Showing posts with label democracy. Show all posts
Showing posts with label democracy. Show all posts

Thursday, 17 January 2019

የጎሳ አስተዳደር አንድ እና አንድ ችግር ነው፤ የግጭት ምንጭ ነው

ፖለቲካ በሃሳብ ብቻ ነው ምሆነ ያለበት እንጂ በጎሳ መሆን የለበትም ሲባል ዋናው ምክንያቱን አጥብቀን ማስረዳት አለብን። ምክንያቱ የብሄር ፖለቲካዊ ጥያቄ ስለሌለ አይደለም፤ ጎሳዎች ስላልተጨቆኑ አይደለም፤ የርዕዮት ዓለም ጉዳይ አይደለም። መሰረታዊ ምክንያቱ፤

«ጎሳ ወደ በፖለቲካ ሲገባ የግጭት ምንጭ ይሆናል ነው»።

ይህ ደግሞ የርዕዮት ዓለም ወይንም የቴኦሪ አመለካከት ሳይሆን በተግባር empirically በሀገራችን (ሌሎችን ሀገራት ምሳሌ ትተን) የያእነው እያየን ያለው ነው። በህወሓት ዘመን የጎሳ አስተዳደር የግጭት ምንጭ ነበር። ግጭቶቹ ሀውሓት የሰራቸው ብቻ ሳይሆኑ በርካታ ሌሎች ነበሩ። በዴሞክርሲ እጦት ሳይሆን በሌላ ምክንያቶች የተነሱ ነበሩ።

አሁን ደግሞ «ነፃነት» ባለበት የጠ/ሚ ዓቢይ ዘመን የጎሳ ግጭቶች እየቀጠሉ ነው። ይህ አስምሮ የሚያሳየው የጎሳ አስተዳደር ወይንም የጎሳ ፖለቲካ በነፃነት እና ዴሞክራሲያዊ አገዛዝም ግጭቶች የመጣል ነው።

ስለዚህ የጎሳ ፖለቲካ/አስተዳደር የግጭት ምንጭ ነው። መብት ነው። ጥያቄዎችን ያስተናግዳል። ግን ግጭት እና ጦርነት ያመጣል።

አማራጩ ምንድነው። የጎሳ ጥያቄዎች በጎሳ አስተዳደር ሳይሆን በሌላ መልኩ ይመለሱ። ለምሳሌ «የአካባቢዬ ባህል አይናድ» ከሆነ በአካባቢ ፖለቲካዊ መብቶች ይመለስ። «ቋንቋዬ ይስፈን» ከሆነ በአካባቢ ፖለቲካ እና በብሄራዊ ዴሞክራሲ መንገድ ይመለስ። ወዘተ። የጎሳ ጥያቄዎች በዚህ መልኩ ሊመለሱ ይችላሉ። እንኳን እንደ ኦሮሞ አይነት የግዙፍ ጎሳ ጥያቄ የአናሳዎችም በዚህ መልኩ ይመለሳል።

Saturday, 29 December 2018

The 'democracy manual' is not for us...

I'm afraid that too many of our political elites think that bringing about political peace and justice in Ethiopia is just a matter of following the 'democracy manual', that is, implementing the standard formula (that comes with funding) given by organizations such as the NDI and NED and many others eager to neocolonise. Just look how well this formula has done in Eastern Europe, where most countries are rapidly depopulating and are wallowing in depression, psychological and economic. Or in Iraq, Afghanistan, Ukraine, or many of the other countries that well funded 'democracy promotion' NGO's have had the opportunity to work their magic! I, for one, wouldn't want Ethiopia to become another Latvia.

