Wednesday 1 August 2018

ስለ አማራ ብሄርተኝነት አንድ የውይይት ምዕራፍ

1. አማራ የተጠቃው በብሄር ስም ስላልተደራጀ ነው ከሆነ የጎሰኝነትን ፍልስፍና አምነንበታል ማለት ነው። አማራ 60 ዓመት በፊት በተለየ መልኩ እየተጠቃ ነበርን? አይደለም ከሆነ መልሱ ጥቃቱ የተጀመረው የጎሳል ፖለቲካ ሀገር ውስጥ ሲገባ ነው ማለት ነው። ይሄውን ያጠቃንን ፍልስፍና መቀበል ሽንፈት እና ይበልጥ ጥቃት ነው።

2. አማራ በብሄር መደራጀቱ የአማራን ጥቅም አያስከብርም ብዬ ነው የማምነው። ለምን? በብሄር ተደራጀን ማለት ክልላችንን አስከበርን ማለት ነው በዛሬው ፖለቲካ ሌላ ትርጉም የልውም። ከአማራ ክልል ውጭ ያለውን አማራ አዲስ አበባም ላለው አማራ ምንም ልናደርግለት አንችልም። ነገ በኦሮሚያ የአማርኛ ትምሕርትቤቶች ሁሉ ይዘጋሉ ቢባል (በዴሞክራሲያዊ ምርጫ በድምጽ ብልጫ ማለት ነው) አማራው ምን ሊያደርግ ነው። ኦሮምኛ በአማራ ክልል መከልከል?! በሶማሌ ክልል ጅግጅጋ ሶማሌ ተናጋሪ በመንግስትም ሌሎችም ስራዎች ቀድሞ የሚቀጠረው ቢባል አማራው ምን ያደርጋል። ድምጽ ብልጫ የለውም። አዲስ አበባ አተሰፋም ቢባል አማራው ድርጅት ምን ያደርጋል? ከአማራ ክልል ውጭ ያሉት አማሮች የአማራ ድርጅቱ አባል ቢሆኑ ምን ይጠቅማቸዋል ጥቃት ብቻ ይሆናቸዋል እንጂ። ግን አማራው በስመ ኢትዮጵያዊነት ቢደራጅ ከሌሎች (የዘር ቅልቅሎች እና ሌሎች ብሄሮች) ስምምነት ( alliance) እያደረገ ይበልጥ ኃይል ይኖረዋል። ይህ ይበልጥ መላው ሀገር ውስጥ ያለውን አማራ መብት ያስከብራል።

3. «ውሸት አንድነት ይብቃ፡፡ ስንቴ እንታለል፡፡» ይህ በትክክል የጎሰኞቹ አቋም ነው። አቋማቸው እንዲህ ነው 1) ኢትዮጵያ ስለካደችን ወደ ጎሳችን እንመለስ 2) ኢትዮጵያ የካዳችን የፈረሰችበት ምክንያት መጀመርያውኑ ሀገር ሳይሆን የጎሳዎች እስር ቤት ስለሆነች ነው። መፍረስዋ ይህን ነው የሚያመለክተው ነው አቋማቸው። አሁንም የአማራ ብሄርተኝነት እንዲህ ነው የሚለው። እራስህን መጠየቅ ያለብህ «አንድነት» እንደምትለው «ውሽት» ወይም ውድቅ የሆነው በኛ በአስፈጻሚው ድክመት ነው ወይንም «አንድነት» የሚለው ጽንሰ ሀሳብ ከመጀመርያ ውሸት ስለሆነ ነው? የመጨረሻው ከሆነ መልስህ መጀመርያውኑ ያጠቃህ የጎሰኝነትን ፍልስፍና ጠቀብለሃል ማለት ነው። የመጀመርያ ከሆነ መልስህ ማድረግ ያልብን አንድነትን መተው ሳይሆን መትክክሉ ማስፈጸም ነው። «አንድነት» የተበላሸው እኛ የአንድነት ደጋፊዎች ከነ ሁሉም አማራ (በዛን ጊዜ) እርስ በርስ በፈረንጅ ፍልፍና ተለክፈን ስለተከፋፈልን ነው እንጂ አንድነቱ ራሱ ችግር ኖሮት አይደለም። አይደለምን?

4. ለላይ ጠቅሼዋለሁ እንጂ የራሱ ነጥብ ይገባዋል፤ በስመ አማራ መደራጀት ከሌሎች «ኢትዮጵያዊ ነን» ከሚሉ ጋር ለመጋራት ያለንን እድል ይቀንሳል። ለምሳሌ አዲስ አበባ ወይንም ናዝረት የህብረ ብሄር ድርጅት በቀላሉ ምርጫ ያሸንፋል ግን የአማራ ድርጅት አያሸንፍም። የህብረ ብሄር ድርጅቱ ያአማራውን መብት በደምብ ያስከብራል። የሚበጀን ምን እንደሆነ ግልጽ ነው።

5. መጠቃት ስሜትን ይነካል ይገባኛል። ግን ስሜታዊ ሆኖ ላለ ችግር ወደ ተሳሳተ መፍትሄ መግባት ጎጂ ነው ባለፉት 60 ዓመት የሀገራችን ታሪክ ነው። «መሬት ላራሹ» ብለን መሬትን ለመንግስት ሰጥተን። አንባገንነት ብለን ወደ ጎስኝነት ገባን። ወዘተ። አሁንም አማሮች ተጠቃን እንላለን መፍትሄው ግን በኢትዮጵያዊነት መደራጀት ነው።

6. በኢትዮጵያዊነት መደራጀት ያልቻልንበት ምክንያት እንደጠቀስኩት ከ60 ዓመት በፊት በፈረንጅ ፍልስፍና ተወክፈን እርስ በርስ መፋጀታችን ነው። ይህ የሆነው በኢትዮጵያዊነት ስለተደራጀን አይደለም። አሁንም በስመ አማራ እንደራጅ በኢትዮጵያዊነት ከመደራጀት ይቀላል የሚለው እጅግ የተሳሳተ ነው። በርካታው አማራ በስመ አማራ መደራጀት አይፈልግም። ምናልባት ከመቂ ፕሮፓጋንዳ በኋላ ቁጥሩ ይጨምር ይሆናል ግን ዛሬ የአማራ ብሄርተኝነት ከፋፋይ ሀሳብ ነው። ባሁኑ ወቅት አንድ በመሆናችን ጊዜ ከፋፋይ አቋምን መግፋት ምን ማለት ነው። የግቡን ተቃራኒ ነው።

No comments:

Post a Comment

ለሀሳብዎ አመሰግናለሁ!