Showing posts with label የኢትዮጵያ ብሄርተኝነት. Show all posts
Showing posts with label የኢትዮጵያ ብሄርተኝነት. Show all posts

Friday, 14 September 2018

ከፍሬያቸው ታውቋቸዋላችሁ…

…ከእሾህ ወይን ከኩርንችትስ በለስ ይለቀማልን?

ሌላ ሰውን በኛን ሃሳብ ለማሳመን ስንሞክር ከአንደበታችን ይልቅ ስራችን ማለትም ምሳሌአችን ነው ዋና ሚና የሚጫወተው። ምንም ጥሩ ሃሳቦች ቢኖሩን፤ ምንም ጥሩ አቀራረብ ቢኖረንም፤ ሃሳባችንን በተግባር የምናውል ጥሩ ምሳሌ ካልሆንን ማንም አይሰማንም፤ አያምነንም፤ አይከተለንም።

በ«ኢትዮጵያዊነት» ወይንም በ«ኢትዮጵያ ብሄርተኝነት» የምናምነው ይህን ነጥብ ጠንቅቀን ብናሰብበት ጥሩ ይመስለኝም። የኛም የኢትዮጵያም ህልውናን ይመለከታልና። የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ፖለቲካ ታሪካችን የእርስ በርስ (አለ ጥሩ ምክንያት) መቃረን እና መጋጨት ነው (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/07/blog-post_31.html)። በኃይለ ሥላሴ ዘመን ሹማምንቶቹ እየተጣሉ ለፍርድ እና ለዳኝነት  ጃንሆይ ደጅ ረዥም ሰልፍ ይሰለፉ ነበር። ዛሬም የፖለቲካ ድርጅቶቻችን ከሚገባው ማለትም ብዙሃን ደጋፊዎቻቸው ቁጥር አንጻር እጅግ ደካማ ናቸው የመሰባሰብ፤ መወያየት፤ መስማማት እና መተባበር አቅማችን ደካማ ስለሆነ። ይህ የሚያሳየው የኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች የረዥም ዓመታት የንትርክ፤ የመጣላት፤ የአለመተማመን ወዘተ ታሪክን ነው።

ይህን ታሪክ ሁሉም አይቶታል እና ያውቀዋል። በተለይም የጎሳ ብሄርተኞች (ጸንፈኛም ለዘብተኛም) የሚባሉት ከኛ «ተቃራኒ» የፖለቲካ አቋም ያላቸው ይህንን የኛ ደካማ የፖለቲካ ጠባይ አይተውታክ። ንቀውናልም ማለት ይቻላል። በአንጻሩ እኛ እነሱን «ዘረኛ አትሆኑ»፤ «በግለሰብ እኩልነት እና መብት እመኑ፤ «ከኛ ሰላማዊ እና ፍትሃዊ አቋም ተማሩ» ወዘተ እንላቸዋለን። ግን በጎሳ አስተዳደር የሚያምኑት እኛን የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ሲያዩ እርስ በርስ ስንጣላ እና ስንለያይ ነው የሚያዩት። ከኛ ጥሩ ምሳሌ አያዩም። ታድያ እንዴት እኛ የምንለውን ሊያምኑ እና ሊከተሉ ይችላሉ። ይከብዳቸዋል።

ግን እኛ ጥሩ ምሳሌ ብንሆን፤ የፖለቲካ ጎራችን ንፁ ቢሆን፤ እርስ በርስ ያለን ግንኙነት በፍቅር እና በሰላም የተሞላ ቢሆን የጎሳ ብሄርተኞችም ሌሎችም ወደኛ አቋም ይበልጥ ይሳቡ ነበር። «የነሱ አስተሳሰብ ይህንን ሰላም እና ስልጣኔ የሚያመጣ ከሆነ እኛም ወደነሱ እንጠጋ እና ከዚህ ብልጽግና እንካፈል» ይሉ ነበር። «እውነትም ፖለቲካ አቋማቸው ልክ መሆን አለበት» ይሉ ነበር።

ስለዚህ አሁን ባለው እና በሚመጣው የፖለቲካ ግንባታ እና ውድድር በደንብ ከመግባታችን በፊት እኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች መጀመርያ እራሳችንን መፈተሽ አለብን። ቀጥሎ የነ ጠ/ሚ አብይን ምሳሌ ተከትለን ንስሃ ገብተን ይቅርታ መጠየቅ ያለብን ይመስለኛል በህዝቡ ዘንድ እምኔታ ለማግኘት እና ህሊናችንን ለማርካት። እኛ ፍፁም ነን ችግሩ ከኢህአዴግ፤ ህወሓት፤ ደርግ ወዘተ ነበር ማለቱ ልክ አይደለምም አዋጪም አይደለም። እውነታ የሆነውን የኛ ታሪካዊ ጥፋቶችን ልክ እንደ ጠ/ሚ አብይ አምነን፤ ተቀብለን መናገር አለብን። ከዚህ በኋላ ነው የፖለቲካ እንቅስቃሴአችን ውጤታማ መሆን የሚችለው።



Tuesday, 31 July 2018

ከኢትዮጵያ ብሄርተኞች (አንድነት ኃይሎች) የእርስ በርስ መጠፋፋት ታሪክ እንማር!

