Friday, 16 March 2018

ስለ ትህትና

እግዚአብሔር ክፉ መናፍስትን የማስወጣት ጸጋ የሰጣቸው አንድ ባሕታዊ ነበሩ። በአንድ ወቅት ጋኔኖቹን የሚያስፈራቸውና ከሰዎች እንዲለቁ የሚያደርጋቸው ምን እንደሆነ ለመረዳት ፈልገው ጠየቁ።

«ጾም ይሆን?» ብለው አንዱን ጠየቁት።

«እኛ መቼም አንበላም አንጠጣምም» ብሎ ክፉ መንፈሱ መለሰላቸው።

«የለሊት ሙሉ ጸሎት ይሆን?»

«እኛ አንተኛ።»

«ዓለምን ትቶ መመንን?»

«ይህ እንደ ትልቅ ነገር ይቆጠራል። ግን እኛ አብዛኛው ጊዜአችንን በየ በርሃው እየዞርን ነው የምናጠፋው።»

«ታድያ ምንድነው ይዞ ሊቆጣጠራችሁ የሚችለው፤ እባካችሁ ንገሩኝ» ብለው ታላቁ አባት ደግመው ጠየቁ።

ክፉ መንፈሱ በተአምራዊ ኃይል ጥያቄውን እንዲመልስ ተገደደ፤ «ትህትና ነው። ይህን መቼም ልናሸንፍ አንችልምና።»

ቤተክርስቲያን የፈውስ ቦታ ናት

«ወደ ቤተክርስቲያን ግባ እና ከኃጢአትህ ታጠብ። ቤተክርስቲያን የፈውስ ቦታ እንጂ የዳኛ ፍርድ ቤት አይደለችም እና። ወደ ቤተክርስቲያን በመግባትህ አትፈር። ኃጢአት ሰርተህ ንሰሐ ባለመግባትህ ግን እፈር።»

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ

Thursday, 8 March 2018

ዴሞክራሲ

ስለ ዴሞክራሲ ብዙ ተጽፏል። በንደፈ ሐሳቡ ደረጃ ምንም መጨመር አልፈልግም። በዚህ ጽሁፍ አሁን ባለን የኢትዮጵያ የፖለቲካ ጉዳይ ዙርያ ስለ«ዴሞክራሲ» ያለን አመለካከት ምን ቢሆን ይበጀናል የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ ነው የምወደው።

እንደ እስክንድር ነጋ አይነቶቹ በርካታ (ጀግና) የነፃነት ታጋዮቻችን የችግራችን መፍትሄ ዴሞክራሲ ነው ይላሉ። በአንድ ወቅት እኔም እንደዚሁ ይመስለኝ ነበር። ግን ጉዳይ ከዛ እጅግ ውስብስብ እንደሆነ ተረድችያለሁ።

ዛሬ ባለን ህገ መንግስትና ጠቅላላ የመንግስታዊ አወቃቀር የነፃ ምርጫ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ቢካሄድ ችግሮቻችን ይፈታሉ ብለን እንገመታለን? አሸናፊዎቹ፤ ተሸናፊዎቹ፤ ጦር ሰራዊቱ፤ የክልል መንግስታት ወዘተ ውጤቱን ተቅብለው ተስማምተው ይሰራሉ ብለን መገመት ኢንችላለን? አዲሱም መንግስት ሰላምና ፍትህ ያመጣል ወይም የፓርላማ ስልጣንና ኃይሉን ተጠቅሞ ግፍና ጭቆና ያሰፍን ይሆን? ህገ መንግስቱን ይቀየር የምንለውሳ? በቂ ድምጽ ካለን አናሳ ድምጽ ያላቸውን የራሳችሁ ጉዳይ ብለን በዚህ ድምጽ ኃይል እንቀይረውና አዲስ ህገ መንግስት እንጭንባቸው ይሆን? ዛሬ እነዚህ አይነቶቹ ከባድ ጥያቄዎች ጥሩና የተሟላ መልስ አላቸው ብዬ እርግጠኛ መሆን አልችልም። ለእነዚህ ጥያቄዎች በሚገባው መልስ ሳይኖረን ወደ ዴሞክራሲ የምንለው ምርጫ ከገባን ደግሞ አደጋ ነው የሚሆነው።

