለም የመዋደድ የፍቅርም ውጤት አይደለም።

መቻቻል እንዲህ ከሆነ ለኛ ኦርቶዶክስ ክርስትያኖች ምን ማለት ነው? መቻቻል አለብን ወይ? የሌላ ሃይማኖት ተከታዮችን «መቻል» አለብን ወይ? «የሃይማኖት መቻቻልን» መተግበር አለብን ወይ? በፍፁም! በመጀመርያ እንደ ክርስትናችን «መውደድ» ነው ያለብን። አምላካችን እንዳለን እሱ እንደሚወደን ያህል ባለንጀራችንን መውደድ አለብን። የኛ የክርስትያኖች ተዕልኮ «ፍቅር» ነው እንጂ «መቻቻል» አይደለም! ማንም ሰው ከልምድና ምቾት አንጻር መቻቻል ይችላል፤ ግን ክርስትያኖች መውደድ ነው ያለብን።

ወደ ቅድሙ ምሳሌአችን ከተመለሰን የሙስሊም ጎረቤቴን ስለ ጸሎት ዝግጅቶቹ የማላስቸግረው ምክንያት «መቻቻል» ሳይሆን «ፍቅር» ነው መሆን ያለበት። ስለ ዝግጅቱ ካላማረርኩኝ አለማማረሬ ከፍቅር የመነጨ መሆን አለበት እንጂ ለራሴ ጥቅም ብዬ መሆን የለበትም። እሱም ይሉኝታ ኖሮት ዝም ይለንኛል ብዬ ከሱ ጠብቄ ሳይሆን ምንም ሳልጠብቅ ምሆን አለበት። ስለዚህ ክርስትያኖች መቻቻልን መተግበር አለባቸው ማለት ትርጉም የለውም። ከመቻቻል በላይ ሰማይ ጠቀሱን ፍቅር መተግበር ነው ያለን።

እንግዲህ አንዳንዶቻችሁ «አምላካችሁ ውደዱ ቢላችሁም አትሰሙትም» ትሉኝ ይሆናል። «እናንተ ኦርቶዶክስ ክርስትያኖች ድሮም አሁንም ፍቅርን አታውቁም።» አልክድም፤ እውነት ነው፤ እኔ ኦርቶዶክስ ክርስትያን ብሆንም ኃጢአተኛ ነኝ ፍቅር ይጎለኛል። ፍቅር የሆነውን ተልዕኮኤን ሁል ጊዜ እየሳትኩኝ ነው የምኖረው። ይህ ኃጢአተኝነቴ ግን የሚስተካከለው ወይንም በትክክሉ ቋንቋ የሚታከመው መቻቻልን መተግበር በመሞከር አይደለም። ፍቅርን በመተግበር ነው። ካልቻልኩኝ ከወደቅኩኝ ተመልሼ መሞከር መነሳት ነው። ይህ ነው የክርስትና ኑሮ። እንጂ መውደድ አልችልም ብዬ ተስፋ ቆርቼ እስቲ መቻቻልን ልሞርክ ማለት ውድቅ ሀሳብ ነው።

ስለዚህ ፕሮቴስታንት ወንድሜ፤ ሙስሊም እህቴ፤ ሴኩላሪስት ወንድሜ፤ ካስቀየምኩህ ካስቸገርኩህ ከጎዳሁህ እኔን ኃጢአተኛውን ይቅር በለኝ። መሻሻል እሞክራለሁ። ልችልህ ሳይሆን በእግዚአብሔር እርዳታ ልወድህ እሞክራለሁ።