ኢትዮጵያዊነትን የምናራምድ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ባለፉት 60 ዓመታት በተደጋጋሚ እርስ በርስ መጣላት ሀገራችንን አደጋ ላይ መጣላችን ይታወቃል (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/07/blog-post_15.html)። መቼም በዚህ እፍረታችን ምክንያት የሀገራችንን ችግሮች በሌሎች (ጎሳ ብሄርተኞች፤ የውጭ ኃይሎች ወዘተ) ማሳበብ ሱስ ቢሆብንም እውነቱ የኛ ጥፋት መሆኑን መቀበል ግዴታችን ነው። ለሀገራችን ችግሮች ዘላቂ መፍትሄ የኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች አንድነት እና ታላቅ ተሳትፎ አስፈላጊ መሆኑ የታወቀ ነው።

ከዚህ ጽሁፍ ትምሕርት እንዲሆነን እና ወደ ፊት ስህተቶቻችንን እንዳንደግም ዘንድ ወደ ኋላ ሄጄ እኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች እርስ በርስ የተፋጀንበት ታሪኮችን ማስታወስ እወዳለሁ። ዛሬ በሀገራችን ፖለቲካ ታላቁ ጉዳይ የጎሳ ብሄርተኝነት ስለሆነ እኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ከታሪካችን ተምረን ለሚመጣው የፖለቲካ ሂደት በደምብ መዘጋጀት አለብን። አሁን ያለንን የታሪክ እድል መጠቀም ግድ ነው። እግዚአብሔር ከዚ በኋላ ሌላ እድል ላይሰጠን ይችላልና።

እንሆ ላለፉት 60 ዓመታት የኢትዮጵያ ብሄርተኞች እርስ በርስ መጣላት ታሪክ ዝርዝር፤

1. የነ መንግስቱ ነዋይ እና ግርማሜ ነዋይ የመንግስት ግልበጣ ሙከራ (1953)፤ አስፈላጊ ለውጦችን ለማምጣት ባለው መዋቀር ውስጥ በትእግስት ከመስራት ፋንታ ግርማሜ በውጭ ሀገር በተማረው «ማርክሲዝም» ፍልስፍና ተመስርቶ ወደ «ስር ነቀል ለውጥ» ወይንም አብዮት አመራ። ይህ የተከሰተው ኃይለ ሥላሴ ወደ ሀገራቸው ከተመለሱ ገና 18 ዓመት ካላፈ በኋላ ነው። ኢትዮጵያ ገና አቅም የሌላት ደሃ ሀገር ነበረች። ግርማሜ እና ደጋፊዎቹ ኃይለ ሥላሴ ወደ ውጭ ሀገር እንዲማሩ ከላኳቸው ተማሪዎች ነበሩ። ይህ ነበር የመጀመርያው ጊዜ የኃይለ ሥላሴ የፈረንጅ ትምሕርት ፖሊሲ በራሳቸው ላይ ጥቃት ያመጣባቸው። የኃይለ ሥላሴ መንግስት ከዚህ ተምሮ አስፈላጊ ለውጦችን ከማድረግ ፋንታ ስልጣንን ይበልት ሰበሰባ ለሰላማዊ የፖለቲካ መፍትሄ ከፍተቶችን ዘጋ።

2. የተማሪዎች ንቅናቄ፤ ከነመንግስቱ ነዋይ ግልበጣ ሙከራ በኋላም የኃይለ ሥላሴ መንግስት ተማሪዎችን ለትምሕርት ወደ ውጭ ሀገር መላክ አላቆመም። የኢትዮጵያን ባህል እና ትውፊት ከማስተማር ፋንታ የምዕራባዊ ፍልስፍና እና ሶሺያል ሳየንስ እንዲማሩ አደረገ። እነዚህ ተማሪዎች ኢ-ኢትዮጵያዊ አስተሳሰቦች ይዘው ወደ ኢትዮጵያ መንግስት እና ሌሎች መስርያቤቶች ገቡ። የቀለም ትምሕርት አለአግባብ በመደነቁ ምክንያት «የተማረ ይግደለኝ» የሚለው አባባል ተፈጠረ (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2016/12/blog-post_7.html)። ይህ እሳት እየተለኮሰም መንግስት በትምሕርትም ደረጃ በፍትህ በተለይም በመሬት ፍትህ ዘርፍ ምንም አላደረገም። የኃይለ ሥላሴ መንግስት የኢትዮጵያ ለረዥም ዓመታት መርዝ የሚሆናት ትውልድ እና ባህል ፈጠረ። የ«ጨቋኝ ተጨቋኝ» አስተሳሰብ እንዲሰፍን አደረገ። የመደብ እና የጎሳ ጦርነት እንዲጀምር አደረገ። ዛሬ የዚህን "legacy" ነው የወረስነው።

3. የደርግ አብዮት፤ በኃይለ ሥላሴ መንግስት ተሃድሶ የሚፈልጉ በርካቶች ነበሩ ግን እድሉ ሳይደርሳቸው የተማሪዎች ንቅናቄ የሚፈልገው ስር ነቀል አብዮት መጣ እና ሀገሪቷን አፈነዳ። በርካታ ልሂቃን ተገደሉ ተሰደዱ። ለኢትዮጵያ ብቻ ስያሆን ለማንም ሀገር የማይሆን የፖለቲካ ፍልስፍና ሰፈነ። መሰረታዊ ነገር እንደ «መሬት ለአራሹ» ወደ «መሬት ለመንግስቱ» ሆኖ ቀረ። ኢትዮጵያ በደምብ ቁልቁል መውረድ ጀመረች። የደርግ በኃይል የተመሰረተ ጨቋኝ አገዛዝ ለጎሳ ብሄርተኞች በንዚን ሆናቸው እና በደምብ መንቀሳቀስ ጀመሩ። ድሮ በቀላሉ በትናንሽ ሰላማዊ ለውጦች መስተካከል የሚችሉት የጎሳ ጉዳዮች ወደ ጦር ሜዳ ገቡ።