ስለዚህ እንደኔ እንደኔ በመጀመርያ ሰፊ ውይይት በተለያዩ ደረጃዎች ያስፈልጋሉ። የዚህ ውይይት ግብ በርካታ ባለጉዳዮቹ ከብዙሃን እስከ ልሂቃን የአገራችን ማንነትና ፖለቲካ ምን መምሰል አለበት በሚለው ጥያቄና መልስ አንድ ገጽ ላይ እንዲሆኑ ነው። ሰፊ ስምምነት እንድውል ነው። አሁን ያለንበት ደረጃ አገር መገንባት ላይ ነው። በህዝቡም በልሂቃኑም የፖለቲካ መተማመንና መሰረታዊ ስምምነት የለምና። ከላይ የጠቀስኳቸው አይነቶች መሰረታዊ የሆኑ ጥያቄዎች እንኳን ሊመለሱ አልተጠየቁም አልተወያየንባቸውም። ይህን የውይይት ሂደት ሳንጨርስና መሰረታዊ ስምምነት ላይ ሳንደርስ ወደ ምርጫ መሄድ አደገኛ ይመስለኛል። እንደ ግብጽ፤ ኢራቅ፤ እና ሌሎች ምርጫ ያላቸው ወይም የነበራቸው ግን ሰላምና ፍትህ የሌላቸው አገሮች እንድንሆን አይፈለግምና።

እሺ፤ በርካታና አስፈላጊዎቹ ባለጉዳዮች አንድ ገጽ ላይ መሆናቸውና ስምምነት ላይ መድረሳቸው እንዴት ልናውቅ እንችላለን? አንዱ ዋና ምልክት የሚመስለኝ የተቃዋሚ ፓርቲዎች በስል ማለት ነው። ጠንከር ያለ ተቃዋሚ ፓርቲ ከሌለ ወይም ፓርቲዎቹ በጎሳ ብቻ የተመሰረቱ ከሆነ ይህ ጥሩ ምልክት አይመስለኝም። ተመሳሳይ የሆኑ አቋም ያላቸው ተቃዋሚዎች የመዋኸድን ሂደት ለማሟለት ብቃት ከሌላቸው ጥሩ ምልክት አይሆንም። ይህን ያልቻሉ እንዴት አብረው መንግስት ይሆናሉ ወይም እንዴት የአስተዳደሩን ህግ ያከብራሉ? የጎሳ ፓሪቲ ብቻ ካለ ደግሞ እንዴት ነው ፖለቲካ ስረአቱ የማይቀረውን የጎሳ ውድድሩን በሰላም ማስተናገድ የሚችለው? አሁንም ከባድ ጥያቄዎች። እንደምናየው ወደ ምርጫ ከመግባታችን በፊት ብዙ ስራ አለ ቀድመሁኔታዎችም መሟላት አለባቸው።

ይህን ካልኩኝ በኋላ እስቲ ይህን ጥያቄ ልጠይቃችሁ፤ ዴሞክራሲ ቢኖር ሰላምና ፍትህ ይኖራል ማለት ነው? እስቲ አንድ አንድ እውነታዎች እንመልከት። በዓለም ታላቅ የሚባለው ዴሞክራሲ አሜሪካ ነው። በጦሩ ኃይል በርካታ የዴሞክራሲ አገርዎች በሰላም እጠብቃለሁ እሸከማለሁ ባይ ነው። ግን ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ አሜሪካ ወደ 20 ሚሊዮን ሰዎች በተለያዩ ጦርነቶች ገድሏል ይባላል። አጭር ትዝታ ያለን መቼም ስለ ኢራቅ፤ ሊብያ፤ ሶርያ እናውቃለን። ኢህአዴግ  ከዚህ ጋር ሲወዳደር መለአክ ነው ማለት ይቻላል! ግን አሜሪካ ለኑሮ ጥሩ አገር ነው። ገንዘብ አለ፤ ከሞላ ጎደል ፍትህ አለ፤ የተወሰነ ነፃነት አለ። ሁላችንም ወደዛ ለመሄድ እንሻለን። ግን ገንዘቡ ባይኖር በአሜሪካ ምን ይሆን ነበር?

