Showing posts with label compensation. Show all posts
Showing posts with label compensation. Show all posts

Monday, 4 March 2019

ተረት ተረት፤ አዲስ አበባ የኦሮሞ ገቤሬዎችን አፈናቅሏል

1. የአዲስ አበባ ህዝብ ምንም ፖለቲካዊ ውሳኔ አድርጎ አያውቅም። በኢህአዴግ (ከነ ኦህዴድ) የተገዛ ህዝብ ነበር። ስለዚህ የአዲስ አበባ ህዝብ ማንንም አላፈናቀለም። አፈናቃይ ካለ ኢህአዴግ ከነ ኦህዴድ ነው።

2. ከአዲስ አበባ የተፈናቀሉት ባብዛኛው ኦሮሞ ቢሆንም የተወሰኑ አማሮች እና የሌላ ጎሳ አባላት ነበሩ።

3. ካአዲስ አበባ ውስጥ የተፈናቀሉት ደግሞ ከሁሉም ጎሳ ነበሩ። እነዚህ የአዲስ አበባ ተፈናቃዮች ከአዲስ አበባ ዙርያ የተፈናቀሉት ገበሬዎች ይበልጥ ተበድለዋል በደልን በገንዘብ ከተረጎምነው። ከካዛንቺስ 50 ካሪሜትር ቦታው የተፈናቀለው ምናልታብት ሁለት ሶስት ሚሊዮን ብር ነው ያጣው። ከቡልቡላ የተፈናቀለው ገበሬ የዚህ ሩብም አልከሰረም።

4. ገበሬዎች እና ሌሎች «ተፈናቀሉ» ስንል መንግስት የማይመጥን ትንሽ ካሳ ሰጥቷቸው በግድ ከመሬታቸው አስነሳቸው ነው። አድግራጊው የአዲስ አበባ ህዝብ ያልመረጠው የአዲስ አበባ መንግስት ውየንም አብዛኛው ጊዜ የኦህዴድ መንግስት ነው። ገበሬውን አነስተኛ ካሳ ሰጥቶት ለኢንቬስተር በከፍተኛ ዋጋ ሽጦ ትርፉን ኪስ አስገብቷል። ለዚህ የአዲስ አበባ ህዝብ ትጠያቂ አይደለም፤ ኢህአዴግ እና ኦህዴድ ናቸው።

5. ታላቁ ግን ማንም የማያነሳው ጉዳይ የሀገራችን የመሬት ፖሊሲ ነው። መሬት የመንግስት በመሆኑ ነው ገበሬዎችም ሌሎችም የሚፈናቀሉት እና «ተፈናቀሉ» የሚባለው። አዲስ አበባ ሲሰፋ (እንደ ከተማ ይሁን እንደ metropolis) ዙርያ ያሉት ገበሬዎች ዋና ተጠቃሚ ነበር መሆን ያለባቸው፤ ይሆኑም ነበር መሬት የግል ቢሆን። አዲስ አበባ ዙርያ ያሉት ገበሬዎች ከተማው እየሰፋ ስለሄደ መሬታቸውን በእጅግ ውድ ዋጋ ሊሸጡ እና ሊጠቀሙ ይችላሉ። ቡልጋ ያለው ገበሬ የመሬቱ ዋጋ አንድ ብር በካሬ ቢሆን ይው መሬት አዲስ አበባ ዙርያ መቶ ብር ሊሆን ይችላል። በዚህ መንገድ ነው የትም ሀገር ከተማ ሲሰፋ ዙራይ ያሉት ገበሬዎች ሎተሪ እንዳሸነፉ የሚቆጠረው። ግን ኢትዮጵያ ገበሬው መረቱን መሸት ስለማይፈቀድ እና መንግስት ሲፈልግ መንጠቅ ስለሚችል ከተማ ዙርያ ያለ ገበሬ ጭራሽ ይሰጋ! ስለዚህ በዚምህ ረገድ ጥፋቱ የአዲስ አበባ ህዝብ ሳይሆን የኢህአዴግ እና ኦህዴድ የመሬት ፖሊሲ ነው። አዲስ አበባ ዙርያ ያሉ ገበሬዎች በኢህአዴግ/ኦህዴድ ምክንያት በሚሊዮኖች የሚቆጥር ብር አጥቷልና!

