Showing posts with label Amhara. Show all posts
Showing posts with label Amhara. Show all posts

Monday, 24 October 2022

መልካም አስተዳደር በአማራ ክልል

 እንደሰማሁት ከ2011 ጀምሮ በአማራ ክልል በቀበሌ ደረጃ ህዝቡ የሚያስተዳድረውን የመንግስት ሹማምንቶችን በገምገም እና ካስፈለገ ማጋለጥ ጀመረ። ህዝቡ «መንግስት የህዝብ ተወካይ እና አገልጋይ ነው» ይሚለው መርህ ገብቶት መርህውን በተግባር ማዋል ጀመረ። መልካም አስተዳደር እንዲኖር እኛ እንደ ህዝብ ስራ መስራት አለብን ሃላፊነትም አለብን ብሎ አመነ። ጥሩ ንቃት ነው።

ይህን ተከትሎ ህዝቡ ሙሰኞችን መጠቆም እና ማጋለጥ ጀመረ። ግን እንደሰማሁት መንግስት ሙሰኞቹን ለፍርድ ከማቅረብ ይልቅ ወደ ሌላ ቦታ ወስዶ ሌላ ብዙ ጊዜ የተሻለ ሹመት ሰጣቸው። ህዝቡ ይህንን ተመልክቶ ታዝቦ ተስፋ ቆረጠ። በአስተዳደሩ ሃላፊነት አለብኝ ማለት ተወ እና ወደ ድሮ «አክሩፎ ዝምታ» ገባ። ሙስናው እንደገና ጀመረ።

በዚህ ታሪክ ማን ተጎዳ ብለን ከጠየቅን መልሱ ግልጽ ነው፤ ህዝቡ እና ክልሉ ነው ተጎጂው። መፍትሄ ደግሞ ከተጎጂ ነው መመንጨት ያለበት። መፍትሄው ቀላል ነው። ህዝቡ የኢ-ሙስና ትግሉን መቀታል እና ማጠንከር አለበት። ልሂቃኑ፤ ሚዲያ እና «አንቂው» ደግሞ ትግሉን መደገፍ አለበት። የፍርድ ሂደቱን ተከታትሎ ሙሰኞች የት እንደደረሱ ማጋለጥ እና ተካውሞ ማስነሳት አለበት። ተቃውሞ መንግስት ላይ ሳይሆን ሙሰኞቹ እና የሙሰኞቹ አገልጋዮች ላይ ማነጣጠር አለበት። «መንግስትን ስለምንደግግ ከነዚህ መንግስትን የማይወክሉ ሙሰኞች ልናጸዳው ይገባል» አይነት የስራ መፈክር (mission) ሊኖረው ይገባል።

ለአንድ ህብረተሰብ ጥንካሬ መልካም አስተዳደር ቁልፍ ነው። መተማመን ቁልፍ ነው። አንድነት ቁልፍ ነው። አለነዚህ ህዝቡ የተበታተነ እና ግለኛ ይሆናል ለጠላቶች ተጋላጭ ይሆናል። 

የአማራ ልሂቃን በዚህ ዋና ጉዳይ ላይ በሙሉ አቅሙ ቢሳተፍ እራሱንም ህዝቡንም ይጠቅማል። ሌሎች የማይጥቅሙ የሚጎዱ አጄንዳዎችን ትተን።

Sunday, 10 February 2019

በ«ቤተሰብ ምጣኔ» ስም የሚፈጸመው ጉዳት



 

በ«ቤተሰብ ምጣኔ» ስም በአማራ ክልል እየተፈጸመ የነበረው ማህበረሰባዊ ጉዳት ይህ ደብዳቤ / መመርያ ይገልጻል። አንብቡት።

ከዚህ ደብዳቤ የምንረዳው ዋና ነገሮች እነዚህ ይመስሉኛል፤

፩፤ የመጀመርያ ነጥብ የድርጅቱ አንዱ ግብ (target) የወሊድ መቆጣጠርያ የሚጠቀሙ ሴቶች ቁጥር መጨምር እንደሆነ ግልጽ ያደርጋል። እነዚህ ግቦች የሚመነጩት ደግሞ ከጤና ጥበቃ ቢሮ ብቻ ሳይሆኑ በዋና ደረጃ ከለጋሾቻቸው ማለትም ከተለያዩ የውጭ ሀገር ለጋሾች እንደ ኢዩ እና ዩኤሴይድ (አንድ ምሳሌ፤ http://www.healthpolicyproject.com/index.cfm?ID=country-Ethiopia)። ይህ ማለት የክልሉ መንግስት፤ የጤና ጥበቃ ቢሮ ሃላፊዎች፤ እና የጤና ቢሮ በታቾች ለገንዘብ ብለውም እንደዚህ አይነት ጉዳት የሞላው ፖሊሲ ፈጽመዋል። አዲሱ ቅኝ ግዛት እንዲህ ነው የሚሰራው።

፪፤ እነዚህን ግቦች ለመምታት በጣም ግልጽ የሆኑ ስህተቶች ተፈጽመዋል። ለምሳሌ በሁለተኛ፤ ሶስተኛ እና አምስተኛ ነጥቦች እንደሚገለጸው በረጅም ጊዜ መቆጣጠርያ ላይ የማይሆን ትኩረት ተደርጓል። የጤና ተቋሙ ገንዘቡን ለማምጣት ጸንፈኛ የሆነ አቋም እና ፖሊሲ ለማራመድ ወደኋላ አላለም። ለምሳሌ ሁሉንም ሴቶች የወሊድ መቆጣጠርያ ተጠቃሚ የማድረግ ታርጌት እና ፖሊሲ ከጫፍ የያዙ ጽንፈኝነት በቀር ሌላ ቃል ሊሰጠው ያችልም።

፫፤ ነጥብ ሰባት የጤና ጥበቃ ቢሮው እንደ ተቋምም ሰራቶኞቹም ለገንዘብ ብለው የተለያዩ የወሊድ መቆጣጠርያ እንደሚያስተዋወቁ እና ሴቶች ላይ እንደሚጭኑ በግልጽ ያስረዳል። ፖሊሲው የሚመራው ለህዝቡ ጤንነት ምን ይበጃል በሚለው መርህ ሳይሆን ምን ገንዘብ / ጉቦ ያመጣልናል በሚለው ነው። ስለዚህ የፖለሲው እና የተግባሩ አለቆች እና ወሳኞች የውጭ ሀገር ለገሾች እና የወሊድ መቆጣጠርያ ሳጭ ኩባኒያዎች ናቸው ማለት ነው።

፬፤ ይህ የብሉሹ እና የበሰበሰ አሰራር የጤና ተቋሙ ሚስኪን ሴቶች ላይ የቅስቀሳ ዘመቻ እያካሄዱ የሴቶቹ ስነ ልቦና እና ጤና የሚጎዳ ነገሮች እንዲያደርጉ እንደሚያደርግ ነጥብ ስምንት ያረጋግጣል። የጤና ጥበቃ ቢሮ ቢሮው ገንዘብ እንዲአገኝ፤ ሰራተኞቹም ለግላቸው ገንዘብ / ጉቦ / ስኮላርሺፕ እንዲያገኙ ጉዳት እንደሚፈጽሙ ግልጽ ነው።