ምናልባት አውሮፓ ያላችሁ ኢትዮጵያዊያን ለምን አሜሪካን እንደ ምሳሌ ትጠቀማለህ ትሉ ይሆናል። ሰላማዊዋ ስዊድንሳ? እውንቱን ለመናገር የስዊድን የጦር መሳርያዎች በዓለም ዙርያ ምን ያህል ሰው እንደተገደለ የተቆጠረ አይመስለኝም። ግን ትንሽ አይመስለኝም። ደግሞ ከሳውዲ አራቢያ ያላቸው ጓደኝነታቸው እንዴት ፍቅር የተሞላ ነው?!

ዴሞክራሲ ለሰላምና ፍትህ ሊበጅ ይችላል፤ ይህ ጥያቄ የለውም። ግን ሰላምንና ፍትህን ለማስፈን ሥርዓቱ በራሱ አይበቃም።  ብዙሃኑም ልሂቃኑም ቀድሞ በትወሰኑ መሰረታዊ ጉዳዮችና አስተሳሰብ መስማማት አለባቸው። ከህግና የሂደት ደምብ አስተሳሰብ ይቀድማል። አሰተሳሰቡ ካለ ህጉ ይመጣል በሚገባውም ይተገበራል። ህጉ ካለን አስተሳሰቡ ከሌለ ዋጋ የለውም። ብዙ ነገር በጽሁፍ ላይ የዋለ ህገ ደምቦች ሊካታቱ ይችላሉ ግን አስተሳሰብ በጽሁፍ ሳይሆን በልብ ውስጥ የሚሰክን ባህል ነው መሆን ያለበት። ከዛ በኋላ እንቅፋት ሲያጋጥም ይህ አስተሳሰብ፤ ስምምነትና አንድነት ናቸው ከወረቀት ላይ ከሰፈረው ህግ ይልቅ ወደ መፍትሄ የሚመሩን።

ስለዚህ ዴሞክራሲን እንደ ዋና ግብ ወይንም እንደ ጣዖት አንመልከተው። ዋናው ግብ ፍቅር፤ ሰላምና ፍትህ ነው። እነዚህ እንዲሰፍኑ ዴሞክራሲ አንዱ መሳርያ ሊሆን ይችላል። በዴሞክርሲ ዘንድ ፍቅር፤ ሰላምና ፍትህ ሊሰፍኑ ይችላሉ። ግን ቀድሞ ዝግጅቶች ካልተደረጉ፤ ግባችን እነዚህ እንደሆኑና ዴሞክራሲ መንገድ ወይም ሂደት ባቻ እንደሆነ ካልተረዳን ፍቅር፤ ሰላምና ፍትህ የሌለው ዴሞክራሲ ሊሰፍን ይችላል። እንደዚህ አይነቱ ዴሞክራሲ ደግሞ በበርካታ አገራት ልምድ እንደምናየው አይበጅም።

