Showing posts with label ንስሀ መግባት. Show all posts
Showing posts with label ንስሀ መግባት. Show all posts

Tuesday, 25 October 2016

የአንድ ዲያስፖራ ኑዛዜ

2009/2/15 ዓ.ም. (2016/10/25)

በአንድ ዲያስፖራ የተጻፈ…

ችግርን ለመፍታት በመጀመሪያ የችግሩ ዋና ምክንያቶች በትክክሉ መገኘት አለባቸው። እነዚህ ምክንያቶች ተገኝተው ሲፈቱ ነው ዋናው ችግር የሚፈታው። የችግሩ ምክንያቶች ወይም ምንጮች በትክክሉ ካልተገኙ ችግሩ መቼም አይፈታም። ይህን ሁላችንም የምናውቀው እውነታን በመጀመርያ የምጠቅሰው እኔ ከሀገሬ ኢትዮጵያ የፖለቲካና መሃበረሰባዊ ችግሮች ምክንያቶች አንዱ ነኝ ብዬ ስለማምን ነው።

ከማልፈልገው መንግስት ለመሸሽ «ኑሮ ለማሸነፍ» ብዬ ያሳደገችኝን ሀገሬ ኢትዮጵያን ትችያት ወጣሁኝ። በምሳሌ ደረጃ ቤቴን ትቼ ወጣሁኝ ማለት ይቻላል፤ በጣም በመቸኮሌም የቤቴን ቁልፍ ለማንም በአደራነት አልተውኩም። ባዶና አለ ጠባቂ የተውኩትን ቤት ሌላ ሰው ገብቶ ማስተዳደር ጀመረ። የቤቱን እቃ በሚፈልገው መልክ አሸጋሸገ፤ የማይፈልገውን እቃ ሸጠ ወይም ጣለ፤ የሚፈልገውን አዲስ እቃ ደግሞ ገዛና አስገባ። እኔ ከሩቅ ከዲያስፖራ ሆኜ እመለከተለሁ አዝናለው እናደዳለው እጮሃለውም። ቤቴን በመጀመሪያው ባልተውኩኝ ኖሮ።

በርካታ የትምህርት ጓደኞቼ እንደኔ ውጭ ሀገር ናቸው። አቃቸዋለሁ፤ ጥሩ ችሎታ ያላቸው ደህና ሰዎች ናቸው። ዩኒቨርሲቲ ለመግባት የበቁ የሀገራችን ምርጥ ተማሪዎች ነበሩ፤ ሀገሪቷን በደምብ ማገልገል የሚችሉ። ግን ዛሬ ሀገራቸውን ለቀው ውጭ ናቸው፤ አሜሪካንን ያገለግላሉ፤ ወይ ስዊድንን ያገለገላሉ። ታድያ እነዚህ ሁሉ ከሀገር ወጥተው ማን ነው የቀረው? እኔ ከሀገራችንን ከሚመሩት የተሻልኩኝ፤ እንደነሱ ክፉ ያልሆንኩኝ፤ ሀገር ወዳድ ነኝ ብዬ የማምን ከሆነ ከሀገሬ መውጣቴ ምን ይባላል። እራሴን አውጥቼ ሀገሬን ለክፉ ናቸው የምላቸው ሰዎች ትችያታለሁ ማለት ነው። ትልቅ ጥፋት አለብን።