፭፤ የአማራ ህዝብ ልሂቃኑን በደምብ መፈተሽ እና ማስተካከል እንዳለበት ግልጽ ነው። ከላይ ደጋግሜ የገንዘብ ሚና እንዴት የአማራ ጤና ጥበቃ ቢሮ የውጭ ሀገር ለጋሾች እና የመድሃኔት ሻጮች መሳርያ እንዲሆን እንዳደረገ ገለጽኩኝ። ገን ከዚም አልፎ ተርፎ በርካቶች በርዕዮት ዓለም ደረጃ በዚህ ጸንፈኛ ፖሊሲ የሚያምኑ የአማራ «የተማሩ» ልሂቃን አሉ። ከሁሉም በላይ ይህ ነው የሚያሳዝነው። ልሂቃኖቻችን በበአድ አስተሳሰብ አዕምሮአቸው ተገዝቷል። ወደ ኋላ ብለው የጠጡትን ፕሮፓጋንዳ መፈተሽም አይችሉም። የህዝብ ቁጥር ምጣኔ ከሌላ አንጻር መመልከትም አይችሉም። ህዝቡ እራሱ የራሱን የቤተሰብ ምጣኔ መወሰን እንደሚችል፤ ሃብታም በሆነ ቁጥር እራሱ የሚወልደውን ቁጥር እንደሚቀንስ፤ የቤተሰብ ምጣኔ የህዝብ ቁጥርም መቀነስ ጉዳይ አለመሆኑ፤ ወዘተ መገንዘብ የማይችል ልሂቃን ተፈጥሯል። የህዝቡን ስነ ልቦና እና ማህበረሰባዊ እሴቶች የማያውቅ ልሂቃን ተፈጥሯል። በዚህ ላይ ብዙ ስራ ሊሰራ የሚያስፈልግ ይመስለኛል።

Tuesday, 1 January 2019

የአማራ «ልሂቃን» እና የአማራ ህዝብ ቅነሳ

ማንም በማይክድበት ደረጃ በአማራ ክልል የተካሄደው የወሊድ ቅጥጥር (በተዘዋዋሪ የህዝብ ቁጥር ቅነሳ) ዘመቻ ከሁሉም ክልል በላይ በደምብ «ተሳክቷል»። ማለት የህዝብ ቁጥር ጭማሬ በደምብ እንዲቀንስ አድርጓል።

ይህ ለኔ እጅግ የሚያሳዝን ክስተት ነው። የአማራ ክልላዊ መንግስት በአማራ ልሂቃን ተደግፎ ያልተሟላ እና ኋላ ቀር የህዝብ ብዛት መጥፎ ነው የሚል ፍልስፍና ተሸክሞ የአማራ ክልልን ህዝባዊ አቅምን መንምኖታል። ህዝቡም በመርፌ የሚወገ የወሊድ መቆጣጠርያ መድሃኔት በmarketing እና coercion ኃይል እንዲጠቀም በማድረግ ከባህሉ፤ ከጤንነቱ እና ከራሱ (ከህሊናው) ጋር እንዲጣላ አድርጓል። ሌሎቹ ክልሎች ይህንን መርዛማ አካሄድ ላለመከተል ሲታገሉ የአማራ መንግስት እና ልሂቃን አዋቂ እና ተምረናል ባዮች ሙሉ በሙሉ capitulate አደረጉ። እውነትም «የተማረ ገደለን» (https://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2016/12/blog-post_7.html)።

ዛሬ የኢትዮጵያ መሰረታዊ ችግር የህዝብ ብዛት አይደለም። ከመሰረታዊ ችግሮች መካከል የመሬት ፖሊሲው (መሬት የመንግስት መሆኑ) እንደ ችግር ይበልጠዋል። የህዝብ ብዛት እንዲህ እንዲጨምር ያደረገው ገበሬው መሬቱን ሽጦ ወደ ከተማ መምጣት ስለማይችል የኢትዮጵያ ህዝብ ለ40 ዓመታት artificially ገጠር እንዲቆይ ተደርጓል። ገበሬው በነጻነት መሬት መሸጥ መለወት ቢችል ኖሮ ዛሬ 80-85% የገጠር ነዋሪ ከሚሆን ወደ 60% ደርሰን ይሆን ነበር። የገጠር ህዝብ ስድስት ልጅ ይወልዳል የአዲስ አበባ ህዝብ ሁለት ልጅ ይወልዳል። 40% የከተማ ነዋሪ ሆኖ ከስድስት ፋንታ ሁለት ልጅ በአማካኝ ሲወልድ የህዝብ ቁጥራችን እንዲህ አይጨምርም ነበር። ስለዚህ ልክ እንደ ቻይና በማኦ ዘመን የመሬት ፖሊሲው ነው የዝብ ቁጥራችንን artificially እንዲንር ያደረገው። አሁን ታድያ መሰረታዊ ችግሩን አምኖ ለመቅረፍ ከመሞከር symptomኡን ለማከም እንሞክራለን። ይህ ታላቅ ጥፋት ነው።

በሁለተኛ ደረጃ አንድ ህዝብ የሚወልደውን ልጅ መጠን እራሱ የራሱን ጥቅም አይቶ በholistic እና organic መንገድ ቢቆጣጠር ነው የሚሻለው (በስነ ልቦና እና ማህበራዊ ሰላም ደረጃ)። ከተሜ ሲሆን፤ ቆይቶ ሲያገባ፤ ወዘተ እራሱ አስቦ መወሰን ይጀምራል። በመንግስት እና ኤንጂኦ ኃይል በግፊት እና ጫና በቅኝ ግዛት መልክ ከተመጣበት ችግሩን በደምብ ሳያውቀው ወደ አደገኛ የወሊድ ቁጥጥር ይገባበታል። ከዛ ዛሬ የምናየው backlash ይመጣል። ሴቶች መውለድ አቃተን ይላሉ። ልጆች ጠፉ ይባላል። ወዘተ። የብአድ መፍትሄ ብዙ ጊዜ መፍትሄ አይደለም።

ሶስተኛ፤ መላ ኢትዮጵያም አማራም ለህዝብ ቁጥር እድገት በቂ ቦታ አላት። አልተጨነቀችም። ሌሎች የመንግስት ፖሊሲዎች ናቸው ችግሮቹ። አልፎ ተርፎ አንዱ ላለፉት አመታት የኤኮኖሚ እድገት ያመጣው ግበአት የህዝብ ብዛት ነው። የ100 ሚሊዮን ገበያ እና ሰራተኛ ኃይል ቀላል አይደለም። ጥቅም አለው። ይህ በአማራ ክልል እና ልሂቃን የታሰበበት አይመስለኝም። ውሳኔዎችን በ one track mind ሆነው ነው የወሰኑት።