Monday, 5 March 2018

እውነት አማኞች

ስለ ታላቁ የሩሲያ ኦርቶዶክስ ካህን አባ አርሴኒ በተጻፈው አንዱ መጸሃፍ አቭሴንኮቭ የሚባል ባለ ታሪክ አለ። አባ አርሴንይ ለሁለተኛ ጊዜ ጉላግ የሚባለው የሶቪዬት የሞት እስርቤት ገብተው እያለ የመንግስት ባለስልጣንና ዳኛ የነበረው የኮምዩኒስት ፓርቲ አባል አቭሰንኮቭ ታስሮ ወደሳቸው እሰር ቤት ይገባል። እንዴት እንደ አቭሴንኮቭ አይነቱ ከፍተኛ ባለ ስልጣን ታሰራ። ወቅቱ እንደ የኢትዮጵያ ቀይ ሽብር ነበር። የሰው ስልጣን ወይም ስራ ለመቀማት፤ ሰው በመጠቆም ሹመት ለማግኘት፤ የሚጠሉትን ሰው ለመጉዳት፤ ጥቅም ለማግኘት ወዘተ ምክንያቶች ፖለቲከኞችም ብዙሃንም እርሰ በርስ እየተጠቋቆሙ እስር ቤቶቹንና መቃብሮቹን እየሞሉ ነበር። በዚህ ሂደት በርካታ ባለ ስልጣኖችም ታስረዋል ተገድለዋልም። አቭሴንኮቭ አንዱ ከታሰሩት ነበር

አቭሴንኮቭ ሶቪየቶች «እውነት አማኝ» ኮምዩኒስት ከሚሏቸው አንዱ ነበር። ይህ ማለት በኮምዩኒስም ርዕዮተ ዓለም፤ በፓርቲውና በአስተዳደሩ በእውነት ያምን ነበር። «ባለጥቅም» ከሚባሉት ለስልጣ፤ ለገንዘብ፤ ለሹመት፤ ለጥቅም፤ ሰው በማሰርና በማስጨረስ ብሶቱን ለመወጣት ወዘተ አልነበረም የኮምዩኒስት ፓርቲ አባልና ባለ ስልጣን የሆነው። በእውነት የኮምዩኒዝምን መሰረተ ሐሳቦች ያምን ነበር። ለዚ ለሚያምንበት ርዕዮተ ዓለም ለማሳሰር ለመፍረድና በሞት ፍርድ ለመፍረድ ዝግጁ ነበር።

ግን እንደ ማንኛውም ድርጅት ወይም ፖለቲካ ፓርቲ የኮምዩኒስት ፓርቲም በርካታ «እውነት አማኝ» ያልሆኑ አባላት በበረው። እነዚህ ቅድም እንደጠቀስኩት ለስልጣን፤ ለገንዘብ፤ ብሶት ለመወጣት፤ ጥቅም ለማግኘት ወዘተ ፓርቲ ውስጥ የገቡ ናቸው። አንዱ እንደዚህ አይነቱ የአቭሴንኮቭ የከፍተኛ ዳኛ ስልጣንን ለመቀማት ብሎ ቀስ ብሎ ሴራ ፈጥሮ አቭሴንኮቭን ከስሶ ወደ ጉላግ የሞት እሰርቤት እንዲላክ አደረገ።

አቭሴንኮቭ እስር ቤት እንደገበ መታሰሩን እንደ የአስተዳደር ስህተት ነበር የቆጠረው። በኮምዩኒዝምም በመንግስቱና አስተዳዳሪዎቹና መዋቅሮ እምነቱ እንዳለ ሆኖ በስህተት ነው የታሰርኩትና ከትንሽ ጊዜ በኋላ ስህተቱ ተደርሶበት እፋታለው ብሎ ይጠብቅ ነበር። በእውነት አማኞች ዘንድ ይህ የተለመደ አስተሳሰብ ነበር። የእምነታቸው ጥንካሬ የፓርቲውንና የመንግስቱን መሰረታው ሐሳቦች በጥያቄ ውስት ማድረግ እንዳይችሉ ያረጋቸው ነበር።