Our elites need to think beyond copy and paste. Beyond Huntington and Fukuyama and whoever else is the mode. They need to learn to look to their own rich heritage to find robust solutions for our political and social problems, solutions built on stone rather than sand. Ethiopians value peace, love, and forgiveness. These are fundamental characteristics of our tradition. We may not always practice what we value - in fact, we often don't - but these are the things we value. The overwhelming support that Prime Minister Abiy Ahmed received for his (simple) message of peace, love, and forgiveness is a testament to this. I cannot imagine another country where such a simple message would have worked the wonders it did in Ethiopia.

Elites: We need confidence in our tradition and we need imagination. Please move beyond your academic indoctrination. Look towards your elders. Look towards your rich tradition with neither rose nor dark coloured glasses, but with the right mix of empathy and understanding. Develop self-confidence as Ethiopians, as well as a prudent humility. Aim for the goal of Ethiopia not becoming another Germany, but becoming truly Ethiopian.

Tuesday, 24 July 2018

የጠ/ሚ አብይ ነፃ ምርጫ ፍላጎት

በቅርብ ጠ/ሚ አብይ አህመድ ለምሁራን ባደረጉት ውይይት የነፃ የመድበለ ፓርቲ ምርጫ በሁለት ዓመት ውስጥ ማካሄድ እወዳለሁ ብለዋል። ምሁራኑ ቆሞ አጨበጨበ ተብለናል። እውነትም ነፃ ምርጫ ጥሩ ነው አብዛኞቻችን የምንመኘው ነው። ነገር ግን በቂ ቀድሞ ዝግጅቶች ካልተደረጉ ምርጫው የግጭት መፍትሄ ሳይሆን የግጭት ምንጭ እና ማባባሻ ይሆናል (https://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/03/blog-post_8.html)።

በተለመደው የፖለቲካ «ቴኦሪ» የሀገር ራእይ በህገ መንግስት ይገለጻል። ስለዚህ አንድ አዲስ ሀገር ሲፈጠር (እንደ ኤርትራ 24 ዓመት በፊት) ወይንም ወደ «ዴሞክራሲ» ሲሸጋገር አንድ የሽግግር ውየንም ሽማግሌዎች ቡድን ይቋቋም እና የህዝቡን እና የልሂቃኑን አስተያየት እና ራእይ ይሰበስባል። በዚህ ሂደት መሰረት ህገ መንግስት ይደነገጋል (ወይንም ያለው ይታደሳል)። ህገ መንግስቱ እንደ ሀገሩ ህዝብ የመሃበራዊ ስምምነት ይሰራል። ይህን ተመስርቶ ምርጫ ይቃሄዳል ውጤቱም ይከበራል። ይህ ነው የቴኦሪው አካሄድ።

ግን አብዛኛው ጊዜ እንደዚህ አይሳካም! የቅርብ የኢትዮጵያ እና የኤርትራ ታሪኮች ይመሰክራሉ። ህገ መንግስት ተደንግጎ «ዴሞክራሲ» አልመጣም። ሌላ ጥሩ ምሳሌ የግብጽ ሀገር የቅርብ ታሪክ ነው (https://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2016/09/blog-post_8.html)። ታሪኩ ባጭሩ እንዲህ ነው። ተቃዋሚዎች ለረዥም ዓመታት እርስ በርስ ባለመተማመን እና ባለመስማማት በጦር ስራዊቱ የሚደገፈው የሙባረክ (የሳዳትም) መንግስት በስልጣን ቆየ። ተቃዋሚዎች የማይስማሙበት ምክንያት ህብረተሰቡ የተከፋፈለ ስለሆነ ነው። «ለዘብተኛ» ሙስሊም፤ «አክራሪ» ሙስሊም»፤ ክርስቲያን፤ ሃብታም፤ ደሃ፤ ኮምዩኒስት፤ ነጋዴ እያለ ተከፋፍሏል ክፍፍሉ በፖለቲካ ፓርቲዎች ይንጸባርቃል። ሙባረክም ሲገዛ አንዱን ጎራ ከአንዱ ጎራ እያጣላ ወይንም ባላቸው ጥል እየተጠቀመ ነበር።