አራተኛ፤ በዛሬው የጎሳ ችግር ሁኔታ ዴሞግራፊ ወሳኝ ነገር ነው። የአማራ ክልል ህዝብ ቁጥር ቀነሰ ማለት በአንድነት የሚያምነው ህዝብ ቁጥር ቀነሳ ማለት ነው (አማራው ከሞላ ጎደል እንዳለ ከአንድነት ኃይሉ ውስጥ ስለሆነ)። ዛሬ ይህን ሃቅ መካድ አይጠቅምም። ይህ ፖለቲካዊን ይቀይራል። መሃሉን ያደክማል ጎሰኝነትን የሚያራምድ ፖለቲካን ያጠነክራል። ፖለቲካው ይዛባል። የአማራ ክልል መንግስት እና ልሂቃን ይህን እንደ አንድ ግበአት አለማሰባቸው እጅግ ያሳፍራል። ወይ ክፋት ወይንም ጅልነት ነው፤ ይቅርታ አድርጉልኝ። ነባራዊ እውነታን አለመቀበል ነው። ለጎሳ ፖለቲካ ተብሎ የህዝብ ቁጥር እንዲንር ይደረግ ማለቴ እንዳልሆነ መችሄስ ግልጽ ይመስለኛል። ግን ሁሉ ነገር መታየት አለበት እና ሚዛናዊው መንገድ መከተል አለብን ነው የምለው።

መፍትሄው ምንድነው? የወሊድ መቆጣጠርይ ይከልከል ወዘተ አይነት የማይሆን ነገር አደለም የምለው፤ ከአንዱ ጸንፍ ወደ ሌላው! መንግስት ለወሊድ መቆጣጠርያ marketing እና እርዳታ ይተው ነው የምለው። በዚህ ዘርፍ የሚሰሩ ኤንጂኦዎች ይከልከሉ። የታወቁ ጉዳታቸው ያነሰ የወሊድ መቆጣጠርያ መንገዶች ይሸጡ ግን ህዝቡ ላይ አይጫኑ። ህዝቡ አለ ጫና እና ግፊት በorganic እና holistic መንገድ የራሱን ግላዊ ውሳኔ ያድረግ። አለ ጫና እና ግፊት። ይህ መፍትሄ ሁለት ግቦች ይኖሩታል፤ 1) የህዝቡ ስነ ልቦና እና የማህበረሰቡ ስነ ልቦና ይገጋጋል እና ይጠበቃል እና 2)  የህዝብ ቁጥር ጭማሬ ከፍ ይላል፤ ወደ naturally መሆን ያለበት ደረጃዎች ይሄዳል እና ከሌሎች ክልሎች ብዙ አያንስም። በአጭሩ የክልሉ ፖሊሲ ከጫፍ ወደ ሚዛን ይመለሳል ነው (https://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/04/blog-post_6.html)።

Tuesday, 14 August 2018

ተረት ተረት፤ የትግራይ ገዥ መደብ አገዛዝ እና የ«አማራ ገዥ መደብ» አገዛዝ አንድ ናቸው

«የትግራይ ገዥ መደብ አገዛዝ እና የ«አማራ ገዥ መደብ» አገዛዝ አንድ ናቸው»። ይህ ተረት ተረት (myth) በበርካታ ሰዎች ሲደጋገም ወደ እውነታ እያማራ ነው። በቅርቡ ባደረጉት ኑዛዜአቸው የቀድሞ ጠ/ሚ ታምራት ላይኔም ደግመውታል። «የአማራ ገዥ መደብ ብይ አማራ ብዙሃን እንደነገዱት ነው ህወሓት የትግራይ ገዥ መደብ በትግራይ ብዙሃን የነገዱት» ብለዋል። ይህ አስተያየት እጅግ የተሳሳተ ነው።

የሁለቱ አገዛዞች መሰረታዊ ልዩነት ይህ ነው፤ በደርግ እና በንጉሳዊው ስርዓት ጎሳ፤ ዘውግ፤ ብሄር አይነት ጽንሰ ሀሳቦች በህግ ደረጃ አልነበሩም። አገዛዙ በህግ ደረጃ ከጎሳ እና ከጎሰኝነት ውጭ ነበር። በህወሓት አገዛዝ ግን ጎሳ እና ጎሰኝነት በህግ የተደነገገ ነው። ጎሰኝነቱ በልምድ ወይንም በባህል ደረጃ ሳይሆን ህጋዊ ነው። ይህ መሰረታዊ ልዩነት ነው።

በኃይለ ሥላሴ መንግስት ማንኛውም ግለሰብ በጎሳ ምክንያት ከመንግስታዊ ስልጣን እና ሹመት አይከለከልም ነበር። አይከለከልም ብቻ ሳይሆን ጎሳው ጭራሽ እንደ ጉዳይ አይነሳም፤ በህግ እና ስረዓት ደረጃ ጎሳ የሚባል ጸንሰ ሀሳብ የለም። በዚህም ምክንያት በኃይለ ሥላሴ መንግስት በርካታ ከተለያዩ ጎሳ የሆኑ ባለ ስልጣኖች ነበሩ።

ሆኖም የአስተዳደር ቋንቋው አማርኛ ነበር። ይህ ከጅማ ለተወለደው ኦሮሞ መሰናከል ነበር። የገዥ ስረዓቱ ንጉሳዊ ነበር። ይህ ከኮንሶ የተወለዱት ባዕዳዊ ስረዓት ነበር። በነዚህ አይነት ምክንያቶች አማራ ያልሆኑ ወደ ስልጣን ለመቅረብ ከአማራ ይልቅ ይከብዳቸው ነበር ማለት ይቻል ይሆናል። አማራ ቋንቋውን በማወቅ ከሌላው ይበልጥ እድል ነበረው ማለት ይቻላል። እንዲሁም የአዲስ አበባ ተወላጅ ይበልጥ እድል ነበረው ማለት ይቻላል። በዚህ ደረጃ በተለያዩ የጎሳ ተወላጆች የስልጣን እና ሹመት እድል ልዩነት መኖሩን መካድ አይቻልም። ግን ይህ ልዩነት የታሪክ አጋጣሚ ነው እንጂ በህግ የተደነገገ አልነበረም። ስለዚህ አማራ ያልሆነው ቢከብደውም ወደ ስልጣን መምጣት ይችል ነበር። አድሎ ነበር ግን አድሎው ህጋዊ አልነበረም ስለዚህ ሊቀለበስ የሚችል አድሎ ነበር።

የህወሓት አገዛዝ ግን መሰረቱ ጎሰኝነት ነበር። ህወሓት የትግራይ ድርጅት ለትግራይ ህዝብ ነው። አማራው በአማራነቱ ቦታ የለውም። ቋንቋ ባለመቻሉ ወይንም የፖለቲካ ባህሉን ባለማወቁ ሳይሆን በአማራነቱ ምክንያት ስልጣን ሊይዝ አይችልም። በህወሓት ዘመን አድሎ መቀልበስ የማይችል የጎሳ የደም አድሎ ነበር።

ይህን የ«ትግራይ ገዥ መደብ» እና የ«አማራ ገዥ መደብ» አገዛዝ ልዩነት ስንመለከት አንድ ትልቅ ትምሕርት እንማራለን። ይህ ስለ የጎሳ አገዛዝ አደገኝነት ነው። ጎሳ የትውልድ የደም ጉዳይ ስለሆነ በመሰረቱ ህዝብን የሚለይ እና አድሎ (discrimination) የሚያመጣ ነው። በዚህ ምክንያት ነው የጎሳ አገዛዝ የግጭት (conflict) ፋብሪካ የሚሆነው።