ግን አቭሴንኮቭ በእስር ቤቱ በቆየ ቁጥር መቀየር ጀመረ። እንደ አባ አርሴኒ አይነቱን በጸረ አብዮትነት የተሳሩትን ባልደረቦቹን ሲመለከት፤ ስነ መግባራቸው፤ እምነታቸው፤ ትህትናቸው፤ ፍቅራቸውን ሲመለከት ንፁሃን እንደሆኑ ቀስ በቀስ መረዳት ጀመረ። ከእስር ቤት አስተዳዳሪዎችና አዛጆቻቸው የሚመነጨው ክፋትን ሲአይ ደግሞ ያምንበት የነበረውን የፖለቲካ መዋቅሩን መጠራጠር ጀመረ። አቭሴንኮቭ ቀስ በቀስ የመንግስቱንና ርዕዮተ ዓለሙን ክፋት እየተረዳ ሄደ፤ ወደ አባ አርሴኒ አይነቱን እያየ ወደ ክርስትና መለወጥ ጀመረ። መጨረሻ ላይ የአባ አርሴኒ ንሰሀ ልጅ ሆኖ ነበር እድለኛ ሆኖ ከእስር ቤት ሳይሞት የወጣው።

ቅድም እንደጠቀስኩት ማንኛውም የፖለቲካ ሥርዓት ወስጥ እውህነት አማኞችና ባለጥቅሞች አሉ። ሁለቱም አይነቶች አሉ። ብዙዎቻችን እውነት አማኞችን እናከብራለን ባለጥቅሞችንን እንንቃለን። ግን እንደዚህ መሆን አለበትን? ማን ነው በርካታ ጉዳት ሊአይደርስ የሚችለው፤ እውነት አማኙ ወይም ባለ ጥቅሙ? ማን ነው ይበልጥ ክፉ መሆን የሚችለው?

አቭሴንኮቭ ረስቷቸው ነበር እንጂ እሱ ነበር አባ አርሴኒን ፈርዶባቸው ወደ ሞት እስር ቤት የላካቸው። የኮምዩኒዝምና የሶቪዬት ህዝብ ጠላት ናቸው ብሎ። ሌሎችም በርካታ ሰዎችን ወደ እስር ቤትና ሞት ሲልክ ለሚያመልከው ርዕዮተ ዓለም ስለሆነ ሰው መሆናቸው ረስቶ ልቡን ደንድኖ ድርጊቱን በቀላሉ አደረገው። እውነት አማኞች እጅግ አደገኛና ጎጂ ሊሆኑ ይችላሉ። የሚያምኑበት አካዬድ መጥፎ ከሆነ ይህን መጥፎነት በሙሉ እምነትና አቅማቸው ስለሚያራምዱ በርካታ ጉዳት ይፈጽማሉ። እውነት አማኝ በጥሩና ትክክለኛ ነገር ካመነ በጣም ጥሩ ውጤት ይኖረዋል። በመጥፎ ነገር ካመነ ደግሞ መጣም ከባድ ጉዳት ያደርሳል።

ባለጥቅሙ ግን ልቡ በሙሉ ስለማያምንበት የሚፈጽመው ጉዳት አናሳ ሊሆን ይችላል። ከጥሩም ከመጥፎም ወገን ቢሰለፍ ውጤቱ መካከለኛ ነው የሚሆነው። ክፉ ስርዓት ውስጥ ከተሳተፈ የሚያመጣው ጉዳት እንደ እውነት አማኙ ላይሆን ይችላል። ጥሩ ስርዓት ውስጥም ቢሳተፍ ወጤቱ እንደ እውነት አማኙ ያህል አይሆንም።

ስለዚህ እውነት አማኞችን ከባለጥቅሞች ይበልት ልናከበራቸው አይገባም። የአብዛኛው ጸንፈኛ የፖለቲካ ንቅናቄዎች መሰረት ጠንካራ የእውነት አማኝ ቡድን እንደሆነ መርሳት የለብንም። በኢትዮጵያ ፖለቲካ ዙርያ ከተመለከትን የግራ ርዕዮተ ዓለም ትከታይ የሆነው የተማሪ ንቅናቄ የደረሰበት ደረጃና ያደረሰው ጉዳት አለ እውነት አማኞች አይሆንም ነበር። ላይ ያሉት መሪዎች መካከል በርካታ ባለጥቅሞች ቢኖሩም አለ ጠንካራ የእውነት አማኝ አምድ የትም አይደርሱም ነበር። እነ ህወሓትና ሻብያም የእውነት ዓማኝ አምዳቸው ነው እዚህ ያደረሳቸው አንዳይታደሱም የሚከለክላቸው።