ከዓመታት በኋላ በ2003 ተቃዋሚዎቹ ተስማሙና ይህ ስምምነታቸው የህዝብ አብዮትን ለማካሄድ እና ለማሳካት አበቃቸው። የተቃዋሚው ልሂቃን እና ብዙሃን የሙባረክን በጦር ኃይሎች የተመሰረተውን መንግስትን ገለበጠ። ዓለም አጨበጨበ። ተቃዋሚዎች ተሰብስበው ምርጫ ለማድረግ የሚያስፈልጋቸውን ቀድሞ ስምምነቶች አድርገው ምርጫ አካሄዱ። «ለዘብተኛ/አክራሪ» የሚባለው የሙስሊም ወንድማማቾች ፓርቲ አሸነፈ እና በፓርቲዎቹ ስምምነት እና ባለው ህገ መንግስት መሰረት ስራ ጀመረ። ግን ሌሎቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የሙስሊም ወንድማማቾች አገዛዝን እየተጠራጠሩ እየተቃወሙ መጡ። ወደ የከረረ እና የማይፈታ ግጭት ገቡ። መጨረሻ ላይ እነዚህ ፓርቲዎች እና ተከታዮቻቸው ይህ የሙስሊም ወንድማማቾች መንግስት ከሙባረክ መንግስት አይሻለንም ብለው ደመደሙ። መጀመርያ ላይ የገለበጡት ጦር ኃይልን እባካችሁ ተሳስተን ነበር ይህን መንግስት ገልብጡልን ብለው ጠየቋቸው። «ዴሞክራሲ» በግብጽ አበቃ። ዛሬ የግብጽ ጦር ኃይሎት ተመልሰው የአምባገነን ስርአት መስርተዋል።

ይህ ታሪክ የሚያስተምረን ሁለት ነበር ነው። 1) «ዴሞክራሲ» እና «ምርጫ» በራሱ ፍቱን አይደለም በሀገሩ ራእይ ቀድሞ መስማማት ያስፈልጋል። 2) የሀገሩን ራአይ የሚገልጽ ህገ መንግስት ወይንም ሌላ ቀድሞ ስምምነት ቢራቀቅም የልብ ስምምነት ከሌለ በወረቀት የተጻፈ ዋጋ የለውም። ለምን ብነል ይህን ስምምነት የሚያስከብር የበላይ ኃይል የለም። ሀገ መንግስቱን በግድ አክብሩ የሚል የዓለም የበላይ መንግስት የለም! ከስምምነቱ በኋላ የልብ ስምምነት ባለመኖሩ አንዱ የስምምነቱ (ግዙፍ) አካል ሌቀዳደው ከፈለገ ምንም ማድረግ አይቻልም። ስምምነቱ የሚደነገገው ሁሉም የተስማሙበትን እንዲያቁ ነው እንጂ በግድ ለማስከበር አይደለም።

ይህን ሁሉ ተገንዝበን ጠ/ሚ አብይ ነፃ ምርጫ ላማካሄድ መጀመርያ ሀገር አቅፍ ራእይ እንዲመሰረት ማድረግ አለባቸው። ቴኦሪው እንደሚለው የተለያዩ ህዝብ ወቃዮችን ሰብሰበው ስለ ህገ መንግስቱ እና ምርጫው አካሄድ ስምምነት እንዲኖር ማድረግ አለባቸው። የልብ ስምምነት እንዲኖር ማድረግ አለባቸው። ልድገመው፤ የልብ ስምምነት ማድረግ አለባቸው። ይህን በተወሰነ ወራት ማድረግ ይችላሉ ወይ ነው ጥያቄው።