የጎሳ መብቶችን ለማስተናገድ የጎሳ አስተዳደርን ከመጠቀም ወይንም የጎሳ መብቶች በህግ ከማወጅ የቋንቋ እና የባህል መብቶችን ማደንገድ ይሻላል። ቋንቋ እና ባህል ማንም መማር መቀየር የሚችለው ስለሆነ መሰረታዊ አድሎ የላቸውም። በዚህ ምክንያት በአድሎ የተነሳ የተጨቋኝ ስሜቶችን አያዳብርም ስለዚህ ግጭትን አያበዛም።

ይህን ተመስርተን ነው የኢትዮጵያ ህገ መንግስት ጸንፈኛ ነው የምንለው። ዓለም ዙርያ ሀገራት የቋንቋ እና ባህል መብቶችን በህጋቸው ያስተናግዳሉ። የጎሳ መብቶችን በዚህ መንገድ ያስተናግዳሉ። ግን የትም ሀገር ጎሳን በህጋቸው አያስተናግዱም። በጎሳ እና በቋንቋና ባህል ያለውን ልዩነት በግጭት መጋበዝ አኳያ በድምብ የታወቀ ስለሆነ ነው እንዲህ የሆነው። ግን ኢትዮጵያ ብቸኛዋ ጎሳን በህግዋ ውስጥ ያካተተች ናት። ለሀገራችን ህልውና ይህን መቀየሩ አስፈላጊ ነው።

Friday, 20 April 2018

ህወሓትን የሚያመልኩ «አማሮች»

ታማኝ በየነ በቅርቡ ባቀረበው «የቁልቁለት ዘመን» የሚባለው ትረካ የተለያዩ የብአዴንና ሌሎች ህወሓት ያልሆኑ የኢህአዴግ መሪዎች ለህወሓትና ለትግራይ ህዝብ ልክ የሌለሽ ሙገሳ ስያደርጉ አየን። ከሙገሳው ይሁን ግን አልፎ ተርፎ እነዚህ ሰዎች ሌላውን በተለይ የአማራ ህብረተሰብን ሲተቹ ሲሰድቡ ይታያል። እንደዚህ አይነት አመለካከት ለ27 ዓመታት ያየነው የሰማነው የኖርነው ቢሆንም እንዲዝህ አይነቱን ክስተት ደግሞ አይቶ መመርመሩ አስፈላጊ ይመስለኛል። ከነዚህ ሰዎች ባሕሪና አስተያየት የምንማረው ነገሮች ለፍትሕ እና ነፃነት ትግላችን ይጠቅማናልና።

ከትረካው ላይ እነ ካሳ ተክለብርሃን፤ አዲሱ ለገሰ፤ ዓለምነህ መኮነን፤ በረከት ስመዖን፤ ተፈራ ዋልዋ፤ ኃይለማርያም ደሳለኝ፤ ታምራት ላይኔ፤ ወዘተ በዚህ አይነት አስተያየት ሲናገሩ ይታያል። ንግግራቸውም አነጋገራቸውም ስሜታዊ ነው። ለህወሓት ድርጅት እና ፍልስፍና ያላቸው ስሜት እና ተገዥነት በደምብ ይታይባቸዋል። እነዚህ አይነት ሰዎች ቁጥራቸው ትንሽ መሆኑ ቢታወቅም ህብረተሰባችንን ለመጉዳት ትልቅ ሚና ተጫውተዋል ይጫወታሉም። እንደዚህ አይነት ሰዎች ወይም እንደዚህ አይነት አስተሳሰብ እንዴት ሊመጣ ይችላል የሚለውን ጥያቄ ካሰላሰልን እና መመለስ ከቻልን  ላሁንም ለወደፊቱም እንደዚህ አይነት ሰዎች እንዳይፈጠሩ ለማድረግ ይረዳናል። ብዚህ መንገድ ትግላችን ይረዳናል።

ዛሬ የነዚህ አይነት ሰዎች እና አስተሳሰብ አመጣትን በዚህ መንገድ እንየው… ለማቅለል ያህል
የንጉሳዊ መንግስቶቻችን የአገዛዝ መርህ በመደብ የተወሰነ ነው እንበል። እርግጥ እንደ አውሮፓ «ፍዩዳሊዝም» አልነበርም ከአንድ መደብ ወደ ሌላ ምሻገገር ይቻላል ግን ዞሮ ዞሮ ንጉሱ መሳፍንቱ ያሉበት የገዥ መደብ አለ ሌሎቹ ደግሞ ተገዥ መደም ውስጥ ናቸው። በዚህ ሥርዓት ሁሉም የራሱ ተልዕኮ አለው ውድድርና ግጭቶች በቀጥታ ከስልጣን እና መሬት ወይም ንብረት የተያያዙ ናቸው።

«ዘመናዊ» መንግስቶቻችን ደርግና ኢህአዴግ ግን በጨቋኝ እና ተጨቋኝ ርዕዮተ ዓለም የተመሰረተ መርህ ነው የሚመሩት። ሁልጊዜ ጨቋኝ ተጨቋኝ፤ በዳይ ተበዳይ፤ ተራማጅ አድሃሪ ወይን ኋላ ቀር፤ አብዮተኛ ትምክተኛ፤ ሰፊ ጠባብ፤ ወዘተ መኖር አለበት። በአንድ በኩል በጥላቻ የተመሰረተ ርዕዮተ ዓለምና ፍልስፍና ነው ማለት ይቻላል።

በዚህ አይነቱ ርዕዮተ ዓለም የሚመራ መንግስት ሁለት አይነት ሰዎችን ይገኛሉ። አንዱ አይነት «ቢሮክራት» ብለን እንሰይመው። እነዚህ ሰዎች በተለያየ ምክንያቶች ለርዕዮተ ዓለሙን «እውነት አማኞች» ሆነዋል። እውነት ነው ብለው አምነውበታል። ምሳሌ ልስጣችሁ። በ1966 አንድ አዲስ አበባ የተወለደ ባለ መጀመርያ ዲግሪ ወጣት ለስራ ወደ ክፍለ ሀገር ይላካል። የሚያየው ድህነት እና ረሃብ እጅግ አሳዝኖት ለ«እኩልነት» መታገል ይጀምራል። ደርግ ስልጣን ሲይዝ ዳኛ ሆኖ ይሾማል «አድሃሪዎችን» ያስቀጣል ንብረታቸውን ያስወስዳል። ለአድሃሪዎቹ ጥላቻ የለውም ብዙም አይተቻቸውም አይሰድባቸውም። ግን ርዕዮተ ዓለሙን በደምን ስላመነበት ጥያቄ ሳይጠይቅ እራሱን ሳይመረምር የፖለቲካ ተልዕኮውን ይፈጽማል። ይህ አይነቱን «ቢሮክራት» እንበለው።