ለኛ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ተሳታፊዎች ይህ ታላቅ ትምህርት ሊሆነን ይገባል። «አምኖበት ነው ያእደረገው» «ለአቋሙ የቆመ ነው» «ፕሪንሲፕለድ ነው» «ለአገር ብሎ ነው ያደረገው» አይነቱን አባባሎቻችንን መተው አለበን። አንድ ሰው የሚያራምደው ርዕዮተ ዓለም ክፋት የሚጎትት ከሆነ እውነት ዓማኝ መሆኑ «ፕሪንሲፕልድ» መሆኑ ምን አይጠቅምም። ጭራሽ ጉዳት ነው። በደምብ ስለሚያምንበት ይበልጥ ጉዳት ያደርሳልና። ዋናው አላማችን በተሳሳተ ርዕዮተ ዓለም ወይም አቋም አለማመን። በተቻለ ቁጥር ማንኛውም ርዕዮተ ዓለም ወይም የፖለቲካ አመለካከት ከሰው በላይ አለማረግ። ዋናው ነገር ሰው ነው። ለሰው የሚያስፈልገው ፍቅርና ፍትህ ነው። ሌላው በሙሉ እነዚህን ማግኛ ዘዴ ነው። የምናምንበት ርዕዮተ ዓለም ጭራሽ ጥላቻና ጉዳት እያደረሰ ካየን የተሳሳተ መሆኑን ቶሎ ተረድተን መተው መቻል አለብን። ጣዖታችን ሊሆን አይገባም። ከኢግዚአብሔር በቀር ለምንም የእውነት አማኞች መሆን የለብንም።

Friday, 2 March 2018

የምዕራባዊያን አገራት አምልኮ

የአባቴ ትውልድ የምዕራባዊያን አገሮችን የሚተቹባቸው በርካታ ጉዳዮች ነበሩ። ዘረኛ ናቸው። ታላቂቷ ምዕራባዊ አገር አሜሪካ አሁንም በጥቁር ዜጎቿ ታላቅ ግፍ እያደረሰችባቸው ነው። ዓለምን በቅኝ ግዛት አሰቃይተዋል። ቅኝ ግዛታቸውን እየተውዉ ቢሆንም አሁንም በ«አዲሱ ቅኝ ግዛት» መርህ ዘንድ ጥቅማቸውን የማያስከብሩ መንግስታትን በመፈንቀለ መንግስትና የተለያዩ ዘዴዎች ያፈርሳሉ።

የአሁኑ ትውልድ ደግሞ የምዕራባዊያን አገሮችን እንደ ጣዖት የሚያመልክ ይመስላል። ነፃነት ከነሱ ጎራ ነው የሚገኘው። ተራማጅነት ከነሱ ነው። ሀብት ከነሱ። ዴሞክራሲ ከነሱ። ቴክኖሎጂ ከነሱ። ስነ መግባር ከነሱ። ወዘተ።

በኔ ኢይታ ይህ አምልኮ ለአገራችን ለያንዳንዳችንም አደገኛ ነው። ለምን ብትሉኝ ይህ አመለካከት ከባህላችን፤ ትውፊታችን፤ ማንነታችን ነጥቆ እንደ ስሩ የተነቀለ አትክልት ነው የሚያደርገን።