አንዱ ትልቅ እንቅፋት የሚመስለኝ በአሁኑ ኢትዮጵያ በቂ ህዝብን የሚወክል ተቋማት የሉም። ተቃዋሚ ፓርቲዎች እጅግ ደካማ ናቸው። ማንን እንደሚወክሉ እነሱም እኛም ለማወቅ ይከብደናል። አቅምም መዋቅርም የላቸውም። ተከፋፍለዋልም። በተጨማሪ ሁለቱ ትልቅ የፖለቲካ ጎራዎች የኢትዮጵያ ብሄርተኞች እና የጎሳ ብሄርተኞች የተራራቁ ናቸው። እንኳን እርስ ብሰር ውስጣቸውም አይስማሙም አንድ ሀገራዊ ራእይ የላቸውም።

በኔ እየታ በዚህ ጉዳይ ላይ ብዙ ስራ ይጠበቃል። ተቃዋሚዎች መጎልበት አለባቸው። ምናልባት 1500 ፊርማ ፋንታ 100,000 ፊርማ ነው የሚያስፈልፈው እንደ ተቃዋሚ ለመመዝበብ ማለት ያስፈልግ ይሆናል በግድ ትብብረና አቅም ለማጎልበት። ምናልባት ከመንግስት የተወሰነ ድጎማ ሊያስፈልጋቸው ይችላል። ዋናው ግን የመወያያ መድረክ እና ጊዜ፤ በተለይም ጊዜ፤ ያስፈልጋቸዋል። ምናልባት መጀመርያ የከተማ እና የክልል ምርጫዎች እንደ ሙከራ ማካሄድ ያስፈልግ ይሆናል። እንደዚህ አይነት ብዙ ነገሮች መታሰብ አለባቸው። ይህን ሁሉ ስል ደግሞ የኢህአዴግ ውስጣዊ ጉዳይ አለ…።

ስለዚህ ነፃ ምርጫ ሁላችንም የምንፈልገው ነገር ቢሆንም እዛ ለመድረስ ሂደቱ ትልቅ ጥንቃቄ ያስፈልገዋል። ቀድሞ ሁኔታዎች በደምብ በማያሻማ ሁኔታ እስኪሟሉ ምርጫ አለማካሄድ ነው የሚመረጠው። ዋናው ነበር ምርጫው ሳይሆን የህዝብ ለህዝብ በሀገራችን ራእይ ያለ ስምምነት ነው። ያንን ስምምነት በትክክሉ ገደረስንመት ሌላው ሁሉ በቀላሉ ይሳካል።

Thursday, 8 March 2018

ዴሞክራሲ

ስለ ዴሞክራሲ ብዙ ተጽፏል። በንደፈ ሐሳቡ ደረጃ ምንም መጨመር አልፈልግም። በዚህ ጽሁፍ አሁን ባለን የኢትዮጵያ የፖለቲካ ጉዳይ ዙርያ ስለ«ዴሞክራሲ» ያለን አመለካከት ምን ቢሆን ይበጀናል የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ ነው የምወደው።

እንደ እስክንድር ነጋ አይነቶቹ በርካታ (ጀግና) የነፃነት ታጋዮቻችን የችግራችን መፍትሄ ዴሞክራሲ ነው ይላሉ። በአንድ ወቅት እኔም እንደዚሁ ይመስለኝ ነበር። ግን ጉዳይ ከዛ እጅግ ውስብስብ እንደሆነ ተረድችያለሁ።

