Showing posts with label ቅራኔን መፍታት. Show all posts
Showing posts with label ቅራኔን መፍታት. Show all posts

Monday, 26 March 2018

ቀደም ተከተል

በ«ተቃዋሚዎች» መካከል ስለ አማራ ማንነት አይነቱ ክርር ያለ ጭቅጭቅ ሲነሳ «መጀመሪያ የሁላችንም ጠላት የሆነውን ህወሓትን ከስልጣን መፈንቀል ላይ ተባብረን እናተኩር ፤ ከዛ በኋላ ስለ ሌሎች ጉዳዮች መነጋገር ይቻላል» ይባላል።  ለ27 ዓመት በተደጋጋሚ የሰማነው አሁንም የምንሰማው አባባል ነው።

አዎ ግባችን ህወሓትን ከስልጣን ማውረድ ከሆነ ከማንም ጋር ተባብረን ሌሎች ጉዳዮችንን በሙሉ ዘርግፈን ግባችን ላይ ማተኮር ነው ያለብን። ነገር ግን ይህን ማድረግ አልተቻለም። ለ27 ረዥም ዓመታት አልተቻለም! ተስማምተን ለአላማችን ብለን ተማምነንና ተባብረን አንድ ሆነን መስራት አልቻልንም።

ለምን? ለምን ግባችንን ለመምታት ግድ የሆነውን አንድነት መመስረት አልቻልንም? ያልቻልንበት ምክንያት እኛ «ተቃዋሚዎች» በርካታ የማንስማማባቸው የአገራችን የፖለቲካ ጉዳዮች ስላሉ ነው። በነዚህ ጉዳዮች ስለማንስማማ ተማምነን አብረን መስራት አልቻልንም።

ስለዚህ ይህን ችግር ለመፍታት ቁጭ ብለን መወያየት፣ ጉዳዮቹን ማብሰልሰል፣ መከራከር፤ መስማማት አለብን። ይህን የውይይት ስራችንን እስካሁን በጭራሽ አልሰራንም ማለት ይቻላል። እስካሁን ጊዜአችንን አቅማችንን 95% በኢህአዴግ ማልቀስ 5% በራሳችንን ማጎልበት ነው ያዋልነው! አንድ ላይ መስራት የምንችለው በኢትዮጵያ ያለንን ራዕይ ዙርያ በቂ ውይይታዊ ስራ ካደረግን በኋላ ነው።

ስለዚህ ቀደም ተከተሉ እንደዚህ መሆን አለበት፤ 1ኛ) እርስ በርስ ያለንን ጉዳዮች ተወያይተን ጨምቀን ወደ የምንተመመንበት  የምንስማማበት መድረስ። ይህ ስራ ዓመታት ሊፈጅ ይችላል። 2ኛ) ከዚያ በኋላ የመሰረትነውን መተማመን፣ ስምምነትና አንድነት ተጠቅመን ህወሓትን መፎካከር።

ለማጠቃለል ትኩረታችን ህውሓትን ከስልጣን ማውረድ ከሆነ በመጀመሪያ በመካከላችን አንድነት መፍጠር አለብን። አንድነት ለመፍጠር እርስ በርስ በሁሉም መልኩ እንዳንተማመን፤ እንዳንስማማ እና አንድነት እንዳንፈጥር የሚያደርጉንን ጉዳዮች በደንብ መወያየት አለብን። ከዚያም የገነባነውን አንድነት በመጠቀም ህወሓትን ለማሸነፍ እንችላለን።

ስለዚህ ስለ አማራ ማንነት፤ የጎሳ አስተዳደር፤ የትግል ስልት፤ እና ሌሎች በርካታ የማያስማሙን ወይም ማሻሻል የሚኖሩብን ጉዳዮችን መወያየት ህወሓትን ለማሸነፍ የግድ አስፈላጊ ብቻ ሳይሆን ቅድመ ሁኔታ ነው።

እዚህ ላይ ለመጨመር ያህል በኔ እይታ ህወሓትን ከስልጣን ማስወገድ አንደኛ ላማችን ሊሆን አይገባም። አላማችን ሰላም፤ ፍትሕ፤ ፍቅር፤ መልካም አስተዳደር ማምጣት ነው። ሀውሓትንም ማስወገድ የምንፈልገው የነዚህ ተቃራኒ ስለሆነ ነው። ግን ህወሓትን ከስልጣን አባረን የሱን ቢጤ የሆነ መንግስት አንፈልግም። ከላይ የዘረዘርኩት አካሄድ ግን እንደዚህ እንዳይሆን የሚከላከል ነው! ስለ አገራችን ያለንን ራዕይ ላይ ቀድሞ በደምብ ተወያይተን ከተስማማን ከተማመንን አምባገነን ከመካከላችን አምባገነን ሊፈጠር አይችልም አምባገነን የአለመግባባት የአለመስማማት ውጤት ስለሆነ። ስለዚህ ካሁን ወድያ ይህ ዋና ስራችን ላይ እናቶኩር።