Friday, 16 November 2018

ብራቮ ኤርሚያስ ለገሰ!

ይህን የኤርሚያስ ለገሰ ቃለ ምልልስን እዩት!

https://www.youtube.com/watch?v=WB2enMd2Ilk&t=3990s

ሁለት ታላቅ ነገሮች ያስተምረናል፤

1) ሃላፊነት፤ ጸጸት፤ እና ንስሃ፤ ኤርሚያስ ከመጸሃፎቹ ሺያች ገንዘብ ለተለያዩ የኢህአዴግ ሰለቦች (እንደ አበበ ክንፈ ሚካኤል)መስጠቱን አውቅ ነበር (ይታወቃል)። ለምን ብሎ ሲጠየቅ የሰጠው መልስ ሃላፊነት፤ ጸጸት እና ንስሃ ምን እንደሆኑ በጥሩ መንገድ የሚያስተምር ነው።

ኤርሚያስ ለኢህአዴግ በመስራቴ ኢህአዴግ ላደረገው ኃጢአቶች ህሊናዬ ስለሚወቅሰኝ ቢያንስ እንደ አቶ አበበ አይነቱን ተጎጂዎች በመርዳት ከራሴ ጋር እታረቃለሁ እና ላደረግኩት እንደ ካሳ ይሆናል ነው። ኤርሚያስ ማንንም አላሰረም አላሰቃየምም። ግን ሃላፊነት እንዳለበት አምኖ በሚመስለው መንገድ ይቅርታ እየጠየቀ ነው። ይህ የሚያስተምረን ሁላችንም በማድረግም ባለማድረግም ከመንግስት ሩቅ ብንሆንም በኢትዮጵያ ለተደረጉት ጥፋቶች ቢያንስ የተወሰነ ሃላፊነት እንዳለብን ነው። ታላቅ ትምሕርት ነው። ሁላችንም ይህን ትምሕርት ተምረን እራሳችንን እንደ ንፁሃን ከመቁጠር እንደ ኤርሚያስ ካሳ ለመክፈል ብናስብ ጥሩ ይመስለኛል።

2) የሰው ልጅ አስተዳደግ እና ጠቅላላ የኑሮ ጉዞ ለባህሪው እና ድርጊቱ አስተዋጾ አለው። ኤርሚያስ ስለ በረከት ስምዖን እና ባልደረባው ሽመልስ ሲጠየቅ «የሰው ልጅ ከመሬት ተነስቶ ክፉ አይሆንም» ብሏል። አስተዳደግ እና ታሪካዊ ምክንያቶች አሉ አለ። ይህን ሃቅ ሁላችንም ብናውቀውም ለመፍረድ ስንቸኩል እንረሳዋለን።

ይህ ሰውን አስተዳደግ እና ታሪክ ድርጊቱ ላይ ሚና አለው ስንል ለድጊታቸው ሰበበ ለማግኘት አይደለም። ለሁለት ምክንያት ነው፤ 1) ከመፍረድ እንዲቆጥበን ነው እና 2) መሰረታዊ ችግሮችን እንድናርም ነው። ለምሳሌ ከሰፈራችን አንድ ቤተሰብ ከማህበረሰቡ አላግባብ ተገልለው ኖረው ልጃቸው የደርግ/ህወሓት ጨቃኝ አሳዳጅ እና አሳቃይ ከሆነ ብዙ ሊገርመን አይገባም። ህብረተሰባችን እንደዚህ አይነት ሰዎችን የማይወልድ አይነት እንዲሆን መስራት እንዳለብን ያስታውሰናል።