4. የኢዲዩ መፈራረስ፤ ማርክሲስት ያልሆኑት የደርግ ተቃዋሚዎች በኢዲዩ ድርጅት ስር ለመታገል ወደ ሱዳን ገቡ። ከሞላ ጎደል አንድ አቋም እና አንድ አመጣጥ ኖሯቸውም እርስ በርስ መስማማት ባለመቻላቸው ከትንሽ ጊዜ በኋላ ተበታተኑ። ይህ በአንድ አቋም ያላቸው ኢትዮጵያ ብሄርተኞች መካከል እርስ በርስ መጣላት ታሪክ እስካሁን እየተደጋገመ ነው።

5. የኢህአፓ፤ መኢሶን፤ ደርግ ግጭት፤ እንዴ ማንኛውም የማርክሲስት አብዮት አብዮተኞ የፍልስፍና፤ የጥቅም እና የስልጣን ልዩነቶቻቸውን በተብ መንጃ ነው እነ ኢህአፓ፤ መኢሶን፤ ደርግ እና ሌሎች የተወጡት። የእነዚህ ድርጅቶች አብዛኛው አባላት በ«አንድ ኢትዮጵያ» የሚያምኑ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ነበሩ። እነ ኢህአፓ በመገንጠል እናምናለን ቢሉም ብዙ ኤርትራ እና ትግራይ ብሄርተኞች ቢኖሯቸውም አብዛኞቻቸው ኢትዮጵያ ብሄርተኞች ነበሩ። መኢሶንም የኦሮሞ ብሄርተኞች ቢኖሩትም አብዛኛው በአንድነት ያሚያምን ነበር። ደርግም እንዲሁም የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ስፍራ ነበር። ሆኖም የነዚህ ድርጅቶች መፋጃጀት ለጎሳ ብሄርተኞች ታላቅ ድል ሆነ። የኢትዮጵያ ብሄርተኛው እርስ በርስ ሲተላለቅ የጎሳ ብሄርተኛ እየቀረ ሄደ ካስፈለገ ወደ ሻዕብያ፤ ህወሓት እና ኦነግ ገባ። ቀይ ሽብሩ ካበቃ በኋላ የተቆሳሰለች ኢትዮጵያ ናት የቀረችው። በጎሳ ብሄርተኞች ለመገዛት ዝግዱ የሆነች ደካማ ኢትዮጵያ ናት የቀረችው። ደርግ ከስልጣን ሲወርድ የኢትዮጵያ ብሄርተኛ ልሂቃን ራሱን አጥፍቶ ርዝራዡ ብቻ ነው የቅረው። ብዙሃኑም የፖለቲካ ልቡ ተስብሮ እየተንገዳገደ ነበር። የኢትዮጵያ የወደፊት የጎሰኝነት ዘመን ተወሰነላት።

6. የመላው አማራ እና መላው ኢትዮጵያ ፓርቲዎች ግጭት፤ ደርግ ኤኮኖሚውን ገድሎ፤ ህዝቡን አጥፍቶ፤ የሶቪየት ህብረት ሲፈርስ ገንዘብ አጥቶ እነ ሻዕብያ እና ህወሓትን ወደ መንግስት አስገባ። የኢትዮጵያ ብሄርተኛው ጎራ እራሱን አትፍቶ ሜዳውን ሙሉ በሙሉ ለጎሳ ብሄርተኞቹ ተወ። እነሱም ደንግጠውም ቢሆን ያልጠበቁትም ቢሆን ሜዳውን ለመቆጣጠር ቶሎ ስራ ጀመሩ። የኢትዮጵያ ብሄርተኛ ጎራው ከድንጋጤው በኋላ ልደራጅ ሲል የለመደው አብሮ መስራት አለመቻል እርስ በርስ መጣላት በሽታው እንደገና ተነሳበት። «መላው ኢትዮጵያ» ይህን ወይንም «መላው አማራ» ይሁን አውራ ፓርቲአችን በሚለው ጥያቄ የኛ «ወታደሮች» በ«ጠላት ሜዳ» ላይ እርስ በርስ መጣላት ጀመሩ! ላለመስማማት መስማማት እና በጋራ ጥቅም አብሮ መስራት ፋንታ አንዳችን ብቻ ነው የሚቀረው ብለው እርስ በርስ ተፋጁ እና ሁለቱንም ድርጅቶች («መላው ኢትዮጵያም» «መላው አማራም») አደከሙ። የጎሳ ብሄርተኞች ከዳር ሆነው በሳቅ ሞቱ። ግን አሁንም እኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ጥፋታችንን ከማመን እነ ከመፍታት ፋንታ የጎሳ ብሄርተኞች ጥፋት ነው እነሱ ናቸው ያከፋፈሉን ብለን እንደ ህጻናት አሳበብን። እንሆ ችግራችንን ስላላመንን አልፈታነውም። አልፎ ተርፎ ይህን ስህተትን ወደፊት ለመድገም እራሳችንን አዘጋደን!