Wednesday, 7 December 2016

የተማረ ገደለን

የኢትዮጵያ ወዳጅ ዶናልድ ሌቪን (ነፍሳቸውን ይማረው) ከ50 ዓመታት በፊት ጅምሮ ባህልንና ማንነትን የማያከብርና የሚክድ ህብረተሰባዊ ለውጥ አገር አፍራሽ ነው እያሉ ኢትዮጵያዊያንን ያስጠነቅቁ ነበር። ኃይለ ሥላሴ ወደ ምዕራብ አገር የላኳቸው ተማሪዎች በኢባህላዊ የሆነ  ከራስ ጋር የሚያጣላ ርዕዮት ዓለም ተነክረው ወደ አገራቸው ሲመለሱ በአስተሳሰባቸው ሰውዉን አስተንግጠዋል። አቶ ዶናልድ ሌቪን አንድ ያጋጠማቸውን እንደዚህ አስታወሱ ነበር፤ አንዱን «የተማረ» ምሁራንን እንደዚህ ብለው ጠየቁት «እንደምትመኘው የሶሽያሊስት አብዮት ቢካሄድ በሚሊዮን የሚቆጠር ህዝብ እንደሚሞቱ ታውቃለህን?» ይህ የተማረ ምህር «በ10 ሚሊዮንም ቢሞቱ ይህን ርዕዮት ዓለምን ለማድረስ ስለሆነ ያዋጣል» ብሎ መለሰላቸው። ከራስ ባህል፤ ወግ፤ ትውፊት፤ ምንጭና ማንነት መራቅ እንደዚህ አይነቱን ቅዠታዊ አስተሳሰብ ነው የሚያመጣው።

ዛሬም ይህ አይነት የቀለም ትምህርት አምልኮ ለኢትዮጵያ ዋናው አጥቂና ጠላት ነው። የምዕራብ ዘመናዊ የቀለም ትምህርት በአገራችን እንደ ጣዎት እንደሚመለክ የሚገልጸው በኃይለ ሥላሴ ዘመን የተሰየመው አባባል «የተማረ ይግደለኝ» ነው። ይህ ዛሬም በኢትዮጵያዊያን ጭንቅላት ይንጸባረቃል። ፖለቲካችንን ካየን አብዛኛው የሚንጸባረቁት ሃሳቦችና አስተያየቶች ከኢትዮጵያ ውጭ የመነጩ ናቸው። የኛ ምሁራኖች እነዚህ ሃሳቦችን እየሰገዱላቸው ኢትዮጵያን ወደ እኒዝህ ርዕዮት አለምን ማስተካከል ይፈልጋሉ። ቢያንስ መደረግ የነበረበት እነዚህን ርዕዮት ዓለሞችን ለኢትዮጵያ እንዲሆኑ ማስተካከል።

ይህ አቋሜን የሚደግፉ አንዳንድ ማስረጃዎች እንመልከት። በመጀምርያ ወደ ኋላ ሄደን የኃይለ ሥላሴ መንግስትን ተመልስን እንመልከት። የዛን ጊዜ ውጤቶች ዛሬ ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ ስለሆነ። በሳቸው መንግስት ዘመነ የምዕራብ «ዘመናዊ» ትምህርት በኢትዮጵያ ውስጥ ተስፋፋ። ተማሪዎች በሞላ ጎደል አለምንም መበረዝ ቀጥታ የምዕራብ ትምህርት ነበር የሚማሩት። ስለአገራቸው ጥቂት ውይም ምንም ነገር ሳይማሩ ይመረቁ ነበር። ለምሳሌ ስለ ዓለም ዙርያ መልክአምድር ተምረው ስለኢትዮጵያ መልክአምድር ምንም አያቁም ነበር! ስለራሳቸው ታሪክ፤ ትውፊት፤ ባህልና ሃይማንቶ አይማሩም ነበር። ሳይታወቅ ግራ የገባው ከፊል ኢትዮጵያዊ ከፊል ፈረንጅ የሆነ ትውልድ ተወለደ። የዝቅተኛ መንፈስ ያደረበት ትውለድ ተፈጠሪ። ሳያውቀው እራሱን የሚንቅና የሚጠላም ትውልድ ተፈጠረ። ግን ከዚህ ትውልድ ልጆች መካከል ግማሾቹ ኢትዮጵያዊነታቸው ቢሸረሸርም ለኃይለ ሥላሴ ታማኝ ነበሩ በሳቸውም «የዘመናዊ ስልጣኔ እቅድ» ይስማሙ ነበር። ሌሎቻቸው ግን እንኳን ታማኝ ለመሆን ጠላት ሆነው ተገኙ። አገሪቷን ያስከወሰ አብዮትን አስነሱ። ሁላችንም እንደምናውቀው ይህ አብዮት በአገራችን አስፈላጊ የሆኑ ለውጦችና መስተካከሎች ከማምጣት ፋንታ በጸረ ኢትዮጵያ የሆነውን በምዕራባዊያኑ ርዕዮት ዓለም በኮምዩኒዝም ስር አገራችንን እንድትወድቅ አደረጋት።