አንድ አስተማሪ የቤተ ክርስትያን ተረት ልንገራችሁ… በአንድ ወክት የቤተ ክርስትያን አመራርና ካህናት በከባድ የመንፈሳዊ ፈተና ተይዘው ነበር። በካህናቱ መካከል የእምነት ጉድለት፤ የስነ መግባር ጉድለት፤ የሙስና ብዛት፤ ወዘተ ይታይ ነበር። እጅግ ከባድ ዘመን ነበር። በዚህ ጊዜ አንድ ደህና ኑሮ ያላት ሴት ወይዘሮ ወደ አንድ የታወቁ መንፈሳዊ አባት ለራስዋ ጉዳዮች ምክር ለማግኘትና ንስሀ ለመግባት ትሄዳለች። ከኚህ አባት ጋር ቁጭ ብላ መወያየት ስትጀምር ግን ዋና ጉዳይዋን ትታ ስለ ቤተ ክርስቲያን አመራሮችና ካህናት ችግር ብቻ ታወራለች ታጉረመርማለችም። የምታማክራቸው አባት በትዕግስት አቤቱታዋንና ወሬዋን እስክትጨርስ ድረስ አዳመጧት። ሁሉንም ተችታና ኮንና ጨረሰች። ቀጥሎ እኚህ ታላቅ አባት ልጆች እንዳሏት ጠየቋት። አዎን ሁለት ሴቶችና ሁለት ወንዶች አሉኝ አለች። ከነዚህ ወንድ ልጆችሽ አንዱ ቄስ ቢሆንስ ብለው ጠየቋት። በፍጹም፤ እንዴት ይሆናል ብላ ተቆጣች። እንዴት ለልጀ ገንዘብም እውቀጥም የሌለውን ስራ እመኝለታለሁ አለች! ታድያ የራስሽ ልጆች ካህን እንዲሆኑ ካልፈለግሽ ማን ነሽ በፈቃዳቸው ካህን እንሆናለን ያሉትን የምትኮንኙ ብለው ታላቁ አባት ወቀሷት አስተማሯትም።

ሀገር ችግር ላይ በሆነበት ጊዜ መሸሽ ክህደት ነው ማለት ይቻላል። እኔ ሀገሬን ከድጂያታለሁ ለማለት ወደኋላ አልልም። ጥፋትንና ድክመትን ማመን የመጀመሪያ የችግርን መፍታት እርምጃ ነው። አንድ ሰው ቤተሰብ ውስጥ ችግር ካለ ቤተሰብነቱን ክዶ ሸሽቶ አይሄድም። ልጀ ካስቸገረኝ ልጄ አይደለህም ብዬ አላባርረውም። ካባረርኩት ካድኩት ማለት ነው። ሀገርም እንደዚህ ነው። ሀገር ወዳድ ነኝ ማለትና ሀገር ችግር ላይ ስትወድቅ መሸሽ ተጻራሪ ናቸው!

እውነት ነው፤ አንዳንዴ ሽሽት ግድ ነው። ድንግል ማርያም ልጇን ክርስቶስን ይዛ ሸሽታለች። ግን ሽሽቱ አላማን ለማሳካት ነው እንጂ ለመሸሽ አይደለም። እውነቱን ለመናገር እኔ ግን ወደ ዲያስፖራ የመጣሁት ለመሸሽና የሀገሬን ችግር ለሌሎች ለመተው ነው። ለሀገሬ አላማ ኖሮኝ አይደለም። ኢትዮጵያ ያሉት ታግለውልኝ ደህና መንግስት ሲያመጡ እመለሳለሁ ብዬ ነው። ግን ያም ቢሆን የምመለስ ይመስላችኋልን? ከሃዲ ነኝ፤ እውነት ነው፤ ጥፋቴን አምናለሁ።

ግን ሀገሬን እውዳለሁ፤ ፖለቲካዋ እንደዚህ ወይም እንደዛ መሆን አለበት፤ መሃበረሰቧም እንደዚህ ወይም እንደዛ መምሰል አለበት፤ ህዝቡ መሰልጠን አለበት፤ መንግስትም አሰራሩ እንደዚህ መሆን አለበት ብዬ አስባለሁ እለፈልፋለውም። ሀሳብና ወሬ ብቻ ሀገር ወዳድ የሚያደርግ ይመስለኛል።