7. የቅንጅት ግጭት፤ ወደ ምርጫ 97 ስንገባ ጠ/ሚ መለስ ዘናዊ በተለያዩ ምክንያቶች ነጻ ምርጫ እናሸንፋለን ዓለም ያከብረናል ብለው ነጻ ምርጫ አወጁ። ድንቅ ውሳኔ ነበር አሁንም ይደንቃል። ግን በዛን ግዜ የኢትዮጵያ ብሄርተኛ ጎራው በራሱ ካመጣው ቁስሎቹ ገና አልዳነም ነበር። ጠንካራ ድርጅት ከሀገር ውስጥም ውጭም አልነበረም። የእርስ በርስ ጥሉ እንዳለ ነበር። በዚህም ምክንያት ነው የኢትዮጵያ ብሄርተኛው ወደ አንድ ስምምነት (ቅንጅት) የገባው በመጨራሻው ደቂቃ ከምርጫው ሶስት ወር በፊት! ግን አርፍዶ ቢዘጋጅም እንደምንም አድርጎ የኢትዮጵያ ብሄርተኛው ጎራ በምርጫው ተሳትፎ በሚደንቅ ሁኔታ አሸነፈ። ካሸነፈ ብኋላ የምናውቀው ፈተናዎች አጋጠሙት። እነዚህን ፈተናዎች በደምብ አድርጎ ወደቀ። በሰው የተፈጥሮ ባህሪ ጓዶች አብረው ሲታሰሩ ፍቅራቸው እና ትብብራቸው ይጨምራል። የቅንጅት መሪዎች ሲታሰሩ ጭራሽ እርስ በርስ ተጣሉ!ድርጅቱም ምን ያህል ባዶ እንደነበረ ታየ። ከላይ የተወሰኑ መሪዎች በ100 የሚቆጠሩ ነበሩ ከዛ በታች ግን መዋቅር የሚባል ነገር አልነበረም። መዋቅር ስል በይፋ ብቻ ሳይሆን በልብም አልነበረም። ስለዚህ መንግስት ቅንጅትን ሲያጠቃ በምርጫው 70% እንዳሸነፈ ድርጅት ጥቃቱን ጠንክሮ ከመቋቋም ይልቅ እንደ ምንም ድጋፍ የሌለው ድርጅት ቀለጠ። ቅንጅት አሸዋ ላይ የተገነባ ቤት መሆኑን አየን። ግን ለዚህ ሽንፈት ምክንያት እንደነበረ እንገንዘብ። የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ልሂቃን ከዛ በፊት ለ30 ዓመታት እርስ በርስ መፋጀት ታሪክ ምክንያት በጣም ሳስቶ ነበር። ለዚህም ነው ቅንጅት በተንሽ ግፊት የፈራረሰው። መሪዎቹ "cream of the crop" ሳይሆኑ ካለፈው 30 ዓመት የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ጎራ እርስ በርስ መጨራረስ የተራረፉ ነበሩ። ታሪካችን ምን ያህል እንደ ጎዳን አየን።

8. ዛሬ፤ አሁንም የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ጎራ እጅግ ደካማ ነው። አሁንም ሀገር ውስጥም ውጭም ብዙሀኑን በሚገባው የሚወክል ድርጅት የለውም። ግን ብዙሃኑ አለ ልሂቃን እየታገለ እንደሆነ የሚያሳየው እንደ ጠ/ሚ አብይ አህመድ አይነቱን ሰዎች ከዚህ ብዙሃን መውለዳቸው ነው።  እንጂ ከ27 ዓመት የጎሳ ብሄርተኝነት በኋላ ኢትዮጵያ እውነትም የብሄር ብሄረሰቦች እስር ቤት ብትሆን እና በርካታ የሀገር ብሄርተኛ ባይኖራት እንደ አብይ አይነቱ አይፈጠርም ነበር እንቋን ወደ ስልጣን መግባት። ግን ይህ ብዙሃን ልሂቃን ያስፈልገዋል። እነ ጠ/ሚ አብይ በርካታ እገዛ ያስፈልጋቸዋል። ቢያንስ እንቅፋት አያስፈልጋቸውም!

አንድ እንቅፋት ሊሆን የሚችለው አዲሱ የ«አማራ ብሄርተኝነት» (https://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/06/blog-post_14.html) ነው። የአማራ ብሄርተኝነት በኢትዮጵያዊነት አምናለው ይላል ግን  የኢትዮጵያ ብሄርተኛውን ጎራ የመከፋፈል እና የማድከም አዝማምያ አለው። የአስተያየት ልዩነት መልካም ነው በአንድ አንድ ነገር ሳይስማሙ አብሮ መስራት ይቻላል። ግን አሁን የሚታየው የአብሮ መስራት አዝማምያ ሳይሆን የጥሎ ማለፍ መንፈስ ነው። የአማራ ብሄርተኛው ጎራ አንዱ መፈከሩ የኢትዮጵያ ብሄርተኝነት ድርጅቶች ዋጋ የላቸውም ነው። ከኢትዮጵያ ብሄርተኛ ድርጅቶች ጋር አብሮ ከመስራት ያጣጥልዋቸዋል። ያው የነ ሻዕብያ፤ ህወሓት፤ ኦነግ ፎቶኮፕይ ማለት ነው። የህዝብን ብሶት በጎሳ ቤንዚን ለኩሶ የፖለቲካ ኃይል ማግኘት ነው። ልክ ህወሓት በመጀመርያ ነባር የጥግራይ ልሂቃንን እንዳጠፋ አንድ አንድ የአማራ ብሄርተኞች የኢትዮጵያ ብሄርተኝነት ድርጅቶችን ማጥፋት ይፈልጋሉ። እንደነ ኢህአፓ/መኢሶን/ደርግ የማርክሲስት ዜሮ ድምር ፖለቲካ ማለት ነው።

ይህ የሚመስልኝ ታሪክን መድገም ነው። የኢትዮጵያ ብሄርተኞች እንደገና እርስ በርስ ሲፋጁ የጎሳ ብሄርተኖች ስልጣን ይቆጣጠራሉ የኢትዮጵያ ብሄርተኛ ብዙሃን እንደገና መሪ አልባ ሆኖ ይጠቃል። ከታሪካችን ብንማር ይበጀናል። በዛሬው የፖለቲካ ለውጥ እግዚአብሔር የማይገባንን እድል ሰጥቶናል። እኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኛ ልሂቃን ምንም የሚጠቅም ነገር ሳናደርግ ከኢህአዴግ መሃል የለማ ቡድን ተነስቶ ለአንድነት መንፈስ ቆሟል። ታላቁ «ኢትዮጵያዊ» ዶናልድ ለቪን ደጋግመው እንዳሉት በርካታ እድሎቻችንን አበላሽተናል (https://scholarworks.wmich.edu/ijad/vol1/iss1/3/)። ይህን እድል ደግሞ ካበላሽን ታሪክ ለዘለዓለም ይወቅሰናል።