Wednesday, 21 March 2018

የፖለቲካ ውይይት ስልት፤ «ከጠንካራ ወገኑ ተሟገት»

የኛ የ«ተቃዋሚዎች» የፖለቲካ ችሎታችን፤ ብስለታችን፤ አቅማችን ምን ያህል ደካማ መሆኑን የቅንጅት ታሪክ አጉልቶ ካሳየን 12 ዓመት አልፎታል። አሁንም ደካማ ነን። ብዙኃኑ ንሯል ልሂቃኑ ኋላ ቀርቷል። ምክንያቱ ፖለቲካችንን ለማጠናከር የሚያስፈልጉን ባህሪዎች እንደ መወያየት፤ መተባበር፤ መተማመን፤ መስማማት፤ አብሮ መስራት፤ ቅራኔን መፍታት ወዘተ አሁንም ይጎሉናል። ይህ ጉድለት ነው ለሰላምና ፍትህ ትግላችን ዋና እንቅፋት የሆነው።

ዛሬ በነዚህ ዙርያ አንድ ነጥብ ላይ ማተኮር እወዳለው። ውይይት ሙግት ክርክር የፖለቲካም የማንኛውም የህብረት ስራም መሰረት ነው። የውይይት አንዱ አላማ ሀሳቦችን መፈተንና ማጣራት ነው። የትኛው ትክክል እንደሆነ፤ የትኛው የተሳሳተ እንደሆነ፤ የትኛው ጠቃሚ እንደሆነ፤ የትኛው ተጨማሪ መጠናት እንዳለበት፤ ወዘተ።

ስንወያይ የራሳችን ሀሳብ መናገር ብቻ ከሆነ የምናደርገው እና የሌሎችን ሀሳብ በትክክል የማናዳምጥ ከሆነ ውይይቱ ግቡን እንደማይመታ ግልጽ ነው። እያንዳንዳችን የራሳችን ሀሳብ ብቻ ነው ተቀባይነት የሚገባው ከሆነ ሀሳባችን ሊገመገምና ሊጣራ አይችልም ልንስማማም አንችልም። ሀሳቦቻችን ስላልተገመገሙ ደካማ ይሆናሉ ስላልተስማማን አብረን ደካማ ሆነን እንቀራለን። ስለዚህ ተጠንቅቀን የሌሎችን ሀሳብ ብቻ ሳይሆን አመለካከታቸውንም መረዳት አለብን።

እንደዚህ ለማድረግ የተሟጋቾቻችን ወይም የተቃራኒዎቻችን ሀሳቦች «ጠንካራ ወገንን» መመልከት አለብን። የውይይታችን ዓላማ ማሸነፍ ሳይሆን መገምገምና ማጣራት ስለሆነ። አልፎ ተርፎ የተቃራኒአችን ወይም ተሟጋችን አመለካከትና ሀሳብ ልክ እንደሱ አውቀን መከራከር መቻል አለብን። ከጥንት ዘመን እንደሚባለው ተቃራኒውን ወይም ጠላቱን ያላወቀ ይሸነፋል። ማወቅ ማለት ላይ ላዩን አባባሉን ድርጊቱን ማወቅ ሳይሆን ልከንደሱ ማሰብ ምቻል። ይህን የቻለ ሰው የተቃራኒውን ሀሳብና አቋም ከሱ በተሻለ መንገድ ማሳመን ይችላል! ተቃራኒን በደምብ ማወቅ ማለት ይህ ነው። ከዚህ ብኋላ የተቃራኒውን ሀሳብ በትክክል ሊሟገት ሊያሸንፍ ወይም ሊጠቀምበት ይችላል።

ስለዚህ ጉዳይ ከራሴ አንድ ምሳሌ ልስጣችሁ። ለረዥም ዓመታት ከ«ጎሰኞች» ጋር ስሟገት የራሴ አቋም እውነት ነው ስነ መግባርና ፍትህ የተሞላ ብቸኛ ሀሳብ ነው ብዬ እነሱን አላዳምጥም ነበር። «ጎሰኝነት ዘረኝነት ነው» እያልኩኝ ከዚህ ሳላልፍ እንደመድም ነበር። ለኔ የሙግቴ አላማ እነሱን የራሴን ሀሳብ ማሳመን ብቻ ነበር። አልሰራም።