ሀገር ወዳድ ሆኜ ግን እንዴት ነው ተግባሬ ያንን የሀገር ፍቅርን ሊያንጸባርቅ የሚችለው? ልጆቼን እንኳን ቋንቋቸውን አላስተማርኳቸውም። ሀገረ ወዳድነት ይህ ነው? ያውም «አላስተማርኳቸውም» የሚለው ቃል በቂ አይገልጸውም፤ አላስተማርኳቸውም ሳይሆን እንዳይማሩ ከልኪያቸዋለሁ። ሌላው ሁሉ መጤ፤ ሂስፓኒኩ፤ ቻይናው፤ ሶማሌው፤ ጣሊያኑ፤ ወዘተ ቋንቋውን ከቤት እየተናገረ ልጆቻቸው በተዘዋዋሪ ቋንቋቸውን ይችላሉ። እኔ ግን ከቤቴ በደምብ የማልችለውን እንግሊዘኛ (ወይም ጀርመን ስዊድኛ ወዘተ) እየተናገርኩኝ ልጆቼ ቋንቋቸውን እንዳይችሉ አረጋለሁ። ባህላቸውን ወጋቸውንም ላይላዩን ብቻ ነው የማስተምራቸው። እውነቱን ለመናገር ልጆቼን ፈረንጅ እንዲሆኑ አድርግያለሁ። ኢትዮጵያዊ ትውልድ በኔ ቆሟል። ታድያ ምን አይነት ሀገር ወዳድ ነኝ?

ወደ ክህደቴ ልመለስና… እርግጥ እራሴን ለማጽናናት ያህል አንዳንድ ግዜ ለክህደቴ ስበቦችና አጉል ምክንያቶች እፈጥራለሁ። አንዱ «ከሀገሬ ብቆይ እታሰር ነበር» ነው። «ህሊናዬን ሽጥቼ ካልሆነ ሀገሬ መስራት አልችልም።» ታድያ ሀገር ቤት ያሉት ወገኖቼ በሙሉ ወይ ታስረዋል ወይ ህሊናቸውን የሸጡ አደርባዮች ሆኖዋል ማለት ነው? ወይ ፍርድ! በአንድ በኩል ገዥው መንግስት የአናሳ ህዝብ ነው እላለሁ። በሌላው በኩል ሁሉንም ይቆጣጠራሉ እላለሁ። እነዚህ የሚጻረሩ ሀሳቦች ናቸው! እውነቱ እንደዚህ ነው፤ አብዛኛው ህዝብ ክፉ ላለማድረግ ከወሰነ ከተባበረ በሀገሪቷ ያለውን ክፋት ይጠፋ ነበር። እራሴን እንደዚህ ማታለል አልችልም፤ ከሀገሬ ሆኜ ለሀገሬ በርካታ ጠቃሚ ነበር አፈራ ነበር።

አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ክሀገሬ የሸሸሁት ኑሮ አሸንፌ ቤተሰቤን ለመርዳት ነው ብዬ እራሴን ማጽናናት እሞክራለሁ። ከቅዠቴ ስነቃ ግን ለዚህም አጉል ምክንያት መልስ አለኝ። ሀገር የሚያድገው ገንዘብ ሲያገኝ ነው ወይም ህዝቡ በእውቀትና ችሎታ ሲበለጽግ ነው? ጃፓን ምንም ተፈጥሮ ሃብት ሳይኖራት ህዝቧን በእውቀትና ችሎታ እንዲበለጽግ አድርጋ ነው ያደገችው። ሳውዲ ደግሞ በተፈጥሮ ሃብት ምክንያት በገንዘብ ሃብታም ሆና ግን በህዝብ ደሃ ናት። ገንዘብ ለቤተሰቤ መላክ ምን ያህል ሀገሪቷንም እነሱንም ይጠቅማል? እርገጥ አንዳንድ ቤተሰብ ገንዘቡን ለዘላቂ ነገር ለትምህርት ለንግድ ወዘተ ይጠቅምበታል። በርካታው ደግሞ ለለት ኑሮ ይጠቀምበታል። ምንም ቢሆን ገንዘቤ እኔን አይተካም ሊተካም አይችልም ይተካል የሚለው አስተሳሰብም ጎጂ ነው። ማንም በድጎማ አይበለጽግም። ይህ ከሀገር ለመሸሽ ምክንያቴ ሊሆነ አይገባም።

አዎን ለክህደቴ ምንም ስበብ የለም። አምኛለሁ። ንስሀ ገባለሁም። እግዚአብሔር ሀገር ቤት እንድመለስና ከወገኖቼ አብሬ ደስታቸውንም ችግራቸውንም እንድካፈል ብርታቱ ይስጠኝ። እራሴንም ማታለል እንዳቆም ይርዳኝ። አሜን።