Sunday, 15 July 2018

የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ጥፋታችንን ካላመንን ካላስተካከልን ኢትዮጵያን ዳግም እንሸጣታለን

ያለፉት 60 ዓመት የኢትዮጵያ ብሄርተኛ የፖለቲካ ጎራው ታሪክ እጅግ አሳዛኝ እና አሳፋሪ ነው። ከዛ በፊት እስከ ወደ 1955 ሀገራችን ዓለም ዙርያ የተከበረች ነበረች። በዲፕሎማሲ፤ በሀገራዊ ኃይል ወዘተ ከአቅሟ በላይ የምትሰራ ነበረች። አንድ አንድ ምሳሌዎች፤

1. የበርካታ የዓለም ሀገሮች ተቃውሞ በላቀ የዲፕሎማሲ ስራ አሸንፋ ኤርትራን ወደ ኢትዮጵያ መለሰች። ይህ የዲፕሎማሲ ድል ከሀገራችን ከአቅማችን አስር እጥፍ በላይ ነበር ግን አደረግነው።

2. የአፍሪካ ቁንጮ ሆንን ሁሉም የአፍሪካ ሀገራት እኛን እንደ ምሳሌ ያይን ነበር። በዲፕሎማሲ እና ሀገር ኃይል ደረጃ ብቻ ሳይሆን በታሪክ እና ባህል። ይህ ክብሬታ ለኢትዮጵያ ብዙ ጠቅሟታል።

3. በዓለም ዙርያ ያሉት ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያኖች ስብሰባ አቀደች የኦሪዬንታል ኦርቶዶክስ ስብሰባውን አከናወነች ስምምነቶች አስፈጸመች።

ከ1955 አካባቢ በኋላ ግን እኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኖች እርስ በርስ በመጣላት ሀገራችንን ድራሹን አጥፍተናል። መጀመርያ አስፈላጊ የፖለቲካ ለውጦች ባለማድረግ ቀጥሎ ልዩነቶቻችንን በጡንቻ በማካሄድ ሀገራችንን አሳልፈን ለጎሳ ብሄርተኞች ሰጠን። የመጨረሻ ውጤት ምን ሆነ ሻዕብያ እና ወያኔ የሀገራችን 10%ን ወክለው ኢትዮጵያን ተቆጣጠሩት። ይህ ለኛ 90% እጅግ አሳፋሪ ክስተት ነበር አሁንም ነው።

ይህ ታሪክ እንዳለ ሆኖ አሁን ያለፉትን ስህተቶቻችንን ለማርም የሀገራችን ሆደ ሰፊ ብዙሃን እና እግዚአብሔር ዳግም ለማረም እድሉን ሰጥተውናል። ሆንም አንታረምም ብለናል። ዋናው እና መሰረታዊ ችግራችን ያለፉትን አሳፋሪ ድርጊታችንን አለማመናችን ነው ሰው ችግሩን ካላመኑ መፍትሔ አያገኝምና። ጥፋቶቻችንን ላለማምን እና ለመደበቅ ብለን ይመስለኛል ሁል ጊዜ ለችሮቻችን ወያኔ፤ ሻዕብያ፤ ኦነግ፤ «አሜሪካ»፤ ሩሲያ፤ ኤርትራ፤ «አራብ ሀገራት» ወዘተን የምንወቅሰው። እኛ የገዛ ቤታችንን በር ከፍተን እነዚህ ደብተው እንደፈለጉት ሲያደርጉ በራችንን እንዴት ተከፈተ እንዝጋው ከማለት ለሚን ይገባሉ ብለን መጮህ! ዋናው ጣፍቱ የኛ እንደሆነ እናውቃለን ግን እፍረታችን ከባድ ነው መሸሽ ብቻ ነው የምንፈልገው።

ለማስተዋስ ያህል ባለፈው ኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት አንድ የኤርትራ የጦር አዛዥ ያለው ነገር አለ። አንድ ኤርትራዊ አስር ኢትዮጵያዊ ዋጋ አለው ብሎ ፎከረ። ይህ አዲስ ፉከራ አልነበረም በደርግ ጦርነት ላይ የተመሰረተ ነው። የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ምን ያህል እንደተናቁ ነው የሚያሳየው። ድሮ ኤርትራ በሰላም ያጠቃለልን ዛሬ ይቀልዱምን ጀመረ። እስከ ዛሬ በጦር ሜዳ ብቻ ሳይሆን በሌሎች የፖለቲካ ዋይንም የንግድ ዘርፎች በሙሉ ኤርትራዊዎችም ትግሬዎችም እደዚህ ያስባሉ። እኛ ደደብ አህዮች እነሱ አስር እጥፍ ጎበዝ። ከኢትዮጵያዊዎች ብልጥ፤ ጠንካራ፤ የተማርን ወዘተ ነን ብለው ያስባሉ። ይህ የተሳሳተ አስተሳሰብ ግን የነሱ ጥፋት አይደለም። በፍፁም የነሱ ጥፋት አይደለም። እኛ እርስ በርስ ተጨራርሰን እራሳችንን ከታላቅ ህዝብ እና ሀገር ወደ ደካማ ለማኝ ስላወረድን እነሱ የሚያዩትን እውነታ ነው የሚናገሩት። ይህ ለኛ እጅግ አሳፋሪ ነው።