ሌላው አይነቱን «ብሶተኛ» ብለን እንበለው። እንደገና በምሳሌ ልግለጸው። የልጁ አስተዳደግ ምቹ አልነበረም። ትንሽ ሆኖ መንገድ ላይምን ትምሕርትቤትም ከሌሎች ልጆች በላይ ጥቃትና ስድም ይደርስበታል። እያደገ ሲሄድ ቤተሰቡ ከሰፈሩ የተገለሉ መሆናቸውን መረዳት ይጀምራል። የተገለሉበትን ምክንያት በትትክል ማወቅ አልቻለም ግን የተለያዩ ፍንጮችን ሲያቀናብር ድሮ አባቱ ባደረጉት ድርጊት ምክንያት መሆኑን ይረዳል። ሆኖም ልጁ እንደተሰደበ እንደተገለለ ያድጋል። ኢህአፓ አባላት ሲመለምል ጓደኝነት እና ማህበርነት ፍለጋ ልጁ ይሳተፋል። ጫካ ገብቶ በህውሓቶች ይማረካል። ጥሩ ወገናቸውን ያሳዩታል ሃላፊነት እና የቤተሰባዊ ስሜት ያሳዩታል። ኖሮት የማያውቀው ጓደኞች እና ዘመዶች ይሆኑለታል በዚህ ምክንያት ይወዳቸዋል። አብሮ ታግሎ አዲስ አበባ ይገባል። የህወሓት ስኬታማነት ይበልጥ እንዲወዳቸው እንዲወድሳቸው ያደርጋል። ፍልስፍናቸውም እውነት መሆኑን ያረጋግጥለታል። ትግሬ ባይሆንም ቀንደኛ የህወሓት ተቀናቃኝ ይሆናል። ሀወሓትን የማይወዱትን እንደ ጠላት ያያቸዋል። በተለይም የተወለደበት እና ያደገበት ህብረተሰብ ላይ ያለው ጥላቻ ይብሳል። አሁን ካለው ወርቃማ ሁብረተሰብ ጋር ሲያወዳድራቸው …

ስለዚህ «ቢሮክራት» እና «ብሶተኛ»። እርግጠኛ ነኝ ሁላችንም እንደዚህ አይነት ሰዎች እናውቃለን። (እራሳችንም እንደዚህ እንሆን ይሆናል።) ግን ምናልባት ይህ ሰው ክፉ ነው ወይም የተሳሳተ ነው ብለን ላዩን ወይም ሰሙን ብቻ አይተን ትተነዋል። ምንድነው እንደዚህ ያደረገው ብለን ሳንመረምር አልፈነዋል። ግን ለፍርድ ባንቸኩል እና ሰውየውን ተቆርቁረን ብንመለከተው ህይወቱ ለመን ወደዚህ እንዳመራ ለማየት እንችላለን።

ምን ዋጋ አለው እንደዚህ አይነቶችን ሰዎች ማስወገድ ነው ትሉኝ ይሆናል። ግን እንደዚህ ቀላል ቢሆን ኖሮ ድሮ አስወግደናቸው ሰላም አግኝተን ነበር! ያልቻልንበት ምክንያት ህብረተሰባችን እንዲዝህ አይነት ሰዎችን በርካታ አድርጎ ስለሚወልድ ነው። «ቢሮክራቱ» የሚፈጠረው 1) በህብረተሰባችን የእኩልነት፤ ስብዕና፤ ፍትሕ እጦት ስላለ 2) ትምሕርታችን ባህል እና ትውፊትን ንቆ የ«ዘመናዊ» ትምሕርት ላይ ስለሚያተኩር ተማሪዎቻችን መሰረታቸውን ማንነታቸውን ትተው ወደ የማያቁት ጸንፈኛ እና በአድ የሆነ ፍልስፍና ይገባሉ። ስለዚህ ህብረተሰባችን ያልፈታውን ችግር አይተን ችግሩን በራሳችን ትውፊት ከመፍታት በማይሆነው ጸንፈኛ እና በአዳዊ መንገድ መፍታት እንሞክራለን።

ምሳሌ ልስጣችሁ… በኃይለ ሥላሴ መንግስት የነበረው ዋና ቅራኔ የመሬት ጉዳይ ነው። ባላባቶች ሌሎችም በተለያየ አግባብ ያልሆነ መንገድ መሬት አግኝተው ወይም ወርሰው ጭሰኛውን ያሰቃያሉ። የተውፊታችን ምሶሶ የሆኑት ሃይማኖቶቻችን መስረቅ፤ መዝረፍ፤ መጭቆን፤ ወዘተ ልክ አይደለም ይላሉ። ሀብታም ድሃን መርዳት ግድ ነው ይላሉ። ይህን ተከትሎ የመሬት ሽግሽግ እንዲደረግ በርካታ ሰዎች እየሞከሩ ነበር። ቢያንስ ጪሰኞች የመሬቶቻቸው ባለቤት እንዲሆኑ ባላባቶች ሌላውን መሬቶቻቸውን ይዘው እንዲጠብቁ። ግን ይህን ትውፊታዊ አካሄድ ማድረግ ባለመቻላችን ጉዳዩን በማርክሲስት አብዮታዊ መንገድ እንፍታው ለሚሉት መንገድ ከፈትን። ከዚህ ጽሁፍ «ቢሮክራት» የምላቸው ከዚህ ጎራ ናቸው።

ይህ አይነቱ ክስተት እንዳይከሰት ህብረተሰብም ግለሰብም ማድረግ ያለብን በተቻለ ቁጥር ቢያንስ በግል ኑሮዋችን ሰላም እና ፍትሕ እንዲኖር የተጎዱትን ድኾችን መርዳት ነው። ከህብረተሰባችን መሰረታዊ ክፍፍሎችና ችግሮች እንዳይኖሩ ማድረግ ነው። በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ልጆቻችን ባህል እና ትውፊታቸውን ተምረው እንዲያድጉ በበአድ አስተሳሰብ እንዳይዋዥቁ ማድረግ ነው።

ወደ «ብሶተኛው» ስንመጣ ደግሞ… ከ«ቢሮክራቱ» ይብሳል ጉዳቱም ኃይለኛ ነው። ቢሮክራቱ በመረጃ ሀሳቡን ሊቀይር ይችላል ግን ብሶተኛው በጥላቻ ምክንያት እውነትን ማየት አይፈልግም ጭለማ ውስጥ ነው። ስለዚህ እንደ ማህበረሰብም እንደ ግለሰብም እንደዚህ አይነት ሰዎች እንዳይፈጠሩ ከተፈጠሩም ከማህበረሰቡ እንደ «ሽፍታ» ከሚፈነግሉ አቅርብን መያዝ ነው። «ንቀት» የሚባለውን ነገር በማጥፋት ነው።

ብሶተኛ እንዳይኖር ማህበረሰብ ውስጥ ክፍፍል እንዳይኖር ማድረግ አለብን። እስቲ የኃይለ ሥላሴ መንግስት ሲወርድ የሰማነውን «ሌባ፤ ሌባ» የሚለውን መፈክር እናስታውስ። ማን ነው በስሜት እና ንዴት እንደዚህ የጮኸው። ይንቁኛል ብሎ የሚያምን። በመደቤ በማንነቴ ወደ ታች አድርገው ያዩኛል ብሎ የሚያምን። ወዘተ።

