Wednesday 21 September 2016

«ወያኔ» እኛው የወለድነው ልጅ እንደሆነ አንካድ!

2009/1/11 .. (2016/9/21)

የጽሁፎቼ ሁሉ ዋና አላማ ለኢትዮጵያ ችግሮች ከኢትዮጵያዊ ብሄርተኝነት አኳያ መፍትሄ ለማጋኘት ነው። ስሜት ለማተንፈስ፤ ለመሳደብ፤ በባዶ ቤት ለመዛት ወይም ለመለመን አይደለም። መፍትሄ መፍትሄ መፍትሄ ነው አላማዬ። የአንድ ችግር መፍትሄ ለማግኘት ደግሞ ምንጩን ማወቅ ግድ ነው። ምንጩን ካወቅን መፍትሄው ይመጣል።

«ወያኔ» እኛው ሀገር ወዳድ ነን የምንለው ኢትዮጵያዊ ብሄርተኞች የወለድነው ልጅ እንደሆነ ከገባን ምን ስህተሀቶች አድርገን ልጃችን እንደዚህ እንደሆነም እነዚህንም ስህተቶች እንዴት በመአረም የኢትዮጵያ ጠክላላ የፖለቲካና መሐበራዊ ችግሮችን እንዴት መፍታት እንደምንችል እንረዳለን።

የኢትዮጵያ ዋና የፖለቲካ ችግርን በቀላሉ ማስቀመጥ ይቻላል፤ ያለው መንግስት በቂ ኢትዮጵያዊያንን አይወክልምም መላው ህብረተሰቡም በአንድ ሀገራዊ ውል (የሀገሪቷ ፖለቲካ ምን መምሰል እንዳለበት – social contract) አልተስማማምም።

ሁላችንም እንደምናውቀው ኢህአዴግ በህወሃት ትጽዕኖ የሚገዛ ድርጅት ነው። ርዓዮት ዓለሙም በጎሳ ብሄርተኝነት የተመሰረተ ነው። ከዚህ «ስዕል» ማን ነው የሚጎለው? ወይም ከሀገራችን ፖለቲካ የትኛው በርካታ ህዝብ የሚወክል ጎራ ነው የጠፋው? ኢትዮጵያዊ ብሄርተኛ ነኝ የሚለው ጎራ ነው የጠፋው። እንዴት እንደዚህ አይነት አገዛዝ በኢትዮጵያ ሊሰፍን ቻለ?! ከሌሎች ጽሁፎች እንደጠቀስኩት የኢትዮጵያ ብሄርተኞች በኃይለ ስላሴም በደርግም ዘመን የራስ ማጥፋት ዘመቻ ስላካሄዱ ነው። የኃይለ ስላሴ መንግስት እንደ መሬት ለአራሹ አይነት አስፈላጊ ለውጦች ባለማድረግና በኢትዮጵያዊነት ፋንታ ዘመናዊነትን እከተላለሁ ብሎ ሀገር አፍራሽ የሆነ የተማሪ ንቅናቄ የሚባል ትውለድ አፈራ። ደርግን ሻእብያን ህወሃያትን ኦነግን ኢህአፓ ወዘተ አፈራ። 1983 ሲደርስ እራሱን በደምብ አጥፍቶ የኢትዮጵያ ፖለቲካ የገዢ ወገን በጎሳ ብሄርተኛ ብቻ ሞልቶ ቀረ። ለዚህ ነው ዛሬ ያለነው ሁኔታ የተፈጠረው እንደዚህም ነው ህወሃት ተፈጥሮ ያደገው።

ላለን ችግር ታድያ ምክንያቱ በመጀመርያ ህወሃት ነው? በፍጹም። ህወሃትም ኢህአዴግም እኛ በቀደድንላቸው ግዙፍ ቀዳዳ ባላቸው የመንፈስና የጭንቅላት አቅም የሚችሉትን እያደረጉ ነው። ከነሱ እስከ ዛሬ ያደረጉት በላይ መጠየቁ አግባብ አይደለም።

እስቲ ስሜታዊ ሳንሆን ተረጋግተን እናስበው፤ ኢህአዴግ ኢትዮጵያን እገዘዋለሁ ብሎ በፍጹም አስቦ አያውቅም። ኃይላችን ውስን ነው፤ የመኻል ሀገር መንግስቱ በርካታ ኃይልና አቅም አለው፤ ብሎ እንኳን ህወሃት ከሱ ጠንካራውም ሸአብያ ደርግን ከማሸነፍ ድርድርን በበር የሚያስበው። ህወሃት አሸንፎ ሙሉ ሀገሪቷን ሲገዙ ዱብዳ ነው የሆነባቸው።

በተፈጥሮ ትዕቢትን ይጨምራል። ኢህአዴግ ደግሞ እንደ ዳዊት ታላቁን ኃይለኛ ጎሊያድን ያሸነፈ ስለመሰለው ይበልጥ ኩራትና በራስ መተማመን አደረበት። ይህን ግብ መምታት መቻሌ ድርጊቴ በሙሉ ትክክል ነው ማለት ነው ብሎ ማሰብ ጀመረ። እራሱንም ከሌሎች ድርጅቶች በሙሉ ልዩ ጎበዝና የበላይ አድርጎ ማሰብ ጀመረ። ህወሃት በዚህ መንፈስ ነው በ1983 ስልጣን የያዘው።

ከዛ ቀጥሎ ስልጣኑን በሚያረጋግጥበት ሰሞን ተቀናቃኞቹ አንድ በአንድ ሲፈርሱ አየ። ኦነግን በቀላሉ አሸነፈ። ኢህአፓም ሌሎችም እንደዚሁ። የኢትዮጵያዊ ብሄርተኛ የፖለቲካ ጎራ ደግሞ ጭራሽ ምንም ኃይል ስላልነበረው ኢህአዴግ ምንም ማድረግ አላስፈለገውም።