የሰው ልጅ ግን እፍረቱ ስለሚያሳምመው ሊደብቀው ይፈልጋል። ለችግሮቹ ሃላፊነት ከመውሰድ ሁል ጊዜ በውነትም በውሸትም ሌሎችን ይወነጅላል። እኛም አሳፋሪ ድርጊቶቻችንን እና ውድቀታችንን ለመደበቅ ያህል ለ27 ዓመት መጀመርያ ሻዕብያን፤ ኦነግን፤ ወያኔን ወዘተ እየወቀስን ቆይተናል። አሁንም እግዚአብሔር የማይገባንን ጠንካራ የድሮ ዘመን አይነት ኢትዮጵያዊ መሪ ልኮልን አሁን ላሉን ችግሮች ህወሓትን እንወቅሳለን! እንደ ወቀሳችን መጠን ህወሓት ማንም የማይሳነው ግዙፍ ኃይል እንዲመስለን አድርገናል! (ግን 6% ነው የሚወክለው እንላለን!) የራሳችንን ድክመንት ለመሸፈን ላለማየት ለህወሓት የሌለውን አቅም ፈጠርንለት የሌለውን ጥንካሬ ሰየምንለት።

አሁንም እዛው ላይ ነን። አሁንም ከኢትዮጵያ ብሄርተኛ ፖለቲከኛ ተንታኝ አስር ጽሁፎች ካነበብን አስሩም ስለ «ሌሎች»፤ ወያኔ፤ ጎሰኞች፤ ኦነጎች ወዘተ ለቅሶ ነው። እንጂ አንድም ስለራሳችን ጥፋቶች እና ማረምያኦች የሚናገር የሚጽፍ የለም። ኢሳትን ከተመለከትን ስለ«ጠላት» ለቅሶ ነው። ጋዜቶች ሌሎች ማህበራዊ ሚዲያዎች እንዲሁ። የኛ የ«ተፎካካሪ» ድርጅቶች ወሬም እንዲሁ ምናላባትም ይብሳል። እንደ ሚና እና አቅም የሌላው ተጨቋኞች ማልቀስ፤ ማልቀስ፤ ማልቀስ።

እንደዚህ በማድረግ ለራሳችን ጥልቅ የሆነ የእፍረት ጉድጓድ ቆፍረናል። የራሳችን ህልውና በራሳችን ሳይሆን በሌሎች የተቆጣጠረ ነው ብለናል። እነዚህ ሌሎች ደግሞ ከኛ እጅግ አናሳ የሆኑ ናቸው። ይህ አስተሳሰብ ግልጽ የሆነ የዝቅተኝነት መንፈስ እንዲያድርብን አድርጓል። እውነት ነው በተፈጥሮ ሻ'ዕብያዎች፤ ወያኔዎች፤ ኦነጎች ወዘተ ከኛ ይሻላሉ ይበልጣሉ ብለን አምነናል! ይህን የተሳሳተ እምነት የገባንበት ለችግሮቻችን በሙሉ እነሱን ፈላጭ ቆራች እራሳችንን አቅመ ቢስ ስለምናደርግ ነው። ይህ የዝቅተኝነት መንፈስ የሚፈጥረውን እፍረት ለመሸፈን ደግሞ እንደገና እነሱ ላይ እንወርዳለን ከእፍረታችን ለመሸሽ ብለን። ይህ "vicious cycle" ሆኖናል ማቆም ያልቻልነው ሱስ ሆኖናል። የድሮ መሪዎቻችን (ከነ ስህተቾቻቸው) ይህን ቢያዩ ኢትዮጵያዊ መሆናችንን የሚያምኑ አይመስለኝም።

እግዚአብሔር ችር ነው እና አሁን በራሱ የሚኮራ፤ ሃላፊነት የሚወስድ፤ ጥፋቱን የሚያምን፤ ለጥፋቶቹ ንስሃ ገብቶ ይቅርታ የሚጠይቅ፤ ሌሎችን ለራሱ ጥፋቶች እና ችግሮች ከመውቀስ እራሱን በተገቢው ወቅሶ መፍትሔውን ፈልጎ አግኝቶ ስራ ላይ የሚያውል ጀግና መሪ ሰጥቶናል። ለኛ ለኢትዮጵያ ብሄርተኞች ምሳሌ ሊሆን የሚገባን መሪ። ከ60 ዓመት ጥፋታችን በኋላ አሁንም እራሳችንን ለማረም እድል ተሰጥቶናል። ይገርማል!

አሁን የ60 ዓመት ጥፋታችን ውጤት ግልጽ ሊሆንልን ይገባል። እኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ተዝናንተን አድሃሪ፤ ተራማጅ፤ ደርግ፤ ኢዲኡ፤ ኢህአፓ፤ ሜሶን ወዘተ እየተባባልን ተጨራረስን። ባቃጠልነው ባዶ ሜዳ የጎሳ ብሄርተኞች ገቡ። አሁንም የሀገራችን ታላቅ የፖለቲካ ችግር የጎሳ ብሄርተኝነት ነው ብለን እናምናለን ላለፉት 27 ዓመት ያመጣውን ግጭቶች አይተናልና። ስለዚህ የእርስ በርስ መጣላታችን የመስማማት እና አብሮ መስራት አለመቻላችን ምን አይነት ውጤት እንደሚያመጣ እናውቃለን። በዚህ ምክንያት ጎሰኝነትን ለመቀነስ ለማጥፋት ከፈለግን እኛ የሀገር ብሄርተኞች አንድ መሆነ እንዳለብን የእርስ ብሰር ችግሮቻችንን መፍታት መችሃል እንዳለብን ለጋራ ጥቅም አብሮ መሰለፍ እንዳለብን ግልጽ ሊሆንልን ይገባል። ግልጽ ብቻ ሳይሆን ብቸኛ መንገዳችን እንደሆነ ሊገባን ይገባል። አማራጭ የለንም።