ዛሬ ባለን ህገ መንግስትና ጠቅላላ የመንግስታዊ አወቃቀር የነፃ ምርጫ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ቢካሄድ ችግሮቻችን ይፈታሉ ብለን እንገመታለን? አሸናፊዎቹ፤ ተሸናፊዎቹ፤ ጦር ሰራዊቱ፤ የክልል መንግስታት ወዘተ ውጤቱን ተቅብለው ተስማምተው ይሰራሉ ብለን መገመት ኢንችላለን? አዲሱም መንግስት ሰላምና ፍትህ ያመጣል ወይም የፓርላማ ስልጣንና ኃይሉን ተጠቅሞ ግፍና ጭቆና ያሰፍን ይሆን? ህገ መንግስቱን ይቀየር የምንለውሳ? በቂ ድምጽ ካለን አናሳ ድምጽ ያላቸውን የራሳችሁ ጉዳይ ብለን በዚህ ድምጽ ኃይል እንቀይረውና አዲስ ህገ መንግስት እንጭንባቸው ይሆን? ዛሬ እነዚህ አይነቶቹ ከባድ ጥያቄዎች ጥሩና የተሟላ መልስ አላቸው ብዬ እርግጠኛ መሆን አልችልም። ለእነዚህ ጥያቄዎች በሚገባው መልስ ሳይኖረን ወደ ዴሞክራሲ የምንለው ምርጫ ከገባን ደግሞ አደጋ ነው የሚሆነው።

ስለዚህ እንደኔ እንደኔ በመጀመርያ ሰፊ ውይይት በተለያዩ ደረጃዎች ያስፈልጋሉ። የዚህ ውይይት ግብ በርካታ ባለጉዳዮቹ ከብዙሃን እስከ ልሂቃን የአገራችን ማንነትና ፖለቲካ ምን መምሰል አለበት በሚለው ጥያቄና መልስ አንድ ገጽ ላይ እንዲሆኑ ነው። ሰፊ ስምምነት እንድውል ነው። አሁን ያለንበት ደረጃ አገር መገንባት ላይ ነው። በህዝቡም በልሂቃኑም የፖለቲካ መተማመንና መሰረታዊ ስምምነት የለምና። ከላይ የጠቀስኳቸው አይነቶች መሰረታዊ የሆኑ ጥያቄዎች እንኳን ሊመለሱ አልተጠየቁም አልተወያየንባቸውም። ይህን የውይይት ሂደት ሳንጨርስና መሰረታዊ ስምምነት ላይ ሳንደርስ ወደ ምርጫ መሄድ አደገኛ ይመስለኛል። እንደ ግብጽ፤ ኢራቅ፤ እና ሌሎች ምርጫ ያላቸው ወይም የነበራቸው ግን ሰላምና ፍትህ የሌላቸው አገሮች እንድንሆን አይፈለግምና።

እሺ፤ በርካታና አስፈላጊዎቹ ባለጉዳዮች አንድ ገጽ ላይ መሆናቸውና ስምምነት ላይ መድረሳቸው እንዴት ልናውቅ እንችላለን? አንዱ ዋና ምልክት የሚመስለኝ የተቃዋሚ ፓርቲዎች በስል ማለት ነው። ጠንከር ያለ ተቃዋሚ ፓርቲ ከሌለ ወይም ፓርቲዎቹ በጎሳ ብቻ የተመሰረቱ ከሆነ ይህ ጥሩ ምልክት አይመስለኝም። ተመሳሳይ የሆኑ አቋም ያላቸው ተቃዋሚዎች የመዋኸድን ሂደት ለማሟለት ብቃት ከሌላቸው ጥሩ ምልክት አይሆንም። ይህን ያልቻሉ እንዴት አብረው መንግስት ይሆናሉ ወይም እንዴት የአስተዳደሩን ህግ ያከብራሉ? የጎሳ ፓሪቲ ብቻ ካለ ደግሞ እንዴት ነው ፖለቲካ ስረአቱ የማይቀረውን የጎሳ ውድድሩን በሰላም ማስተናገድ የሚችለው? አሁንም ከባድ ጥያቄዎች። እንደምናየው ወደ ምርጫ ከመግባታችን በፊት ብዙ ስራ አለ ቀድመሁኔታዎችም መሟላት አለባቸው።