በደርግ ዘመነ መንግስት ደግሞ አብዛኛው የኢትዮጵያ የፖለቲካ ንቅናቀዎች የጸረ ኢትዮጵያ አቋምና ርዕዮት ዓለም ይዘው ነበር የሚራመዱት። ጸረ ሃይማኖት ነበሩ። ጸረ ባህልና ጸረ ትውፊት ነበሩ። እርግጥ በዛን ዘመን ሙዚቃ ጭፈራ ወዘተ «ትስፋፍቷል»። ግን የተስፋፋው በምዕራባዊያን አመለካከት ዘንድ ነው - ስር የሰደደ የማንነት የሆነ ሳይሆን እንደ ልብስ ከላይ የሚለበስ ወይም እንደ ቴአትር የሚታይ ነበር። በመጀመርያ ኮምዩኒስት ነን፤ ግን እስክስታ የምንጨፍር ኮምዩኒስት ነን! በጠቅላላ አብዛኛው ፖለቲከኞችና ምሁራንም የኢትዮጵያ ማንነት መቀየር አለበት ብለው የሚያምኑ ነበሩ።

በኢህአዴግ ዘመን ይህ ወደ ውጫዊ አመለካከት ማድላት ወደ ጸንፍ ደረሰ። በሶሺአሊዝም የተሞላ በጎሳ የተመሰረተ ጸንፈኛ ህገ መንግስት በኢትዮጵያ ተጫነባት። ይህ ክስተት ከኢትዮጵያዊ «የተማረ» ኃይል በተደጋጋሚ የሚታይ አንድ ጸባይን በደምብ ያብራራል። ይህ ጸባይ ጸንፈኝነት ነው። የኢትዮጵያ መሰረታዊ ችግር የብሄር እኩልነት ነው ብሎ ቢታመንም ቋንቋ፤ ባህል፤ መልክአ ምድር፤ ጎሳም የሚያካተት ግን ለዘብተኛ የሆነ ህገ መንግስት ሊመሰረት ይቻል ነበር። ግን ያኔ የነበሩት ኃይሎች ጸንፍ ካልያዝን አሉ! በምድረ ዓለም ታይቶ የማይታውቅ አይነት ህገ መንግስት - ከሶሺያሊስት በላይ ሶሺያሊስት የሚያሰኝ ህገ መንግስት ካልደነገግን አሉ። ጭራሽ ከደቡብ አፍሪካ በቀር የሌለውን ጎሳ በመታወቅያ ጀመሩ! ሁላችንም እንደምናውቀው እስካሁን ይህ መርዝ ነው እያሳመመን ያለው።

ይህ ሁሉ ሆኖ የአገራችን ገዥም ተቃዋሚም ፖለቲከኞችና ምሁራን አሁንም ውጫዊ በተለይ ምእራባዊ አመለካከት ነው ያላቸው። ገዝ ፓርቲ «ዘመናዊነት» የሚባለው አመለካከት ነው ያለው። ሃይማኖት ኋላ ቀር ነው። እግዚአብሔር ሳይሆን ሰው ነው የዓለም ቁንጮ። ባህል፤ ትውፊትና ወግ ውሸት ናቸው። ህዝብ ባህልን ትቶ ወደዚህ አይህነት አመለካከት እስኪ ገባ ድረስ እንደ ያላደገ ህጻን ነውና እኛ ስልጣን ተቆጣጥረን ልናሳድገው ይገባል። ካደገ በኋላ፤ ማለት እንደኛ የ«ዘመናዊ» አስተሳሰብ ካደረበት በኋላ - ስልጣናችንን እንለቃለን። በሌላ አባባል ኢትዮጵያዊነቱን አርግፎ ከኛ ይበልጥ «ያደጉትንና የሰለጠኑትን» ምእራባዊያን ከመሰለ በኋላ ነው ሰው የሚሆነው። ይህ ራስን ማንነትን መጥላት ካልሆነ ምንድነው?