የታማኝን ትረካ ሳይ ይሄ ነው በአዕምሮኤ የታየኝ። አንዳንድ «ቢሮክራቶች» ግን አብዛኛው «ብሶተኛ»። ያሳዝናሉ። የራስን ህዝብ የራሽን ማንነት መጥላት እና መናቅ ከባድ ነገር ነው። ለብሶተናውም ከባድ ነው ለማህበረሰቡም ከባድ ነው። እግዚአብሔር ብሶተኛ የማንወልድ ማህበረሰብ ያድርግን። ልጆቻችንን በአግባቡ በባህልና ተውፊታቸው እንድናሳድግ ይርዳን። ብሶት ያላቸውንም ብስታቸውን አይተን፤ ገብቶን፤ ሳንፈርድባቸው ከማህበረሰቡ ሳይሸፍቱ እንድንረዳቸው ይርዳን።

Thursday, 15 September 2016

በፈቃዳችን ነው የምንገዛው

2009/1/4 ዓ.ም. (2016/9/14)

ይህን ነጥበ በተደጋጋሚ በተለያየ መንገድ ለማስረገጥ እወዳለሁ። የዛሬው የኢህአዴግ አገዛዝን የኢትዮጵያ ህዝብ አይፈልገውም የምንለው የዚህ አባባላችንን ሙሉ ትርጓሜ ልንረዳ ይገባል። የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ኢህአዴግን የማይፈልግ ከሆነ ኢህአዴግ የአናሳ ሰዎች አገዛዝ ነው ማለት ነው። አናሳ ድጋፍ ያለው መንግስት ያለ የሌላው ፈቃደኝነት ሊገዛ አያችልም። ልድገመው፤ የአናሳ ድጋፍ ያለው መንግስት ያለ ሌላው ፈቃድ ሊገዛ አይችልም! 

ስለዚህ «የኢህአዴግ አገዛዝን የኢትዮጵያ ህዝብ አይፈልገውም» ስንል የምንገዛው በገዛ የራሳችን ፈቃደኝነት በራሳችን ጥፋት በራሳችን ድክመት ነው ማለት ነው። ሌላ ትርጉም የለውም። የችግሩ ምንጭም መፍትዬውም ከኛ ነው። ኢህአዴግ እንደ በሩ ክፍት የሆነ ቤት ያገኘ ሌባ ነው። ወደ ቤታችን ብንመለስ ሰተት ብሎ ይለቃል። ታድያ መችሄ ነው ወደ ቤታችን የምንመለሰው?

«ድጋፉ አናሳ ቢሆንም ፖሊሱ ደህንነቱ የጦር ሰራዊቱም በሙሉ ከነሱ እጅ ናቸው» ይባላል የኢህአዴግን ኃይልና ጥንካሬ ለማስረዳት። ለማስረዳት ብቻ ሳይሆን ለድክመታንንና ለሽንፈታችን ምክነያት ለመፍጠር። ኢህአዴግን ለማሸነፍ እጅግ ከባድ መሆኑን ለመግለጽ። እንዲሁም ኢህአዴግ ስልጣን በመያዙ ሃላፊነታችንን ለመሸሽ። 

ግን ለዚህ መልሱ ቀላል ነው። መሳሪያው በማን እጅ ነው? በጣም አብዛኛው ፖሊስና ጦር ሰራዊት አማራ ኦሮሞና ከትግራይ ያልሆኑ ጎሳዎች ናቸው። ይህ ማንም ያማይክደው ሀቅ ነው። የፖሊስና የጦር ስራዊቱ አመራር ብቻ ነው ባብዛናው ህወሓቶች ወይም ትግሬዎች። መሳሪያ ደግሞ በአመራር እጅ ሳይሆን በተራ ወታደሩ እጅ ነው ያለው። ስለዚህ መሳርያው በአማራና በኦሮሞ እጅ ነው ማለት ይችሃላል!

እሺ ጡንቻውን ደግሞ ትተን በመንግስት መስርያቤት አብዛኛው ማን ነው። በዚህም ረገር ትግራዩ አናሳ ነው። ለመደምደም ያህል የኢትዮጵያ ስምንት በመቶ ሆነው የትግራይ ህብረተሰብ አገሩን በሙሉ ሊያስተዳድሩት አይችሉም። ሊያስተዳድሩም ሊቆጣጠሩም ሊከታተሉም አይችሉም።

ሌሎቻችን ሃላፊነታችንን ድክመታችንን ለማምለት ምክነያት ፈልገን «ትግራይ ብቻ ሳይሆን ከሌሎቹ ጎሳዎች አደርባዮች እየረዷቸው ነው» እንላለን። ታድያ አደርባዮቹና ትግራዩ ሲደመር አብዛኛ ነው? ከሆነ ኢህአዴግ አብዛኛውን የሚወክል ጥሩ መንግስት ነው ማለት ነው! ታድያ ነው?አይደለም። በእውነቱ የአደርባዩም ቁጥር ትንሽ ነው።

ታድያ እንዴት ነው ኢህአዴግ የሚገዛው። በሌሎቻችን ፈቃድና ትብብር ነው። ትብብር ማለት እያንዳንዳችን ለዚህ አገዛዝ ያለንን አስተዋጾ ተመልክትን አምነን ከመቀየር ይልቅ «ወያኔ ሴጣን ነው» እያልን ማልቀስ ነው። ለኢህአዴግ ስልጣን ለመያዝ ያለንን ሃላፊነት ማምለጥ የኛ የተቃዋሚ ችግር ላይ ከባዱንና አስፈላጊውን ስራ መስራት እንፈልጋለን። «ወያኔ ሴጣን ነው» ብለን መዝፈን ነው የሚቀለን።

ከአብዛኛው የፖለቲካ ጎራ ደግሞ ኢትዮጵያዊ ነን ኢትዮጵያዊ ብሄርትኞች ነን የምንለው ለኢሃዴግ አገዛዝ ትልቅ ሃላፊነት አለብን። ኢህአዴግን በመጀመርያ የወለድነው እኛ ስለሆንን። በኃይለ ስላሴ ዘመን በቂ ለውጥ ባለማድረጋችን፤ የማይሆን «ፈረንጅ አምላኪ» ትውልድ ወልደን የራስ ማጥፋት ዘመቻ ማድረጋችን፤ የደርግን መንግስት ተቆጣትረን ትክክለኛ መስመር ባለማስያዛችን፤ በቀይ ሽብር እንደገና የራስ ማጥፋት ዘመቻ ማካሄዳችን፤ እነዚህ ቅድመ ሁኔታዎች ናቸው ሻዕብያ ኢህአዴግና ኦነግ በ1983 የኢትዮጵያን ህልውና ብቸኛ ወሳኞች እንዲሆኑ ያደረጉት። ከዛም ለ25 ዓመት እርስ በርስ እየተጣላን ለህብረተሰቡ መጥፎ ምሳሌ እየሆንን አሳለፍን። ሃላፊነቱ ታድያ የኛ አይደለምን?