ስለዚህም ቢዚህ ርእስ ዙርያ የተወሰኑ ጽሁፎች ለማዘጋጀት አቅጅያለሁ። የኢትዮጵያዊነት፤ የሰውነት፤ የማንነት ጉዳይ የተሳሰረበት ርእስ ነው። የምዕራባዊው ፕሮፓጋንዳ እጅግ ከባድ ነው። በመሰረታዊ አስተሳሰባችንን፤ አስተያየታችንን፤ አስተነፋፈሳችንንም ታላቅ ሚና ተጫውቷል። መሰራታዊ ሃሳቦቻችንና ቋንቋችንም ቀይሯል መቀየሩንም አናውቀውም! ይህ ሁሉ በደምብ ልናየው ይገባል።

ጽሁፎቼን ስጽፍ በተለምዶ በመጀመርያ እንደ ክርስቲያን በማቀው ክርስቲያናዊ አመለካከት ነው የምጽፋቸው። እምነቴ በሁሉ ነገር ኢግዚአብሔር አለ ብሎ ሰለሚያስተምር እንቋን የማንነት ጉዳይ ምንም ነገር ከዚህ መነጽር ውጭ ማየት አይቻልም።

ለጽሁፎቼ እንደ መግብያና ሀሳብ ማንሸራሸርያ እስቲ እነዚህን ቃላቶችን እናስባቸው፤

ዘመናዊነት (modernity)
መሻሻል ወይም እድገት (progress)
ዴሞክራሲ (democracy)
ነፃነት (freedom)
ሰው (Man)
ፍትህ (justice)
ልማት (development)
አገር (nation)
ጎሳ (tribe - in the neutral sense)
ተፈጥሮ (nature)
ፍቅር (love)
ስልጣኔ (civilization)
ሴኩላሪዝም (secularism)

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ

ይህንን የምጽፈው ሊህቃኖቻችንም እኛ ብዙሃንም አሁን ባለው የፖለቲካ ሁኔታ ትክክለኛ የሚመስለኝን ግንዛቤ እንዲኖረን ነው። በዛ ግንዛቤ ተመስርቶ ትክክለኛውን ሃሳብና ስራ በተግባር እንዲያውል ነው።

ዛሬ የፀደቀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በርካቶች ከሚያስቡት ተቃራኒ አስተዋሶ ነው የሚኖረው። የነጻነትን እንቅስቃሴውን ይጠቅማል እንጂ አይጎዶም።

ለማስታወስ ያህል ባለፉት ዓመታት ያየነው የህዝብ ተቃውሞና የኢህአዴግ የስልጣን መገለባበጥ በአንድ ጊዜ የምነጣ አይደለም። ለረዥም ዓመታት እየተንከባለለ የመጣ አዝማሚያ ነው። የህዝብ ብሶትና የአስተዳደሩ መሰረታዊ ችግር ያመታው ተቃውሞ ነው። የጎሳ አስተዳደርና የአውራ ፓርቲ የልማታዊ መንግስት አስተዳደር እንደ እሳትና ጭድ የሆኑ የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለሞች በመሆናቸው ኤኮኖሚው ምንም ቢያድግም የህዝብ ቁታ እንዲንር አድርጓል። ይህ አገዛዝ ያመጣው በህዝቡ መካከል ያለው የአድሎ ግንዛቤ ህዝቡን እጅግ አምሮት ለዓመታት የማያቋረት ሰላማዊም አመጻዊም ሰልፍ እንዲካሄድ አድርጓል።

ይህን አዝማሚያ እንኳን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ምንም ሊያቆመው አይችልም። ያለፈው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጀ እንዳላቆመው እናስታውስ! ትልቅ የፖለቲካ ለውጥ ብቻ ነው የህዝቡን ቅሬታ መመለስ የሚችለውና መሰረታዊ የፖለቲካ ብልሽቶችን ማስተካከል የሚችለው።