ተቃዋሚው ደግሞ እንደ አሜሪካ ወይም እንደ አውሮፓ እንሁን ነው! (በጅምላ እየተናገርኩኝ ስለሆነ ይቅርታ።) የኢትዮጵያዊነት ራዕይ የለውም። እርግጥ አንዳንድ ጥሩ የሆነ ሃሳቦች እንደ ገዳ አሰራር አጥንቶ በተወሰነ መጠቅም ተነስተዋል። አንዳንዱም ደፋር የንጉሳዊ አስተዳደር (በወግ ደረጃ ብቻ ቢሆንም) ይመለስ የሚሉ አሉ። እነዚህ ሃሳቦች በርካታ ውይይትና ክትትል ያስፈልጋቸዋል ከነዚህ አይነቱ ባህላዊ መንገድ ነውና የአገራችን ውበት የሚመለሰው።

በብዙሃኑ ደረጃ ደግሞ ቤተሰብ ልጁን የምእራባዊ ባህልና ቋንቋ ለማስተማር ይሯሯጣል! ለልጁ ከቀለም ትህምሕርት በላይ በዚህ ዓለም ምንም የለም የሚል መልክት ነው ደጋግሞ የሚያስተላልፍለው። ልጁም የቀለም ትምሕርትን ጣኦት አድርጎታል። ከዛ በኋላ የልጁ አኗኗር ግራ የገባው ሲሆን፤ ትምሕርትና ስራ አለው ግን በሌላው ንሩው ያልተረገጋ መሰረተ ቢስ የሆነ ሲሆን - ወላጅ ግራ ይገባዋል። የዛሬው ትውልድ እንደዚህ ነው እንደዛ ነው ብሎ ያማርራል። ታድያ ባህሉን ያልወረሰ ሰው ሁልጊዜ ኑሮው እንደሚናወጥ አናውቅምን?

በትህትና ባይመስልም ግን የትህትና ምክሬ እንደዚህ ነው። በመጀመርያ የዘመናዊ ትምህርት ምን ያህል ጸረ ባህል፤ ጸረ ትውፊት፤ ጸረ ማንነት፤ ጸረ ኢትዮጵያ እንደሆነ እንረዳ። ሞያ፤ ሳየንስና ቴክኖሎጊ ችግር የለውም ከጥንትም የነበሩ ዘርፎች ናችሀው ከምንምም ጋር አይጋጭም። አደገኛው ግን «ዘመናዊነት» የሚባለው ርዕዮት ዓለም ነው። ቅድም የጠቀስኩት ጸረ ሃይማኖትና ጸረ ባህል የሆነ አስተሳሰብን እንደ መርፌ ይወጋል። ይህን አውቀን ስንዴውን ከንክርዳዱን መለየት አለብን። ጠቃሚውን ትምህርት እየተማርን ጎጂውን እራሳችንን እንድንጠላ የሚያደርገውን ለይተን አውቀን እንተው። የምንማረውን በባህልና ሃይማኖታችን መነጽር ወይም አመለካከት እንማረው። ለልጆቻችንም እንደዚሁ።

ይህ ነው ምክሬ። ዶናልድ ሌቪን እንዳሉት - ክሁሉ ጥቅሳቸው ይህን ነው እጅግ የምወደው - "The vitality of a people springs from feeling at home in its culture and from a sense of kinship with its past. The negation of all those sentiments acquired in childhood leaves man adrift, a prey to random images and destructive impulses…" ከኔ የምትሻሉት ተርጉሙት!