አንድ ወቅት ማዳመጥ ጀመኩኝ። እስቲ በነሱ ቦታ ሆኜ ላስበው አልኩኝ። እንደነሱ ሆኜ ከራሴ ጋር መሟገት ጀመርኩኝ። እንደዚህ ሳረግ የነሱ አስተሳሰብ አመጣጥና ሀሳብ እይገባኝ ሄደ። የነሱን አቋም ይዤ መከራከር ቻልኩኝ። ይህ የራሴን አቋም እንዳጠራው ጠቀመኝ። እነሱም እንደማዳምጣቸው ሲረዱ እኔንም ማዳመጥ ጀመሩ። መተማመን ጀመርን እንደ ጥላት መተያየት አቆምን። ብዚህ ምክንያት ጎሰኝነትን አሁን ከድሮ ይልቅ በደምብ እረዳለሁ ማለት እችላለሁ። የጎሰኝነትንም አጉል ወገን እንዴት ማስወገድና ማጥፋት እንደሚቻል ይበልጥ የገባኝ ይመስለኛል።

በተዘዋዋሪ ይህን «ማዳመጥ» ወይም ለሰው መቆርቆርና ራስን በሌላው ቦታ ማድረግ የደረስኩበት ከክርስትና ተልእኮአችን ነው። «አትፍረዱ» «ማሩ» «ራሩ» መሰረታዊ የክርስትና ትምሕርቶች ናቸው። አንዱ ታላቅ ቅዱስ ዮሐንስ «ዘመሰላል» እንደዚህ ብለዋል፤
«አስተዋይ ሰው ወይን ሲበላ የበሰሱትን ይበላል ያልበሰሉትን የሚጎመዝዙትን ይተዋል። እንዲሁም አስተዋይ አዕምሮ በማንድ ሰው የሚያየው (ትንሽም) ጥሩነት ተጠንቅቆ ይመዘግባል። አዕምሮ ቢስ የሆነ ድክመትና መጥፎ ባህሪያትን ይፈልግበታል… ሰው ኃጢአት ሲፈጽም በአይንህም ብታይ አትፍረድ፤ አይኖቻችንም ሊታለሉ ይችላሉና።»
ይህን መንገድ የሚከተል የሌሎችን አስተያየትና አመለካከትን አክብሮ በነሱ ቦቶ እራሱን አስቀምጦ ሁኔታውን ይገመግማል። «አትፍረዱ» «ማሩ» «ራሩ» ማለት እራስን በሌላው ቦታ አድርጎ ማሰብ መቻል ነው!

Tuesday, 20 February 2018

ታሪክን አንድገም፤ ሀገርን እንገንባ

አሳፋሪና አገር አፍራሽ ታሪካችንን እንዳንደግም ነው ይህን ጽሁፍ የምጽፈው። ታሪክ እንደመዘገበው ከኢህአዴግ ውጭ ያለነው ምሁራን፤ ፖለቲከኞችና ብዙሃን በፖለቲካ ረገድ ቁም ነገር ለማድረግ እድል ባጋጠመን ቁጥር እልዳችንን አበላሽተናል። በተደጋጋሚ ጊዜ ለአገራችን የፖለቲካ መስተካከል ከኢህአዴግም ይበልጥ እንቅፋት ሆነን ተገኝተናል።  ይህን ደፍሬ መናገር የምችል ይመስለኛል።

አንዱ የድክመታችን ምክንያት ተልዕኮአችንን አለማወቃችን ወይም መርሳታችን ነው። ተልዕኮአችን የአገር ፖለቲካ ግንባታ ነው እንጂ የፖለቲካ ውድድር አይደለም። የአገር ፖለቲካ ስርዓት ግንባታ ሲባል ሁላችንም ስለ ህገ መንግስትን ማርቀቅ ነው የምናስበው። ግን ከዚህ ህገ መንግስት ማርቀቅ ስራ በፊት  የልብ ለልብ መተዋወቅ፤ በተወሰነ ደረጃ መተማመን፤ መግባባትና መስማማት ያስፈልጋል። እነዚህ ለአገር ግንባታ የፖለቲካ ድርድር ቀድሞ ሁኔታዎች ናቸውና። አለነዚህ ማንኛውም በወረቀት ያለ ህግ፤ ምንም አይነት ወርቅ የሆነ ህግ ቢሆነም፤ በስራ ሊተገበር አይችልም