ካሁን ወድያ ከማህላችን ጣት መጠቆም ስለ ሻዕብያ፤ ወያኔ፤ ጎሰኞች ወዘተ ማልቀስ ክልክል ይሁን! ክልክል ይሁን! ይህ አስተሳሰብ ነው ወደ ኋላ የሚጎትተንና። እንደ ጠ/ሚ አብይ ችግር ሲያጋጥምን እራሳችንን ምን አድርገን ነው ይህ ችግር የገጠመን ነው ማለት ያለብን። ወሬዎቻችንን፤ አነጋገራችንን፤ አስተሳሰባችንን፤ ጽሁፎቻችንን እንቀይር። ሌሎች አጎልብተን ስለነሱ በኛ ያላቸውን ሚና ከማውራት እራሳችንን አጎልብትን እንገኝ እራሳችን ለራሳችን አለቃ ነን ችግር ካለን እንፈታለን እንበል። ያህን አይነት ባህል ማዳበር አለብን የ60 ዓመት የውድቅ ልምድ ለመቀየር። ታላቅ ስራ ነው ግን እድለኛ ነን እንደ አብይ አይነቱ የጎላ ምሳሌ ሰጥቶናል።

በመጨረሻ አንድ የጠ/ሚ አቢይ ምሳሌ ልጥቀስላችሁ። ከኢሳያስ ጋር ያለውን ግንኝነት እንየው። እራሱን እንደ ታናሽ ወንድም ትሁት አድርጎ ነው የሚያሳየው። እራሱን ዝቅ ያደርጋል ለምሳሌ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሲመጣ እራሱ ጠቅላይ ሚኒስጤር ሆነ ይቀበላል። የ100 ሚሊኦን ህዝብ መሪ ሆኖ ወደ ስድስት ሚሊዮንዋ ኤርትራ መጀመርያ እሱ ነው የሄደው። ለምን። ይህን ማድረግ የሚችሉ በራሱ ስለሚተማመን ነው። ሁኔታውን እራሱ እንደሚቆጣጠር ስለሚያውቀው የራሱን አጀንዳ ማስረገጥ እንደሚችል ስለሚያውቅ እራሱን ዝቅ ማድረግ ምንም አይመስለውም። በራሱ የሚኮራ ብቻ ነው እራሱን ዝቅ ማድረግ የሚችለው። ሌሎቻችን በራሳችን የምናፍር ሰውው ገበናችንን ያቅብናል ብለን የውሸት ጭምብል አድርገን እንኮፈሳለን። አያችሁ እንዴት በራስ ሃላፊነት መውሰድ ሌሎችን ለራስ ችግር ሌሎችን አለመወንጀል እራስን እንደሚያጎለብት። ሌላው መንገድ እራስን አቅመ ቢስ ያደርጋል። ለራስ ሃላፊነት መውሰድ ግን ያጎለብታል። ዶ/ር አብይም የፖለቲካውን ጉልበት ከዚህ ነው የሚያገኘው። እስቲ ትንሽም እንማር!

Tuesday, 10 July 2018

የብሄር ጥያቄ ዛሬ

ዛሬ የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ሁኔታ ተገለባብጦ ቢሆንም አሁንም «የብሄር ብሄረሰብ ጥያቄ» ዋና ጉዳያችን ነው። በዚህ ዙርያ ያሉት ጥያቄዎች ናቸው ዋና የሀገራችን የክፍፍል እና የግጭት ምንጭ። ይህ አሳዛኝ ሁኔታ በዋናነት የተፈጠረው በጎሳ ብሄርተኞች ሚና ሳይሆን በሀገር ብሄርተኛ ጎራው ነው። እኛ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ብሄርተኞች ደጋግመን በሰራናቸው ስህተቶች እና ሀገራችንን በሚገባው ማስተዳደእር ስላልቻልን ነው የብሄር ጥያቄው እንደዚህ የሰፈነው። ለምሳሌ ያህል ጠቅላይ ሚኒስቴር አብይ አህመድ በማያሻማ አገላለጽ አስቀምጠውታል፤ ኢህአዴግ ደርግን አላሸነፍም፤ ደርግ እራሱን አሸነፈ እንጂ። እኛ የሀገር ብሄርተኞች አድሃሪ፤ ተራማጅ፤ ኢህአፓ፤ ምኤሶን ወዘተ እየተባባልን አሳፋሪው ደርግን ፈጠርን ደርግ ሀገሪቷን አጥፍቶ ለኢህአዴግ፤ ኦነግ እና ሻዕብያ ስልጣን አስረከበ።

ለምንድነው ይህ ነጥብ ላይ የማተኩረው? ለምንድነው ለኢትዮጵያ የፖለቲካ ችግሮች እንደ ኢህአዴግ አይነቱ የጎሳ ብሄርተኞችን ጥፋተኛ ከማድረግ የአንድነቱን ጎራ የሀገር ብሄርተኞችን ጥፋተኛ የማደርገው?