ይህን ካልኩኝ በኋላ እስቲ ይህን ጥያቄ ልጠይቃችሁ፤ ዴሞክራሲ ቢኖር ሰላምና ፍትህ ይኖራል ማለት ነው? እስቲ አንድ አንድ እውነታዎች እንመልከት። በዓለም ታላቅ የሚባለው ዴሞክራሲ አሜሪካ ነው። በጦሩ ኃይል በርካታ የዴሞክራሲ አገርዎች በሰላም እጠብቃለሁ እሸከማለሁ ባይ ነው። ግን ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ አሜሪካ ወደ 20 ሚሊዮን ሰዎች በተለያዩ ጦርነቶች ገድሏል ይባላል። አጭር ትዝታ ያለን መቼም ስለ ኢራቅ፤ ሊብያ፤ ሶርያ እናውቃለን። ኢህአዴግ  ከዚህ ጋር ሲወዳደር መለአክ ነው ማለት ይቻላል! ግን አሜሪካ ለኑሮ ጥሩ አገር ነው። ገንዘብ አለ፤ ከሞላ ጎደል ፍትህ አለ፤ የተወሰነ ነፃነት አለ። ሁላችንም ወደዛ ለመሄድ እንሻለን። ግን ገንዘቡ ባይኖር በአሜሪካ ምን ይሆን ነበር?

ምናልባት አውሮፓ ያላችሁ ኢትዮጵያዊያን ለምን አሜሪካን እንደ ምሳሌ ትጠቀማለህ ትሉ ይሆናል። ሰላማዊዋ ስዊድንሳ? እውንቱን ለመናገር የስዊድን የጦር መሳርያዎች በዓለም ዙርያ ምን ያህል ሰው እንደተገደለ የተቆጠረ አይመስለኝም። ግን ትንሽ አይመስለኝም። ደግሞ ከሳውዲ አራቢያ ያላቸው ጓደኝነታቸው እንዴት ፍቅር የተሞላ ነው?!

ዴሞክራሲ ለሰላምና ፍትህ ሊበጅ ይችላል፤ ይህ ጥያቄ የለውም። ግን ሰላምንና ፍትህን ለማስፈን ሥርዓቱ በራሱ አይበቃም።  ብዙሃኑም ልሂቃኑም ቀድሞ በትወሰኑ መሰረታዊ ጉዳዮችና አስተሳሰብ መስማማት አለባቸው። ከህግና የሂደት ደምብ አስተሳሰብ ይቀድማል። አሰተሳሰቡ ካለ ህጉ ይመጣል በሚገባውም ይተገበራል። ህጉ ካለን አስተሳሰቡ ከሌለ ዋጋ የለውም። ብዙ ነገር በጽሁፍ ላይ የዋለ ህገ ደምቦች ሊካታቱ ይችላሉ ግን አስተሳሰብ በጽሁፍ ሳይሆን በልብ ውስጥ የሚሰክን ባህል ነው መሆን ያለበት። ከዛ በኋላ እንቅፋት ሲያጋጥም ይህ አስተሳሰብ፤ ስምምነትና አንድነት ናቸው ከወረቀት ላይ ከሰፈረው ህግ ይልቅ ወደ መፍትሄ የሚመሩን።

ስለዚህ ዴሞክራሲን እንደ ዋና ግብ ወይንም እንደ ጣዖት አንመልከተው። ዋናው ግብ ፍቅር፤ ሰላምና ፍትህ ነው። እነዚህ እንዲሰፍኑ ዴሞክራሲ አንዱ መሳርያ ሊሆን ይችላል። በዴሞክርሲ ዘንድ ፍቅር፤ ሰላምና ፍትህ ሊሰፍኑ ይችላሉ። ግን ቀድሞ ዝግጅቶች ካልተደረጉ፤ ግባችን እነዚህ እንደሆኑና ዴሞክራሲ መንገድ ወይም ሂደት ባቻ እንደሆነ ካልተረዳን ፍቅር፤ ሰላምና ፍትህ የሌለው ዴሞክራሲ ሊሰፍን ይችላል። እንደዚህ አይነቱ ዴሞክራሲ ደግሞ በበርካታ አገራት ልምድ እንደምናየው አይበጅም።