ሃላፊነት ወስደን ምን እናድርግ። ሁሉም በበኩሉ ማድረግ የሚችለው አለ። ሆኖም ሁሉ ስራችን መፈከር መሆን ያለበት «ክፉ አታድርግ» ነው። ይህ ማለት አብዛኞቻችን በመሃበራዊ ኑሮው ክፉ ነገር ከማድረግ ብንቆጠብ፤ ከጎረቤቶቹ ጋር ተፋቅረን ብንኖር፤ ከስራ ባልደረቦቹ ጋር ብንግባባ፤ ለስራተኞቻችን ደግ ብንሆን፤ የተቸገሩትን በደምብ ብንረዳ፤ ወዘተ ለውጥ ወድያው ይመጣል። ኢህአዴግም ምንም ሊከላከለው አይችልም።

ዛሬ እነዚህ አይነት አዝማሚያ እያየን ነው። በአማራ ክልል ለምሳሌ አመራሩም ፖሊሱም ወታደሩም ክፉ ነገር አላደርግም የራሴን ህዝብ አልገልም አልጎዳምም ስላለ ነው የእምቢተኝነት ንቅናቄው እዚ የደረሰው። የብአዴን አመራር ፖሊስና ወታደር በመቅጣት ብቻ ሳይሆን በተለያየ መንገድ ህዝቤን እረዳለሁ፤ በትክክል አስተዳድራለሁ፤ አልጎዳም፤ ወዘተ ካለ ኢህአዴግ ከሌሎች ክልሎች አስተዳዳሪ ፖሊስና ወታደር ወደ አማራ አምጥቶ ለመቆጣጠር ቅንጣት አቅሙ የለውም። (አለው ካልን አናሳ መሆኑን አጣን ማለት ነው!) ለጊዜው ለማስፈራራት ያህል የብዙ ሰው መግደልና ማሰር አቅም አለው እያደረገውም ነው ግን ከተወሰና ደረጃ ማለፍ አይችልም። 

ኢህአዴግም በፖለቲካ የበሰለ ስልሆነ ይህን በደምብ ይገባዋልና በዚህ ማስፈራራትና ጭቆና ነገሩን ካላበረድኩኝ መቆጣጠር አልችልም ብሎ ያምናል። በተዘዋዋሪ ዛሬም የሚካሄደው ማስፈራራት የአማራ ከሃዲዎች ባይኖሩበት ሊካሄድ አይችልም ነበር። (ከሃዲዎቹንም እኛ ነን የወለድናቸው። ቁጥራቸው በርካታ ከሆኑ በአማራ ክልል በኛ መሃል ችግር አለ ማለት ነው የከሃዲ ፋብሪካ ሆነናል ማለት ነው! ከሃዲዎቹ ላይ ከማተኮር የሚፈጠሩበትን ምክንያት አጣርቶ ማስተካከል ነው ያለብን።)

ለአማራ ህዝብ ምክሬ እንደዚህ ነው። እርስ በርሳችሁ ሰላም፤ አንድነት፤ መታማመንና ፍቅር አዳብሩ። መሃበራዊ ኑሮአችሁ ያማረ ይሁን። የቀበለ አስተዳደርን በጥሩ ሁኔታ አስፈጽሙ። ካህናት የህዝቡን የህሊና ንቃትን አዳብሩ በስብከት ሳይሆን ይበልጥ ምሳሌ በመሆን። ውስጣችሁ ያሉትን ቅራኔ ያለባቸውን ቡድኖች እንደ የተለያዩ አናሳ ጎሳዎች በጥበብና በፍቅር ያዙም የጥፋት አካል እንዳይሆኑ ተንከባከቧቸው! በማህላችሁ ያሉትን የተጎዱ ስራ ያጡ ማደርያ ያጡ ወዘተን ተንከባከቧቸው። ሰላማዊ ሁኑ፤ የሰው ቤት ማቃጠል ንብረትንም ማውደም ይቅር። ይህ የህሊናም የፖለቲካም ጉዳት ብቻ ነው የሚያመጣው። ከፍተኛ አስተዳደር ቦታ ላይ ያላችሁ በትክክል አለ ሙስና አለጥፋት አለክፋት አስተዳድሩ። ፖሊስና ወታደሮች መትፎ ነገር አታድርጉ። ሄዳችሁ እሰሩ የሚል አለአግባባ የሆነ ትዛዝ ብታገኙ እምቢ ከማለት ሰውየውን አጣን ብላችሁ ተመለሱ! ወዘተ።

እንደዚህ አይነት እርምጃዎች ሁሉም ህብረተሰብ ማድረግ ይችላል በቀላሉም መንግስትን ይለውጣል። እግዚአብሔር ከኛ ጋር ይሁን ያጠፋውንም ይቅር ይበለን ለፈተናም ካኑ ወድያ እንዳንገዛ ብርታቱ ይስጠን።

Thursday, 8 September 2016

ሙባረክና መለስ

2008/13/2 ዓ.ም. (2016/9/7)

ስልጣን ላይ በነበሩበት ግዜ ፕሬዘዳንት ሆስኒ ሙባረክ ከሃይማኖት ጋር ያልተያያዙ (“secular/liberal”) የግብጽ የዴሞክራሲ ተቀናቃኞችንና ደጋፊዎቻቸውን ለማስፈራራትም ለመተንኮስም «እኔ ከስልጣን ብወርድ የሙስሊም አክራሪዎቹ ይገዟችኋል፤ የምትጠሉትን የሙስሊም ሃይማኖት አገዛዝ የሸሪያ ህግንም ይጭኑባችኋል» ይሏቸው ነበር። ከዛ ደግሞ ወደ ሙስሊም ወንድማማቾች የሚባሉት ትንሽ «ከረር» ያሉ የሙስሊም ፖለቲካ ፓርቲና ደጋፊዎቹ ፕሬዘዳንት ሆስኒ ዞር ብለው «እኔ ባልገዛ ኖሮ እነዚህ ሃይማኖታችሁን የማያከብሩ፤ ሃይማኖት የሌላቸውና ክርስቲያኖች ይገዟችሁ ነበር» ይሏቸው ነበር! ሁለቱም ሙባረክን የሚጠሉትና ዴሞክራሲ እንፈልጋለን ባይ የሆኑት ከሃይማኖት ውጭ ዴሞክራሲ ተቀናቃኞችና የሙስሊም ወንድማማቾች ተፈራርተው አንዱ ሌላው ስልጣን እንዳይዝ ብለው ሙባረክ በስልጣን ላይ እንዲቆይ ፈቀዱ።

ሆኖም ግን አንድ ቀን ሁለቱ የዴሞክራሲ ተቀናቃኝ ጎራዎች በአምባገነኑ ሙባረክ መገዛት በቃን አሉ። ፕሬዘዳንት ሆስኒ ሙባረክን ከስልጣን ለማውረድ ተባበሩ። የሁለቱ ድጋፍ ተደምሮ የሙባረክ መንግስት ከነበረው ድጋፍ እጅግ ከፍተኛ ስለነበር በ2011 እ.ኤ.አ. ወደ 1000 አካባቢ ሰው በሞተለት «የአረብ ፀደይ» ተብሎ በተሰየመው ዓብዮት የሙባረክን መንግስት ገለበጡ። የምዕራብ ዓለም ሚዲያዎች በሙሉ አጨበጨቡ።