1. ሁለት አይነት ሰዎች አሉ። አንዱ ችግር ሲደርስበት ማንነው ይህን ያመጣብኝ ብሎ የሚአማርር
ሌላውን አድራጊ እራሱን ሰለባ በማድረግ እራሱን አቅሜ ቢስ ያደርጋል። ሌላው ሰው ምን አድርጌ ነው ይህ የደረሰብኝ ብሎ እራሱን በመገምገም እና ሃላፊነት በመውሰድ እራሱን አቅም እንዲኖረው ችግሩን መፍታት እንዲችል የሚያደርግ ነው። እኔ በአንድነት የማምን የሀገር ብሄርትኛ ነኝ እና ጥፋቴን ማምን ሃላፊነቴን መቀበል እፈልጋለሁ። ጣቴን በሌሎች ላይ በማተቆር የራሴን ጥፋቶች መካድ አልፈልግም። በተጨማሪ ሃላፊነት በመውሰዴ የችግሩ ምንጭ እኔ ነኝ በማለት የመፍትሄው ምንጭም እኔው ነኝ ማለት ነው። መፍትሄውን ከሌላ ሰው አልጠብቅም። ይህ ተመልካች ሳይሆን አስፈጻሚ ያደርገኛል። ይህ አቅሜን ከመመንመን ያጎለብተዋል።

2. እውነት ነው፤ እኛ የሀገር ብሄርተኞች ነን የኢትጵያ የፖለቲካዊ ችግሮች ያመጣነው። በጃንሆይ አገዛዝ ሀገሪቷን በተቆጣጠርን ጊዜ አስፈላጊ ለውጦች ባለማድረግ የመደብ እና የጎሳ ጥያቄዎችን አስነሳን። የሀገሩን ትውፊት የሚንቅ የተማሪ እንቅስቃሴን ወለድን። ደርግ የኃይለ ሥላሴን መንግስት አልገለበጠም የኃይለ ሥላሴ መንግስት ነው አስፈላጊ ለውጦች ባለማድረግ እራሱን ለአብዮት ያጋለተው። አብዮቱን የአንድነት ጎራውን ለሁለት ለ«አድሃሪ» እና «ተራማጅ» ከፋፈከው ተራማጁ አድሃሪውን አጠፋ። ከዛ ደግሞ ተራማጆቹ እርስ በርስ ተጨራረሱ። አልፎ ተርፎ ደርግ በ«ኢትዮጵያ ብሄርተኝነት» ስም «ነግዶ» ህዝብን ጭቆነ እና ለሀገር ብሄርተኝነት መጥፎ ስም ሰጠ። ይህ መጥፎ ስም የጎሳ ብሄርተኞችን እንቅስቃሴን አበረታታ። ደርግ ሲወድቅ የሀገር ብሄርተኝነት ጎራ እራሱን አጥፍቶ አልቋል። የጎሳ ብሄርተኞቹ ሙሉ በሙሉ ስልጣን ተቆጣጠሩ። በኃይለ ሥላሴ ምንም አቅም ያልነበርው የጎሳ ብሄርትኝነት አሁን ሀገራችንን ገዝቶ ኤርትራን አስገነጠለ። ይህ በአጭሩ እኛ የሀገር ብሄርተኞች ዛሬ ያለብንን የጎሰኝነት ችግር እንዴት እንዳመጣን ይገልጻል።

3. አሁንም ዋናው የሚያሳስበኝ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ጎራ የሀገር ብሄርተኛው ነው። በህዝብ ደረጃ ይህ ጎራ ቢንገዳገድም ደህና ነው። እንደ አብይ አህመድ አይነቱን መሪዎች እየወለደ ነው። ገን በልሂቃን (elite) ደረጃ ችግር እንዳለ ነው። አንድ ሆነን ሀገራችንን ማዳን እንችላለን ወይንም እንዳለፉት 50 ዓመት እርስ በርስ ተከፋፍለን እንደገና የጎሳ ብሄርተኝነት እንዲሰፍን እናደርጋለን? ዋና ጥያቄ ነው። የቅርብ ታሪካችን ጥሩ አይደለም። ይሄው ለኢህአዴግ የ27 ዓመት አገዛዝ አንድ ጠንካራ የፖለቲካ ድርጅት ሀገር ውስጥም ውጭም ማቋቋም አልቻልንም። አሁንስ አንድ ሆነን ከ«ለማ ቡድን» ጋር እየሰራን ሀገራችንን ማዳን እንችላከን? ወይንስ እንደልማዳችን እንከፋፈላለን እና ሀገራችንን ለቀውስ እና ግጭት የሚፈጥረው ጎሰኝነት እንደገና አሳልፈን እንሰአለን? ቁም ነገር ከማድረግ አቅሙ አለን ትያቄ የለውም። ግን ፍላጎቱ አለን ወይ ነው ጥያቄው።

በነዚህ ምክንያቶች ነው በዚህ ወቅት ከሁሉም የፖለቲካ ጎራዎች የሀገር ብሄርተኛ ጎራው የሚያሳስበኝ። እንደ ህወሓት ምናልባትም ኦፌኮ አይነቱ የጎሳ ብሄርተኞች ምንም አያሳስቡኝም። የታወቁ ናቸው በልመና ልንቀይራቸው አንችልም። በስልት፤ በዘዴ እና በውይይት ከነሱ ጋር እንደራደራለን። ግን ለመደራደር እና ውጤታማ ለመሆን የአንድነት ጎራው አንድ እና ጠንካራ መሆን አለበት። ድርድር የሚሳካው እራስን መጀመርያ እራስን ጎልብቶ ነው አለበለዛ ደካማ ከሆንን አይሳካልንም። እርግጠኛ ነኝ የአንድነት ጎራው አንደና ተንካራ ከሆንን በነዚህ ድርድሮች እርግጥ ውጤታማ እንሆናለን የጎሳ ብሄርተኞችን በጥሩ መልክ እንይዛቸዋለን። ግን ከተከፋፈልን የበፊቱ 60 ዓመት ችግሮችን እንቀጥላለን።