Thursday, 13 October 2016

ኦርቶዶክስ ክርስትናና ፖለቲካ

2009/2/3 .. (2016/10/13)

«እግዚአብሔር በሁልም ስፍራ አለ በሁሉም ነገርም ይገኛል» (God is everywhere present and in all things) አንድ የኦርቶዶክስ ሃይማኖት መሰረታዊ እምነት ነው። ይህ አባባል እግዚአብሔር የፈተራት ዓለም በሁለት በ«አለማዊ» እና በ«ሃይማኖታዊ» ስፍሮች እንዳልተከፈለች ይገልጻል። ወደ ቤተሰባችን፤ ስራችን፤ ንግዳችን፤ ዘፈናችን፤ መዝኒያናችን፤ ስፖርታችን፤ ትምህርትቤታችን፤ እርሻችን፤ ፖለቲካችንም ስንሄድ እግዚአብሔርንና እምነታችንን ትትን መሄድ አይቻላም! እግዚአብሔር በነዚ ስፍሮች ሁሉ አለና። ግድብ የለውም። ስለዚህ ፖለቲካና ክርስትና የተለያዩና የማይገናኙ ናቸው ማለት አይቻልም።

ስለዚህ ክርስትያኖች በፖለቲካ ልንሳተፍ እንችላለን። የማህበራዊ ኑሮ ፖለቲካን ስለሚይካትት ብንፈልግም ባንፈልጉም በተወሰነ ደረጃ ቢሆንም ፖለቲካ ውስጥ ተሳትፈናል። ሁለት ምሳሌዎች ልስጣችሁ፤ ቀረጥ መክፈል ማለት ገንዘብ ለመንግስት መስጠት ነው። የዚህን ገንዘብን አጥቃቀም የሚወስኑት ፖለቲከኞች ናቸው። በገንዘባችን ለሚያደርጉት ግን ተጠሪ ነን ግንዘባችን ነውና። በቀበሌ ወይም በማንኛውም የምንግስት መሥሪያቤት ስንገለገል ፖለቲከኞች የዘረጉትን የአስተዳድራዊ ዘዴ መቀበል ማለት ነው። ብለት ኑሮአችን ፖለቲካ አይጠፋም። ፖለቲካ አንዱ የህይወታችን ዘርፍ ነው።

ታድያ የአንድ ክርስትያን ፖለቲካዊ ኑሮ እንዴት መሆን አለበት? ይህን ለመመለስ በመጀመርያ አንዳንድ መሰረታዊ የሆኑ የክርስትና እምነቶች እንመልከት። ከላይ እግዚአብሔር ከሁሉም አለ የሚለውን አባባል ጠቅሽያለሁ። ቀጥሎ «በዐይነህ ውስጥ ያለውን ግንድ ሳትመለከት፤ በወንድምህ ዐይን ያለውን ጉድፍ ለምን ታያለህ» የሚለውን እስቲ እንመልከት። ባለንጀራችሁን እንደራሳችሁ ውደዱ ይበልጥ ደግሞ እኔ እንደምወዳችሁ ያህል ውደዱት ብሎ ክርስቶስ አዞናል። ይህን አባባልንም እንመልከት።

ሌላ አባባል፤ ቅዱስ ባስሊዮስ እንደዚህ አሉ፤ « የባለንጀራህ ሀጥያት ብቻ ከሆነ የሚታይህ ያንን ብቻ ከማየት ይልቅ በፊትም አሁንም የሚያደርገውን ጥሩ ነገሮች እንዳሉ ተገንዘብ። መፍረድን ትተህ ይህን ለማድረግ ስትሞክር ጭራሽ እርሱ ካንተ የተሻለ እንደሆነ ትረዳለህ።» ይህ አባባል ሁለት መሰረታዊ እምነቶታችንን ይገልጻል፤ እግዚአብሔር የፈጠረው ሁሉም ሰው ትንሽም ቢሆን ጥሩነት ስላለው በሌላ ሰው መፍረድ ተገቢ አይደለም።