አንድ መንግስት ጥሩ የሚሆነው እህታችን፤ ዘመዳችን፤ ጎረቤታችን፤ ወዘተ ሲመሩት ነው። ማለትም በህብረተሰቡ ክብር እና ተቀባይነት ያላቸው ሰዎች ሲመሩት ነው። በህብረተሰቡ ላይ ቂም ያላቸው ሰዎች (እንደ መለስ ዘናዊ) መንግስትን ሲመሩ መንግስቱን የቂም መወጫ ነው የሚያደርጉት። የማህበረሰባችን ዋና ስራ ቂም ያላቸውን ሰዎች አለመፍጠር ነው፤ ሁሉንም አቅፎ መያዝ።

ለማንኛውም ይህን የኤርሚያስ ቃለ ምልልስ እዩት። በጣም አስተማሪ ነው።

Tuesday, 14 August 2018

ተረት ተረት፤ አዲስ አበባ የሰፋችው ኦሮሞ ገበሬን በማፈናቀል ነው

እንደ አብዛኛው ውሸት «አዲስ አበባ የሰፋችው ኦሮሞ ገበሬን በማፈናቀል ነው» የሚለው የተወሰነ እውነታ አለው። አዎን በኢህአዴግ አገዛዝ በአዲስ አበባ ዙርያ ያሉ ገበሬዎች ለመሬታቸው ከሚገባው እጅግ ዝቅተኛ የሆነ ካሳ ተከፍሏቸው በግዴታ ከመሬታቸው ተባረዋል። ግን ይህ ሙሉ ታሪኩ አይደለም።

እንደሚታወቀው በሀገራችን መሬት የመንግስት ነው የሚል አሳዛኝ ህግ ነው ያለው። ይህ ህግ ሲተገበር ስናይ መንግስት ባሰኘው ጊዜ የከተማም ይሁን የገጠር መሬት ከነዋሪዎች ይወስዳል። ሲወስድ ደግሞ የሚከፍለው ካሳ የ«ገበያ» ዋጋ ሳይሆን መንግስት እራሱ የሚተምነው እጅግ አናሳ ካሳ ነው። ልምሳሌ አዲስ አበባ ውስጥ ለ«ልማት» ተብሎ መሬትን መንግስት ሲወስድ የሚከፍለው ካሳ የቤትና የጊቢው አብሮ ዋጋ ሳይሆን የቤቱ (የግንቡ) ዋጋ ብቻ ነው። ለምሳሌ 100 ካሬ ላይ ቤት አለኝ ከሸጥኩት 500,000 ብር ያመጣል እንበል። መንግስት ሊወስደው ከፈለገ ግን የቤቱ ግምብ ዋጋ ብቻ እራሱ (ሶስተኛ ወገን ሳይሆን) ገምቶ ምናልባት 50,000 ብር ከፍሎኝ በግድ ይወስደዋል። በገጥር ደግሞ እንደ ክልሉ እና ዞኑ ቢለያይም አንድ ምሳሌ ልስጣችሁ። መንግስት ከገበሬ መሬቱን ሲወስድ የሶስት ዓመት ገቢውን ለካሳ ይከፍለዋል። ገጠር መሬት መሸጥ ባይኖርም የዚህ መሬት ዋጋ ከዚህ በላይ እንደሚሆን መገመት ይቻላል። የሶስት ዓመት ገቢ ሳይሆን ቢያንስ የአስር ነው መታሰብ የነበረበት።

ከዚም አልፎ ተርፎ ይግባኝ የለም። መንግስት አንዴ ትፈናቀላላችሁ ካለ ይህን ውሳኔ መታገል አይቻልም። ከመሬት ንትቅያው በስተጀርባ ያለው የገንዘብ እና የፖለቲካ ኃይል እጅግ ከባድ ነው። የኢህአዴግ ባለሟሎች አሉ፤ ኢነቬስተር ዩኖራል፤ ጉቦኛ መንግስት ሰራተኛው አለ፤ ባለ ስልጣን አለ። ባለ መሬቱ ከነዚህ ጋር መጋፋት አይችልም እና ተዛዙ ሲመጣ እሺ ጌታዬ ብሎ መንግስት የሚሰጠውን ካሳ ተቀብሎ መሄድ ነው።