ቀጥሎ በነዚህ ተመስርቶ ህገ መንግስትና ሌሎች የርዓይና የህግ ሰነዶች ይደነገጋሉ። ቅራኔ ወይም አለመግባባት ካለ በህግ መሰረት ይፈታል ህጉ ደግሞ በቂ ካልሆነ ያለው መተማንና ስምምነት ለፍትህ ይረዳል። የአገር የፖለቲካ ግንባታ ሂደት እንደዚህ ነው መሆን ያለበት።

የፖለቲካ ውድድር ደግሞ የሚጀምረው የፖለቲካ ስረዓቱ ከተዋቀረ በኋላ የሚመጣው የፖለቲከኞችና ሌሎች ለመሪነት እርስ በርስ በህጉ መሰረት መወዳደር ነው። በምእራብ «ዴሞክራሲዎች» እንደዚህ አይነቱ ውድድር በርካታ ክርክር፤ ክስ፤ ዘለፋም ወዘተ ያካትታል። የህጉን ገደብ ዳር ዳር እየነኩ ግን ሳያልፉ እነዚህን አይንቶች ባህሪዎችን ያንጸባርቃሉ። ይህ ስልጣን ለመያዝ ሊበጃቸው ይችላል ግን ምንም አይገነባም። እርግጥ መተማመንንና ውይይትን ይጎዳል ግን ከምርጫው በኋላ የደረሰውን ጉዳት ይጠግኑና የአገር ማስተዳደር ስረአቸውን ይጀምራሉ። ይህ ነው በተለምደው የምናውቀው የፖለቲካ ውድድር።

የፖለቲካ ውድድር ደግሞ የፖለቲካ ስርዓቱ ከተዋቀረ በኋላ የሚከተለው የፖለቲከኞችና ሌሎች ለመሪነት እርስ በርስ በህጉ መሰረት መወዳደር ነው። በምእራብ «ዴሞክራሲዎች» እንደዚህ አይነቱ ውድድር በርካታ ክርክር፤ ክስ፤ ዘለፋ ወዘተ ያካትታል። የህጉን ገደብ ዳር ዳር እየነኩ ግን ሳያልፉ እነዚህን አይንቶች ባህሪዎችን እያንጸባርቁ ይወዳደራሉ። ይህ ስልጣን ለመያዝ ሊበጃቸው ይችል ይሆናል ግን አገርን አይገነባም ይጎዳልም። ሰልዚህም ነው ውድድሩ ምርጫው ካለፈ አሸናፊዎቹ ውድድሩ ያደረሰውን ንዴት፤ ቂምና ጉዳት ይጠግን ዘንድ ትሸናፊዎቹንም መላው የአገሪቷን ህዝብ አንድ የሚያረግ እርቃዊ ንግግርና ተግባር የሚአደርጉት። ይህ ነው በተለምዶ የምናውቀው የፖለቲካ ውድድር።

ስለዚህ አገርን መገንባትና የፖለቲካ ውድድር የተለያዩ ባህሪያት፤ ተግባራትና ልምድ ያስፈልጋቸዋል። የአገር ግንባታ ሂደት እንደ መተማመን፤ ስምምነት፤ አንድነት፤ መግባባት፤ ህብረት፤ ቅራኔን መፍታት፤ ውይይት ወዘተ አይነቱ ባህሪያትና ልምዶች ያስፈልጉታል። የፖለቲካ ውድድር ግን ክርክር፤ ውድድር፤ ፉክክር፤ መካሰስ፤ ህግና ስረዓትን ዳር ዳሩን መጣስ፤ ወዘተ አይነቱን ልምዶች ያካትታል። በአገር ግንባታ ሂደት መካከል እነዚህን የፖለቲካ ውድድር ባህሪያትና ልምዶች ይዘን ከገባን አገርን መገንባት ሳይሆን ማፍረ ነው የምናደርገው።