በተዘዋዋሪ የኢትዮጵያዊ ብሄርተኝነት የፖለቲካ ጎራ በዛን ጊዜ ኃይል ማጣቱ ኢህአዴግን እጅግ የተሳሳተ ድምዳሜ ላይ እንዲደርስ አድርጎታል። ኃይል ስላጣ ከጥቂት የሆኑ የተማሩ ወገኖች በስተቀር ይህ ጎራ ከህብረተሰቡ ምንም ድጋፍ የለውም ብሎ ኢህአዴግ ገመተ። የቀዝቃዛ ጦርነት፤ የደርግ የኮሙኒስት አቋም፤ የኤኮኖሜው መበላሸት፤ ወዘተ እንደ ምክንያት ሳይቆጠር ደርግ መሸነፉ ኢትዮጵያ ብሄርተኝነት እንደተሸነፈም ብሀገሪቷም እንደማይፈለግ ተቆጠረ። ይህ ታልቅ ስህተት መሆኑን ኢህአዴግ በየጊዜው እየገባው ሄዷል።

ዞሮ ዞሮ ኢህአዴግ ሀገሪቷን ተቆጣጠረ። ማንም አልተፎካከረውም። ትዕቢቱም እየጨመረ ሄደ!

ኢህአዴግ ስልጣኑን ካረጋገጠ በኋላ ህዝቡ አልፎ አልፎ መንግስት ላይ መነሳት ጀመረ። ኢህአዴግ ሁሉንም አይነት አመጽ (ለምሳሌ የ1986ና የ1993) በቀላሉ ተቆጣጠረ። ትዕቢቱ መጨመሩ ቀጠለ።

በዚህ ጊዜም አንዳንድ ተቃዋሚ ድርጅቶች ቢያንስ መንግስትን ለመተቸት ያህል ይበቁ ነበር። ግን እርስ በርስ ሲጣሉና በትንሽ ግፊት ሲፈርሱ ሲያይ የኢህአዴግ ትዕቢት ማየል ቀጠለ።

ከዛ ቀጥሎ የኤርትራ ጦርነት ተነሳ። ኢህአዴግ ይሄንንም ፈተና እንደ ድርጅት ቆስሎም ቢሆን 70,000 በላይ ወታደር ሞቶም ቢሆን አሸነፈ። የሚፈራውን ታላቅ ወንድሙን በማሸነፉ የዝቅተኛ መንፈሳቸውን አስወገዱ። ኢትዮጵያንም ለብቻው ተቆጣጠረ! ትዕቢቱም ጨመረ። እኛ ኢትዮጵያዊ ብሄርተኞች ከዳር ሆነን አጨበጨብን።

አምስት ዓመት በኋላ ኢህአዴግ የምርጫ 1997 ፈተና አጋጠመው። ፈተናው እጅግ ከባድ ቢሆንም በመጨረሻ ኢህአዴግ ያለውን የተቃዋሚ ጎር ድራሹን አጥፍቶም የሀገሪቷን ኤኮኖሚ ክፍ አድርጎ ተቃውሞን ገደለው። ለዚህ ሁሉ ድል እራሱን ለመሸለም ያህል የ2007 ምርጫን መቶ በመቶ እንዲያሸንፍ አደረገ። ትዕቢቱ ናረ!

ይህንን ታሪክ ስንመለከት እኛ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ህወሃትን እንደፈጠርነው፤ አጣመን እንዳሳደግነው፤ ጥሩ ምሳሌ ባለመሆናችን እንዲክደን ያደረግነው፤ እራሳችንን በማጥፋት ልቅ እንዳደረግነው ሁሉ ማመን አለብን። ኢትዮጵያ በኛ እጅ ሆና ደጋግመን ተሳሳትን አጠፋን ጨኮንንም አበላሸንም። ለእነ ህወሃት መንገዱን ጨርቅ አደረግንላቸው።

ስልጣን ከያዙም በሗል ጠፋንባቸው። እርስ በርስ ያለመተባበርም የመጠራጠርም ብሽታ ይዞን እነሱን የሚፎካከር የፖለቲካና ህዝባዊ ኃይል መዋቀር አልቻልንም። ይህም ኢህአዴግ የተሳሳተ መንገዱን እንዲቀጥል ረዳው ብቻ ሳይሆን አስገደደውምም ማለት ይቻላል። አንድ ድርጅት እራሱን ለማስተካከል ሃሳብ ብቻ ሳይሆን ተግባራው ምክንያት (incentive) ያስፈልገዋ። ኢህአዴግም የሚቀናቀነው ኃይል ፊቱ ቢቆም ኖሮ የተሻለ ሃሳብን እንዲያሰላስል ይገደድ ነበር። እኛ የኢትዮጵያዊ ብሄርተኞች ግን ይሄንን ትንሽ ግዴታችንንም አላሟላንም።


ታድያ ሀገራችን የፖለቲካ ችግር ምንጭ ዬት ነው? ከኛ ከኢትዮጵያዊ ብሄርተኞች ነው። መፍትሄውም ከኛ ነው። ኢህአዴግን መክሰስም መፍትሄ ከሱ መጠበቅም ዋጋ ዬለውም። እኛ ነን ችግሩን ያመጣነው እኛም ነን የምንፈታው። ከፈታነው በኋላ ልጆችንን «ወያኔን» ይቅርጣ እንጠይቀዋለንም።


No comments:

Post a Comment

ለሀሳብዎ አመሰግናለሁ!