ይህ ሁኔታ ያለው በመላው ሀገሪቷ ነው በአዲስ አበባ ብቻ አይደለም። ከመሬታቸው አለ አግባብ የሚፈናቀሉት ኦሮሞ ብቻ ሳይሆኑ ሌሎች ሁሉ ናቸው። ገበሬዎች ብቻ ሳይሆን ከተሜዎችም ናቸው። አዲስ አበባን ከመሬታቸው የሚፈናቀሉትን ካየን ከአዲስ አበባ ዙርያ ካሉት ገበሬዎች ይልቅ የከተማው ተፈናቃይ ነው ይበልጥ መፈናቀል የሚጎዳው። ለምን? አራት ኪሎ 100 ካሬ ላይ የሚኖር ቤቱን ከነ ጊቢው ቢሸጠው አንድ ሚሊዮን ያገኝበት ነበር 50,000 ተሰጥቶ ይባረራል። ገበሬው ግን ሰፋ ያለ መሬት ቢኖረውም ከከተማ ሩቅ በመሆኑ ዋጋው ያን ያህል ውድ አይደለም በሚሰጠው ካሳ እና በመሬቱ እውነተኛ ዋጋ ያለው ልዩነት እንደ ከተማው መሬት አይሆንም። ስለዚህ አዲስ አበባ እና ዙርያ ሁሉም በመንግስት ከመሬታቸው የተፈናቀሉ ቢጎዱም በአማካይነት የከተማው ከገበሬው ይበልጥ ተጎድቷል።

በመጨረሻ ማን ነበር እነዚህን ገበሬዎች የሚያፈናቅለው ብለን ከጠየቅን የኦሮሚያ የኦህዴድ ቀበሌ እና ውረዳ ሰራተኞች እና የነሱ አዛዦች ናቸው። ለምሳሌ ባለ ሃብት ወይንም የአዲስ አበባ መንግስት በኢህአዴግ ድጋፍ መጥተው የለገጣፎን ባለስልጣኖች መሬት እንፈልጋለን ይላሉ። እነዚህ የኦህዴድ ባለ ስልጣኖች አላማቸው ትንሽ ካሳ ለገበሬው ሰጥቶ በትልቅ ዋጋ ለአዲስ አበባ ወይንም ለባለ ሃብት መስጠት እና በመካከል ከዋጋ ልዩነቱ ጉቦ መብላት ነው። አዲስ አበባ ውስጥም ይህ ነበር አሰራሩ። በጠቅላላ ላለፉ 27 ዓመት መሬት ለመንግስት ሹማምንት ታላቅ የጉቦ የገቢ ምንጭ እና ለኢህአዴግ ታላቅ የካድሬ መያዣ መንገድ ነበር። ስለዚህ አዲስ አበባ ሳይሆን የራሱ የኦህዴድ ካድሬ ነው አዲስ አበባ ዙርያ ያለውን ኦሮሞ ገበሬ አለ አግባብ ያፈናቀለው። አዲስ አበባ ናት ያፈናቀለቻቸው ማለት ሃሰት ነው።

ሙሉ እውነታው ይህ ነው፤ አዲስ አበባ ዙርያ ሳይሆን አዲስ አበባ ውስጥም ሀገር ዙርያም በየቀኑ ዜጎቻችን ከመሬታቸው አለ አግባብ እና አለ በቂ ካሳ ይፈናቀላሉ። የሚፈናቀሉት ደግሞ ኦሮሞዎች ብቻ ሳይሆኑ ሁሉም ነው። ችግሩ በአዲስ አበባ እና በኦሮሚያ መካከል ሳይሆን የመሬት የመንግስት ነው የሚለው ፖሊሲ (http://asfawdarguemeshal.blogspot.com/2018/03/blog-post_47.html) ነው። መሬት የግል ቢሆን እነዚህ ገበሬዎች በነፃነት በሚያስደስታቸው ዋጋ መሬታቸውን ሽጠው ነበር።