ለዚህ ደግሞ በርካታ ታሪካዊ ምሳሌዎች አሉን። እስቲ ወደ 15 ዓመታት ወደ ኋላ ተመልሰን የ«ተቃዋሚ» ምሁራን፤ ጋዜጠኛና ፖለቲከኞች እያደረጉ፤ እየተናገሩ፤ እየጻፉ ምን እንደነበር እናስታውስ። ስራቸውን ባጭሩ ለመግለጽ «እርስ በርስ መበላላት» ማለት ይቻላል! ተቃዋሚዎች ኢህአዴግ ከሚተቹት ይበልጥ እርስ በርስ ነበር የሚፋጁት። ጋዜጣ ላይ ቁም ነገር ሳይሆን ስድብና የመንደር ወሬ ነበር የሰፈነው። ከሞላ ጎደል ስራቸው 90% አፍራሽ 10% ገምቢ ነበር። ስለዚህም ነው ተቃዋሚው ጎራ ምርጫ '97 በግንቦት ሆኖ እሰከ የካቲት አካባቢ የትብብር መዋቅሮች ያላደራጀው! ለዚህም ነው ከምርጫው በኋላ ተቃዋሚዎች በቀላሉ የተበታተኑት። በበፊቱ ዓመታት እዱሉ እያለን ቅስ ብለን በትብብር ጉዳይ ተወያይቶ ትብብርን ከመፈጸምና ጠንካራ መሰረት የሆነ መዋቅርን ከመገንበት እንደ ምርጫ ተዋዳዳሪዎች እየተሰዳደብን ዋልን። ችግር ሲመጣ ለመቋቋም አቅሙ አልነበረንም። እርስ በርስ ተፋጅተን አለቅን። የግንባታ ስራ ያልተሰራባቸው ቅንጅትና ህብረት በቀላሉ ፈረሱ። የፖለቲካ መዋቅር ግንባታንና የፖለቲካ ውድድርን መለየት ያልቻሉትም ከፖለቲካ ወጡ። የህዝብም ትዝብት አደረባቸው።

በርካታዎቻችን በምዕራብ የሚዲያ ዜና፤ ትምህርትና ፕሮፓጋንዳ ስላደግን የነዚህ አገራት ፖለቲካ ስናይ ፖለቲካ እንደዛ መሆን እንዳለበት ይመስለናል። የናየው ደግሞ የፖለቲካ ውድድራቸውን ነው። ክርክሩን፤ ዘለፋውን፤ ስድቡን፤ ሴራውን ወዘተ። እኛም እንደነሱ ማድረግ እንወዳለን መሰለኝ። ግን ኢትዮጵያ ያለችበት ቦት፤ ለረዥም ዓመታት ያለችበት ቦታ፤ ገና የአገር ፖለቲካ ግንባታ ላይ ናት። ብዙሃኑም ልሂቃኑም የፖለቲካ መደቦቻችን እስካሁን በእምነት የተመሰረተ አገራቷን ምን መምሰል አለበት የሚል ሰፊ ስምምነት ላይ አልደረስንም። አሁንም ያለው ዋና ስራችን የህ ነው። አዎን ህገ መንግስት አለን ግን ሰፊው ርአይና ስምምነት የለንም። ነገ ኢህአዴግ ከስልጣን ቢወርድም ይህ ስምምነቱ ስለሌለ ሁከትና አብዮት ይከተላል።

በዚህ ምክንያት ሁላችንም፤ ምሁራን፤ ብዙሃን፤ ፖለቲከኛ፤ የመንግስት ሰራተኛ፤ ወዘተ ትኩረታችን ወደ አገር ግንባታ መቀየር አለበት። ይህ ማለት ከታች የተጠቀሱትን ለአገር ግንባታ አስፈላጊ የሆኑትን ብሃሪያት፤ ተግባሮችና ልምዶች ከራሳችን ጋር መዋሃድና በዚህ አስተሳሰብ ወደ ፊት መራመድ።

ስምምነት፤ አንድነት፤ መግባባት፤ ህብረት፤ መተማመን፤ በስነ ስረዓት መነጋገር፤ ውይይት፤ ቅራኔን መፍታት።

የሚቀጥለው ጊዜ አንድ ሰውን ወይም ቡድንን መዝለፍ ወይም መስደብ ካሰኘን ቆመን እናስብ። የፖለቲካ ውድድር ውስጥ አይደለንም። እንደዚህ አይነቱ ባህሪያት ታሪካችን እንደሚያረጋግጠው ሁላችንንም ጠርጎ ገደል ውስጥ ያስገባል አገራችንን ያፈርሳል። በሰላም እየተከባበርን እየተማመንን ነው መወያየት ያለብን። ይህ የሁላችንንም ጥቅም ያስከብራልና። ይህንን ብቻ ተግባራዊ ካደረግን አለ ምንም ጥርጣሬ ታላቅ አገር እንገነባለን ጠላት የምንላቸውም ምንም ሊጎዱንም አይችሉም።