ክርስቶስ «እኔ በልቤ የዋህና ትሑት ነኝ» ብሎ እኛም እንደሱ እንድንሆን አዞናል። ትሕትና የቀደመውና ዋናው ሀጥያታችን «ትዕቢት» ተቃራኒና መድሀኒት ስለሆነ የሃይማኖት አባቶች የምያተኩሩበት መልካ መግባር ነው። አባ ይስሐቅ ዘሶሪያ እንዲህ ብለዋል፤ «ጨው ለምግብ እንደሚሆን ትህትና ለሁሉ መልካ መግባር ይሆናል።»

የክርስትያን ፖለቲካ ኑሮ ከላይ በጠቀስኳቸው አባባሎች የሚያስተምሩን መልካ መግባሮች ነው መካተትና መመራት አለበት፤ 1) እግዚአብሔር ከሁሉም አለ፤ 2) የሌላውን ሀጥያት ከማየት ፋንታ የራሳችንን ሀጥያት አይተን ንስሃ እንጋባ እናርማቸውም፤ 3) ባለንጀራችንን ክርስቶስ እንደሚወደን እንውደድ፤ 4) በሰው አንፍረድ፤ ትሑት እንሁን ከትዕቢትና ትምክህት እንራቅ።

በዛሬው የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሁኔታ አንድ ክርስትያን እነዚህን እምነቶች ተከትሎ ምን ሊያደርግ ይገባዋል? አትፍረዱ፤ ትሑት ሁኑ፤ የራሳችሁን ሀጥያት ተመልከቱ፤ አብዛኞቻችን በፖለቲካ ዙርያ የሌላው ሰው፤ ወገን፤ ጎሳ፤ ፓርቲ ጥፋት ብቻ ነው የሚታየን። የኢህአዴግ፤ የህወሓት፤ የኦነግ፤ የሻእቢያ፤ የኢዴፓ፤ የደርግ፤ የኢሀፓ፤ የኃይለ ስላሴ፤ የዘንድሮ ተቃዋሚ፤ የዲያስፖራ፤ ወዘተ። አንድ ክርስትያን እራሱን ሳይመረምር የራሱን ጥፋቶች ተረድቶ ንስሀ ሳይገባ የማንንም፤ የኢህአዴግንም፤ ጥፋትና ስህተትን ላይ ማተኮር የለበትም።

ግን ምን የፖለቲካ ሀጥያት አለብኝ ብለን የምንጠይቅ ብዙ ነን። ከበርካታ ሰዎች ከገደለው ካሰቃየው ኢህአዴግ፤ ደርግ፤ ወዘተ ምኔ ሊወዳደር ይችላል። እስቲ ይህን ጥያቄ በምሳሌዎች ለመመለስ ልሞክር።