ምናልባት አንዳንድ ተቃዋሚዎች ስለኢህአዴግ ያላቸው ግንዛቤ የተጋነነ ስለሆነ በቀላሉ የተስፋ ምቁረጥ ባህሪ አላቸው። ይህ አዋጅ የህዝቡን ተቃውሞ ያቆመዋል ያከሽፈዋልና ከምርጫ 97 በኋላ እንደሆነው ለበርካታ ዓመታት የኢህአዴግ አገዛዝ ይቀጥላል ብለው ያምናሉ። ይህ ምን ያህል የተሳሰት እንደሆነ የሚያሳየው የኢህአዴግ አባል ድርጅቶችንም ስለማያስቡት ነው! ስልጣናቸው እንደተነጋ ለሁሉም ግልጽ ነው። የሚሉትም ነገሮች፤ የሚወጣው ሚስጥሮች፤ የሚያደርጉት ድርጊቶች ሁሉ ይህንን ይመሰክራል። እስረኞችን የፈቱት ብርሀን ስላዩ አይደለም። ተሃድሶ እያሉ እርስ በርስ የሚፋጁት ከንቱ አይደለም። እነ ለማ መገርሳ እራሳቸውን ከፍ ያደረጉት አለ ምክንያት አይደለም። የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ያስፈለገውም ክንያት አለው! የህዝቡ ተቃውሞ ጋብ ይል ይሆናል ማለትም አለበት ግን ቀስ በቀስ ይቀጥላል ለውጥ እስኪመጣ።

ሌላው ማስተካከል የምወደው የተሳሳተ የሚመስለኝ አመለካከት ስለ ጦር ስራዊቱ ነው። የጦር መሪዎቹ ባብዛኛው የህወሓት አባሎች ቢሆኑም ጦሩ እራሱ ባብዛኛው አይደለም። ጠመንጃ የያዘው ኦሮሞ፤ አማራ፤ ሲዳማ ወዘተ ነው። ጦር ሰራዊት ውስጥ የታወቀ የፖለቲካ ክፍፍል አለ። በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ወታደሩ ብዙ ቅራኔዎች ካላጋጠሙትና ባብዛኛው ሰላማዊ የፍተሻና የሚመሳሰል የማያስጨንቅ ስራ የሚሰራ ከሆነ ይህ ክፍፍል ብዙ ላይታይ ይችላል። ግን ኃይለኛ አመጽ ከተነሳና በርካታ ቅራኔና ግድያ ከተከሰተ የወታደሩ የውስጥ የፖለቲካ ክፍፍል - በዘር ምክንያት - መውጣት ይጀምራል። ጦር ሰራዊቱን ወደ መከፋፈል ይገፋዋል። የጦር ሰራዊት መሪዎች ደግሞ ይህንን "risk" እጅግ ይፈራሉና ይሸሻሉ። ግን የአቸኳ አዋጁ በቆየ ቁጥር ይህ የመከሰቱ እድል እየጨመረ ስለሚሄድ የጦር ሰራዊቱ መሪዎችም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ቶሎ እንዲቋረጥ ነው የሚፈልጉት።

ስለዚህ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ብዙ ሌከርም አይችልም። ጊዜ መግዣ ነው። የአገሪቷ መንገዶችና ንግዶች እንዲንቀሳቀሱና ሰውዉ ለተወሰነ ጊዜ ቢሆንም ወደ ዘውትር ኑሮ እንዲመለስ ነው። ፖለቲከኞቹ ማቀዳቸውንና ውይይታቸውን እንዲቀጥሉ ነው። አይከፋም። የአገሪቷ የፖለቲካ ጠቅላላ አዝማሚያውን አይቀይርም ሊቀይርም አይችልም። ኢህአዴግ ባለበት አወቃቀር ከስጣን መውረዱ አቀርም። ወይ ለጉድ ይቀየራል ወይም ከስልጣን ይወርዳል። ጉዳዩ አልቋል። አሁን የጭዋታው መጨረሻ ("end-game") ላይ ነን። ስለዚህ ስለ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከመጨነቅ ይልቁኑ እኛ ተቃዋሚዎች በርካታ የተጠራቀመ የቤት ስራችንን እንስራ። ጊዜውን እንጠቀምበት።