የሙባረክ መንግስት ከወረደ በኋላ አዲሲቷ ግብጽ ምን መምሰል አለባት በሚለው ጉዳይ በርካታ ፓርቲዎች ተወያዩ ተስማሙና  አገሪቷንም ለነፃ ዴሞክራሲያዊ ምርጫ አበቋት። ምርጫውን የሙስሊም ወንድማማቾች ፓርቲ በትንሽ ልዩነት አሸነፈ። የቀሩት የፓርላማ መቀምጫዎች በሌሎቹ በበርካታ የዴሞክራሲ ተቀነቃኝ ፓርቲዎች ተያዙ።

ልክ የሙልሲም ወንድማማቾች ስልጣን ከያዘ በኋላ ችግሮች መታየት ጀመሩ። በመጀመርያው ሌሎቹ ፓርቲዎች የሙስሊም ወንድማማቾች ከሃምሳ በመቶ በላይ ድምጽ አገኝቶ ሙሉ ስልጣን ማግኘቱን ቅር ብሏቸው ነበር። ከዛም ቀጥሎ የሙስሊም ወንድማማቾች መሪ መሃመድ ሞርሲ የፓርቲያቸውን ኃይል የሚያጠነክርና ቀስ ብሎ የሸሪያ ህግ ለማምጣት የሚያመቹ እርምጃዎች መውሰድ ጀመረ። እርግጥ አላማቸው የሸሪያ ህግ ላይሆን ይችል ነበር፤ ነገር ግን የሌሎቹ የፖሊቲካ ፓርቲዎች ጠንካራ ጥርጣሬ ይህ ነበር። በተጨማሪም የሙስሊም ወንድማማቾች ቀስ በቀስ ስልጣኑን እየጨመረ እራሱን ሰዎች በየቦታው እየሾመ የሌሎችን ስልጣን እየሸረሸረ ነበር።

በግብጽ ከሃይማኖት ነጻ የሆኑት ፓርቲዎችና እንደ የሙስሊም ወንድማማቾች አይነት የሃይማኖት ፓርቲዎች መካከል ያለው ጥርጣሬና ጥላቻ እንደገና መታየት ተጀመረ። ሙባረክን ለመጣል ብቻ ነበር የተስማሙት እንጂ ከዛ በኋላ ለሚመጣው የግብጽ የፖሊቲካ ሁኔታ ከልባቸው አልነበረም የተስማሙት። የዓመታት ጥርጣሬና አለመስማማታቸውን አላስወገዱም ነበር። በአንድ አገር በሰላምና ሁሉንም በሚያስማማ ህግ ስር አብሮ ለመኖር አልተስማሙም ነበር። ትንሽ አለመግባባት ሲመጣ ወዲያው ወደ ድሮው ጥርጣሬና ጥላቻቸው ተመለሱ።

የዚህ ታሪክ የመጨረሻው ክፍል እጅግ አሳዛኝና አሳፋሪ ነው። አስተማሪም ነው። ከሃይማኖት ነጻ የሆኑት ፓርቲዎች ሁለተኛ አቢዮት አስነሱ። ሙባረክን በስልጣን ላይ ያቆየውን ኃይል የግብጽ ጦር ሰራዊትን የሞርሲን መንግስት እንዲገለብጡ ለመኑ! የሞርሲ መንግስት በዴሞክራሲ ከሚገዘን አምባገነኑ ጦር ሰራዊት ይግዛን አሉ! ይህም የመንግስት ግልበጣ ተካሄደና ይባስ ብሎ ሞርሲና በርካታ ባልደረቦቹ ታሰሩ፤ የሞት ፍርድም ተፈረደባቸው!

ጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ዘናዊም በስልጣን ላይ በነበሩበት ዘመን ህወሓት ወክለው ደጋግመው አማራውን «እኛ ከስልጣን ብንወርድ ኦሮሞ ብሄርተኛው ያርዳችኋል»፤ ኦሮሞውን ደግሞ «እኛ ከስልጣን ብንወርድ ነፍጠኛው አማራ መሬታችሁን ይነጥቅና ባርያ ያደርጋችኋል» እያሉ ይዘፍኑ ነበር። ሁለታችሁ አትስማሙም ልትስማሙም ስለማትችሉ እኛ ህወሓት መግዛት አለብን ይሉ ነበር። ዛሬም በርካታ የህወሓት አክራሪዎች በዚህ አስተሳሰብ እንደተመረዙ ያሉ አሉ።

ሆኖም ይህ የህወሓት ዘፈን የተወሰነ እውነታ እንዳለው እኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ማመን አለብን። ችግራችንን ለመፍታት ችግራችንን ማመን አለብን። በአማራና ኦሮሞ ፖለቲከኞች መካከል ብቻ ሳይሆን በስመ ኢትዮጵያ የሚንቀሳቀሱ ፖሊቲከኞች መካከል እጅግ ከባድና አሳፋሪ ቅራኔ፤ ሽኩቻ፤ አለመተማመንና አለመስማማት አለ። ባለፉት የተወሰኑ ዓመታት ግን እነዚህ ቅራኔዎች እየቀነሱ ሄደዋል። ይህ መሻሻልና ለውጥ አስፈላጊና ለሁላችንም ህልውና ግዴታ ነው።

አንድ ምሳሌ ልስጥ፦ በዛሬ በአማራ ክልል ያለው ንቅናቄ ምክንያት ኢህአዴግ ኦሮምኛን የአዲስ አባባ ቋንቋ አደርጋለሁ ብሎ ጭምጭምታ እያሰማ ነው። ይህ የተለመደው የኢህአዴግ ዘፈን አማራንና ኢትዮጵያዊ ነኝ የሚሉትን የአዲስ አበባ ነዋሪዎችን «ኦሮሞ ሊገዛችሁ ነው» በማለት ለማስፈራራት ነው! ህዝቡ ግን ይህ ማስፈራሪያ አሁን አይሰራም፤ ኦሮምኛን ጭራሽ የኢትዮጵያ ሁለተኛ ብሔራዊ ቋንቋ አድርጉት እያለ ነው። ኢህአዴግ ምን ይበጀው ይሆን!

ይህ ምናልባት ህልም ሊሆን ይችላል፤ ነገር ግን ይህ ህልም በተግባር እንዲውል የኢትዮጵያ ብሄርተኛ ነን የምንለው ወገን ታላቅ ሃላፊነት አለብን። የኛ የፖለቲካ ጎራ በመጀመሪያ እርስ በርሳችን አንድ ሆነን ሽኩቻን አስወግደን ጠንካራ ሆነን ከዛም በዚህ ጉዳይ ላይ መስራት አለበን፤ ከኦሮሞ ፖለቲካ ወገን ጋር በደምብ ስምምነት ላይ ባስቸኳይ መድረስ አለብን። እንደ ግብጽ አገር በመጨረሻ ደቂቃ እንስማማ ማለት ውድቀትን መጋበዝ ይሆናልና።