ጎረቤቴ ለ«ኢንቬስተር» ተብሎ መሬቱን ሲነጠቅ ረዳሁትን? ትንሽም ነገር አደረግኩለት?የምፍረአቸውን የሰፈሬን ዱሪዬዎችን ለመርዳትና ጥሩ መስመር ለማስያዝ ያረግኩት ነገር አለ? ወይም የራሳቸው ጉዳይ ብዬ ዞር ብዬም አላያቸውም። ችግር እስኪያመጡ። በፖለቲካ ዙሪያ «ኦሮሞ» ሲባል በልቤ ፍርሃትና ጥርጣሬ አይሰፍንም? ነው በንጹ ልቦና ጉዳዩን እመለከታለሁ? «እነሱ ከሚገዙን ወያኔ ይግዛን» ብዬ አስቤ አላቅምን? ግን አንድ ቀንም «ከነሱ» ጋር ቁጭ ብዬ ተወያይቼ አላቅም። ከጎረቤቶቼ ጋር ድሮ ተጣልቼ አሁንም አልተቀየምኳቸውም? በዚህ ጥላቻ ምክነያት እንኳን ለፖለቲካ ለውጥ ለምንም ነገር ከነሱ ጋር መተባበር አልችልም አይደ? ከባልደረባዬ ምሁር በትንሽ አስተሳሰብ ልዩነት ምክነያት ጠላቶች አልሆንም? እንኳን አብረን ለመስራት መተያየትም አንፈልግም አይደለምን? ስራተኞቼን እንደ ሰው ቆጥሬ አላውቅም እሁድ ቤተክርስትያን ለመሄድም እድል አልሰጣቸውም! ዘላለማዊ ቂም አልፈጠርኩባቸውም? ኢህአዴግ ይህንን ቂም ተጠቅሞ እነዚህን ሰራተኞቼን እኔን ለመግዳት ወይም የኔን አቋም ለማዳከም መጠቀም አይችልምን? የማይገባኝ ጥቅም ለማግኘት ጉቦ ሰጥችሄ አላውቅምን? ከስራ ቦታዬ በኔ ሃሳቦች የማይስማሙትን አልኮንንም? ሰራተኞች ሲሳሳቱ ችግራቸውን ከመረዳት ፋንታ አልፈርድባቸውም? ልጄ ውትድርና ገብቶ የማያምንበትን ክፉ ድርጊቶች እንዲያደርግ ይታዘዛል ያደርጋል። ልጄ ነው የሚጦረኝ እና እንደዚህ አይነቱን ጉዳይ ለሱ በማንሳት ላበሳጨው አልፈልግም እላለሁ። ታድያ እንደ የኢግዚአብሔር ልጅ ሃላፊነቴን አልካድኩምን?

እራሳችንን በደምብ ከመረመርን እነዚህ አይነቶቹ ሀጥያቶች እንዴት ከኛ ወደ ህብረተሰቡ፤ ከህብረተሰብ ወደ መንግስታችን እንደሚተላለፍ እንደሚያንጸባርቅ ልንገነዘብ እንችላለን። ክርስትያኖች የሁላችንም ኃጢአት የተገናኘው እንደሆነ እናምናለን። ለሌሎችንም ኃጢአት ሃላፊነት እንዳለብን እናምናለን። አባቶች ይህን ተጠንቅቀው ነው የሚያስተምሩን። ከላይ እንደምሳሌ የጠቀስኳቸው ኃጢአቶች እንዴት አሁን ካለው የምንግስት ስረዓት ባህሪ ጋር እንደሚገናኙ ግልጽ እንደሆነ ተስፋ አለኝ።

ክርስትያን በመሆኔ መጠን ለነዚህ ኃጢአቶች ንስሃ ገብቼ እየወደኩኝ እየተነሳሁኝ እያስተካከልኩኝ መኖር ነው የሚጥበቅብኝ። የፖለቲካ ኑሮዬም እንደዚህ ነው መሆን ያለበት። የምደግፈው የፖለቲካ አቋም፤ አመለካከት፤ ፓርቲ፤ ርዕዮተ ዓለም፤ ወዘተ ከክርስትያንነቴ ስር ነው መሆን ያለባቸው። እንደ ክርስትያን እስከኖርኩኝ ድረስ ፖለቲካው እራሱን ያስተካክላል።

ሆኖም ማንም ሰው አጥፊና ክፉ ነበር የሚያደርግ መንግስት ወይም ተቋምን መታገል የለበትም ማለት አይቻልም። እያንዳንዱ የራሱን ልብ ያውቃልና ልታገል ቢል በሱ ልፈርድ አልችልም፤ ግን ትግሉ ውጤታማ እንዲሆን በመጀመርያ የራሱን ልብና ገበና መፈተሽ አለበት። ሳይፈትሽ ሌላውን ለማስወገድ ብቻ ከታገለ ትግሉን አያሸንፍም። ወይም ይባስ ያሸንፍና ከታገለው የባሰ ሆኖ ይገኛል። ይህን እውነታ ሃይማኖታችን ያስተምረናል። እውነታም ስለሆነ በታሪክ በትደጋጋሚ ሲከሰት አይተናል! ስለዚህ በመጀመርያ ክርስትያን እንሁን፤ ሙሉ ክርስትያን እንሁን። ከሆንን ሌላው እራሱን ያስተካክላል።